Administrator

Administrator

ወይዘሮ ፈለቀች ለማ እባላለሁ፡፡ የቤተሰብ አስተዳዳሪና የአስራ አንድ ልጆች እናት ነኝ፡፡ በጥሩ ቤተሰብ ውስጥ ነው ያደግሁት፡፡ ትምህርት የጀመርኩት በቄስ ትምህርት ቤት ነው፤ ከዚያም በመንግሥት ትምህርት ቤት ገብቼ እስከ ስድስተኛ ክፍል ከተማርኩ በኋላ በሀገሩ ባህልና ወግ መሠረት በጣም በልጅነቴ ተዳርኩ፡፡ ሆኖም ያኔ ሲንጀር ካምፓኒ የሚሰጠውን የዲዛይን ትምህርት ጨርሼ ከተመረቅሁ በኋላ፣ በጅማ የሴቶች በጎ አድራጎት ድርጅት፣ ከጓደኞቼ ጋር በመሆን፣ ሴቶች ራሳቸውን እንዲችሉ፣ የልብስ ስፌትና ጥልፍ ስልጠና በመስጠት እናስመርቅ ነበር።

አዲስ አድማስ ከመጀመሩ በፊት ባለቤቴ ሁሌም ጋዜጣና መፅሔት እንዲሁም መጻሕፍት እየገዛ ያመጣ ስለነበር፣ ንባብ የቤታችን ባህል ሆኗል፡፡ በኋላም አዲስ አድማስ ቅዳሜ መውጣት ሲጀምር ልጆቹም በዚያው ቀጠሉበት፡፡ እኔም ጋዜጣውን ማምጣት እንዳይረሱ ሁሌም አስታውሳቸዋለሁ፤ በጣም የሚወደድ ጋዜጣ ስለሆነ ምንጊዜም እንዲያልፈኝ አልፈልግም፡፡

አዲስ አድማስን ለብዙ ዓመታት አንብቤአለሁ፤ ወደፊትም አነባለሁ፡፡ ጋዜጣውን እንዳገኘሁ መጀመሪያ የማነበው የነቢይ መኮንንን (ነፍሱን ይማረውና) ርዕስ አንቀጽ ነው፤ ሁለተኛ የማነበው ደግሞ የዮሐንስ ሰ.ን ጽሁፍ ነው፡፡ እኔ ከልጆቹ ቀድሜ ካነበብኩ ጥሩ የምላቸውን ጽሁፎች እንዲያነቡ እጠቁማቸዋለሁ፡፡ ሁሉም አምዶች ሳምንቱን ሙሉ የሚነበቡ ናቸው፡፡ በእኔ በኩል፣ አዲስ አድማስን በድረ ገፅ አላነብም፤ለዕድሜዬ አይሆንም፤ በዚያ ላይ ጋዜጣው ሁሌም በእጄ ነው።

በአዲስ አድማስ ላይ በርካታ አስገራሚና አስደማሚ ታሪኮችን አንብቤአለሁ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አንዱና ሁሌም የማይረሳኝ፣ ኮፊ አናን ኢትዮጵያ በነበሩ ጊዜ የቤት ውስጥ ረዳታቸው የነበሩትን ሴት ተመልሰው ሲመጡ ሊያገኟቸው ፈልገው፣ ሴትየዋ በቀጠሮው ሰዓት ባለመድረሳቸው ሳይገናኙ መቅረታቸውን የሚያትተው ታሪክ ነው፡፡ የቀጠሮ ሰዓት የማያከብር ሰው ስለሚገርመኝ ይሆናል፣ ይሄ ታሪክ ሁሌም ትዝ የሚለኝ፡፡

በእርግጥ የማነበው ጋዜጣ ብቻ አይደለም፤ መፅሔቶች የታሪክና የሀይማኖት መጻሕፍትንም አነባለሁ፡፡ ዜናም አያመልጠኝም፡፡ ማንበብ ብዙ ጠቀሜታዎች አሉት፡፡ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ዕውቀትን ያስታጥቃል፡፡ መረጃን ከሰው አፍ ከመስማት አንብቦ መረዳት የተሻለ ነው፡፡

የአዲስ አድማስ ፀሐፊዎችና አዘጋጆች፣ ከአንባቢዎቻቸው ቀድመው መገኘት አለባቸው፤ በሁሉም ረገድ ሊበረቱ ይገባል፡፡ ጋዜጣው አምዶቹን መጨመር እንጂ መቀነስ የለበትም፤ የተቀነሱ አምዶች ስላሉ የጎደሉትን ማሟላት ያስፈልጋል፡፡ በመጨረሻ እንኳንም ለአዲስ አድማስ 25ኛ ዓመት አደረሳችሁ እላለሁ፡፡ መልካም የሥራ ዘመን ይሁንላችሁ።

• በስሙ አደባባይ ለመሰየምና ሐውልት ለማቆም ከከተማ
አስተዳደሩ ምላሽ እየተጠበቀ ነው ተብሏል

ከ60 ዓመታት በላይ በተወዳጅነት ያቀነቀነው “የትዝታው ንጉስ” ማህሙድ አህመድ፣ በነገው ዕለት ጥር 3 ቀን 2017 ዓ.ም፣ በሚሊኒየም አዳራሽ፣ በአድናቂዎቹ በክብር ከመድረክ ይሸኛል።

ዛሬ በሚሊኒየም አዳራሽ የመርሃ ግብሩ አዘጋጆች ጆርካ ኢቨንትስ ኦርጋናይዘር እና ዳኒ ዴቪስ በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንደተናገሩት፤ የስንብት ኮንሰርቱ ለጋሽ ማህሙድ በሚመጥን መልኩ የተዘጋጀ ነው። በኮንሰርቱም ላይ ተወዳጆቹ ድምጻዊያን ጎሳዬ ተስፋዬ፣ ኤፍሬም ታምሩ፣ ብዙአየሁ ደምሴ፣ አደም መሐመድ፣ ወንዶሰን መኮንን (ወንዲ ማክ) እና ዜና ሃይለማሪያም ታላቁን አርቲስት አጅበው ያቀነቅናሉ ተብሏል።

አርቲስቶቹ ከጋሽ ማህሙድ በተረፈው ሰዓት ታዳሚን ለማስደሰትና፣ አንጋፋውን ሙዚቀኛ በክብር ለመሸኘት በከፍተኛ ደረጃ እየተዘጋጁ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ጋሽ ማህሙድም “አሳድጎ ለዚህ ክብር ያበቃኝን አድናቂ፣ በተቻለኝና አቅሜ በፈቀደው መጠን በመጫወት አስደስቼ ለመሰናበት ተዘጋጅቻለሁ” ያለ ሲሆን፤ “ሁላችሁም መጥታችሁ ብትሸኙኝ ደስታውን አልችለውም” ሲል ሁሉም እንዲታደም ጥሪ አቅርቧል።


ጋሽ ማህሙድን አጅበው የሚያቀነቅኑት ለምን ወንዶች ብቻ ሆኑ፣ ሴት አቀንቃኞች ለምን አልተካተቱም? በሚል ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ለቀረበው ጥያቄ፣ ከስንብት ኮንሰርቱ አዘጋጆች አንዱ የሆነው ዳኒ ዴቪስ በሰጠው ምላሽ፤ " አስቴር አወቀ እንድትሳተፍ ፈልገን ጋብዘናት ነበር፤ ወደ ውጪ በመውጣቷ ልትገኝ አልቻለችም፤ እኛም የፈለግነው እሷን ነበር፤ አልሆነም" ብሏል።

የአንጋፋውን ሙዚቀኛ የጋሽ ማህሙድ አህመድን የህይወት ታሪክ የሚተርክ መፅሐፍ በትላንትናው ዕለት የተመረቀ ሲሆን፤ በስሙ አደባባይ ለመሰየምና ሐውልት ለማቆም ከከተማ አስተዳደሩ ምላሽ እየተጠበቀ መሆኑም በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ተብራርቷል።

“መጻሕፍት ሻጮች ህይወትን ይታደጋሉ”


ጄምስ ፓተርሰን በዓለም ዝናው የናኘ እጅግ ታዋቂና ትጉህ አሜሪካዊ ደራሲ ነው። የ77 ዓመቱ ፓተርሰን እ.ኤ.አ ከ1976 ዓ.ም ጀምሮ 200 ገደማ ረዥም ልብ ወለዶችን ጽፎ ለህትመት ያበቃ ሲሆን፤ መፃህፍቱ በዓለም ዙሪያ ከ425 ሚሊዮን ቅጂዎች በላይ ተሸጠውለታል። 1 ሚሊዮን ያህል ኤሌክትሮኒክስ መፃሕፍት (e-books) በመሸጥም የመጀመሪያው ደራሲ ነበር፡፡
ፓተርሰን እ.ኤ.አ በ2016 ዓ.ም በፎርብስ የከፍተኛ ተከፋይ ደራሲያን ሰንጠረዥን በመቆጣጠር ለሦስት ተከታታይ ዓመታት ዘልቋል- በ95 ሚሊዮን ዶላር ገቢ። አጠቃላይ ገቢው ደግሞ ከአሰርት ዓመታት በላይ ለሚሆን ጊዜ 700 ሚሊዮን ዶላር ይገመት ነበር፡፡
ሚሊየነሩ አሜሪካዊ ደራሲ ከተወዳጅ የሥነጽሁፍ ሥራዎቹ ባሻገር የመጻሕፍት ሻጮች አለኝታም ነው፡፡ የመፅሐፍ ኢንዱስትሪውን የጀርባ አጥንት በመደገፍ ይታወቃል - የግል የመፃሕፍት መደብሮችን።
በዚህ የፈረንጆች በዓል ሰሞን በመላው አሜሪካ በሚገኙ 600 የግል መፃህፍት መደብሮች ውስጥ ለሚሰሩ ሰራተኞች በአጠቃላይ የ300ሺ ዶላር የበዓል ቦነስ አበርክቷል - በነፍስ ወከፍ 500 ዶላር!
“መፃህፍት ሻጮች ህይወትን ይታደጋሉ- አራት ነጥብ!” በማለት ለABC ኒውስ የተናገረው ደራሲው፤ “በዚህ የበዓል ወቅት ለእነሱም ሆነ ለትጋታቸው ዕውቅና መስጠት በመቻሌ ደስተኛ ነኝ።” ብሏል።
ለዓመት በዓል የገንዘብ ስጦታው የታጩት የ600 መፃሕፍት መደብር ሠራተኞች አንድም ራሳቸው ያመለከቱ አሊያም በመደብር ባለቤቶች፣ በደራሲያን ወይም በደንበኞች የተጠቆሙ ናቸው ተብሏል- በትጋትና ታታሪነታቸው።
“የሚስተር ፓተርሰንን የገንዘብ ልግስናና የልብ ቸርነት እናደንቃለን። ሁላችንም ሚስተር ፓተርሰን ለግል መፃሕፍት ሻጮች ለሚያደርጉት የማያቋርጥ ድጋፍ ምስጋናችን ወደርየለሽ ነው፡፡” ብለዋል፤ የአሜሪካ መፃህፍት ሻጮች ማህበር ዋና ሥራ አስፈፃሚ አሊሰን ሂል በመግለጫቸው፡፡
“መፃሕፍት ሻጮች በኢንዱስትሪው ውስጥ የሚጫወቱትን ወደር-የለሽ ሚና መገንዘባቸውና መሸለማቸው ከምንም ነገር የላቀ ነው” ሲሉም አክለዋል፤ ዋና ሥራ አስፈፃሚው።
ደራሲው ለመፃሕፍት ሻጮች የ500 ዶላር የበዓል ቦነስ ሲያበረክት ያሁኑ የመጀመሪያው አይደለም። ላለፉት አስርት ዓመታት ሲያደርገው የቆየው የልግስና ተግባር ነው፡፡ ሥነ-ፅሁፍን በማሳደግና ንቁ ማህበረሰቦችን በመገንባት ረገድ ወሳኝ ሚና እንደሚጫወቱ በማመን፣ የግል የመፃሕፍት መደብሮችንም ያለማቋረጥ በመደገፍ ይታወቃል፤ በአገረ አሜሪካ፡፡
በመጋቢት ወር ላይ ፓተርሰን ለመፃሕፍት ሻጮች የሚከፋፈል 600ሺ ዶላር እንደሚያበረክት የአሜሪካ መፃሕፍት ሻጮች ማህበር አስታውቆ ነበር፡፡ ቀደም ብሎ እ.ኤ.አ በ2020 ደግሞ በመላው አሜሪካ ለሚገኙ የግል መፃሕፍት መደብሮች 500ሺ ዶላር ለግሷል- ሥራቸውን እንዲያሳድጉና እንዲነቃቁ።
“ዋይት ሐውስ የአየር መንገድ ኢንዱስትሪንና ትላልቅ ቢዝነሶችን ከውድቀት መታደግ ያሳስበዋል - ያንን እረዳለሁ። እኔ ግን በመላ አገሪቱ ዋና ጎዳናዎች እምብርት ላይ የሚገኙ የግል የመፃሕፍት መደብሮች ህልውና ያሳስበኛል።” ብሏል ፓተርሰን በሰጠው መግለጫ።
“የምናሰባስበው ገንዘብ የመፃሕፍት መደብሮችን በጣም በምንፈልግበት በዚህ ወቅት ህያው እንደሚያደርጋቸው ተስፋ አደርጋለሁ።” ሲልም አክሏል፤ ደራሲው።
ጄምስ ፓተርሰን እ.ኤ.አ በ2014 ዓ.ም ለአሜሪካ የግል የመፃሕፍት መደብሮች 1 ሚሊዮን ዶላር ለግሶ ነበር- ለእያንዳንዳቸው 15ሺ ዶላር የሚከፋፈል። ባለፉት ዓመታት ደራሲው ለመፃሕፍት መደብሮችና መጻሕፍት ሻጮች ብቻ ሳይሆን ለቤተመጻህፍት ባለሙያዎችና ለመምህራንም የበዓል ቦነስ ሲያበረክት ቆይቷል።
የመፃሕፍት መደብሮችንና መፃሕፍት ሻጮችን በገንዘብ ከመደገፍና ከማገዝም በተጨማሪ፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ መፃሕፍትን ለት/ቤቶች ቤተ-መፃሕፍት ለግሷል። የህፃናት መፃሕፍትንም በመፃፍ የሚታወቀው ደራሲው፤ ህፃናት የንባብ ባህል እንዲያዳብሩም በትጋት ይሰራል። “ህፃናት በለጋ ዕድሜያቸው የማንበብ ልማድ ካላዳበሩ ለውጭው ዓለም ባዕድ ከመሆናቸውም ባሻገር በራስ መተማመን ይጎድላቸዋል፤ ስለዚህ የግድ ማንበብ አለባቸው፤ ይህን ማድረግ ደግሞ የኛ የወላጆች ሃላፊነትና ግዴታ ነው፡፡” ይላል- ፓተርሰን።
ጄምስ ፓተርሰን የበኩር ስራውን ለንባብ ያበቃው እ.ኤ.አ በ1976 ዓ.ም ሲሆን፤ ርዕሱም “The Thomas Berryman Number” ይሰኛል። ከሌሎች በርካታ የሥነጽሁፍ ሥራዎቹ መካከልም፡- Alex Cross, Michael Bennet, Women’s Murder Club እና Maximum Ride የተሰኙት ልብወለዶች ይጠቀሳሉ። ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ ልብወለዶቹም ወደ ፊልም ተቀይረውለታል፡፡

 

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ፤
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡
በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
በሕመም ምክንያት በየፀበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤
እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያት በሙሉ፤
በምሉእ ፍቅሩ ሰውን ከባርነት ወደ ነጻነት ለመመለስ በሥጋ ሰብእ የተወለደው ጌታችን ኣምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ ሰባት ዓመተ ምሕረት የልደት በዓል በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ፡፡
“ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ለዘሠምሮ ለሰብእ፤ ክብር በሰማያት ለእግዚአብሔር ይሁን›› በምድርም እጅግ ለወደደው የሰው ልጅ ሰላም ይሁን” (ሉቃ ፪÷፲፬)
ይህ ቃለ ሰላም በጌታችን ዕለተ ልደት የተነገረ ነው፣ ቃሉ የተነገረው እንዲሁ እንደ ተራ ነገር ሳይሆን በቃለ መዝሙር እየተደጋገመ ነው፡፡ የተዘመረውም በምድራውያን ደራሲዎች ሳይሆን በሰማያውያን መላእክተ እግዚአብሔር ነው፣ የያዘው መልእክትም ሰማያውያንና ምድራውያንን ሁሉ ያካለለ ነው፡፡ የመልእክቱ ገዢ ሓሳብም አምላክ ከሰውነታችን ጋር ባለመለያየት፣ ባለመጠፋፋት፣ ባለመቀላቀል፣ ባለመዋዋጥ፣ ባለመለዋወጥና ያለባዕድና አንድ አካል፣ አንድ ክዋኔ፣ አንድ ጠባይ ሆኖ በተዋሕዶ ተገልጾኣልና እግዚአብሔር ይክብር ይመስገን፡፡ የተዋሕዶውም ምስጢር ሰላምን ያሰፍናልና እግዚአብሔር ሰውን በእጅጉ መውደዱ ከዚህ ተዋሕዶ ዓውቀናል የሚል ነው፡፡
በእርግጥም እግዚአብሔር ሰውን ለመውደዱ ከዚህ የበለጠ ማሳያ ወይም ማስረጃ የለም፤ እንከን የለሽ ንጹህ አምላክ የእኛን ኃጢአተኛ ሰውነት አካሉ አድርጎ ተወለደ ሲባል ላስተዋለው ሰው ምንኛ ቢወደን ነው የሚለው ጥልቅ አድናቆትን ያጭራልና ነው፡፡ይህ ብቻም አይደለም በዚህ ነገረ ተዋሕዶ ምክንያት ሰውነታችን አምላክ ሆኖ በመንበረ ጸባኦት እንዲቀመጥ መብቃቱ የድኅነታችንና የክብራችን ከፍታ ምን ያህል አስተማማኝ ደረጃ ላይ እንደደረሰ መንፈሳችን በአንክሮ ይረዳዋል፡፡ድምር ውጤቱም በእግዚአብሔርና በሰው መካከል ፍጹምና አስተማማኝ ሰላም መፈጠሩን ያስረዳናል፤ ሰማያውያኑ መላእክተ እግዚአብሔር በመዝሙራቸው ያበሰሩን ይህንን የምስራች ነው፡፡
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!
እኛ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር ፍቅር ነው፣ እግዚአብሔር በእጅጉ ይወደናል ስንል እንዲሁ ከሜዳ ተነሥተን ኣይደለም፡፡ በበደላችንና በኃጢአታችን ሳይጸየፈን ሰውነታችንን በረድኤት ወይም በኅድረት ያይደለ በኩነት ተዋሕዶ ወደ አምላክነት ደረጃ ከፍ ስላደረገው ነው እንጂ፡፡ እግዚአብሔር በዚህ ፍጹምና ምሉእ ፍቅሩ ሰውነታችንን በመበረ ጸባኦት ኣስቀምጦ መላእክት ሳይቀሩ ፍጥረታትን በሙሉ እንድንገዛ አድርጎናል፤ ምክንያቱም መላእክት በዕለተ ልደት የዘመሩለት በተዋሕዶ አምላክም ሰውም ለሆነ ለቤተ ልሔሙ ሕፃን እንጂ ለመለኮት ብቻ ኣይደለምና ነው፡፡ የዕለተ ልደት መዝሙር ዛሬም በሰማያትም ሆነ በምድር በተዋሕዶ ሰውም ኣምላክም የሆነ አንዱ ኢየሱስ ክርስቶስ ይመለክበታል፣ ይመሰገንበታል፡፡የሰማዩና የምድሩ ዕርቅ ወደ ኋላ ላይመለስ ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በዚህ ተከናውኖኣል፣ የእግዚአብሔር ፈቃድ የሰውም አዋጭ ምርጫ ይህ ዕርቅ ተጠብቆ እንዲኖር ነው፣ ያለ ዕርቅ ሰላም ሕይወት የለውምና፡፡
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!
የእግዚአብሔር ክብርና ሰላም በእጅጉ የተሳሰሩና የተቆራኙ ናቸው፤ እኛ እግዚአብሔርን ካከበርነው፣ ካዳመጥነው፣ ከታዘዝነውና ከተከተልነው ሰላም አለ ማለት ነው፡፡ ለሱ ካልታዘዝንና እሱን ካላከበርን ግን ዘላቂ ሰላምን ማግኘት ፈጽሞ የማይታሰብ ነው፤ ምክንያቱም ሰላምን ጨምሮ መልካም ነገር ሁሉ ያለው በእግዚአብሔር እጅ ነውና፡፡ ዛሬ በሁሉም የዓለማችን ማዕዘን የሚታየው የሰላም መደፍረስ እግዚአብሔርን ካለማክበራችንና ለሱ ካለመታዘዛችን የተነሣ እንደሆነ መዘንጋት የለብንም፡፡ ዓለም ከእግዚአብሔር ቃል ርቃ ለመሄድ በእጅጉ እየኳተነች ነው፤ በዚህ እኩይ ተግባርዋ ደግሞ እግዚአብሔር ለስጋትና ለጉስቁልና አሳልፎ እየሰጣት ነው፡፡ እግዚአብሔር በምስጢረ ሥጋዌው ቢታረቃትም ዕርቁን ማክበር አቅቶአታል፤ ይህንን የእግዚአብሔር ጸጋ ቸል ብላ የምታደርገው ሩጫ የትም ሊያደርሳት እንደማይችል ብታውቅና በንስሓ ብትመለስ እግጅ ተጠቃሚ ትሆናለች፡፡
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!
የእግዚአብሔር ቃል “እናንተስ ከማይጠፋ ዘር ተወለዳችሁ” ብሎ ተስፋውን እንደነገረን ምድባችን ከማይጠፋ ዘር እንዲሆን ክርስቲያኖች የሆን ሁላችን በአእምሮ ጐልብተን፣ በሥነ-ምግባር ኣምረን፣ ጤናማ ሕይወትን ልንመራ ይገባናል፡፡
የአምላካችንን በዓለ ልደት ስናከብር ነገረ እግዚአብሔርን፣ ነገረ ፍቅርን፣ ነገረ ዕርቅንና ነገረ ሰላምን በማኅበረሰባችን የማሥረጽ አጀንዳ ይዘን ልናከብር ይገባል፡፡
ጠቡ ፣ ጥላቻው፣ መለያየቱ፣ መጠፋፋቱ፣ ለወንድሜ ከማለት ይልቅ ለኔ ለኔ ማለቱ ሲጎዳን እንጂ ሲጠቅመን ኣላየንም፡፡ አሁንም ወደ ልባችን እንመለስና በፍቅር፣ በዕርቅና በእኩልነት፣ በስምምነትና በወንድምነት ወደሚገኝ አንድነት እንምጣ፤ የልደቱ መዝሙር ያስተማረን ይህና ይህ ብቻ ነውና፡፡ በሌሎቹ ክፍለ ዓለማት እንደሆነው ሁሉ በሀገራችን የተከሠተው አላስፈላጊ ግጭት ብዙዎችን አሳጥቶናል፤ ብዙዎችንም ከቤት ንብረታቸው አፈናቅሎ ሜዳ ላይ ፈሰው የሰቆቃ ኑሮ እንዲገፉ አድርጎብናል፡፡ የሀገር ሀብት እንዲወድም ሆኖአል፤ ልጆቻችን ምናለ ከእንግዲህ ወዲህ ቢበቃንና ምድሪቱን የሰላም አየር እንድትተነፍስ ብንፈቅድላት፤ ይህ የወቅቱ የቤተክርስቲያናችን ዋነኛ መልእክትና ጥሪ ነው፡፡
በመጨረሻም፡-
በዓለ ልደት የእግዚአብሔር በዓል ነውና፣ እግዚአብሔር በምድራችን ሰላምን ያወርድ ዘንድ ካለን ከፍለን ለተፈናቃዮች፣ ለነዳያን እና ለአካል ጉዳተኞች በመለገስ በዓሉን በመንፈሳዊ ደስታና በሰላም እንድናከብር አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፤
መልካም በዓለ ልደት ያድርግልን፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ
ተክለሃይማኖት
ታኅሣሥ ፳፱ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ
እየሱስ ክርስቶስ በሰው ልጆች እና በአምላክ መካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ አፍርሶ በምህረት፣ በይቅርታ እና በታላቅ ፍቅር ወደ ምድር መምጣቱ ሰላምን እና ፍቅርን ለምድር እንዲሁም አብሮነት እንዲጎለብት ምሳሌ ለመሆን ነው::
ስለዚህ በዓሉን ስናከብር የእየሱስ ክርስቶስን ምሳሌነትን በመከተል የሰላም እሴቶችን እየገነባን፣ ፍቅራችንን ይበልጥ እያጎለበትን እንዲሁም አብሮነታችንን እያጠናከርን ሊሆን ይገባል::
በዓሉን ስናከብር ያላቸው ለሌላቸው ማዕድ በማጋራት ፍቅር፣ መተሳሰብና አብሮነት በሚገለጽበት መልክ እንዲሆን ጥሪ እያቀረብኩ፣ የሰላም እና የደስታ በዓል እንዲሆንላችሁ እመኛለሁ።
መልካም በዓል!
ፈጣሪ ኢትዮጵያን እና ህዝቦቿን ይባርክ

ዕንቁራሪቶች፣ ጦጣዎች፣ አይጦችና የዱር አራዊቱ ንጉስ አንበሳ የሚኖሩበት ትልቅ ደን አለ፡፡ እንቁራሪቶቹ ከደኑ አጠገብ ካለው ኩሬ ውስጥ ነው የሚኖሩት፡፡ አንበሳ የሚጠይቃቸውን ሁሉንም በመታዘዝ ነው ሌሎቹ የሚኖሩት፡፡ አንድ ቀን እንቁራሪቶቹ፣ ጦጣዎቹና አይጦቹ አንድ ላይ መስክ ላይ በየበኩላቸው እየለቃቀሙ ሳለ፣ አዳኞች አንበሳውን ሲያሳድዱት ተመለከቱ፡፡ እንቁራሪቶቹ “ለጌታም ጌታ አለው! ሰው’ኮ የአንበሳ ጠላት ነው አይለቀውም፡፡ ከዚህ መዓት ለማምለጥ በሉ ወደ ኩሬያችን እንሂድ” አሉና ወደ ኩሬያቸው አመሩ፡፡ አይጦቹም፣ የደኑ ገዢ አንበሳ ነው ብለው ስለያሚስቡ፣ “ሰዎችና አንበሶች አጥፊና ጠፊ ናቸው፡፡ የዚህ አንበሳ ጣጣ ለእኛ እንዳይተርፈን በጊዜ ወደ ጎሬያችን ገብተን እንሸሸግ” አሉና ሄዱ፡፡ ጦጣዎቹ “ሰው አንበሳ ሲጠላ እንድ ጉድ ነው፡፡ በጊዜ ዛፋችን ላይ እንውጣ” ብለው በየዛፎቻቸው ላይ ተንጠላጥለው ወጡ፡፡
አዳኞቹ አንበሳውን ገድለው ቆዳውን ገፍፈው ወሰዱ፡፡ አዳኞቹ ከሄዱ በኋላ ዕንቁራሪቶቹ ጦጣዎቹና አይጦቹ እንደገና ተሰባስበው፤ ጦጣ ስለ ዛፍ ላይ ኑሮ፤ እንቁራሪት ስለ ኩሬ ኑሮ፣ አይጥ ስለ ከመሬት በታች ኑሮ አወጉና የአንበሳውን አሟሟት እያነሱ በየበኩላቸው የሚያስተዳድሩት ግዛት እንዳላቸው በመጥቀስ ወጋቸውን ሲሰልቁ ቆዩ፡፡
በነጋታው በኩሬ ውስጥ ያሉትን ነብሳት ሁሉ ለመብላት የሚፈልጉ አጥማጆች ሲመጡ ጦጣዎች ወደ ዛፋቸው፣ አይጦት ወደ ጉድጓዳቸው ሮጡ፡፡ እንቁራሪቶች ግን ሁሉም ከኩሬው ተለቃቅመው ተወሰዱ፡፡ ጦጣዎችና አይጦች እንደ ልማዳቸው በሦስተኛው ቀን ተገናኝተው እያወጉ “እንቁራሪቶቹን ምን አድርገዋቸው ይሆን?” እያሉ ተጠያየቁ፡፡ “ሰው እኮ ጨካኝ ነው፡፡ በልቶዋቸው ይሆናል” አሉ ጦጣዎቹ፡፡ “ምናልባት እሰኪበላቸው በእንክብካቤ ያኖራቸው ይሆናል” አሉ አይጦቹ፡፡
ይህንኑ እያወጉ፤ ሳሉ የአይጥ ወጥመድ የያዙ በርካታ ሰዎች መምጣታቸውን አዩ፡፡ ጦጣዎቹ ፈጥነው ወደዛፋቸው ወጡ፡፡ አይጦቹ ወደ ጉድጓዳቸው ሮጡ፡፡ ባለወጥመዶቹ አድፍጠው ወጥመዶቸውን በጥንቃቄ በየጉድጓዳቸው አፋፍና ውስጥ አኖሩባቸው፡፡

በነጋታው አይጦች የወጥመዶቹ ሲሳይ ሆኑ፡፡
ጦጣዎችን “አንበሳው ሰው ጠላቱ መሆኑን ረስቶ ጉልበቱን ተማምኖ በደን ውስጥ ሲጎማለል ተበላ፡፡ ዕንቁራሪቶቹም ማምለጫ በሌለው ኩሬ ውስጥ እንደተወሸቁ መውጫ ሳያበጁ ቀለጡ፡፡ እነዚህ አይጦችም ገብተው ከማይወጡበት ጉድጓድ ውስጥ ተቀርቅረው ብቅ ሲሉ በወጥመድ እየታነቁ ሲጥ አሉ፡፡ እኛ ግን ዛፍ ላይ ነንና ሰው ወደኛ ሲመጣ ወደታች በቀላሉ ስለሚታየን ከዛፍ እዛፍ እየዘለልን ደብዛችንን እናጠፋበታለን” ተባባሉ፡፡
ጥቂት ቀናት ሰነባብቶ ሰዎች ወደጫካው መጡ፡፡ ጦጣዎቹ ማንም አይነካን ብለው ዛፋቸው ላይ እንዳሉ ቆዩ፡፡
የሰው ልጅ ጥፋት ሰለባ መሆናቸውን ያወቁት ግን ከዳር ዳር ደኑ በእሳት መያያዙን ያዩ ጊዜ ነበር፡፡ ዛፍ ላይ ያሉት እዚያው እንደተንጠለጠሉ ተቃጠሉ፤ የወረዱትም በሰው እጅ አለቁ፡፡ የሚገርመው ግን አዳኞቹ ሰዎች ወደ ቤታቸው ሲመለሱ በጠላቶቻቸው ተቃጥሎ ዶግ-አመድ ሆኖ አገኙት፡፡
* * *
ዓለም የአጥፊና ጠፊ መድረክ ናት፡፡ ነግ በኔ ብሎ ገና በጠዋት ያልተጠናቀቀ ዕጣ-ፈንታው እንደቀዳሚዎቹ ሟቾች ነው፡፡ የፋሲካው በግ፣ በገናው በግ እንደሳቀ መሞቱ ከዓመት ዓመት የምናየው ሀቅ ነው፡፡ እኔ የራሴን ታሪክ እሰራለሁኝ እንጂ ሌሎች እኔን መሰሎች በታሪክ ውስጥ ምን ጽዋ ደረሳቸው? ብሎ አለመጠየቅ፣ ምላሹን ካገኙም የእኔንስ ክፉ-ዕጣ እንዴት እመክተዋለሁ? ብሎ አለማውጠንጠን የዓለምንም የሀገራችንንም የፖለቲካ ድርጅቶች ቡድኖች፣ መሪዎችና ታዋቂ ግለሰቦች ታሪካዊ ዕጣ-ፈንታ ሳይታለም የተፈታ እንዲሆን ካደረገው ውሉ አድሯል፡፡ ነግ-በኔ አለማለት ክፉ እርግማን ነው፡፡

ለማርቲን ኒየሞይለር መታሰቢያ የተደረገው ጽሁፍ ይሄንኑ ይነግረናል፡፡ ማርቲን ኒየሞይለር (1892-1984) የፕሮቴስታንት ክርስቲያን የነበረ ጀርመናዊ ቄስ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ውስጥ ናዚዎችን በመቃወም ከባድ ዘመቻ በማካሄዱ እ.ኤ.አ ከ1938 እስከ 1945 ዓ.ም ለ8 ዓመታት ማጎሪያ ካምፕ ውስጥ አስገብተው ሲያሰቃዩት ከርሞ ኋላ ተፈትቶ ከ1961 እስከ 1968 ዓ.ም ለሰባት ዓመታት የአለም አብያተ-ክርስቲያናት መማክርት ፕሬዚዳንት ሆኖ የመራ ጠንካራ ሰው ነበር፡፡ ለሱ መታሰቢያ የተደረገው ፅሁፍ እነሆ፡-
በጀርመን ናዚዎች መጥተው በመጀመሪያ ያጠቁት ኮሙኒስቶቹን ነበር፡፡ የኮሙኒስቶቹን በር እያንኳኩ ለጨፈጭፏቸው እያየሁ እኔ ዝም አልኩ፡፡ ምክንያቱም ኮሙኒስት አልነበርኩም፡፡
ቀጥለው አይሁዶቹን ወረዱባቸው፡፡ የአይሁዶቹን በር ሲያንኳኩም እኔ ዝም አልኩ፡፡ ምክንያቱም እኔ አይሁድ አይደለሁም፡፡

ከዚያ ወደ ሰራተኛ ማህበራቱ ዞሩ፡፡ የሰራተኞቹን በር ሲያንኳኩም እኔ ጭጭ አልኩ፡፡ ምክንያቱም የሰራተኛ ማህበሩ አባል ስላልነበርኩ አይመለከተኝም፡፡
ቀጥለው ካቶሊኮቹ ይፈጁ ጀመር፡፡ የካቶሊኮቹንም በር ሲያንኳኩ አሁንም እኔ ዝም አልኩ፡፡ ምክንያቱም እኔ ፕሮቴስታንት ስለሆንኩ አይመለከተኝም፡፡
በመጨረሻ የእኔን በር አንኳኩ፡፡ በዚያን ሰዓት ግን ተነስቶ ሊናገር የሚችል ምንም ሰው አልተረፈም ነበር፡፡
(ለማርቲን ኒየሞይለር [ፍሬድሪሽ ጁስታቭ ኤሚል]መታሰቢያ የተፃፈ- 1949)
የፈለገው መንግስት ይመቸኛል ባለው መንገድ ያሻውን ሀገር ሲረግጥ ያሻውን መሳሪያ ሲጠቀም፣ በእኔስ ላይ ፊቱን ያዞረ እለት ምን ይውጠኛል? የእኔስ በር የተንኳኳ እለት ማን አብሮኝ ይቆማል? ብሎ አለመጠየቅ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ ዛሬ በየቻናሉ በቀጥታ ሥርጭት በቴሌቪዥን የምናየው ጦርነት እንደተዋጣለት የሲኒማ አሊያም የቴያትር ዝግጅት የውሸት እልቂት እስኪመስል ድረስ ያስገርማል፡፡ በዓለም ታሪክ የመጀመሪያው ሳይሆንም አይቀር፡፡ የጋዜጠኞቹም ድምጽት “ጦርነቱ ሊጀመር ነው አብረን እንከታተል” እንደማለት ሆኗል- የሰው ልጅ ሞት ምፀት! እንደትላንት ወዲያ “ኢምፔሪያዝም ውርደት ቀለቡ ነው”… የሚባልበት የቀዝቃዛው ጦርነት ዘመን አልፎ፤ እፎይ ብሎ አለም ለመተንፈስ አለመቻሉ ከመደገም የማይቀሩ ብዙ የታሪክ ስላች መኖራቸውን ያስገነዝበናል፡፡ እግረ-መንገዱንም ሀያላን መቼም በቃኝ እንደማያውቁ ዳግም ያስታውሰናል፡፡ የወታደራዊ ኃይል ግሎባላይዜሽን የት እንደሚደርስም ይጠቁመን ይሆናል፡፡ “ወተት ሰርቆ ከመጠጣቱ ይልቅ አፍ አለመጥረጉ ያሳፍረዋል” እንዲሉ ትላልቁን የሃያላን ጥፋት ትቶ በእንጭፍጫፊ ላይ ማተኮር ሌላ ጥፋት እንደመፈፀም መሆኑን ሳያስገነዝበን አያልፍም፡፡ ትንሹን አምባገነን ትልቁ አምባገነን፣ ሚጢጢውን ጉልበተኛ ግዙፉ ጉልበተኛ ሊውጠው ይመኛል፡፡ ይንጠራራል፡፡ ይስፋፋል፡፡
እስከዚያ እንቅልፍ የለውም፡፡ ህዝቡና አገሩ ከመጤፍ አለመቆጠሩ ግን የየዘመኑ ትራጀዲ ነው፡፡ የዛሬም፡፡ ታዋቂው ገጣሚ መንግስቱ ለማ “ባንተ አልተጀመረም ያዳሜ ምኞት” “ከተጠቃውሚ ’መራቅ‘ አጥቂን ‘መጠጋት’ የሚለውን እንደመርህ የያዘው በርካታ መሆኑ ደግሞ መራር ትራጀዲ ያደርገዋል፡፡ “ጠባይ ያለው ልጅ ኑክሊየር ይሰጠዋል፡፡ ጠባይ የሌለው ልጅ የአሻንጉሊት ሽጉጡንም ይነጠቃል ዓይነት ሆኗል የሃያላኑ የአባትነት ባህሪ፡፡ [ወይም በግልባጩ ጠባይ ያለው ብልጥ ልጅ አየሩን ለበረራ ይፈቅዳል፡፡
ጠባይ የሌለው ልጅ “በሳዳም የመጣ በእኔ መጣ” ይላል፡፡ ሁሉንም ጠባይ ይዞ የተፈጠረው ደግሞ “ሳዳምንና አሜሪካን ያየ በኑክሊየር አይጫወትም” እያለ ከዛም ነዳጅ እየገዛ፣ ለዚህም ማዕድኑን እየቸረ ይቀመጣል፡፡ ማለትም ያስኬዳል] ጉዳዩ ግን የእኔን በር እስለካላንኳኳ ድረስ “ለእኔን አገር አማን ነው” ብሎ ማሰብ መተው ይጠይቃል፡፡ ሃያላን አልጠግብ ማለታቸው የስር መሰረት ነውና፡፡

የሐያላኑን ተወት አርገን አገራችን ስንገነባም፣ ነግ-በኔ ቁልፍ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ሌላ አገር ሲጠቃ ምን ግዴ ማለት ሌላ ፓርቲ ሲገፋ ምን ቁቤ ማለት፣ ሌላ ሰው ሜዳ ሲወድቅ እንደፍጥርጥሩ ማለት ቀን የጨለመ እለት ክፉ ነገር ነው፡፡ ትላንት በራሳችን መጥነንና ለክተን ያሰፋነውን የድንጋጌና የመርህ መጎናፀፊያ ዛሬ ዳር እስከዳር አገሬውን ካላለበስነው ብለን የምንታገልበት ሁኔታ የኋሊት ጉዞ ይመስላል፡፡ “ትንሽ ስንቅ የያዘ አስቀድሞ ይፈታል” እንዲሉ፡፡ አገርን የሚያህል ሰፊ ባህር፣ የትንጧን ህልማችንን መፍቻ ለማድረግና አንዲቷን ቀጭን ኩታችንን ለልጁም ላዋቂውም አለብሰዋሁ ብሎ አይሆንም ሲባሉ ግትር ማለት ደግ አይደለም፡፡ ቢያንስ የዋህነት ሲበዛ በሰፊው ተወጥሮ መሰነጣጠቅ ነው ውጤቱ፡፡ ሌላ አስቸጋሪ አባዜ የካፒታሊዝምን ሠሪ-አካል፣ በሶሻሊስት ልብ አንቀሳቅሰዋለሁ እንደ ማለት ያለ በውዥንብር የተሞላ መንገድ ላይ የምንራመድ ከሆነ “አንድ በአንድ ተንጠባጥበን እስክንጠፋ የዓላማ ጽናት እናሳያን” ወይም በወትሮው አባባል “እስከመጨረሻው አንድ ሰው እንታገላለን”… “የአብዮቱ ባቡር ፈጣን ው” እየተባባልን በሀገር እየተሳለቅን እንዳንከርም ነግ በኔን ማስተዋ ይበጃል፡፡
“ከቆየን አንድ ዓመት፣ ከበላን የተከለከለ ሣር!” እንዳለችው ላም በድርጅዊ አሰራርና ወገናዊነት በዘመዳምነት፤ በእከክልኝ-ልከክልህ፣ በአራዳነት፣ በወደቀው ዛፍ ምሳር በማብዛት፣ በዕቁብም በዕቁባትም በመመነዛዘር ለጌዜው ሙስናን ቢያስፋፉ የሥር የመሰረት ብቅ በሚልበት ሰዓት ምነው አፉን በቆረጠው ምነው እግሬን በሰበረው፣ ማለትን አሊያም የተሰራንበት ንጥረ ነገር በምንም ዓይነት ካባ ብንሸፍነው የማታ ማታ ብቅ ማለቱ ከቶ አይቀርም፡፡ “በትንባሆ የተገዛ ጦር፣ እገበያ መሀል ቢወረውሩት፤ ጓያ ጫፍ ላይ ይቆማል” የሚለው የወላይታ ተረትም የሚነግረን ይሄንኑ ነው፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓልን አስመልክተው የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገና በዓልን አስመልክቶ ያስተላለፉት መልዕክት ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ይቀርባል፡-

ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚነግሩን ሕግ ጥሶ ከእግዚአብሔር ጋር የታጣላው ራሱ የሰው ልጅ ነበረ፡፡ ዕርቅን አውርዶ ሰላምን ለማስፈን በረት ድረስ የመጣው ግን እግዚአብሔር ነው፡፡ እንደ ቅዱሳት መጻሕፍት አስተምህሮ እግዚአብሔር ሁሉን ቻይ፣ አሸናፊ፣ የሚሳነው አንዳች የሌለ ነው፡፡ ነገር ግን ለዕርቅ እና ለሰላም ሲል ወደ ማይገባው ሥፍራ መጣ፡፡ አሸናፊ ቢሆንም እንደ ተሸናፊ ሆነ፡፡ ዐቅም ቢኖረው እንደ ዐቅመ ቢስ ሆኖ ታየ፡፡ በሁሉ ሀብታም ሲሆን፣ ራሱን ታናሽ አደረገ፡፡ ይህ ሁሉ ለዕርቅና ለሰላም የተከፈለ የታላቅነት ዋጋ ነው፡፡

እግዚአብሔር ለዕርቅ እና ለሰላም ሲል በደካማዋ ከተማ በቤተልሔም፣ በተናቀችው ሥፍራ በበረት መገኘቱ የገባቸውም ያልገባቸውም ነበሩ፡፡ የገባቸው፤ ከሰማየ ሰማያት ወርደው “ሰላም እና ዕርቅ በምድር ይሁን” ብለው ዘመሩ፡፡ የገባቸው፤ ከምሥራቅ ኮከቡን አይተው፣ እጅ መንሻውን ይዘው መጡ፡፡ የገባቸው፤ በረታቸውን ለቅቀው ለድንግል ማርያም እና ለኢየሱስ ክርስቶስ ሰጡ፡፡ የገባቸው፤ የሰማይ መላእክቱን ተከትለው ወደ በረት ሄደው እርቅና ሰላምን አመሰገኑ፡፡

Page 3 of 749