Administrator

Administrator

ከአገራችን ተረቶች አንዱ እንዲህ ይላል፡፡ አንድ ቁራ የሚበላው አጥቶ ከቦታ ቦታ ይዘዋወራል፡፡ አየር ላይ ሲንከራተት አንድ አሞራ ያጋጥመዋል፡፡ አሞራ፤ “አያ ቁራ ወዴት እየሄድክ ነው?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ቁራም፤ “የምበላው ነገር ባገኝ ብዬ ብዙ ዞርኩኝ፤ ግን እስካሁን አላገኘሁም” ሲል ይመልሳል፡፡ አሞራ፤ “እዚያ ማዶ በሬ አርደው ቅርጫ ሲያደርጉ ተመልክቻለሁ፡፡ እሰቲ ሂድና አካባቢው ላይ አንዣብ፡፡” ቁራ፤ “እግዚሃር ይስጥህ ወደዚያው ሄጄ የእለት ጉርሴን ብፈልግ ይሻላል፡፡” ቁራ አንደተነገረው በሬ ወደታረደበት መንደር ይሄዳል፡፡ በአየር ላይ ሆኖ ያንቋርራል፡፡ ቅርጫ የሚካፈሉት ሰዎች ያዩትና ድንጋይ እያነሱ እየወረወሩ ያባርሩታል፡፡ ቁራው ይሸሽና ዞሮ ዞሮ መጥቶ ደሞ ዛፍ ላይ ያርፋል፡፡

ሰዎቹ ያዩትና በቅዝምዝም ዱላ ሊመቱት ያምዘገዝጉበታል፡፡ የድንጋይ እሩምታ ይለቁበታል፡፡ ሸሽቶ ወደ አየር ይበራል፡፡ ይሄኔ አሞራ ያገኘዋል፡፡ አሞራ፤ “አያ ቁራ ጠግበህ በላህ?” ይለዋል፡፡ ቁራ፤ “ምን እበላለሁ ሰዎቹ አይናቸውን እኔ ላይ ተክለው በየትኛውም መንገድ ብሞክር ድርሽ አላስደርግ አሉኝ!” አሞራ፤ “እንግዲያው እንዲህ እናድርግ፡፡ አንተ በድንጋይ ቢወረውሩ የማያገኙህ ቦታ ሁንና ጩህባቸው፡፡ አንተን ለመምታት ወዳንተ ዞረው ሲያተኩሩ እኔ አካባቢው ላይ አድፍጬ እቆይና በአሳቻ ሰዓት ደህናውን ብልት መንትፌ እሮጣለሁ፡፡

ከዚያ እንካፈላለን!” ቁራ በዚህ ይስማማና ከፍ ብሎ በአየር ላይ ሆኖ ጩኸቱን ያቀልጠዋል፡፡ አሞራ እንደገመተው ሰዎቹ እየተሯሯጡ ድንጋይም፣ እንጨትም፣ እያነሱ ወደ አየር እያጐኑ መከላከል ቀጠሉ፡፡ ትርምስ ሆነ፡፡ አሞራ ሆዬ አስቀድሞ በቅርጫው አቅራቢያ ሣር የሚግጡ በጐች ዘንድ ይመጣና አንዱ በግ ላይ አርፎ ድምፁን ፀጥ አድርጐ ይጠብቅ ኖሯል፡፡ በጉ መናገርም፤ ከላዬ ላይ ውረድም፤ ለማለት ባለመቻሉ ዝም ብሎ ሣሩን ይግጣል፡፡ አሞራ ትርምሱ በጣም የተጧጧፈበትን አሳቻ ሰዓት ጠብቆ እንዳለው አንዱን ደህና ሙዳ መንትፎ ክንፌ አውጪኝ ይላል፡፡ ቁራ አሁንም ጩኸቱን ቀጥሏል፡፡ አሞራ ወደማይደረስበት አቅጣጫ በረረ፡፡ ቁራ እንዳንቋረረ ቀረ! “ጩኸትን ለቁራ፣ መብልን ለአሞራ” ይሏል ይሄው ነው፡፡ *** የእለት ሳሩን አቀርቅሮ የሚግጥ በግ ሆኖ የአሞራ መቀመጫ ከመሆን ያድነን፡፡

ቀና ብለን ውረድ ለማለት የማንችለው፣ ገፍተን የማናባርረው፤ ሮጠን የማናመልጠው ባላጋራ፣ መረማመጃ ከመሆን ያውጣን፡፡ እንደ ቁራ ከመጮህ፣ እንደባለቅርጫ ህዝብ ሙዳችንን ከመመንተፍ ያትርፈን፡፡ ከሚዲያ ጩኸትና ዘራፌዋ፣ ከማይናከስ አንበሳ አበሳ፣ ሁኔታዎችን ሳያመዛዝን ጥልቅ ከሚል አድር - ባይ ይሰውረን፡፡ “ቅንዝንዝንና፣ የቀን ጐባጣን ስቀህ አሳልፈው፣ ቢያምርህ ሰው መሆን” የሚለውን የሻምበል ዮሐንስ አፈወርቅን ግጥም ልብ እንል ዘንድ ልብ ይስጠን፡፡ የሀገራችን የመማር ማስተማር ሂደት አሳሳቢ ነው፡፡ የራስ እድገት፣ ሀገራዊ እድገትና ሙያዊ እድገት ነው የመማር-መማማር አላማ፡፡ ይህ በእርግጥ እየሆነ ነወይ፤ ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ በተለይ የሳይንስ ነክና ሂሳብ ነክ ትምህርቶች ስምረት አስፈሪ ነው፡፡ በፍላጐት መመደብ ቅንጦት ከሆነ ሰንብቷል፡፡

የተማሪ ሁኔታ ተስፋ ያስቆረጠው መምህር ቁጥር ጥቂት አይባልም፡፡ ከናካቴው ማስተማሩን ለመተው ያኮበኮበው መምህር በቋፍ ያለ መሆኑን ማስረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ “ዝናቡ የትጋ ስንደርስ ነው የመታን?” ብለን እንደ ቹኒአቸቤ የምንጠይቅበት ሰዓት ነው፡፡ ትምህርት አስቀያሚ የሆነው ከመቼ ጀምሮ ነው? በምን ምክንያት? የትውልድ መሰረት የሆነው ትምህርት ቅጥ ካጣ ነገ ምን መሳይ ሊሆን ነው? ብዛት ነው ጥራት የሚያዋጣን? (Academic excellence or mass production? እንዲል ፈረንጅ፡፡

በጌቶች የሚሠራ ወጥ ወይስ ለብዙሃኑ ታዳሚ የሚሰራ የድግስ ወጥ ነው የሚያዋጣን? እንደማለት ነው፡፡ ተምረን ምን ልንሆን ነው? የኮብል - ስቶን ትውልድ እያልን የምንሳለቀው እስከመቼ ነው? ተማሪና አስተማሪ አንድ ገበያ እየዋለ ምን አይነት ሥነምግባራዊ ግንኙነት ሊኖር ነው? የተማሪ አስተማሪ ግምገማ በት/ቤት አዋጣን ወይስ አላዋጣንም? ይሄ ሁሉ ሆኖ ዛሬ የት ደርሰናል? ሃይማኖትና ትምህርት ለየቅል አይደሉም ወይ? በቅን ልቦና ያልተወያየንባቸው ጥያቄዎች አቤት ብዛታቸው? ያም ሆኖ አሁንም አልመሸም፡፡ ብንወያይበትና እውነቱን ፍርጥ ብናደርገው ይበጀናል፡፡ ጥናት ቢቀርብበት ፍሬ እናገኝበታለን፡፡ አለበለዚያ ሥጋቱና ዋስትና ማጣቱ ይገድለናል! “ሰዎች ሁሉ ስጋትና ዋስትና - ማጣት አላቸው፡፡ በዚህ ዋስትና - ማጣታቸው ላይ ከተጫወትክ ታሸንፋለህ፡፡ ሆኖም ሥልጣንን በተመለከተ ሁሉም ነገር የደረጃ ጉዳይ ነው፡፡

በጣም ትልቅ ሥልጣን ያለው ሰዉ የበለጠ ዋስትና - ማጣት የሚሰማውና የባሰበት ሥጉ ሰው ነው፡፡ ስለዚህም ሌሎችን የሚያጠቃውና አደገኛ የሚሆንባቸው በበለጠና በከፋ ደረጃ ነው፡፡ ስለዚህ ከእንዲህ ያለው ሰው ጋር ስትጫወት ስስ ብልት አይተህ ሊሆን ይገባዋል፡፡ ጥቂት ጥቃት እጅግ በጣም ይሰማዋል! ይህንን አትርሳ” ይለናል ሮበርት ግሪን፡፡ አሞራ፤ ቁራ መጮህ እንደሚቀናው አውቋልና እሱን እያስጮኸ ሙዳውን ይወስዳል፡፡ “የኛ ተግባር መማር መማር መማር!” የሚለውን አሮጌ መፈክር ባንዘነጋው መልካም ነው፡፡ከት/ቤትም መማር፣ ከኑሮም መማር ይጠብቅብናል፡፡ በመምረጥና በማጽደቅ መካከል ልዩነት መኖሩን እንማር፡፡ የኳስ ቲፎዞ በመሆንና የፖለቲካ ቲፎዞ መሆን መካከል ልዩነት መኖሩን እንማር፡፡ “ትላንትማ ቤትህ ደጃፍ ላይ እንቅፋት የመታህ ድንጋይ ዛሬም ከመታህ ድንጋዩ አንተ ነህ፤ የሚለውን የቻይኖች አባባል አንዘንጋ፡፡

በሀገራችን ብዙ ነገሮችን ለመተግበር ከጥናትና እቅድ ይልቅ በዘመቻ ማመናችን የቆየ ባህል ነው፡፡ የዘመቻ ሥራ ደግሞ ያንድ ሰሞን ሆይሆይታ ነው፡፡ ዘራፍ ይበዛዋል፡፡ ስለሆነም “የእነ ቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንበሌጥ መሆኑ አይታበሌ ነው! ለሚዲያ ፍጆታ፣ አሊያም ለውጪ መንግሥታት ተቋማት ጆሮ-ገብነት ብለን በአንድ ወቅት እንደቁራ የምንጮኸውን ጩኸት፣ ነገ ደግመን የማንሰማው ከሆነ፤ የጊዜ፤ የሰው ኃይልና የአቅም ብክነት ብቻ ነው የሚሆነው፡፡ የምንጮኸውን ከልባችን እንጩህ! የምንሰራውን ከልባችን እንሥራ! ይሄን አቀድኩ ይሄን እስካሁን ፈፀምኩ ለማለት ብቻ የምንጣደፍበት ደርዝ-አልባ ጉዞ ከንቱ ነው፡፡ “በችኮላ ቅቤ ያንቃል፤ ቀስ በቀስ ድንጋይ ይዋጣል” የምንለው ያለነገር አይደለም፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የስድስተኛው ፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ÷ ካህናት እና ምእመናን ስድስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባት ሊኾን ይገባል የሚሉትን ዕጩ በመጠቆም እንዲሳተፉ ጠየቀ፡፡ አስመራጭ ኮሚቴው፣ ስለ ስድስተኛው ፓትርያሪክ የምርጫ ሂደትና የተመረጡት ፓትርያሪክ ስለሚሾሙበት ቀን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ካህናትና ምእመናን ግልጽ ለማድረግ ከትላንት በስቲያ በጽ/ቤቱ በሰጠው መግለጫ ባስተላለፈው ጥሪ÷ በሀገር ውስጥ ያሉ ካህናት÷ አገልጋዮች መኾናቸውን፣ ምእመናንና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ደግሞ የአጥቢያው ቤተ ክርስቲያን አባላት መኾናቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ በመያዝ በአስመራጭ ኮሚቴው ጽ/ቤት በአካል በመቅረብ፣ ከሀገር ውጭ የሚገኙትም በፋክስ ቁጥር 011 - 1567711 እና 011-1580540 ከየካቲት 1 - 8 ቀን 2005 ዓ.ም ድረስ ዕጩአቸውን እንዲጠቁሙ ጠይቋል፡፡

አራት ሊቃነ ጳጳሳትን፣ ሁለት የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎችን፣ ሁለት የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎችን፣ አንድ የሰንበት ት/ቤት፣ አንድ የማኅበረ ቅዱሳንና ሦስት የምእመናን ተወካዮችን በአጠቃላይ 13 አስፈጻሚዎችን በአባልነት በያዘውና ታኅሣሥ 10 ቀን 2005 ዓ.ም በቅ/ሲኖዶስ በተቋቋመው አስመራጭ ኮሚቴ ወጥቶ በቋሚ ቅ/ሲኖዶሱ መጽደቁ በተገለጸው መሪ ዕቅድ እንደሚያመለክተው÷ የስድስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ ሂደት የሚጀምረው ለአንድ ሱባኤ/ሳምንት በሚቆይ የጸሎት ጊዜ ነው፡፡ ከትላንት የካቲት 1 ቀን እስከ የካቲት 8 ቀን 2005 ዓ.ም በሚዘልቀው በዚህ የጸሎት ሱባኤ÷ ቤተ ክርስቲያኒቱ ቅን/ርቱዕ መሪ እንድታገኝ፣ እግዚአብሔር የወደደውንና የፈቀደውን በመንበሩ ያስቀምጥ ዘንድ ካህናቷና ምእመናንዋ አምላካቸውን በጸሎት እንዲማፀኑ በዐዋጅ ታዝዘዋል፡፡በምርጫው ለመሳተፍ የሚችሉት መራጮች÷ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች፣ የጥንታውያን ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ካህናት፣ ምእመናን፣ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች እና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ናቸው፡፡

ታኅሣሥ 8 ቀን 2005 ዓ.ም ቅ/ሲኖዶሱ ባጸደቀው የፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንብ አንቀጽ 7 ንኡስ አንቀጽ 1 - 7 ላይ በተዘረዘረው የመራጮች ማንነት÷ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በሙሉ፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ም/ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያና የድርጅት ሓላፊዎች፣ የየሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች፣ በሀገር ውስጥና በውጭ አገር የሚገኙ ገዳማት አበምኔቶች፣ እመምኔቶች እና የታላላቅ አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ከየሀገረ ስብከቱ ሰበካ ጉባኤያት የተወከሉ አራት የካህናት፣ አራት የምእመናንና አራት የሰንበት ት/ቤት ተወካዮች ጠቅላላ ብዛታቸው ከእያንዳንዱ ሀገረ ስብከት 12 ሰዎች፣ የመንፈሳዊ ኮሌጆች መምህራንና ተማሪዎች ተወካዮች ከየኮሌጆቹ ሁለት ሁለት ሰው፣ ቤተ ክርስቲያን ሕጋዊ ዕውቅና የሰጠቻቸውና ከቤተ ክርስቲያኗ ጋራ አብረው በመሥራት ላይ የሚገኙ ማኅበራት ተወካዮች ከየማኅበራቱ አንድ አንድ ሰው እንደኾኑ ተደንግጓል፡፡

በዚህ ድንጋጌ መሠረት በስድስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ የሚሳተፉ መራጮች አጠቃላይ ቁጥር 800 ሲሆን ይህም ባለፉት አምስት ፓትርያሪኮች ከተሳተፉት መራጮች ብዛት ጋራ ሲነጻጸር ‹‹በእጅጉ የላቀ ነው›› ተብሏል፡፡ በሀገር ውስጥ በሚገኙት የ53ቱ አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት ሰብሳቢነት በሚመራ የአስተዳደር ጉባኤ ውሳኔ የሚለዩት መራጮች ዝርዝር እስከ የካቲት 16 ቀን ለአስመራጭ ኮሚቴው እንዲላክ፣ መራጮቹም እስከ የካቲት 19 ቀን 2005 ዓ.ም አዲስ አበባ እንዲገቡ መታዘዙን የኮሚቴው መግለጫ ጠቅሷል፡፡

በፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንቡ እንደተደነገገው፣ ምርጫው ታዛቢዎች ይኖሩታል፡፡ እኒህም÷ ከአራቱ አኀት አብያተ ክርስቲያናት (ግብጽ፣ አርመን፣ ሕንድ እና ሶርያ) ከእያንዳንዳቸው አንድ አንድ ሰው፣ ከዓለም አብያተ ክርስቲያናት ማኅበር አንድ፣ ከአፍሪቃ አብያተ ክርስቲያናት ም/ቤት አንድ፣ በቋሚ ቅ/ሲኖዶስ ከቤተ ክርስቲያኗ ምእመናን የሚመረጡ ታዋቂ የአገር ሽማግሌዎች ሦስት፣ በመንግሥት የሚወከሉ ሦስት ሰዎች እንደኾኑ ተገልጧል፡፡አስመራጭ ኮሚቴው እስከ የካቲት 16 ቀን 2005 ዓ.ም በፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንብ የዕጩዎች መመዘኛ መሠረት አጣርቶ ለምርጫ የሚያቀርባቸውን ዕጩ ፓትርያሪኮች ማሳወቅ ይጠበቅበታል፤ ለምርጫ የሚቀርቡት ዕጩዎች ብዛትም አምስት ነው፡፡

ለዕጩ ፓትርያሪክነት የሚጠቆመው ሊቀ ጳጳስ፣ ጳጳስ ወይም ኤጶስ ቆጶስ÷ ዜግነቱ ኢትዮጵያዊ የኾነ፣ የውጭ አገር ዜግነት ካለውም የውጭ ዜግነቱን ሰርዞ ወደ ኢትዮጵያዊነቱ የተመለሰ፣ ዕድሜው ከ50 ዓመት ያላነሰ ከ70 ዓመት ያልበለጠ፣ ከቤተ ክርስቲያኒቱ የአብነት ትምህርቶች ቢያንስ በአንድ ጉባኤ የተመረቀ ቢቻል ሁለገብ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ያለው ኾኖ ከከፍተኛ የመንፈሳዊ ትምህርት ተቋማት ወይም በዘመናዊ ትምህርት ቢያንስ ዲፕሎማ ወይም ዲግሪ ያለው፣ ሙሉ አካል ያለውና ጤንነቱ የተሟላ፣ የቤተ ክርስቲያኗ ቋንቋ የኾነውን ግእዝን የሚያውቅ ኾኖ ቢቻል ከዓለም አቀፍ ቋንቋዎች አንዱን የሚያውቅ፣ በቅድስና ሕይወቱና በግብረ ገብነቱ የተመሰገነ፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በመፈጸም በቂ የአስተዳደር ችሎታና ልምድ ያለው መኾን እንደሚገባው በፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንቡ ላይ በሰፈረው መመዘኛ ተደንግጓል፡፡ ከአምስቱ ዕጩዎች መካከል ለዕጩ ፓትርያሪክነት ይኹንታ የሚሰጣቸውን አባቶች ለመወሰን የመጨረሻ ሥልጣን ያለው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ነው፡፡ ምልአተ ጉባኤው ከየካቲት 16 ቀን ጀምሮ ተሰብስቦ ከተወያየ በኋላ የካቲት 19 ቀን 2005 ዓ.ም አምስቱን ዕጩ ፓትርያሪኮች ለሕዝቡ ይፋ እንደሚያደርግ በኮሚቴው መግለጫ ላይ ተጠቅሷል፡፡

የ፮ኛው ፓትርያሪክ ምርጫ የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም እንደሚከናወን፣ ለፓትርያሪክነት የተመረጠው አባት በዓለ ሢመት ደግሞ የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም እንደሚፈጸም ኮሚቴው ያስታወቀ ሲኾን ምርጫው ኀሙስ፣ የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም ተካሂዶ በዚሁ ዕለት ከምሽቱ 12፡00 ላይ የተመረጠው አባት በብዙኀን መገናኛ አማካይነት ለሕዝብ ይፋ እንደሚኾን ገልጧል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በራሷ ሲኖዶስ መመራት ከጀመረችበት ከ1951 ዓ.ም ወዲህ ስድስተኛ ፓትርያሪክ በመኾን ለመንበረ ተክለ ሃይማኖት የሚመረጠው አባት ሹመት (በዓለ ሢመት) የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም ኮሚቴው አስታውቋል፡፡ በዓለ ሢመተ ፕትርክናውም የሚከናወነው ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የልዩ ልዩ አብያተ ክርስቲያን መሪዎች፣ የሃይማኖት ተቋማት ተወካዮች፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ካህናትና ምእመናን በተገኙበት እንደሚኾን በመግለጫው ላይ ተመልክቷል፡፡

አንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ (አንድነት) በማተሚያ ቤት ዕጦት ምክንያት ለተቋረጠው የፓርቲው ልሳን ዘላቂ መፍትሄ ለመስጠት የተለያዩ የገቢ ማስገኛ ዝግጅቶች እና እርዳታዎችን አሰባስቦ የማተሚያ ማሽን ለመግዛት ማቀዱን አስታወቀ፡፡ ፓርቲው በትናንትናው ዕለት በጠራው ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳስታወቀው፤ ለአንድ ዓመት ከሁለት ወር ያህል የመንግሥት በሆነው ብርሀንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት እየታተመ በየሣምንቱ ማክሰኞ ለገበያ ይቀርብ የነበረውን “ፍኖተ ነፃነት” የተባለ የፓርቲው ጋዜጣ ወደ አንባቢው ለመመለስ በውጭ እና በአገር ውስጥ ከሚገኙ ደጋፊዎቹ በአራት ወር ጊዜ ውስጥ ገንዘብ በማሰባሰብ አንድ ሚሊዮን ብር የሚያወጣ የማተሚያ ማሽን ለመግዛት አቅዷል፡፡

በዕለቱ የፓርቲው ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ እንደተናገሩት፤ በሕጋዊ መንገድ የተቋቋመ ማንኛውም ፓርቲ የራሱን ልሣን የማሳተም መብት እንዳለው ሕጉ ቢደነግግም፤ መንግሥት ማተሚያ ቤቶች ላይ በሚያደርገው የተለያዩ ጫናዎች ምክንያት በተፈጠረ ፍርሀት ጋዜጣ ብቻ ሳይሆን ደረሰኝ ማሳተም እንደተቸገሩ ተናግረዋል፡፡

በማተሚያ ቤት ዕጦትም ለአባላቱና ለኅብረተሰቡ መረጃ በመስጠት የሚገለገሉበትን ጋዜጣ ማተም እንደተቸገሩ ገልጸዋል፡፡ በማተሚያ ቤት ምክንያት ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ላይ የተጣለውን እገዳ ለመታገል የማተሚያ ማሽኑን መግዛት እና የሕትመት ውጤቱን ማስቀጠል አስፈላጊ መሆኑን የተናገሩት ዶ/ር ነጋሶ፤ ከአስፈላጊነቱ ዓላማ በመነሳት የተለያዩ ጥናቶችን ሲያካሂዱ ቆይተው ማሽኑ ከአጋዥ መሣሪያዎቹ ጋር አንድ ሚሊዮን ብር እንደሚያወጣ እንደተረዱ ገልጸዋል፡፡

ማሽኑን ለመግዛት ከአቅራቢ ድርጅቶች ጋር መነጋገር መጀመራቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህንን የፓርቲውን ዓላማ እና ፍላጎት ለማሳካት የሚደረገውን የገቢ ማሰባሰብ ፕሮጀክት ለማከናወን ሦስት ኮሚቴዎች መቋቋማቸውን የገለፀው ‹‹የፍኖተ ነፃነት›› ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ነብዩ ኃይሉ ስለ ገቢ ማሰባሰቢያ እቅዱ እንዳብራሩት፤ መጽሐፍትን በመሸጥ፣ ከ30 ብር እስከ 1ሺሕ ብር ለሚለግሱ ኩፖን፣ ከተጠቀሰው ገንዘብ በላይ መለገስ ለሚፈልጉ የቃል ኪዳን ሰነድ መዘጋጀቱን እና ዓላማውን የሚደግፍ ማንኛውም ሰው በባንክ ሂሳብ ቁጥራቸው ገቢ ማድረግ እንደሚችል ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም በኢንተርኔት ኦን ላይን ከዛሬ ጀምሮ እስከ ሚቀጥሉት አራት ወራት የገቢ ማሰባሰቡን ሥራ እንደሚቀጥሉ ጠቁሟል፡፡

ዶ/ር ነጋሶ በበኩላቸው፤ “ፍኖተ-ነፃነት” ለአባላቱና ለህብረተሰቡ ብቻ ሳይሆን ኢህአዴግም ቢሆን ሃሳቡን ማስተላለፍ ከፈለገ ሊገለገልበት እንደሚችል ተናግረዋል፡፡ ፓርቲዎች በማተም ሥራ ላይ ሲሠማሩ ቀረጥ መክፈል እንደሌለባቸውም በህጉ ማስቀመጡን ገልፀው፤ ማሽኑ የሌላ ሰው የህትመት ሥራ እንደማይሠራና “ከፍኖተ-ነፃነት” በተጨማሪም በኦሮምኛና በሌሎች የአገሪቱ ቋንቋዎች የሚሠራጩ የራሱን ኒውስሌተሮች የመስራት ሃሳብ እንዳለው ዶ/ሩ ገልፀዋል፡፡ የገቢ ማሰባሰቡ ከዛሬ ጀምሮ ለቀጣዮቹ አራት ወራት እንደሚቀጥልም ለማወቅ ተችሏል፡፡

በተያያዘ ዜና የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊና የቋንቋ ምሑር ዶ/ር ኃይሉ አርአያ “ቋንቋና የቋንቋ ፖሊሲ” በሚል ርእስ ነገ ረፋድ ላይ በአንድነት ጽ/ቤት ጥናት እንደሚያቀርቡና ውይይት እንደሚካሄድ የተገለፀ ሲሆን ህብረተሰቡ በውይይቱ ተካፋይ እንዲሆን ግብዣ ቀርቧል፡፡

“... እንግዲህ የእናቶች ጤና ሲባል በቅድሚያ እናቶችን ለጉዳት የሚዳርጋቸው የእናቶቹ ወደ ሆስፒታል ያለመምጣት ችግር ነው፡፡ ይህ ምክንያቱ የተለያየ ሲሆን አሁን አሁን ግን መንግስት የጤና ኤክስንሽን ሰራተኞችን ለህብረተሰቡ ቅርብ በሆነ ሁኔታ እያሰማራ እና እናቶቹም ስለጤናቸው እንዲማሩ እየተደረገ ስለሆነ የተሻለ ነገር አለ ማለት ይቻላል፡፡ ነገር ግን አሁንም ብዙ መስተካከል የሚገባቸው ነገሮች እንዳሉ አይካድም፡፡ እናቶች ለህክምና ወደሆስፒታል ሲመጡም አገልግሎት የሚሰጥባቸው መሳሪያዎች በበቂ ሁኔታ መገኘት ይገባቸዋል፡፡ የህክምናው ባለሙያ ክህሎትና የመሳሰሉት ሁሉ የእናቶችን ጤንነት ለመጠበቅ አንዱም ሳይዛባ በተሟላ መንገድ መገኘት ይገባቸዋል፡፡ ... የጤና ባለሙያው በቂ የሆነ ችሎታ ኖሮት በበቂ መሳሪያ እየታገዘ ህክምናውን እንዲሰጥ ሁኔታዎች መሟላት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህ ካልሆነ የእናቶች ወደሆስፒታል መምጣት አለመምጣት ምንም ልዩነት የለውም፡፡ ምናልባት ልዩነት ሊባል የሚችለው ወደሐኪም ሳይሄዱ ከእቤት መሞት ወይንም ሐኪም ቤት ሄዶ መሞት በሚል ሊገለጽ የሚችል ብቻ ነው...” ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ /የጽንስና ማህጸን ሕምና እስፔሻሊስት የእናቶችና ሕጻናትን ሞት በመቀነስ ረገድ የደብረማርቆስ ሆስፒታል ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር እየሰራ መሆኑን ዶ/ር አብነት ሲሳይ በደብረማርቆስ ሆስፒታል የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ገለጹ፡፡

እንደ ዶ/ር አብነት ገለጻ የደብረማርቆስ ሆስፒታል ከኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ጋር ከሚሰራው ስራ በተጨማሪ አይክ ኢትዮጵያ ከሚባል ግብረሰናይ ድርጅት ጋር በመተባበር የእናቶችን እና ሕጻናትን ጤንነት በሚመለከት ለሚሰራው ስራ ከተመረጡ ሁለት ሆስፒታሎች አንዱ ሆኖአል፡፡ ደብረማርቆስ ከአማራ ክልል ከትግራይ ደግሞ አድዋ ሆስፒታል ተመርጠው ከተወሰኑ ወራት ወዲህ ስራ የጀመሩ ሲሆን ከሕብረተሰቡ ጋር በተቀናጀ ሁኔታ መስራት አስፈላጊ በመሆኑ ንቃተ ህሊናን የማዳበር ስራ ተሰርቶአል፡፡ በጤና ተቋም ወይንም ወደ ሆስፒታል በመቅረብ የሚወልዱ እናቶች ቁጥር 20ኀ የማይሞላ በመሆኑ ይበልጡኑ እናቶችን ለማዳን ወደ ህብረተሰቡ መውረድ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቶአል፡፡ ወደህብረተሰቡ ለመድረስ ደግሞ የጤና ኤክስንሽን ሰራተኞች ዋናዎቹ ድልድዮች በመሆናቸው በደብረማርቆስ ዙሪያ ያሉትን ሙያተኞች ጠርተን የፕሮግራሙን አላማ ከማስረዳት ጀምሮ የጤና ኤክስንሽን ሰራተኞቹ እናቶችን ከጤና ኬላ ወደ ጤና ጣብያ እንዲያስተላልፉ ከዚያም ከፍ ወዳለ ሆስፒታል የመቀባበልን ሁኔታ በተቀናጀና ስርአት ባለው መንገድ እንዲሰራ አስፈላጊ መሆኑን እንዲገነዘቡ በማድረግ ስራው ተጀምሮአል፡፡

እናቶች ብዙውን ጊዜ በእርግዝና ጊዜ ክትትል ሲያደርጉ ቢቆዩም ለመውለድ ወደሆስፒታል ወይንም ክትትል ሲያደርጉ ወደቆዩበት ጤና ተቋም የሚሄዱት በጣም ጥቂቶች የመሆናቸው ጉዳይ አሳሳቢ በመሆኑ ይህንን ሁኔታ መልኩን በመቀየር እናቶች በወሊድ ጊዜ ወደሆስፒታል ለመሄድ የሚያስችላቸውን ቅድመ ዝግጅት እንዲያደርጉ የሚያስችላቸውን ዘዴ መምከር ተገቢ ይሆናል፡፡ ይህንንም በተገቢው ለማስፈጸም እንዲያስችል ከኢሶግ እንዲሁም ከአይክ ጋር የሚሰራው ስራ የእርግዝና ክትትል ስታደርግ የቆየች እናት በመሀከል ብትሰወር ወደየት እንደደረሰች ፣ወልዳ ይሁን ወይንስ? በምን ምክንያት ? የሚለውን ለይቶ ማወቅና እናቶች ያሉበትን ሁኔታ በሚገባ ተረድተው ቅድመ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ለማስቻል የሚደረግ ክትትልን ይጨምራል፡፡ የደብረማርቆስ ሆስፒታል ከኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ጋር በመተባበር 5/ጤናጣቢያዎችን ባካተተ መልኩ የእናቶችንና የጨቅላዎችን ሞትና ደህንነት ሁኔታ በክትትል ይመዘግባል ፡፡ በዚህም መሰረት ከአንድ ወር በፊት ስለነበረው አሰራር በዶ/ር... ያለምወርቅ እንደቀረበው ሪፖርት ከሆነ በጤናጣቢያዎቹ ለሚኖረው አገልግሎት አንድ አምቡላንስ ተመድቦ አስፈላጊ በሆነበት ቦታና ሰአት እናቶችን ወደሆስፒታል ማመላለስ ተጀምሮአል፡፡ ሆስፒታሉ በየወሩ ከየጤናጣብያዎቹ ጋር በየወሩ በስብሰባ የሚገናኝ ሲሆን ችግሮችንም ከስር ከስሩ እየተከታተሉ መፍታት የሚያስችል አሰራር ተዘርግቶአል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ጤናጣብያዎቹ ለእናቶች ማበርከት ያለባቸውን አገልግሎት ጠንቅቀው እንዲያውቁና እንዲተገብሩ ለማስቻል ድጋፍ ይደረግላቸዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በየወሩ በሚኖረው ዳሰሳ የእናቶችን እና ጨቅላዎችን ሞት በተመለከተ በማዋለጃ አካባቢ ብቻ ሳይሆን በሆስፒታሉ በተለያዩ ክፍሎችም ያለው ሁኔታ በሪፖርት እንዲካተት ይደረጋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የእናቶችንና ጨቅላዎችን ሞት በመመዝገቡ ረገድ በሆስፒታሎችና በጤና ጣቢያዎች ያለውን ብቻም ሳይሆን እናቶች በቤታቸው እንዳሉ የተከሰተ ነገርም ካለ በቀበሌና በኤክስንሽን ሰራተኞች አማካኝነት እንዲመዘገብ የሚያስችል አሰራር ተዘርግቶአል፡፡ በደብረማርቆስ ሆስፒታል እንደውጭው አቆጣጠር በኦክቶበር ወር 150/አንድ መቶ ሀምሳ እናቶች የወለዱ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ ከጤና ጣብያዎች እስከ ሰማንያ ኪሎ ሜትር ከሚደርስ እርቀት በቅብብል የመጡና እራሳቸውም ወደ ሆስፒታሉ የመጡ ይገኙበታል፡፡ በአጠቃላይ ወደ 27 የሚሆኑ እናቶች ወደሞት አፋፍ ደርሰው የነበሩ ሲሆን ነገር ግን በሆስፒታሉ የተመዘገበ የእናቶች ሞት የለም፡፡ ለሞት አፋፍ እንዲደርሱ ከሚዳርጉዋቸው ምክንያቶችም አንዱ ደም መፍሰስ ሲሆን ሁለት እናቶች የማህጸን መተርተር የደረሰባቸው ናቸው፡፡ ሁለት እናቶች ደግሞ ከማህጸን ውጭ ያረገዙ ሲሆን ውርጃም የሚጠቀስ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ እናቶች ከወለዱ በሁዋላ የሚከሰት የደም መፍሰስ አብዛኛውን ለሞት አፋፍ የመድረስ ሁኔታ ማለትም 25 በመቶ የሚሆነውን ድርሻ ይይዛል፡፡ ከእርግዝና ጋር ተያይዞ የሚከሰት የደም ግፊትም ያጋጠመ ሲሆን አስፈላጊውን ሕክምና በማግኘታቸው ከሞት ተርፈዋል፡፡ ከዚህ ውጭ የትራንስፖርት፣ የምግብ እጥረት እና የቤተሰብ እቅድ ዘዴን ባለመጠቀም ምክንያት እና ብዙ የወለዱ እናቶችም ለከፋ አደጋ ተጋልጠው ተገኝተዋል፡፡ ወደ ሀያ የሚሆኑ እናቶች በልጅነታቸው ግርዘት የተፈጸመባቸው ሲሆን በጎጂ ልማዳዊ ድርጊት ምክንያት በምጥ ጊዜ ለሚከሰቱ ሕመሞች የተጋለጡም አሉ ፡፡

ለሞት አፋፍ የደረሱ እናቶች እድሜ ከ20-40 የሚደርሱ ሲሆኑ የልጅነት ጋብቻም ለችግር ከሚያጋልጡ መካከል ናቸው፡፡ ከላይ የተጠቀሱትን ችግሮች ለመቅረፍም ህብረተሰቡን በማስተማሩ ረገድ በአቅራቢያው ያሉት የጤና ባለሙያዎች የበኩላቸውን ድርሻ ተወጥተዋል፡፡ በደብረማርቆስ ሆስፒታል የእናቶችን እና የጨቅላ ሕጻናትን ሞት ምክንያት ለማወቅ በሚደረገው አሰራር ያጋጠሙ ችግሮችን በሚመለከት የሕመምተኞች የቅብብል ሁኔታ አንዱ ሲሆን ሌላው የኤሌክትሪክ መስመር አለመኖር ነው፡፡ በማዋለድ ረገድ አንዳንድ ተጨማሪ መሳሪያዎች እንደቫኪዩም የመሳሰሉ ማለት ነው እጥረቱ እንዳለ ተገንዝበናል፡፡ ነገር ግን መፍትሔውን በሚመለከት አንዳንድ ጤና ጣቢያዎች ያለባቸውን የቅጽ እጥረት እራሳቸው በመፍጠር ተገቢውን መረጃ አያይዞ ወደሆስፒታል የመላክ አሰራር ተጀምሮአል፡፡ የኤሌትሪክ አገልግሎትንም በሚመለከት ለአንዳንድ ጤና ጣቢያዎች በቻርጀር የሚሰራ መብራት ለመስጠት ሁኔታዎች ተመቻችተዋል፡፡ የህክምና መርጃ መሳሪያዎችም በተቻለ መጠን በጎደለበት ቦታ እንዲሰጥ ሆስፒታሉ የራሱን መፍትሔ ዘርግቶአል፡፡ በአጠቃላይም ከጤናጣቢያዎቹ ጋር በወር አንድ ጊዜ አጠቃላይ ስብሰባ የሚደረግ ሲሆን በሆስፒታሉ ከሰራው ጋር የሚገኛኙት የሚመለከታቸው ባለሙያዎች በሙሉ ወደጤናጣቢያዎች እየወረዱ የጎደለውን ነገር የማየት ስራ እንዲሰራ ከስምምነት ተደርሶአል፡፡ ከሆስፒታሉ ጋር በትብብር የሚሰሩ ሳላይት ጤና ጣቢያዎችን በምን መንገድ ማጠናከር እንደሚገባ እና ያለውን ክፍተት ማሟላት እንዲሁም ምላሾችን በተገቢው በመመርመር አስፈላጊውን ማድረግ በሆስፒታሉ የተዋቀረው ቡድን ስራ መሆኑ የታመነበት ስለሆነ የእናቶችንና ጨቅላዎችን ሞት ምክንያት ከማወቅ አንጻር የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ እሙን ነው እንደ ዶ/ር ያለምወርቅ፡፡

የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ከአለምአቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ጋር በመተባበር በሚያደርገው እገዛ በኢትዮጵያ ከ9/መንግስታዊ ሆስፒታሎችና 45/ ጤና ጣብያዎች ጋር በመተባበር የእናቶችን ሞት ሁኔታ ለማወቅ ለሚሰራው ስራ እንዲረዳ በየሆስፒታሎች መረጃ ለመሰብሰብ እንዲያስችል አንዳንድ ኮምፒዩተር ገዝቶ አከፋፍሎአል፡፡ ዶ/ር አብነት ሲሳይ ከደብረማርቆስ ሆስፒታል የኮምፒዩተሩን አገልግሎት ሲገልጹ ከአሁን ቀደም ባለው አሰራር የህመምተኞች ካርድ በአካል የሚቀመጥ ሲሆን ከቦታ ጥበት የተነሳ ከተወሰነ ጊዜ በሁዋላ እንዲቃጠል ይደረጋል፡፡ አሁን ግን ኮምፒዩተሩን በማግኘታችን ...ለምሳሌ የዛሬ ሶስት አመት አንዲት እናት ታክማ የነበረ እና ሐኪሙዋ በሌለበት እንደገና ለሕክምና ብትመለስ በኮምፒዩተር የተያዘ መረጃ ካለ በቀላሉ ችግርዋን ለመረዳት እና በወቅቱ ባለው ሐኪም ለመረዳት ትችላለች፡፡ ስለዚህ የህሙማኑን መረጃ በተሙዋላ መንገድ ለረጅም ጊዜ ለማስቀመጥ የሚረዳ በመሆኑ ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያውያን ስደተኞችና እግር ኳስ በደቡብ አፍሪካ
በደቡብ አፍሪካ በስደት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በርካታ ናቸው። የ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ድል እንዲቀናው ስታዲየም ገብተው ድጋፋቸውን በመስጠት ከፍተኛ እንቅስቃሴ አድርገዋል፡፡ ድጋፍ አሰጣጣቸውም ከጨዋታው ቀጥሎ የዓለም አቀፍ ብዙሃን መገናኛውን ቀልብ ከሳበ ጉዳይ አንዱ ሆኖ አልፏል፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጣ የስፖርት አምድ አዘጋጅ ግሩም ሰይፉ በደቡብ አፍሪካ ጨዋታዎቹ በተካሄዱበት ስታዲየም ተገኝቶ ከጥቂቶቹ ኢትዮጵያውያን ጋር እንዴት ደቡብ አፍሪካ እንደገቡ፣ ስለሚገኙበት ሁኔታ እና ስለሰጡት ድጋፍ ጠይቋቸው እንደሚከተለው መልሰዋል፡፡
“ኤርትራዊ ብሆንም ዋልያዎቹን ደግፌአለሁ”
ሰናይ ነጋ

የተወለድኩት በደሌ የሚባል ስፍራ ኢሊባቡር ውስጥ ነው፡፡ከልጅነቴ ጀምሮ ኳስ ስለምወድ እጫወትም ነበር፡፡የአንደኛ ደረጃ ትምህርቴን እዚያው ኢሊባቡር ውስጥ ተማርኩ፡፡ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን ደግሞ በአየር ጤና እና በቦሌ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተከታትያለሁ፡፡በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል በተነሳው ግጭት ኤርትራዊ በመሆኔ ከቤተሰብ ጋር ወደ ኤርትራ ሄድኩ፡፡ኤርትራ የገባሁት የ23 ዓመት ወጣት ሆኜ ነበር፡፡ በኤርትራ ለ11 ዓመታት በውትድርና ቆየሁ፡፡
የውትድርና ህይወት ሲያማርረኝ በሽሬ በኩል አቋርጬ ወደ ኢትዮጵያ ተመለስኩ፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ እህቴ ስለነበረች እርሷ ጋር ለ15 ቀናት ቆየሁ፡፡
ከዚያ በኋላ በሞያሌ አድርጌ ናይሮቢ ገባሁ፡፡ከሁለት ዓመት የናይሮቢ ቆይታ በኋላ በአውሮፕላን ደቡብ አፍሪካ ገብቼ እዚህ ከነበሩ ቤተሰቦቼ እና ጓደኞቼ ጋር ተቀላቀልኩ፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ በንግድ ሥራ ተሰማርቼ እየሠራሁ ነው፡፡ኳስ ጨዋታ ብዙም አልከታተልም ነበር፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ወደ ደቡብ አፍሪካ ሲመጣ ግን እዚህ ካሉ ኢትዮጵያውያን ጋር ስለምሠራ፣ የነበረው መንፈስ ግጥሚያቸውን እንዳይና ቡድኑን ለመደገፍ አነሳሳኝ፡፡ዜግነቴ ኤርትራዊ ቢሆንም የተወለድኩበት ያደግኩበት እና የተማርኩበት አገር ኢትዮጵያ ስለሆነች “ዋልያዎቹን” ደስ ብሎኝ ደግፌአለሁ፡፡

* “Conversation with God” የሚለው መፅሃፍ “እግዚአብሄር ፖለቲከኛ ነው” ይላል * ምርጫ ቦርድ “ሆደሰፊ” እየሆንኩ ነው ብሏል (እንመነው እንዴ?) ዛሬ ከናንተ ምን እንደምፈልግ ታውቃላችሁ? የኢህአዴግን “ትዕግስት” እና የምርጫ ቦርድን “ሆደሰፊነት” ብቻ! (ራሳቸው ሲናገሩ ሰምቼ እኮ ነው!) ሁለቱ አለን የምትሉ ከሆነ ግን በነፃነት ማውጋት፤ አዳዲስ ምስጢሮችን መለዋወጥ፤ ፖለቲከኞችን ማማት፤ ባለሥልጣናትን “መቦጨቅ” (ማስረጃ ባይኖረንም በመረጃ) እንችላለን፡፡ እንዳልኳችሁ እናንተ ብቻ ትዕግስቱና ሆደ ሰፊነቱ ይኑራችሁ፡፡ እኔ የምለው ግን--- ሰሞኑን ምርጫ ቦርድ “ሆደሰፊነቱን” በኢቴቪ ሲናገር ሰምታችኋል? (የአበሻ ይሉኝታ አያውቅም ልበል?) ከኢህአዴግ ጋር የፓርቲዎች ምክር ቤት አባል የሆኑ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የእጩዎች ማስመዝገቢያ ጊዜ እንዲራዘምላቸው ጠይቀው፤ በአስር ቀን አራዘምኩ ብሎ እኮ ነው “ሆደ ሰፊ ነኝ” ያለው (ሆደ ሰፊ አያውቅም ማለት ነው!) ባለፈው ሳምንት የኢህአዴግ ፅ/ቤት ሃላፊ የሆኑት አቶ ሬድዋን ሁሴን ከምርጫው ጋር በተገናኘ ስለተቃዋሚዎች ያሉትን ሰምታችኋል አይደል? (ኢህአዴግ ግን አሳዘነኝ!) በምርጫው ይሸነፋል ብዬ እንዳይመስላችሁ! (መታሰቡስ!) በነገራችሁ ላይ አንድ ፖለቲከኛ ወዳጅ አለኝ --- ሁሌ ምርጫ ሲቃረብ “አስማተኛ ፓርቲዎች ካልተፈጠሩ በስተቀር ኢህአዴግ በምርጫ አይሸነፍም!” ይለኛል (የሚያውቀው ነገር ቢኖር ነው) አስማቱን ትተን ወደ ነባራዊው እውነታ ስንመጣ --- አቶ ሬድዋን ምን ነበር ያሉት? “የተቃዋሚዎች በምርጫው መሳተፍና አለመሳተፍ ትርፍም ኪሳራም የለውም” በዚህ አነጋገራቸው የበሸቀ ሌላ ወዳጄ “የሳቸውም ንግግር ያው ነው!” አለኝ - በንዴት ጨሶ (ትርፍም ኪሳራም የለውም ማለቱ እኮ ነው!) አንድ ታዋቂ የአገር ውስጥ የፖለቲካ ተንታኝ በሰጡት አስተያየት ደግሞ “ንግግሩ ለሃያ አንድ ዓመት በሥልጣን ላይ ለቆየ ፓርቲ አይመጥንም” ብለዋል፡፡

ደግነቱ ይሄን አስተያየት በሰጡ ማግስት ነፃ የትምህርት እድል አግኝተው ወደ አሜሪካ መብረራቸውን ሰምቻለሁ (አሜሪካ የመሸጉ ፖለቲከኞቻችን ስንት ደረሱ ይሆን?) እኔ የምለው ግን--- ኢህአዴግ መቼ ይሆን ዲፕሎማት የሚዋጣለት? (ከዚህ በኋላማ ተስፋ የለውም-- አረጀ እኮ!) አሁን እንግዲህ ለየት ወዳለው የዛሬ አጀንዳችን ብወስዳችሁ ሳይሻል አይቀርም፡፡ ሰሞኑን እጄ ገብቶ ያነበብኩት መፅሃፍ በአንድ አሜሪካዊ ደራሲ የተፃፈ ነው፡፡ እሱ ግን እኔ አልፃፍኩትም ባይ ነው፡፡ (ከደሙ ንፁህ ነኝ ለማለት ይመስላል) እንዴት ሲባል----እግዚአብሄር የነገረኝን በወረቀት ላይ ከማስፈር ውጭ ሌላ ሚና የለኝም ይላል፡፡ ኒል ዶናልድ ዋልሽ የተባለው አሜሪካዊ ደራሲ ከእግዚአብሔር ጋር ያደረግሁት ንግግር ነው ያለው መፅሃፍ ባለ ሦስት ጥራዞች ሲሆን ርዕሱም Conversation with God ይላል፡፡ (ከእግዚአብሔር ጋር የተደረገ ወግ ወይም ጨዋታ ልትሉት ትችላላችሁ) ምልልሳቸውን ስታነቡት ግን ምኑም ጨዋታ አይመስልም፡፡ የጦፈ Hard talk ነው፡፡ በነገራችሁ ላይ ደራሲው ከእግዚአብሄር ጋር ንግግር የጀመረው ድንገት ነው - ሳያውቀው፡፡ በፈረንጆቹ 1993 የፋሲካ በዓል አካባቢ በህይወቴ አስደናቂ ክስተት ተከሰተ ይላል - ደራሲው፡፡ በወቅቱ በግል ህይወቱ፣ በሙያውና በሥነልቦናው ደስተኛ አልነበረም፡፡ ህይወቴ ሁሉ የከሸፈ ይመስለኝ ነበር (እንደኢትዮጵያ ታሪክ ይሆን?) የሚለው ደራሲው፣ የተሰማውን ስሜት በደብዳቤ ላይ እያሰፈረ የማስቀመጥ የዓመታት ልማድ እንደነበረው ገልጿል አንድ ቀን ግን (ሳይመረው አልቀረም ) የተለየ ደብዳቤ መፃፍ ጀመረ - በቀጥታ ለእግዚአብሄር፡፡ ደብዳቤው የቁጣ፣ የምሬት፣ የንዴት፣ የመወነባበድና የወቀሳ ነበር፡፡ ልክ የሚፅፈውን ሁሉ ፅፎ ሲጨርስ ነው ከእግዚአብሄር ጋር ግንኙነት የጀመረው - በመፅሃፉ መግቢያ ላይ እንደገለፀው፡፡ መጀመርያ ላይ መደነጋገጥና መደነጋገር እንደተፈጠረበት ደራሲው ባይካድም፣ በኋላ ግን እንደጓደኞች ያወሩ እንደነበር ይናገራል - ለአንድ ቀን ሳይሆን ለሶስት ዓመት፡፡ እውነት ለመናገር ወጋቸው ፈፅሞ እኮ የፈጣሪና የሰው አይመስልም፡፡

ሰውና ሰው የሚተጋተግ እንጂ ፡፡ የእግዚአብሔርም ምላሽ የማይታመን ነው፡፡ ተጠራጥሬው ነበር ይለናል - ደራሲው፡፡ ወዲያው ግን ራሱ እግዚአብሄር መሆኑን ተረድቼ ሶስት ዓመት አብረን ዘለቅን፡፡ እኔ እጠይቃለሁ፣ እሱ ይመልስልኛል፡፡ የውይይታቸውም ውጤት Conversation with God የሚለውን መፅሃፍ ወለደ፡፡ መፅሃፉ ታትሞ ለገበያ ሲቀርብም ተወዳጅ በመሆን እንደተቸበቸበ ይናገራል - ኒል ዶናልድ ዋልሽ፡፡ የኒውዮርክ ታይምስ Bestseller ነበር፡፡ በነገራችሁ ላይ እግዚአብሔር ከአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ጆርጅ ቡሽን፣ ቢል ክሊንተንና ጂሚ ካርተንን እንደሚያደንቃቸው ለደራሲው ነግሮታል - Conversation with God በተሰኘው መፅሃፍ፡፡ ያለምክንያት ግን አይደለም፡፡ ለአገራቸውና ለዓለም ባከናወኑት ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ሥራዎቻቸው እንደሆነ አስረድቶታል፡፡ እግዚአብሔር ሌላው የሚያደንቀው መሪ ማን መሰላችሁ? የሶቭየቱ ሚኻኤል ጐርባቾቭ! ለምን? ቀዝቃዛውን ጦርነት ማስቆም የቻሉና ብቸኛው ኮሙኒስት የሰላም የኖቤል ተሸላሚ ሲል አድንቋቸዋል - እግዚአብሔር በመፅሃፉ ላይ፡፡ ለነገሩ ትክክለኛው የዓለም ስርዓት ኮሙኒዝም ነው ብሏል ለደራሲው ሲያወጋው - ነገር ግን አተገባበር ላይ ችግር አለ ባይ ነው (የሰው ልጅና ኮሙኒዝም አልተግባቡም እንደማለት) የእግዚአብሄርን ኮሙኒስትነት አስረግጦ መናገር ባይቻል እንኳን ካፒታሊስት እንዳልሆነ በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል፡፡ እንዴት ቢሉ---- በውይይታቸው ላይ የዓለም ሃብት እኩል መከፋፈል አለበት የሚል ሃሳብ ይሰነዝራል - እግዚአብሄር፡፡ እንዳልኳችሁ በመፅሃፉ ውስጥ ደራሲውና እግዚአብሔር ያላነሱትና ያልተከራከሩበት ጉዳይ የለም፡፡ ስለ ትዳር፣ ፍቅር፣ ወላጅነት፣ ታክስ፣ ስለሰይጣንና ሲኦል (ሰይጣንና ሲኦል የሰው ልጅ ፈጠራዎች ናቸው ብሏል) ከሞት በኋላ ስላለው ህይወት፣ ወዘተ በዝርዝር ተወያይተዋል፡፡

የአሁኑ ዘመን ትውልድ ራሱ ከልጅነት ሳይወጣ ልጅ አሳዳጊ መሆኑን ይወቅስና፣ የሰው ልጅ 40 ዓመት ሳይሞላው በፊት ወላጅ መሆን አይገባውም በማለት ልጆችን ማሳደግ የሚገባቸው አያቶች እንደሆኑ ይጠቁማል፡፡ ዓለም ጦርነት የሌለባት ሰላማዊ ፕላኔት ትሆን ዘንድ ምን ይደረግ ለሚለውም ሰፊ መልስ ይሰጣል - እግዚአብሄር፡፡ እስቲ የደራሲውና የእግዚአብሄር ውይይት ምን እንደሚመስል ለማየት ትችሉ ዘንድ አለፍ አለፍ እያልኩ ላስነብባችሁ፡፡ ደራሲ -እባክህ --- አገራት ከአገራት ጋር ሰላም የሚያወርዱበትንና ጦርነት ከነአካቴው የሚገታበትን መንገድ ንገረኝ --- እግዚአብሔር - በአገራት መካከል ሁልጊዜም አለመስማማት መኖሩ አይቀርም፡፡ አለመስማማት ችግር የለውም፡፡ እያንዳንዱ አገር ልዩ መሆኑን የሚያሳይ ጤናማ ምልክት ነው፡፡ አለመስማማትን በኃይል መፍታት ግን ከፍተኛ ያለመብሰል ምልክት ነው፡፡ በዓለም ላይ የሃይል መፍትሄ የማይወገድበት ምክንያት የለም፣ አገራቱ ለማስወገድ ፈቃደኛ እስከሆኑ ድረስ ነው ታዲያ፡፡ አንዳንዶች በገፍ የሚሞቱት ሰዎችና የሚጠፋው ህይወት ይሄንን ፈቃደኝነት ለማምጣት በቂ ነው ብለው ሊያስቡ ይችላሉ፡፡ ኋላ ቀር ባህል ለሰፈነበት እንዳንተ ያለው አገር ግን ነገሩ እነሱ እንደሚያስቡት አይደለም፡፡ ሙግት ማሸነፍ እችላለሁ ብለህ እስካሰብክ ድረስ መሟገትህ አይቀርም፡፡ በጦርነት ማሸነፍ እችላለሁ ብለህ እስካሰብክ ድረስም ትዋጋለህ፡፡ ደራሲ - ለዚህ ታዲያ መፍትሄው ምንድነው? እግዚአብሔር - መፍትሄ የለኝም፡፡ ምልከታ እንጂ! --- የአጭር ጊዜ መፍትሄ የሚሆነው አንድ የዓለም መንግስት መመስረት ነው - አለመግባባቶችን የሚፈታ የዓለም ፍርድ ቤት ያለው! (አሁን እንዳለው ዓለማቀፍ ፍ/ቤት ውሳኔው ችላ የማይባል መሆን ግን አለበት) የትኛውም አገር የቱንም ያህል ጉልበት ቢኖረውና ተፅዕኖ ማሳረፍ ቢችልም ሌላው አገር ላይ ጥቃት እንዳይሰነዝር ዋስትና የሚሆን አንድ የዓለም ሰላም አስከባሪ ኃይል ሊመሰረት ይችላል፡፡

… በዚህ መንገድ ብቻ ነው በዓለም ላይ ሰላም ሊሰፍን የሚችለው፡፡ ያኔ --- የትናንሽ አገራት ዕጣ ፈንታ በትላልቅ አገራት መልካም ፈቃድ ላይ የተመረኮዘ መሆኑ ይቀራል፡፡ በራሳቸው ሃብት ላይ መደራደራቸው ያቆማል፡፡ ቁልፍ መሬታቸውን ለውጭ ወታደራዊ ሃይል (ቤዝ) አሳልፈው አይሰጡም፡፡ … አንድ አገር ብትወረር 160ዎቹም የዓለም አገራት በተቃውሞ ይነሳሉ፡፡ --- ትላልቅ አገራት የዓለምን የሃብት ክምችት ለብቻቸው መቆጣጠርና ማከማቸታቸውም ይቀራል፡፡ ይልቁንም ሃብቱን ለሌሎች አገራት እኩል እንዲያካፍሉ---ይገደዳሉ፡፡ የመላው ዓለም መንግስትም የጨዋታውን ሜዳ ለሁሉም እኩል ያደላድላል፡፡ (ደራሲውና እግዚአብሄር ስለዘመኑ የትምህርት ሥርዓትም የጦፈ ክርክር አድርገዋል፡፡ ቀንጨብ አድርጌ ላስነብባችሁ! ) ደራሲ - ስለትምህርት ልትነግርኝ ትፈቅዳለህ? እግዚአብሔር -- እንዴታ! አብዛኞቻችሁ የትምህርትን ትርጉም፣ ዓላማና ጥቅም በትክክል አልተረዳችሁትም፡፡ የትምህርት አሰጣጥ ሂደትንማ ባናነሳው ይሻላል፡፡ ---- አብዛኛው የሰው ዘር የትምህርት ትርጉምና ዓላማ እንዲሁም ጥቅም ዕውቀት ማስተላለፍ ነው ብሎ ደምድሟል፡፡ አንድን ሰው ማስተማር ማለት - የአንድን ቤተሰብ፣ ጐሳ፣ ህብረተሰብ፣ አገር፣ ዓለም የተከማቸ ዕውቀት መስጠት ሆኗል! ሆኖም ትምህርት ከዕውቀት ጋር እምብዛም የሚያገናኘው ነገር የለም፡፡ ደራሲ -ትምህርት ከዕውቀት ጋር ካልተገናኘ ከምን ጋር ነው የሚገናኘው ታዲያ? እግዚአብሔር - ከጥበብ፣ ከብልሃት ደራሲ-ልዩነታቸው ምንድነው? እግዚአብሔር- ጥበብ ወደ ኑሮ የተቀየረ እለት በእለት የተቀየረ ዕውቀት ነው፡፡ -- ለልጆቻችሁ ዕውቀት ስትሰጧቸው ምን ማሰብ እንዳለባቸው እየነገራችኋቸው ነው፡፡ ማወቅ ያለባቸውን ነው የምትነግሯቸው፤ እውነትን ነው እንዲረዱ የምትፈልጉት፡፡ ጥበብ ስትሰጧቸው ግን ማወቅ ያለባቸውን ወይም እውነቱን አይደለም የምትነግሯቸው፡፡ ይልቁንም የራሳቸውን እውነት እንዴት እንደሚያገኙ ታስተምሯቸዋላችሁ፡፡ ደራሲ -ግን እኮ ያለ ዕውቀት ጥበብ ሊኖር አይችልም፡፡ እግዚአብሔር - እስማማለሁ፡፡

ለዚህ እኮ ነው ጥበብ ሰጥታችሁ ዕውቀትን መዘንጋት የለባችሁም ያልኩት፡፡ የተወሰነ መጠን ዕውቀት ከአንደኛው ትውልድ ወደ ቀጣዩ መተላለፍ አለበት፡፡ በተቻለ መጠን ግን ትንሽ ቢሆን ይመረጣል፡፡ የቀረውን ህፃኑ ፈልጐ ያግኘው፡፡ ዕውቀት ይረሳል፤ ጥበብ ግን ፈፅሞ የሚረሳ አይደለም፡፡ ደራሲ - ስለዚህ ት/ቤቶቻችን ትንሽ ትንሽ ማስተማር ነው ያለባቸው ማለት ነው? እግዚአብሔር - ት/ቤቶቻችሁ አትኩሮታቸውን መለወጥ አለባቸው፡፡ አሁን በእጅጉ ያተኮሩት ዕውቀት ላይ ነው፡፡ ለጥበብ ትንሽ የተቆጠበች ትኩረት በመስጠት፡፡ በትንታኔያዊ አስተሳሰብ፣ በችግር መፍታትና በሎጂክ ዙርያ የሚሰጡ ትምህርቶች ለብዙ ወላጆች አስፈሪ ናቸው፡፡ እንዲህ ዓይነቶቹ ትምህርቶች ከካሪኩለሙ እንዲወጡ ይሻሉ፡፡ እንዲህ የሚያደርጉት የራሳቸውን የአኗኗር ዘይቤ ጠብቀው ለማቆየት ነው፡፡ እንዴት ቢሉ … የራሳቸውን ሳይንሳዊ የአስተሳሰብ ስልት እንዲያዳብሩ የተፈቀደላቸው ህፃናት የወላጆቻቸውን ሥነ ምግባርና አጠቃላይ የኑሮ ዘይቤ መከተል አይፈልጉም፡፡ የአኗኗር ዘይቤያችሁን ጠብቃችሁ ለማቆየት ስትሉ የትምህርት ስርዓታችሁ የህፃናትን ችሎታ ሳይሆን ትውስታቸውን ብቻ እንዲያዳብር አድርጋችሁ ነው የቀረፃችሁት፡፡ እንግዲህ የቀረውን መፅሃፉን ፈልጋችሁ አንብቡት፡፡ እኔ ግን አንድ ነገር በጣም ተመኘሁ--- እንደዚህ አሜሪካዊ ደራሲ ከእግዚአብሄር ጋር የመወያየት እድል ባገኝ አልኩ ለራሴ፡፡ ስለአገሬ ፖለቲከኞች ብዙ ብዙ የምጠይቀው ነገር ስላለኝ እኮ ነው፡፡ የዘመናት የፖለቲካ እንቆቅልሻችን እንዴት እንደሚፈታ ብልሃቱን ይሰጠኝ ዘንድም መወትወቴ አይቀርም ነበር፡፡ የእኛ የፖለቲካ ችግር ሰው ሰራሽ ቢሆንም መፍትሄው በሰው አቅምና ችሎታ የማይገኝ መሆኑን አይተነዋላ!

ሺጉሜን የተባለው የጃፓን ንጉሥ ቻ-ኖ-ዩ የተባለው የሻይ ስነስርዓት በጣም ደስ ይለው ነበር፡፡ በችሎቱ ላይ ዳኛ ሆኖ ሲቀመጥ እንኳ ሻዩን እያደቀቀ ይፈጭ ነበር ይባላል፡፡ ምክንያቱ የሚከተለው ነው፡- 

ከዕለታት አንድ ቀን የሻይ ነጋዴ የነበረ ወዳጁን
“ህዝቡ ስለ እኔ ምን ያስባል?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ነጋዴውም፤
“ማስረጃቸውን በግልፅ የማያቀርቡ ሰዎችን ትቆጣለህ፡፡ ሙልጭ አድርገህም ትሳደባለህ የሚል አስተያየት ነው ያለው፡፡ በዚህ ምክንያትም ህዝቡ እውነተኛውን ህጋዊ ማንነቱንና ጉዳዩን ወደ አንተ ለማቅረብ ስለሚፈራ እውነቱ በግልፅ አይታወቅም” ሲል ይነግረዋል፡፡
ንጉሡም፤
“አመሰግናለሁ! እንኳን ነገርከኝ፡፡ እኔ እስከዛሬ፤ ለሰዎች እቅጩን የመናገር ልማድ ነበረኝ፡፡ ስለዚህም ትሁቶቹና በድፍረት በአደባባይ የመናገር ድፈረት የሌላቸው ጨዋ ሰዎች እውነቱን ፍርጥ አድርገው አይገልፁም፡፡ ወደፊት ጠባዬን ማረም ይኖርብኛል” ይላል፡፡
ከዚህ በኋላ ንጉሡ ዙፋን ችሎት በሚቀመጥበት ጊዜ ሁሉ፤ አንድ የሚያስገርም ነገር ማድረግ ጀመረ ይባላል፡፡ በጨርቅ ተሸፍኖ የሻይ መውቀጫው/መፍጫው ከስሩ እንዲቀመጥለት ያዛል፡፡ በሀር ጨርቅ ተሸፍኖ ጥዋ መስሎ ይቀመጥለታል፡፡ ከዚያም አቤቱታ አቅራቢው ህዝብ አቤቱታውን ሲያሰማ እሱ ሻዩን እየወቀጠ ትኩረቱን ወደ ሙቀጫው በማድረግ ቁጣውን ይቆጣጠራል፡፡
ቀጥሎም የፈጨውን ሻይ በትክክል መድቀቅ አለመድቀቁን በእጁ እየነካ ያየዋል፡፡ ያረጋግጣል፡፡ ሻዩ በትክክል ከተፈጨ መንፈሱ የረጋና ሚዛናዊ መሆኑን ያስባል፡፡ በትክክልም አቤቱታ ማዳመጡን ያምናል፡፡ ሻዩ ያላግባብ የተወቀጠ ከሆነ ግን የተረበሸና ቁጠኛ ስሜት እንደነበረው ያውቃል፡፡
በረጋ መንፈስ የተፈጨው ሻይ፤ ፍርድ በትክክል መስጠቱንና አቤት ባዮቹም ረክተው መሄዳቸውን ይነግረዋል፡፡ ይሄኔ፤
“ተመስገን! ህዝቤ ሳያዝንብኝ፤ ረክቶና ደስ ብሎት ሄዷል ማለት ነው” ብሎ ፈገግ ይላል፡፡
* * *
ለህዝብ የሚቆረቆር ዕውነተኛ መሪ የህዝብን ብሶት ማዳመጥ፤ አቤቱታውን መስማት ያረካዋል። ህዝብ የልቡን ዕውነት የሚደብቅ ከሆነ ትክክለኛ አስተዳደር አለ ለማለት ያዳግታል፡፡ ዐይና - ውጣው በአደባባይ እንደልቡ ሲናገር፤ ጭምቱና ፈሪው ሃሳቡን ሳይገልጽ ይቀራልና ሥርዓቱ ሁሉንም ያስተናግዳል ለማለት አያስደፍርም፡፡ ሃሳቡን የሚገልጽ ህዝብ የዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ምሰሶ ነው። በዚህ ረገድ በጥሞና የህዝብን የልብ ትርታ ለማዳመጥ የሚችል ጆሮ ያለው መሪ ያስፈልጋል፡፡ የመሥሪያ ቤት አለቃ፣ የማህበር መሪም ሆነ የፖለቲካ መሪ አስተዋይ አዕምሮ፣ ሆደ - ሰፊ አመራርና “ወደፊት ይህን ይህን ጠባዬን ማረም ይኖርብኛል” የማለት ድፍረት ሊኖረው ያሻል፡፡ ያን ካገኘን ታድለናል፡፡
የአንድ ሀገር ህዝብ እንደዜጋ የተፃፈን ጽሑፍ በነፃነት፣ በጥሞናና በጥንቃቄ አንብቦ የሚመረምር፤ ያሻውን ዓይነት የፖለቲካ ሥርዓት የሚከተል፣ በነፃነት አገዛዙን የሚቃወም፣ የሚተችና ሲያስፈልግ አይሻኝም የማለት መብቱን የሚያውቅ ሊሆን ይገባል፡፡ እንደአራሽ እንደላብ - አደርም የአቅሙን ያህል ማምረትና የኢኮኖሚ ህልውናውን ሊያጠናክር ይጠበቅበታል፡፡ እንደዜጋም ሆነ እንደሠራተኛ በአገሩ ይኖር ዘንድ የሚያሠራው፣ የሚያሳትፈው ሥርዓትና ህግ ሊያገኝም የግድ ነው፡፡
“ባገር እኖር ብዬ
ልጅ አሳድግ ብዬ
ከብት እነዳ ብዬ፤
ለባሻ ዳርኩለት ሚስቴን እቴ ብዬ”
እያለ የሚያለቅስ ባላገር በምንም ዓይነት ማየት የለብንም፡፡ ጊዜውም ቦታውም አይፈቅድምም። በፖለቲካ የተገፋ፣ በኢኮኖሚ የደቀቀ፣ ማህበራዊ ድርና ማጉ ውሉ የጠፋ ህብረተሰብ እንዳይኖር ነው የስትራቴጂያችን ዒላማ! ውሃ ጋ ከሆን አሣ፣ ግጦሽጋ ከሆን ሥጋ መብላትን ልናውቅበት ወቅቱ ያስገድደናል፡፡
አንድ የገዛ በሬው ሊወጋው የሚያሳድደው ባለበሬ ለአንድ የሰፈር አዛውንት፤ “እረ ይሄ በሬ እያሳደደ አስቸገረኝ“ ቢላቸው፤ “የት ነው የምትተኛው?” ብለው ጠየቁት አሉ፡፡ ባለበሬውም፤ “ቤቴ። ሣር ፍራሼ ላይ!” ይላቸዋል፡፡ ሽማግሌውም፤
“ታዲያ ቀለቡ ላይ እየተኛህ ዱሮስ ላያባርርህ ኖሯል እንዴ?” አሉት ይባላል፡፡ ሰውንም ቀለቡ ላይ ተኝተን ነፃነት አለህ ብንለው የለበጣ ነው የሚሆነው፡፡ ነፃነቱን ከኢኮኖሚ ጥቅሙ የሚያስተሳስር ሥርዓት መፍጠር ተገቢ ነው፡፡ ለተገቢ ሥርዓት ክሳቴ የሚታገሉ ሁሉ ጊዜን መሠረት ያደረገ ስትራቴጂ ይኖራቸው ዘንድ ወቅቱ ይጠይቃቸዋል፡፡
“ፊት የበቀለን ወፍ ይበላዋል” የሚለውን ተረት ሳንረሳ “የዘገየ ፍርድ ካልተፈረደ አንድ ነው”ን እያውጠነጠንን፤ ትክክለኛው ጊዜ ሲደርስ ግን “የሚሥማሩን አናት መምታት”ና አጋጣሚን በአግባቡ መጠቀም ወሳኝ መሆኑን ልናሰምርበት ይገባል፡፡ በወቅቱ ያልዘራም በወቅቱ ያልሰበሰበም ሁለቱም ከመራብና ከማስራብ አይድኑም - “ንገሥ ቢሉት ዛሬ ሰምበት ነው አለ” የሚለው የጉራጊኛ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው!!

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በድጋሚ ተቀጠረ

በዓዲ ኀትመትና ማስታወቂያ ሓላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ስም እየታተመ የሚወጣው “አዲስ ታይምስ” መጽሔት፤ ከብሮድካስት ባለሥልጣን የሞያ ብቃት ማረጋገጫ ምስክር ወረቀት እድሳት በመከልከሉ ከኅትመት ውጪ ሆነ፡፡ አሳታሚው ለዝግጅት ክፍላችን እንደገለጸው፤ የአገሪቱ የፕሬስ ሕግ በሚያዘው መሠረት የመጽሔቱን ዓመታዊ ፈቃድ ለማሳደስ ከድርጅቱ የሚጠበቁትን መስፈርቶች ሙሉ በሙሉ ቢያሟላም የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን ጥር 2 ቀን 2005 በላከው ደብዳቤ ለመጽሔቱ የሞያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት እድሳት እንደማያደርግ አስታውቋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን እድሳቱን እንደማያደርግ ለአሣታሚው በላከው ደብዳቤ ያመለከተው ሦስት ዋና ዋና ምክንያቶችን በመጥቀስ ነው። እነዚህም የአክስዮን ባለቤቶችና የአድራሻ ለውጥ ሲደረግ በ15 ቀን ውስጥ ለባለሥልጣኑ ማሳወቅ አለመቻል፣ ለኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት መወዘክር የዐሥራ አምስት ቀን እትም አለማስገባት እንዲሁም መፅሔቱ “በሕጋዊ ባለቤቶቹ ሳይሆን ምንጩ በማይታወቅ ገንዘብ ነው የሚተዳደረው የሚሉት ናቸው፡፡ የ“አዲስ ታይምስ” መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ተመስገን በበኩላቸው፤ የአክስዮን ባለቤትነት እና የአድራሻ ለውጥ ሲያደርጉ በጊዜው በደብዳቤ ማሳወቃቸውን፣ በየዐሥራ አምስት ቀኑ ለኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ሁለት ሁለት ኮፒ ያስገቡበትን ደረሰኝ ለባለሥልጣኑ ማቅረባቸውን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ማንነቱ በማይታወቅ የገንዘብ ምንጭ ነው የሚንቀሳቀሰው›› የሚለውን የባለሥልጣኑን ምክንያት ደግሞ “በጥንቆላ ላይ የተመሠረተ መረጃ ነው” ሲሉ አጣጥለውታል፡፡ “ጉዳዩን ይዘን ወደ ፍርድ ቤት እናመራለን” ያሉት አቶ ተመስገን፤ የመጽሔቱ መታገድ ‹‹የአቶ ኀይለማርያም መንግሥት የመለስን ራዕይ እናስቀጥላለን ሲል የነበረውን በተግባር እያረጋገጠ መሆኑን ያመለክታል” ብለዋል፡፡ የአራት ወራት ዕድሜ ያስቆጠረው “አዲስ ታይምስ” መጽሔት ከ35 ሺሕ ኮፒ በላይ እየታተመ በየሁለት ሳምንቱ ይሠራጭ እንደነበር፣ ይህም በአገሪቱ ካሉ መጽሔቶች በኅትመት፣ ብዛትና በተደራሽነት ቀዳሚ እንደሚያደርገው አቶ ተመስገን ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡

በኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን የሕዝብ ግንኙነት ተጠባባቂ ሓላፊ የሆኑት አቶ ወርቅነህ ጣፋ በበኩላቸው፤ ባለሥልጣኑ የእድሳት ክልከላውን ከማድረጉ በፊት ከባለአክሲዮኖቹ ጋር የአድራሻ ቅየራ እና የአክሲዮን ድርሻ ለውጥ ሲደረግ አለማወቃቸው እንዲሁም በቤተ መጻሕፍት ወመዘክር የመጽሔቱ ቅጂዎች እየደረሱ እንዳልሆኑ ተወያይተንባቸው ችግሩ እንዳለ አምነው ተቀብለው ነበር ብለዋል፡፡ የመጽሔቱ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ተመስገን ደሳለኝ፤ የአክስዮኑ 93 በመቶ ድርሻ ባለቤት አገር ውስጥ እንዳልሆኑና ሰባት በመቶ ድርሻ ያላቸው ግለሰብ ብቻ አገር ውስጥ መኖራቸውን በመግለፅ አገር ውስጥ ያሉትን ብቻ አነጋግሮ እዚህ ድምዳሜ ላይ መድረስ እንደማይቻል ተናግረዋል፡፡ አቶ ወርቅነህ የፋይናንስ ምንጩን በተመለከተ ሲናገሩ፤ ‹‹አሁን በግልፅ ይፋ ባናደርግም መረጃው አለን” ብለዋል፡፡ ይህ በዚህ እንዳለ የሕዝብን ሐሳብ ማናወጥ፣ ሕዝቡን በሕገ - መንግሥቱ ላይ ማነሣሣትና የመንግሥትን ስም ማጥፋት የሚሉ ሦስት ክሦች የተመሰረተባቸውና ነሐሴ 17 ቀን 2004 ዓ.ም በቃሊቲ ማረሚያ ቤት ለስድስት ቀናት ከታሰረ በኋላ ክሱ ተቋርጦ በነጻ የተለቀቁት የቀድሞው የፍትሕ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ አቶ ተመስገን ደሳለኝ፤ ከሦስት ወር በኋላ ክሱ በዐቃቤ ሕግ ተንቀሳቅሶ በ50ሺሕ ብር ዋስ መለቀቃቸው ይታወሳል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት 16ኛ ወንጀል ችሎት ትእዛዝ ታኅሣሥ 27 ቀን 2005 ዓ.ም ቀርበው ተለዋጭ ቀጠሮ የተሰጣቸው የድርጅቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ማስተዋል ብርሃኑ እና የጋዜጣው ዋና አዘጋጅ አቶ ተመስገን ደሳለኝ ትላንት ጥር 23 ቀን 2005 ዓ.ም ቢቀርቡም “መዝገቡን አልመረመርነውም” በሚል ብይኑ ሳይሰማ የቀረ ሲሆን ችሎቱ ለየካቲት 1 ቀን 2005 ዓ.ም እንዲቀርቡ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

የዘፍጥረት ሁለት ትረካዎች ተመሳሳይ አይደሉም? በየዘመኑና በየሃይማኖቱ የሚነገሩ የውኃ ጥፋት ትረካዎችስ?

ወደ ዙፋን የሚወጣ ንጉስ፤ ነባር ስሙ ይቀየራል። ዘውድ የሚደፋው በቀድሞ ስሙ አይደለም- አዲስ ስም ይወጣለታል - ተፈሪ መኮንን፣ አፄ ኃይለሥላሴ እንደተባሉት። ወይም ካሮል ዎይትላ፣ የሮም ካቶሊቅ ጳጳስ የሆኑትም ጆን ፖል በሚል ስያሜ ነው። የአሁኑ ጳጳስ ቤኔዲክት ደግሞ፤ ጆሴፍ ራትዚንገር ነበር ስማቸው። ንግስናም ሆነ ጵጵስና እንደገና እንደመወለድ፤ አልያም የቀድሞው ማንነት ሞቶ በአዲስ መልክ እንደመነሳት ስለሚቆጠር፣ አዲስ ስም ይጎናፀፋሉ። ወደ አዲስ ሃይማኖት የሚገባ ሰው ላይም ተመሳሳይ የስም ለውጥ ይከሰታል። ለምሳሌ የሚጠመቅ ሰው፤ በፈጣሪው ዘንድ ለሁለተኛ ጊዜ እንደተወለደ ወይም ሞቶ እንደተነሳ ይታመን የለ? እናም ሰዎች ሲጠመቁ አዲስ ስም ይወጣላቸዋል። ከ4000 አመት በላይ እድሜ ያስቆጠረው የግብፃዊያኑ ሃይማኖትም እንዲሁ በዳግም ልደትና በጥምቀት፣ በሞትና በትንሳኤ ዙሪያ ያጠነጠነ ነበር - የስም ለውጥ ጭምር። ልደትና ጥምቀት፣ ንግስናና የ30 አመት ህዳሴ፣ ሞትና ትንሳኤ ጥንታዊዎቹ ግብፃዊያን፣ “የሰማያት አምላክ፣ የምድር ንጉስ” እያሉ የሚያመልኩት ሆረስ፣ በአካል ግብፅን እንደገዛ ይነገርለታል። ከሞተ በኋላም ከዙፋን አልወረደም ማለት ይቻላል። ከሱ በኋላ የነገሱ ሁሉ፣ የሆረስ አምሳል እንደሆኑ ይታመንባቸዋልና - የሆረስ ዙፋን ላይ የተቀመጡ አዲስ ሆረስ እንደማለት ነው። ግብፅን የሚገዛ ፈርኦን፣ በምድር ላይ በስጋ የተገለፀ ሆረስ ነው ይባልለታል (በአካል የመጣ አምላክ)። ታዲያ ፈርኦኑ፤ ንጉስ ብቻ ሳይሆን፤ የሃይማኖት መሪም ጭምር መሆኑ ምኑ ይገርማል? የቤተመቅደስ ራስ ነው - High Priest ይሉታል (በብሪቲሽ ሙዚየም የተዘጋጀው Dictionary of Anciet Egypt ገፅ 228)። እንደ እንደ ሊቀ ጳጳስ ነው ማለት ይቻላል። ፈርኦኑ ወይም እንደራሴው በ12 አጃቢና ረዳት ቀሳውስት ጋር የአገሬውን የአይማኖት እምነት ይመራል። እንግዲህ ከአምላክ የተወለደው ሆረስ በግብፅ ምድር በአካል ንጉስ ነበረ ተብሎ ይታመንበት የለ? የሃይማኖትም መሪ ነበር - ንጉስም ሊቀጳጳስም እንደማለት። 12 አጃቢ ቀሳውስት ይኖሩታል። (የአማልክት ጌታ አሞን ወይም ራዕ በአስራ ሁለት አጃቢ አማልክት ተከብቦ እንደሚታየው ማለት ነው።) ከ3500 አመት በፊት በሕንፃዎች ላይ የተቀረፁ ፅሁፎች ናቸው ይህንን የሚመሰክሩት። ANCIENT RECORDS OF EGYPT በሚል ርዕስ University of CH ICAGO ያዘጋጀው መፅሐፍ ውስጥ ተተርጉመው ከቀረቡት ጥንታዊ የግብፅ ሃይማኖታዊ ትረካዎች መካከል ቀንጭቤ ላካፍላችሁ። ፅሁፉ የንግሥና በአልን ይተርካል። በእርግጥ ንግስናው ያልተለመደ ነው። ሴት ነች የምትነግሰው። እንዴት ተደርጎ? እንዴት ነው አንዲት ሴት እንደ ወንድ ሆረስን ሆና በሆረስ መንበር የምትቀመጠው? ከፅሁፎቹ የምናገኘው መልስ ቀላል ነው። ከአምላክ ተወልዳ፣ እንደ ወንድ ሆና ነው የምትነግሰው። ንግስት ተብላ ሳይሆን ንጉስ ተብላ! ለዚያውም እንደ ሌሎቹ ፈርኦኖች የውሸት ፂም መሰል ነገር አገጯ ላይ አንጠልጥላ። ለማንኛውም ፅሁፉ እንዲህ ይላል። Amon-Re enthroned at the right, before twelve gods in two rows at the left. (የሰማያት ዙፋን ላይ ከተቀመጠው የአማልክት ጌታ አሞን-ራዕ ጎን 12ቱን አማልክት የሚያሳይ ስዕል ከፅሁፉ አጠገብ አለ)። ግብፅን ለመግዛት የታጨችው ሴት የፈርኦን ልጅ ብትሆንም፤ አሞንራዕ “የኔ ልጅ ናት” ይላል። ፈርኦኖች ሁሉ አምላክን የሚወክሉ ናቸዋ። የሆነ ሆኖ አሞንራዕ እንዲህ ይላል፤ “ሁሉንም ግዛቶች፣ ሁሉንም አገራት እሰጣታለሁ። መንፈሴ ከውስጧ አለ፣ በረከቴ እሷ ላይ ነው,... ዘውዴ ከሷ ጋር ነው።

ሰሜኑንና ደቡቡን ትገዛለች፣ ሕያዋንን ሁሉ ትመራለች...” አሁን የምትታወቅበት hatshepsut የተሰኘው ስም የሚወጣላትም በዚሁ ጊዜ ነው። ንግስና ማለት እንደገና እንደመወለድ ይቆጠር የለ? እናም፣ ፈጣሪ አምላክ ሃትሸብሱትን በያኔዋ የፈርኦን ሚስት በእናቷ ማህፀን ውስጥ በማስገባት እንድትወለድ ካደረገ በኋላ፤ “ስሟም፤ ክህነመት አሞን ሃትሸብሱት ይሆናል። ግዛቱን ሁሉ በላቀ ጥበብ የምትፈፅም ንግስት ትሆናለች” አለ። አሞንራዕ ደስ ብሎት፣ ለራሷ ለሃትሸብሱት እንዲህ ይላታል - “Glorious part which has come forth from me; king, taking the Two Lands, upon the Horus-throne forever.” “ከኔ የተፈለቅሽ ቅዱስ አካል። ሁለቱን ምድሮች የምትወስጂና በሆረስ ዙፏን ለዘላለም የምትቀመጪ ንጉስ!” ይላታል። ንግስት ሳይሆን ንጉስ አላት - እንደ ሆረስ ነዋ መቆጠር ያለባት። ሆረስ በሌላ አካል የመጣ ያህል ነው። የሷ ንግግሮችም ይህንን የተከተሉ ናቸው። አንደኛ ራሷን ንጉስ ትላለች - ራሷን እንደሆረስ በመቁጠር። ሁለተኛ ራሷን የንጉስ ሚስት ትላለች። ንጉስም የንጉስ ሚስትም ናት። የምድር አባቷን (ቱስሞስን) ኦሲሪስ ብላ ትጠራዋለች፤ እናቷን (አሞስን) ደግሞ ኢሲስ ብላ ትጠራታለች። ኦሲሪስና ኢሲስ ግን የሆረስ ወላጆች ናቸው። በሃትሸብሱት፣ የንግስና በዓል ላይ ሁለት ነገሮች ይፈፀማሉ። እንግዲህ፤ የግብፅ ፈርኦን በ30 አመት ንግስናው እንደሞተ ይቆጠር የለ? “በ30 አመቱ ተጠመቀና እንደገና ተወለደ። በህዳሴ ከሞት ተነሳ” ተብሎ እሱ ራሱ በስልጣኑ ላይ ሊቀጥል ይችላል። አብዛኛውን ጊዜ ግን፤ በንጉሱ አምሳል ልጁ ይነግሳል - በጥምቀት እንደገና ተወለደ ተብሎ፣ ከሞት ተነሳ ተብሎ። ሃትሸብሱትም እንዲሁ በአባቷ ምትክ ዙፋን ላይ እንድትወጣ፤ የምድር አባቷ ዘውድ ሲደፋላት ይታያል - (ስዕል ላይ ስትታይ ወጣት ናት)። በሌላ በኩል ደግሞ፤ በአማልክት ፊት ትጠመቃለች፤ የአማልክት ጌታ አሞንራዕ በላይዋ ላይ ውሃ እያፈሰሰ ያነፃታል (በስዕል ላይ ስትታይ ህፃን ነች። መጠመቅና ንግስና እንደገነና ነፅቶ መወለድን ያመለክታል ብለው ስለሚያምኑ)። በጥምቀቱ ላይ፤ የአሞን ራዕ 12 አጃቢ መላእክት በአንድነት ይናገራሉ፤ “ከታችኛውና ለላይኛው ግብፅ ታላቅ የንጉስ ክብር፣ ከነፍስሽ ጋር ነፅተሻል (ነፅተሃል)” ይላሉ። “ወርቃማ ሆረስ... የላይኛውና የታችኛው ግብፅ ንጉስ” የሚል ተጨማሪ ስም ይወጣላታል። የወንድ ንጉሥ ልብስ አድርጋ ንግስናዋ ሲታወጅም በስዕል ይታያል። ንጉሥ ብቻ ሳትሆን የአምላክ ተወካይም ነችና፤ እንደ ሊቀ ጰጳስ ነች - እንደ ሆረስ (12 ቀሳውስት የሚያጅቡት ሊቀ ቀሳውስት)።

ANCIENT RECORDS OF EGYPT V.2 ከገፅ 202 - 292። እንግዲህ፤ የአምላክ ልጅነትና ንግስና፣ ውልደትና የሰላሳ አመት ጥምቀት፣ የሞትና የትንሳኤ ... በጥንታዊያኑ የግብፅ ሃይማኖት ውስጥ ምን ያህል ቦታ እንዳለው ከዚህ ትረካ ማየት ይቻላል። የሆረስ ታሪክ ከኢየሱስ፣ ከሚትራ፣ ከክሪሽና፣ ከዲኖስየስ ጋር ይመሳሰላል የሚባልበት አንዱ ምክንያትም ከእንደዚህ አይነት ትረካዎች የተነሳ ነው። በእርግጥ፤ “ምንም ተመሳሳይነት የለም” ብሎ መሸምጠጥም ይቻላል። ነገር ግን፤ የልዩነቶች መኖር ተመሳሳይነትን አያስቀርም። ለልዩነት ለልዩነትማ፤ በዘፍጥረት ምዕራፍ አንድ እና ሁለት መካከልም በርካታ ልዩነት አለ። የዘፍጥረት ሁለት ትረካዎች አንደኛው ትረካ፡ ዘፍጥረት ምዕራፍ 1 ላይ፤ መጀመሪያ ቀንና ሌሊት፣ በሁለተኛው ቀን ሰማይን፣ በሶስተኛው ቀን ምድርና ባህርን እንዲሁም እፀዋትን፣ በአራተኛው ቀን ፀሐይ፣ ጨረቃና ኮኮቦችን ፈጠረ። በአምስተኛው ቀን፤ ከውኃ የባሕር እንሰሳትንና በራሪ አእዋፋትን ፈጠረ። በስድስተኛው ቀን ከምድርም አራዊትን ፈጠረ። በመጨረሻም ሰውን በእግዚአብሔር መልክ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው። እናም ባረካቸው፤ “... የባሕርን ዓሦችና የሰማይን ወፎች በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ግዙአቸው። ...እነሆ መብል ይሆናችሁ ዘንድ በምድር ፊት ሁሉ ላይ ዘሩ በእርሱ ያለውን ሐመልማል ሁሉ፥ የዛፍን ፍሬ የሚያፈራውንና ዘር ያለውንም ዛፍ ሁሉ ሰጠኋችሁ። ለምድርም አራዊት ሁሉ፥ ለሰማይም ወፎች ሁሉ፥ ሕያው ነፍስ ላላቸው ለምድር ተንቀሳቃሾችም ሁሉ የሚበቅለው ሐመልማል ሁሉ መብል ይሁንላቸው” አለ። “እንዲሁም ሆነ። እግዚአብሔርም ያደረገውን ሁሉ አየ፥ እነሆም እጅግ መልካም ነበረ”... በሰባተኛው ቀን እረፍት ሆነ። ሁለተኛው ትረካ፡ በምዕራፍ 2 ላይ የምናገኘው ታሪክስ ምን ይመስላል? እስካሁን እግዚአብሄር እንዲህ አለ፣ እንዲህ አደረገ እያለ ሲተርክ የነበረው “ዘፍጥረት” ምዕራፍ 2 አንቀፅ 4 “እግዚአብሔር አምላክ...” የሚል አጠራር መጠቀም ይጀምራል። እናም ምድርና ሰማይ የተፈጠሩ ጊዜ፣ አንዳችው ቁጥቃጦና ቡቃያ በምድር ላይ እንዳልነበረ በመግለፅ የፍጥረት ትረካውን በአዲስ መልክ መልሶ ያቀርባል። የምድር ቡቃያ ያልነበረው ስላልዘነበ መሆኑን፤ የሚሰራበት ሰውም እንዳልነበረ ይገልፃል። በቀድሞው ትረካ ሰው (ወንድና ሴት) በእግዚአብሔር አምሳያ እንደተፈጠሩ ቢጠቀስም፤ አሁን ግን አዳምን ብቻ ከአፈር ይፈጥረዋል። “እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር አበጀው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት” ይላል። በኋላም “አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ” ይለዋል። ታዲያ ይሄ የእግዚአብሔር አምሳል ነው? የሆነ ሆኖ፤ አዳም ከተፈጠረ በኋላ በምር ላይ እፅዋት ያለበት አካባቢ (ገነት) ይፈጠርና አዳምን እዚያ ወስዶ ያስቀምጠዋል። ከሰው በፊት እፀዋትና እንሰሳት አልተፈጠሩም እንዴ? የመጀመሪያው ትረካ ላይ... አዎ። እና ደግሞ፤ የሁሉም ነገር ገዢ ሆኗል፤ ከቅጠሉም፣ ከፍሬውም፣ ከእንስሳውም ያሻውን መጠቀምና መብላት ትችላለህ የሚል ስልጣን ተሰጥቶታል። ገዢ ሆኗል። ትዕዛዝ አልተጫነበትም። በሁለተኛው ትረካ ግን በቅድሚያ ሰው ተፈጠረና፣ ከዚያ እፀዋት መጣ። እናም ትዕዛዝ ተከተለ። “እግዚአብሔር አምላክም ሰውን እንዲህ ብሎ አዘዘው። ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና”። ከዚያ፤ “እግዚአብሔር አምላክም የምድር አራዊትንና የሰማይ ወፎችን ሁሉ ከመሬት አደረገ” ይላል። በምዕራፍ 1 ላይ፤ እፀዋት ብቻ ሳይሆኑ፤ አራዊትን ከምድር፤ አእዋፍና የባሕር እንስሳትም ከውኃ የተፈጠሩት ከሰው በፊት ነው። በምዕራፍ 2 ትረካ ላይ ግን፤ ሰው በቅድሚያ መፈጠሩን እናነባለን። አእዋፋትም ከውኃ ሳይሆን ከመሬት መፈጠራቸውን ይነግረናል። ሁለተኛው ትረካ ላይ ያለ ሴት የተፈጠረው አዳም፣ ረዳት ያሻዋል ተባለና በተኛበት አንድ የጎድን አጥንቱ ተወስዶ ሴት ተሰራች። (ተፈጠረች፤ ተወለደች)። ከአጥንቴና ከስጋዬ የተገኘች ይላታት። ከዚያ ሚስቱ ትሆናለች። ... ገና ሚስቱ አልሆነችም። እንዲያውም፤ ወንድና ሴት መሆናቸው ግድ አልሰጣቸውም። አላወቁም። አይናቸው አልተከፈተም ነበር። ተንኮለኛው እባብ ነው፤ አይናቸው እንዲከፈት መዘዝ የሆነው። በገነት መሃል ካለው የዛፍ ፍሬ (መልካሙንና ክፉውን ለመለየት ከሚያስችለው ፍሬ) የበላ ይሞታል የሚል ትዕዛዝ ቢኖርም፤ እባብ ግን “አትሞቱም” ብሎ ለሴቷ ለሄዋን ይነግራታል። እንዳትበሉ የተከለከላችሁት፤ “በበላችሁ ቀን ዓይኖቻችሁ እንደሚከፈቱ፣ እንደ አማልክትም መልካምንና ክፉን የምታውቁ እንደምትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው...” ብሎ ያግባባታል። በእርግጥ እባቡ እንዳለውም፤ ፍሬውን ሲበሉ፤ አልሞቱም፤ አይኖቻቸው ተከፈቱ፤ ወንድና ሴት መሆናቸውንም አወቁ። ደግሞም እንደ አማልክት ትሆናላችሁ ብሏቸዋልኮ። በእርግጥሞ ሆነዋል። ምዕራፍ ሁለት ማጠቃለያ እንዲህ ይላል። ... እግዚአብሔር አምላክም፤ እነሆ አዳም መልካምንና ክፉን ለማወቅ ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ አለ። አሁንም እጁን እንዳይዘረጋ፥ ከሕይወት ዛፍ ወስዶ እንዳይበላ፥ ለዘላለምም ሕያው ሆኖ እንዳይኖር፤ እግዚአብሔር አምላክ ከዔድን ገነት አስወጣው፥ የተገኘባትን መሬት ያርስ ዘንድ። በመጀመሪያው ምዕራፍ አተራረክ፤ አዳምና ሄዋን በአምላክ አምሳያ ነው ህልውና ያገኙት። በምዕራፍ 2 አተራረክ ግን፤ ምኑንም ምኑንም የማያዋቁ አዳምና ሄዋን፤ የተከለከለ የዛፍ ፍሬ ከበሉ በኋ ነው የአምላክ አምሳያ የሆኑት። ግን፤ የዘላለማዊነትን ዛፍ እንዳይበሉ ከገነት ተባረሩ። እንግዲህ፤ ከዚህ በኋላ ነው ባልና ሚስት የሆኑት። የኔ ጥያቄ የምዕራፍ 1 እና የምዕራፍ 2 ትረካዎች በርካታ ልዩነቶች ቢኖሯቸውም፤ ተመሳሳይነታቸው የጎላ አይደለም ወይ የሚል ነው። የቅደም ተከተልና የዝርዝር ነጥቦች ልዩነት ቢኖርም፤ ሁለቱ ትረካዎች መሰረታዊ ልዩነት የላቸውም ማለት ይቻላል። በአጭሩ፤ ነገሮቹን በሙሉ እግዚአብሔር እንዳሻው አድርጎ ፈጠራቸው የሚል ነው የሁለቱ ትረካዎች መሰረታዊ ሃሳብ። በዚያ ላይ፤ የተፈጠሩት ነገሮች ያው ተመሳሳይ ናቸው። ሰማይ፣ ምድርና ባሕር፣ እፀዋትና አራዊት፣ እና ሰው! በእርግጥ፤ የ3200 አመት እድሜ አስቆጥሯል በሚባለው ጥንታዊ የፔርሺያ የሃይማኖት መፅሐፍም ስለ ፍጥረት ይተርካል። አምላክ ሁሉን ነገር በ6 ወቅቶች እንደፈጠራቸው የሚገልፀው አቬስታ የተሰኘው ጥንታዊ ሃይማኖታዊ መፅሐፍ፤ በቅድሚ ሰማያት፣ ቀጥሎ ባሕሮች፣ ከዚያ መሬት፣ ከዚያ እፀዋት፣ ከዚያ እንሰሳት፣ በስድስተኛውም ወቅት ሰው እንደተፈጠረ ይተርካል። ... BIBLE MYTHS AND THEIR PARALLELS IN OTHER RELIGIONS (ገፅ 7)። ታዲያ ይሄኛው ትረካና የዘፍጥረት ትረካስ አይመሳሰልም? የኖህ ታሪኮች በየአገሩና በየሃይማኖቱ የኖህ ታሪክን ጨምሮ፣ የ”ባይብል” የመጀመሪያዎቹ አምስት መጻሕፍት፣ ከ2500 እስከ 3000 አመት እድሜ ካላቸው ሰነዶች የተዋቀሩ እንደሆነ የሚናገሩት ተመራማሪዎች፤ ቢያንስ የሁለት ሃይማኖታዊ ቡድኖች የተውጣጣ እንደሆነ ይናገራሉ። የሁለቱ ቡድኖች ትረካ በ”ዘፍጥረት” ተደራርቦ እንደቀረበው ሁሉ፤ በኖህ ታሪክም ላይ ሁለት ትረካዎች ይደጋገማሉ። መቼም የኖህ ታሪክ ቢያንስ በከፊል ምሳሌያዊ አነጋገር መሆኑ አያጠራጥርም። መጽሐፉ እንደሚለው፤ ኖህ ከአዳም በ10ኛ ትውልድ ነው። በ10 ትውልድ እንዴት ነው፤ አለም በሰው ልጆች ቆሻሻና ክፋት ተሞላች ሊባል የሚችለው? እንዲያ ከአዳም ጀምሮ ሁሉም በሕይወት ቢኖሩ እንኳ ቁጥራቸው አንድ ሚሊዮን አይደርስም። እንደ ኖህ ሶስት ልጆችን ወይም እንደ አዳም 6 ልጆችን የሚወልዱ ከሆነ ደግሞ በምድር ላይ የሰዎች ቁጥር በጣም ትንሽ መሆን አለበት። የሆነ ሆኖ ፈጣሪ በጎርፍ ከኖህና ከልጆቹ በቀር ሰዎችን ሊያጠፋ ስለወሰነ፤ ኖህ መርከብ እንዲሰራ ታዘዘ። በአንደኛው ትረካ፡ ኖህ ከምድር ተንቀሳቃሽ ፍጥረታት ሁሉ ሁለት ሁለት ከሴትና ከወንድ ወደ መርከብ እንዲያስገባ ተነገረው ይላል ዘፍጥረት 6፡20። ከእያንዳንዱ የእንሰሳ አይነት አንድ ወንድ አንድ ሴት ለምሳሌ አንድ በሬና አንድ ላም እንደማለት ይመስላል። ሁለት በሬ፣ ሁለት ላም የሚል ትርጉምም ሊኖረው ይችላል። ሁለተኛው ትረካ፡ ንፁሕ ከሆኑት እንሰሳትና አእዋፋት ሰባት ወንድ ሰባት ሴት፤ ንፁሕ ካልሆኑት ደግሞ ሁለት ሁለት ወደ መርከቡ ውስጥ እንዲያስገባ እንደታዘዘ ይገልፃል ዘፍጥረት 7፡2-3። ለምሳሌ ሰባት በሬ ሰባት ላም እንደማለት ነው። ፈጣሪ ለኖህ የሰጠው ትዕዛዝ የትኛውም ቢሆን፤ በሰባት ቀን ውስጥ የጥፋት ውኃው እንደሚጀምር ተነግሮታል። ዝናቡና ጎርፉ ለአርባ ቀንና ሌሊት አያቋርጥም ተብሏል። ኖህ፣ በታዘዘው መሰረት መርከብ ሰርቶ፣ በታዘዘው መሰረት እሱና ቤተሰቡ፤ እንዲሁም ከእንሰሳት ዘር ሁሉ ሰብስቦ አስገባ። ግን ሰባት ሰባት እየሆነ የገባ የእንሰሳ አይነት እንደሌለ ይገልፃል።

በመፅሐፉ መሰረት አንደኛው ትረካ ነው ተግባራዊ የሆነው። አንደኛ ትረካ፡ ከምድር ተንቀሳቃሽ እንስሳት ሁሉ፤ ከወፍና ከነፍሳት ሁሉ፤ ንፁሕ የሆኑም ያልሆኑትም እንሰሳት፤ ሁለት ሁለት ሴት እና ወንድ እየሆኑ ወደ መርከብ እንደገቡ ይገልፃል - ዘፍጥረት 7፡8-9። ከእያንዳንዱ የእንሰሳ አይነት አራት ማለት ነው? ወይስ ሁለት? ለነገሩ ሁለት ብቻ ቢሆን እንኳ ቀላል እንዳይመስላችሁ። በምድር ላይ 5 ሚሊዮን ያህል የነፍሳት አይነቶች እንዳሉ ይገመታል - ዝንብ፣ ንብ፣ በረሮ። ከእያንዳንዱ አይነት ሁለት ሁለት እየተመረጠ በአጠቃላይ 10 ሚሊዮን ያህል ነፍሳት ወደ መርከቡ ይገባሉ ማለት ነው። በባህር ወይም ውሃ ውስጥ የሚኖሩትን ትተን፣ ጥቃቅኖቹን ነፍሳትም ሳይቆጠሩ፤ ወደ 20 ሺ ገደማ የተለያዩ የምድር እንሰሳት አሉ - እንሽላሊት፣ ዝሆን፣ ግመል፣ ጥንቸል፣ ጊንጥ፣ አሞራ... ወዘተ። ሁለት ሁለት እየሆኑ በአጠቃላይ ወደ 40 ሺ እንሰሳት ወደ መርከቧ ይገባሉ። የእግር ኳስ ሜዳ በማታክል መርከብ ውስጥ ማለት ነው። በዚያ ላይ የምግብና የውሃ ስንቅ መያዝ እንደሚገባው ታዟል። የኖህ ቤተሰቦችና እንሰሳቱ ሁሉ ከመርከቧ የሚወጡት ከአስራ ሁለት ወራት በኋላ ነዋ። ለ8ቱ የኖህ ቤተሰቦች፣ በሺህ ለሚቆጠሩ እንሰሳት፤ በሚሊዮን ለሚቆጠር ነፍሳት... የአንድ አመት ቀለብና ውሃ ብዙ ነው። እንግዲህ፤ የነገሩን አስቸጋሪነት ሲታይ ነው፤ የኖህ ታሪክ በከፊል ምሳሌያዊ ትረካ መሆን አለበት የሚባለው። ለማንኛውም የጥፋት ውኃ ከ5 ወራት በኋላ መጉደል እንደጀመረ፣ የኖህ መርከብ በአራራት ተራሮች ላይ እንደተቀመጠች፣ በ10ኛው ወር የተራሮች ጫፍ እንደታየ የሚተርከው ዘፍጥረት፤ ኖር መስኮት ከፍቶ ቁራ እና እርግብ እንደሰደደ ያወሳል። እርግቧ የምታርፍበት ቦታ አጥታ ተመለሰች፤ ከሰባት ቀን በኋላ ሲልካት በአፏ የወይራ ቅጠል ይዛ መጣች። አዲስ የበቀለ ይሁን ለአስር ወራት በጎርፍ ተቀብሮ የነበረ ወይራ ይሁን ባይታወቅም፤ ቅጠሉ ለምለም ነው። እንደገና ከሰባት ቀን በኋላ ለሶስተኛ ጊዜ እርግባን ሰደዳት፤ ተመልሳ አልመጣችም። ከ10 ወር ተኩል በኋላ የመርከቧ ክዳን ተከፈተ። ኖህ ከመርከቡ የወረደው ደግሞ አስራ ሁለት ወር ከደፈነው በኋላ ነው። ለእግዚአብሔርም መስዋዕት አቀረበ።

የሰው ዘር በሙሉ ከኖር ሶስት ልጆች ከሴም፣ ከካም እና ከያፌት ትውልድ የሚመዘዝ ሆነ ማለት ነው። የግሪኮቹ ኖህ ዱካልዮን ይባላል። አምላከ አማልክት ዙውስ፤ በሰው ልጆች የክፋት መንገድ ተቆጥቶ፤ የውኃ ጥፋት አዘዘባቸው። ለዘጠኝ ቀንና ሌሊት ዶፍ ዝናብ ለቀቀባቸው። ዱካልዮን ግን የአማልክቱን ሕግ የሚያከብርና የእውነትን መንገድ (በጽድቅ መንገድ) ይከተል ነበር። በዚህም ምክንያት የሰው ልጅን ከሚያጠፋ የውኃ መጥለቅለቅ እንዲድን ከአምላክ ተነግሮት መርከብ ሰርቷል። ውኃው አለምን እያጥለቀለቀ ሰው እና እንስሳን ሁሉ እየገደለ ሸለቆውን ብቻ ሳይሆን ተራሮችንም ይውጣል። ኩካልዮን እና ሚስቱ ግን መርከባቸው ውስጥ ናቸው። ውኃው መርከቧን እያንሳፈፈ ፓርናሰስ ተራራ ላይ አሳረፋት። በዚህ መንገድ ከሚስቱ ጋር ከጥፋት ውኃ ያመለጠው ዱካልዮን፤ ለአምላክ ዙውስ መስዋዕት አቀረበ። ሦስት ልጆችንም ወለደ። የሰው ዘርም ከሶስቱም ልጆች የሚመዘዝ ነው። በህንድ የሰንስክሪት ሃይማኖታዊ ፅሁፎችም ስለ ውኃ ጥፋት ይተርካሉ። ምድርና ሰማይ ከተፈጠሩ ከብዙ ዘመናት በኋላ በሰዎች ክፉ ተግባር የተነሳ ፈጣሪ በውኃ ሊያጥለቀልቃት ቢወስንም፤ አንድ በፅድቅ መንገድ የሚኖር ነበር - ሳትያራታ የሚባል። ፈጣሪ አምላክም ወደ ሳትያራታ መጥቶ፣ በ7 ቀን ውስጥ የጥፋት ውኃ እንደሚመጣ ነገረው። ግን ላንተ መርከብ ሰርቼ እሰጥሃለሁ። እፀዋትን ሁሉ፣ ከእንሰሳትም ሴት እና ወንድ ጥንዶችን ሰብስበህ ወደ መርከባ ግባ። ከውሃ ጥፋትም ትድናለህ አለው። የባሕር ምንጮች ተከፈቱ፤ የዝናፍ ዶፍ ወረደ። ምድር ተጥለቀለች። ሳትያራታ እና በመርከቧ ውስጥ የገቡ እፀዋትና እንሰሳት ግን ከጥፋት ዳኑ። ዳትያራታም ለአምላክ መስዋእት አቀረበ። BIBLE MYTHS AND THEIR PARALLELS IN OTHER RELIGIONS (ገፅ 24 - 25)። በእርግጥ የሰንስክሪት ፅሁፎች እድሜ 2400 ገደማ እንደሆነ ምሁራን ይገልፃሉ። የባቢሎናዊያኑ ትረካ ግን የ4000 አመት እድሜ አለው። ከ4000 አመት በፊት የተፃፈው የአትናፒሽቲም ታሪክ ከኖህ ጋር እንደሚመሳሰል ለብዙዎች አከራካሪ አይደለም። የዛሬዋ ኢራቅ የያኔዋ ባቢሎን አለምን ካጥለቀለቀው የጎርፍ ጥፋት እንደ ኖህ የተረፈው ሰው አትናፒሽቲም ይባላል። ስለጎርፉ እና ስለ አትናፒሽቲም ታሪክ ተፅፎ የሚገኘው፤ ከጊልጋሜሽ ገድል ጋር ነው። የጊልጋሜሽ ገድል Gilgamesh Epic በመባል የሚታወቀውና በ12 ሸክላዎች ላይ ተፅፎ የተገኘው ትረካ፤ የንጉስ ጊልጋሜሽን ጀግንነት ይዘረዝራል። ከዚሁ ጋር ግን፤ በጥንት ዘመን የሰው ልጅን ከምድረ ገፅ የሚያጠፋ የውኃ መዓት ደርሶ እንደነበር ይተርካል። በእብራውያኑ የኖህ ታሪክ፤ የውኃ ጥፋት የመጣው ከአዳም በ10ኛው ትውልድ በኖህ ዘመን እንደሆነ ይገልፃል። የባቢሎናውያኑ ትረካ ደግሞ፤ በ10ኛው ስርወመንግስት የጥፋት ውኃ አጋጥሞ፤ ኡትናቢሽቲም ብቻ እንደተረፈ ይገልፃል። አምላክ ባዘዘው መሰረት መርከብ ሰርቶ ከሁሉም የእንሰሳት አይነቶችም ሰብስቦ መርከቡ ውስጥ ገባ። በስድስት ቀን ዶፍ ዝናብ አለም ተጥለቀለቀች። መርከቧ ተንሳፍፋ ናሲር ተራራ ላይ አረፈች። በመጨረሻ ዝናቡ ሲቆም፤ ውሃው መጉደሉና አለመጉደሉን ለማወቅ እርግብ ሰደደ። በመጨረሻም ከነሚስቱ ከመርከቧ ወርዶ ለአምላክ መስዋእት አቀረበ። THE EPIC OF GILGAMESH፣ PENGUIN BOOKS 1999፣ ከገፅ 88 -100

 የጎፋ ቅ/ገብርኤል ምእመናን በደብሩ አስተዳዳሪ ተማረዋል

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስትያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ‹‹መሠረተቢስ መረጃዎችን በማስተላለፍ ሕዝቡን ለማደናገር ይሠራሉ›› ባላቸው የሚዲያ ተቋማት ላይ ክስ መመሥረቱን አስታወቀ። በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ በወጣው ደብዳቤ እንደተገለጸው÷ ክሥ የተመሠረተባቸው አራቱ የሚዲያ ተቋማት÷ የኛ ፕሬስ ጋዜጣ፣ አርሒቡ፣ ሊያ እና ሎሚ የተባሉ መጽሔቶት ናቸው፡፡
የቅዱስ ፓትርያሪኩን ዜና ዕረፍት ተከትሎ ያለውን የሽግግር ወቅት በሰላማዊ መንገድ ለማከናወን ቅ/ሲኖዶስ በአንድነትና በመደማመጥ መንፈስ በተለያዩ ጊዜያት ጉባኤያትን በማድረግ፣በውጭም በውስጥም ያለውን ተጨባጭ ኹኔታ በመዳሰስና በሐቅ ላይ በመመርኮዝ የስድስተኛውን ፓትርያርክ ምርጫ ለማካሄድ ተግባራዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ መኾኑን መምሪያው ገልጾ÷ ‹‹አንዳንድ የነጻው ፕሬስ አባላት ሓላፊነት በጎደለው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ የሚመራውን የቅ/ሲኖዶስ ጉባኤ ውሎ በማብጠልጠልና በመተቸት የሚያወጧቸው ዘገባዎች በእጅጉ አሳዛኝና ቤተ ክርስቲያኒቱን ኾነ ብለው ለመበጥበጥ የተነሡ ያስመስላል›› ብሏል፡፡
በሕዝብ ግንኙነት መምሪያው ደብዳቤ እንደተመለከተው፣ በስም የተጠቀሱት ፕሬሶች በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትም ኾነ በሚመለከታቸው አካላት ማብራሪያና መግለጫ ያልተሰጠበትን ዜና ‹‹ከልዩ ልዩ የመረጃ መረቦች አግኝተናል›› በሚል ሽፋን ጽፈዋል፡፡ መምሪያው ‹‹በአባቶች መካከል ጠብና ችግር አለ ብሎ አንባቢው እንዲያምን ለማድረግ የሚጻፉ ናቸው›› ያላቸው እኒህ ጽሑፎች፣‹‹መሠረተቢስ አሉባልታዎች ብቻ ሳይሆኑ ቤተ ክርስቲያኒቱን የማፈራረስና ቅ/ሲኖዶሱን የመበታተን ዓላማ ያነገቡ ናቸው፡፡››
በመኾኑም በስም በተጠቀሱት አራት የፕሬስ ውጤቶች ላይ ቤተ ክርስቲያኒቱ ክሥ መመሥረቷንና ሕግና ሥርዐቱ በሚፈቅደው መሠረት ጉዳዩን በመከታተል የሕግ እርምት እንዲወሰድ በመንቀሳቀስ ላይ መኾኗ ተመልክቷል። ትክክለኛ መረጃን ለሕዝቡ ለማድረስ የሚመለከታቸውን አካላት በማነጋገር እውነተኛውን ዜና የሚያስተላልፉ የግል ሚዲያ ተቋማትን ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደምታደንቅና እንደምታመሰግን በደብዳቤው የገለጸው መምሪያው፣ በሚመለከተው የቤተ ክርስቲያኒቱ አካል መግለጫ ያልተሰጠባቸው ዘገባዎች ሁሉ ‹‹የሽግግር ወቅቱ በሰላማዊ መንገድ እንዳይከናወን የሚጥሩ ሰዎች የሚያናፍሱት የሐሰት ወሬ›› መኾኑን ሕዝቡ እንዲያውቀው ጠይቋል፡፡
በሌላ በኩል በአሁኑ ወቅት በቤተ ክህነቱ የተለያዩ ደረጃዎች የሚታዩ አስተዳደራዊ ችግሮች እየተባባሱ መኾናቸው፣ በየጊዜው ለአዲስ አድማስ ዝግጅት ክፍል እየደረሱ ያሉ የካህናትና ምእመናን አቤቱታዎች ያስረዳሉ፡፡ በተደጋጋሚ የዘገብነው በሰሜን ወሎ ሀ/ስብከት የቅ/ላሊበላ ደብረ ሮሃ ገዳም አስተዳደራዊ ችግር ዋነኛ ማሳያ ሲሆን በአስተዳደሩ ላይ ሲነሣ የቆየውና የከተማውን አስተዳደር ጨምሮ በመንግሥትና በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ከፍተኛ አካላት ዘንድ ሳይቀር በሚገባ የሚታወቀው የካህናቱና ምእመናኑ ጥያቄ በተለያዩ አጋጣሚዎች መመሪያ እንደተሰጠበት ቢነገርም እስከ አሁን በተጨባጭ ምላሽ እንዳላገኘ ነው የተዘገበው፡፡
ለመልካም አስተዳደር እንዲያመች በሚል በጥቅምቱ የቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ ውሳኔ÷ ለአራት በተከፈለው በአዲስ አበባ አህጉረ ስብከት ሥር በሚገኙ አንዳንድ አድባራትም ከሙስናና ብልሹ አሠራር ጋራ ተያይዘው በካህናቱና ምእመናኑ የሚነሡ በርካታ ጥያቄዎች እንዳሉ ለዝግጅት ክፍሉ የሚደርሱ መረጃዎች ያስረዳሉ፡፡ በደቡብ አዲስ አበባ ሀ/ስብከት የጎፋ መካነ ሕያዋን ቅ/ገብርኤል ካቴድራል÷ በካቴድራሉ አስተዳዳሪ ከእርሳቸውም ጋር በጸሐፊነት፣ በሒሳብ ሹምነት እና በገንዘብ ያዥነት በሚሠሩ የአስተዳደሩ ሠራተኞች ላይ ካለፈው ዓመት መጨረሻ ጀምሮ የሚነሡትና ከሀ/ስብከቱ ጽ/ቤት ባሻገር የመንበረ ፓትርያሪክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቱ ጭምር እንደሚያውቀው የተነገረው አንድ የችግሩ አብነት ነው፡፡
በካቴድራሉ ሰንበት ት/ቤት እንደሚያገለግሉ የገለጹት ምእመናኑ ለዝግጅት ክፍላችን በሲዲና በሰነድ ያደረሷቸው መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፣ በክብረ በዓላትና በተለያዩ ጊዜያት ደብሩ በመባዕና በስእለት ለሚያገኘው ገንዘብና ንብረት ቆጠራ የሚካሄደው ግልጽነትንና ተጠያቂነትን የሚያሰፍነውን መመሪያ በመከተል ሳይሆን በአስተዳዳሪው ቀራቢዎች ነው፤የካቴድራሉ ገንዘብና ንብረት በትክክለኛ ሞዴላ ሞዴሎች ገቢ አይደረጉም፡፡ ከካቴድራሉ የንዋያተ ቅድሳት መሸጫና ሱቁ በተጓዳኝ ከሚሠራቸው የጨረታና የጉዞ አገልግሎቶች የሚሰበሰበው ገቢ በአግባቡ አይታወቅም፡፡
ሁለተኛውን ፓትርያሪክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስን ለመዘከር በተሠራው የአንደኛና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ከሚማሩ ተማሪዎች ክፍያ በሁለት ደረሰኞች የሚሰበሰብ ሲኾን አንዱ ደረሰኝ በካቴድራሉ ሰበካ ጉባኤም ሆነ በሀ/ስብከቱ አይታወቅም፡፡ ከፍለው ለመማር አቅም የሌላቸውን ተማሪዎች በበጎ አድራጊዎች ስፖንሰርሽፕ ለመደገፍ አስተዳደሩ የሚከተለው አሠራር ለምዝበራ የተጋለጠ በመኾኑ በችግረኛ ተማሪዎች ስም እየተነገደ ነው፡፡
በካቴድራሉ ደጃፍ መንግሥት በሰጠው ፈቃድ በካቴድራሉ ወጪ የሚሠራው የዝክረ ቴዎፍሎስ ዐደባባይ ሦስተኛ ዓመቱን ቢያስቆጥርም በየጊዜው ኾነ ተብሎ ዲዛይኑንና ጥራቱ ጠብቆ እንዳይሠራ እየተደረገ ግንባታው እየተጓተተ ነው፡፡ በግንባታው ሰበብ የሚገዙ የግንባታ ማቴሪያሎችና በቃል ኪዳን ሰነድ የተሰበሰበው ገንዘብ የግለሰቦች መኖሪያ ቤት መሥሪያና የግል ኑሮን ማበልጸጊያ እንደኾነ በምሬት የሚናገሩት ምእመናኑ÷ በቀድሞው አስተዳደር በአግባቡ ተጠብቆ የቆየው የካቴድራሉ ሕንጻ ቤተ መቅደስና የቅጽረ ቤተ ክርስቲያኑ ገጽታ በወቅቱ አስተዳደር ትኩረት የተነፈገው በመኾኑ በከፍተኛ ደረጃ መጎሳቆሉን፣ በአንጻሩ በካቴድራሉ ይዞታዎች በቤተ ክርስቲያን ቅጽር መገኘት የማይገባቸው ግለሰቦች ከአስተዳደሩ ጋራ በፈጠሩት የጥቅም ትስስር ለቤተ ክርስቲያን ቅድስናና ክብር ተቃራኒ የኾኑ ንግዳዊ ሥራዎችን (የከሰል፣ የአጠና ሽያጭና የአሳማ ርባታ) እንደሚያካሂዱ የሚናገሩት በከፍተኛ የሐዘን ስሜት ተውጠው ነው፡፡
ምእመናኑ በሰነድና በቃል ማብራሪያ አስደግፈው በካቴድራሉ አስተዳደር ላይ የሚያሰሟቸው አቤቱታዎች÷ የሰበካ ጉባኤ ቃለ ዐዋዲን፣ የቀኖና ቤተ ክርስቲያንንና የክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር ጥሰትን የተመለከቱ ተጨማሪ አቤቱታዎችን ያካተተ ሲሆን ካለፈው ዓመት ሐምሌ ወር ጀምሮ ለመፍትሔው እንቅስቃሴ ሲደረግባቸው መቆየቱ ተገልጧል፡፡ አቤቱታዎቹ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በሠየመው አጥኚ ኮሚቴ በሚጣሩበት ወቅት የካቴድራሉ አስተዳደር ያመነባቸው ከመኾኑም በላይ ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ ለአምስት ዓመታት በአስተዳዳሪነት የቆዩት ቆሞስ አባ ኀይለ መለኰት ይኄይስ ከሓላፊነት ተነሥተው ለካቴድራሉ መንፈሳዊ አገልግሎትና የልማት አቅም በሚመጥን አለቃ እንዲተኩ ተወስኖ እንደነበር ምእመናኑ ያስታውሳሉ፡፡
ውሳኔውን በአግባቡ ተፈጻሚ በማድረግ መፍትሔ እንዲሰጣቸው በጥቅምት መጨረሻና በጥር መጀመሪያ ላይ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጽ/ቤትና ለቅ/ሲኖዶስ ጽ/ቤት ጥያቄዎቻቸውን በተደራጀ አኳኋንና በሰላማዊ መንገድ እያቀረቡ እንደሚገኙ ምእመናኑ ገልጸው÷ የካቴድራሉ አስተዳደር ግን ይባስ ብሎ ‹‹አቤቱታ አቅራቢዎችን ተባብረዋል›› በሚል ዐሥር የካቴድራሉን ካህናት ከደመወዝና ከሥራ ማገዱን፣በካቴድራሉ ይዞታ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቶቻቸውም እንዲለቁ ማዘዙን፣ ካቴድራሉ የሚገባውን ብቁ አስተዳደር እንዲያገኝ በሥርዐት የሚንቀሳቀሰውን የሰንበት ት/ቤት አመራርም በዐመፀኝነትና በፖለቲከኝነት በመወንጀል ከፍተኛ ጫና እየፈጠሩበት መኾኑን አስረድተዋል፡፡ በሓላፊነት ላይ የሚገኙት የካቴድራሉ አስተዳዳሪ ከሥልጣናቸው መነሣት ብቻ ሳይሆን የሕዝብን ሀብት ለብክነትና ለምዝበራ በመዳረጋቸው በሕግ መጠየቅ እንዳለባቸው የሚከራከሩት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፣ በሕግ አገባብ ለሚመለከተው የፍትሕ አካል አስፈላጊውን ማስረጃ ለማቅረብ ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን አስታውቀዋል፡፡