Administrator

Administrator

 ወቅቱ እ.ኤ.አ 73 ዓ.ም.፣ ስፍራው ደቡብ እስራኤል። በመሳዳ አምባ ምሽግ ላይ በጅምላ መስዋዕትነት የተደመደመው የአይበገሬነት ፅናት በመላው ዓለም ከአፅናፍ እስከ አፅናፍ ናኘ። የኃያላን ኃያል የነበሩት ሮማውያን እየሩሳሌምን በጭካኔ ሁኔታ ሲወሩ፣ 967 አይሁዳውያን አመፁ። “በባርነት አንገዛም” ብለውም ራሳቸውን መከላከል ወደሚያስችላቸው የመሳዳ አምባ ሸሽተው መሸጉ። ውሎና ሰንብቶ ሽንፈት አይቀሬ ሲሆን ደግሞ እጅ ከመስጠት ይልቅ በህብረት ራሳቸውን እስከ ወዲያኛው ለማጥፋት መረጡ። ለጭቆና አልበገር ባይ የሆነው የጀብደኝነታቸው ተምሳሌትነት፣ ዘመናትንና አህጉራትን አቋርጦ ተደመጠ። እንደ ገደል ማሚቶ ከአድማስ እስከ አድማስ አስተጋብቶም፣ በሌላ የአምባ ምሽግ ላይ በተመሳሳይ መልኩ በ1860 ዓ.ም. ተደገመ - በመቅደላ አምባ ኢትዮጵያ!

የሁለት አምባ ምሽጎች ወግ
ታሪክ በፈታኝ ሁኔታ ቢሆን እንኳ አልገዛም ብለው ጀብድ በሚፈፅሙ ጀግኖች ታሪክ የበለፀገ ነው ይባላል። ይህን መሰል ጀብድ ከተፈፀመባቸውና የአምባ ምሽግን ተገን ካደረጉ አስደናቂ ስፍራዎች መሀል የእስራኤሉ መሳዳን እና የኢትዮጵያው መቅደላን መጥቀስ ይቻላል። በመልክዓ ምድራዊ ስፍራቸው የትየለሌ ቢሆኑም፣ ሁለቱ የአምባ ምሽጎች የተጋሩት የእምቢተኝነት ገድል ልክ በአለት ላይ ተጠርቦ እንደተፃፈ ታሪክ ሁሉ ዘመን ተሻጋሪ ነው።
የመሳዳ አምባ ምሽግ ለጉዞ አስቸጋሪ በሆኑ በልሙጥ ገደሎች የተከበበ ስፍራ ነው። እ.ኤ.አ ከ66-73 ዓ.ም. በተካሄደው የአይሁድና የሮማ ጦርነት ወቅት ለአይሁድ ተፋላሚዎች ተፈጥሯዊ ጋሻና መከታ ሆኖ አገልግሏል። ለሮማውያኑ ጦረኞች እንደ ግድግዳ ቀጥ ያለውን ዳገት መወጣጣት እጅግ ፈታኝ ነበር። ለተከላካዮቹ ደግሞ ረዘም ላለ ወቅት አሌ የማይባል ጥቅም አስገኝቶላቸዋል። ሆኖም ሮማውያን ከእስራኤል የማረኳቸውን ብዙ ሺህ ባርያዎች አስገድደው ከመሳዳ ሥር ባለ በአንድ ጉብታ ላይ የመረማመጃ ክምር በማስከመራቸው፣ አይደፈሬው የመሳዳ አምባ ምሽግን በተሻለ ብቃት ለማጥቃት ችለዋል። ይህ ቦታ በመጽሐፍ ቅዱስ በቀጥታ ባይጠቀስም ዳዊት ከሳኦል ሸሽቶ (1ኛ ሳሙ 23፡ 14) የኖረበት ሳይሆን አይቀርም ይባላል።
በፅናት የተቆመባቸው የአምባ ምሽግ አምዶች
ልሙጥ ባለ ገደል የተከበበውን የመሳዳን አምባ ተገን በማድረግ አይሁዶች ለበርካታ ወራት የሮማውያንን ጥቃት በጀግንነት መክተው ነበር። ሆኖም ግን የአምባው ምሽግ መገርሰስ አይቀሬ እየሆነ መጣ። ቢሆንም የተዋጊዎቹ የመንፈስ ጽናት ፍንክች አላለም።
ይህ የተጋድሎ ታሪክ አህጉር አቋርጦ እና ሺህ ዓመታትን ተሻግሮ ራሱን በኢትዮጵያ ደገመ። የሀገር ውስጥ ተቀናቃኞች ከአውሮፓውያን ወራሪ ጦር ጋር ተረዳድተው፣ አጤ ቴዎድሮስን ጦርነት የገጠሟቸው ከመቅደላ አምባ ምሽጋቸው ነበር። ይህ ከፍ ያለ ጠረጴዛማ ስፍራ ለዝንጀሮ እንኳ በሚያዳግት መልኩ ዙሪያውን ጭው ባለ ገደል የተከበበ ነው። ከላዩ ላይ ከተወጣ በኋላ ግን ሰፊና ሜዳማ ነው። እዚህ ስፍራ ላይ ነው እንግዲህ አጤ ቴዎድሮስ ተፈጥሮን፣ ሴባስቶፖል መድፋቸውንና ጀግንነታቸውን አቀናጅተው በጄኔራል ናፒየር የሚመራውንና ዘመናዊ ጦር መሣሪያ የታጠቀውን 32,000 የአንግሊዝ-ህንድ ሰራዊት ሊመክቱ ያደፈጡት።

አይበገሬው የመቅደላ አምባ ምሽግ
መቅደላ አምባ በገደላማነቱ የሚኮራና ተፈጥሯዊ የመከላከያ ጠቀሜታን የተጎናፀፈ ነው። አጤ ቴዎድሮስ በጋፋት ያሰሩትንና ክብደቱ ከ8,000 ኪሎ ግራም በላይ የሚመዝነውን የሴባስቶፖል መድፍ በጋሪ ጭነው ከ320 ኪሎ ሜትር አስቸጋሪ ምድርና ሽፍቶች ጋር እየታገሉ፣ ከስድስት ወር ተኩል በላይ በማጓጓዝ ከአምባው በመድረስ የምሽጉን አቅም አፈርጥመዋል።
በተፈጥሮ አቀማመጧ ሳቢያ የመቅደላ አምባ በአስተማማኝ የወታደራዊ ምሽግነትና  ያመጠኛ ወንጀለኛ እስረኛ ማስቀመጫነት ትታወቃለች። በተለይም አጤ ቴዎድሮስ በስተመጨረሻው የሥልጣን ዘመናቸው መቅደላ አምባን እንደ ዋና መዲናቸው አድርገው ይቆጥሯት ነበርና በርካታ ውድ ንብረታቸውን የማስቀመጫ ስፍራ አድርገዋት ነበር። በተጨማሪም ዳግማዊ ምኒልክ ገና ልጅ ሳሉ በአጤ ቴዎድሮስ ተወስደው በ1857 ዓ.ም እስከ አመለጡበት ወቅት ድረስ ለዐስር ዓመታት በዚሁ በመቅደላ አምባ ምሽግ ተወስነው እንደቆዩበት ይታወሳል።

የጋራ እንቢተኝነት ትሩፋት
ምንም እንኳ የመሳዳ እና የመቅደላ አምባ ምሽጎች በመልክዓ ምድራዊ ስፍራና ጠባያቸው እጅግ ቢለያዩም፣ ጭቆናን በመቋቋም ረገድ ጥልቅ በሆነ አይበገሬነት መንፈስ የተጋመዱ ናቸው። ፍፃሜው ቢያሳዝንም በሁለቱም የአምባ ምሽጎች የተመረጠው መፍትሄ እጅ መስጠት ሳይሆን የሞትን ፅዋ በክብር መጎንጨት ነበር።

የነጻነት ተዋጊዎቹ ልብ ሰባሪ ምርጫዎች
ምንም እንኳ እውነትነቱን ጥያቄ ውስጥ ያስገቡ ጸሐፍት ቢኖሩም፣ በጉብኝቱ ስፍራ ላይ የሚነገረው ታሪክ እንዲህ ነው። የመሳዳ አምባ ምሽግ አለቆች እያንዳንዱ የአይሁድ ባል ሕይወቱን ከማጥፋቱ በፊት ሚስትና ልጆቹን እንዲገድል ኃላፊነት ተጣለበት። በውጤቱም ቁጥራቸው ወደ አንድ ሺህ የሚጠጉ የመሳዳ አማፂያን ራሳቸውን በራሳቸው በማጥፋት (ማስ ሱይሳይድ) ሮማውያኑ በስተመጨረሻ እጃቸውን በመያዝ ሊያገኙ የሚችሉትን ርካታ ነፍገዋቸዋል። በተመሳሳይ መልኩ በመቅደላ አምባ ምሽግም አጤ ቴዎድሮስ ለእንግሊዝ ወራሪ ጦር እጅ ከመስጠት ይልቅ በገዛ ሽጉጣቸው የመስዋዕትነትን ፅዋ በጀግንነት ተጎንጭተዋል።

ትሩፋትን ማዝለቅ
የመሳዳ አምባ ምሽግ በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገበ ታሪካዊ ስፍራ ሲሆን፤ ለአይሁድ ሕዝብ የዓላማ ፅናት ለቀጣይ ትውልድም ሆነ ለመላው ዓለም ጉልህ ማሳያ ሆኗል። ጎብኚዎች የአርኪኦሎጂ ቅሪቶችን ማየት ብቻ ሳይሆን አማፂያኑን የመጨረሻውን የሞት ፅዋ የተጎነጩበት ስፍራ ላይ ቆመው ታሪክን የኋሊት እንዲመለከቱ ተመቻችቶላቸዋል። ወደ ተራራው አናት በሚያደርስ የገመድ ላይ ተንጠልጣይ ትራንስፖርት በመጠቀም ጎብኚዎች ሙት ባሕርን ጨምሮ አስደናቂ የሆነ ዙሪያ ገባውን መቃኘት ይችላሉ፤ ለስፍራው ከፍተኛ የገንዘብ ጥቅምም ያስገኛሉ።
ባንፃሩ ምንም እንኳ በዓለም አቀፍ ደረጃ ብዙም ባይታወቅም የመቅደላ አምባ ምሽግ ተመሳሳይ የተጋድሎ መስዋዕትነት የተከወነበት ድንቅ ስፍራ ነውና ተገቢው እውቅና እና ክብር ሊቸረው ግድ ይላል።

ከመቅደላ አምባ የምንማራቸው
ከአጤ ቴዎድሮስ መስዋዕትነት ጋር ተያይዞ አራት አንኳር ትምህርትን መቅሰም ይቻላል። ቁርጠኛ ፍላጎት ካለ አገርን ለማሳደግ የሚያስችል እቅድ በማቀድ ወደ እድገት ጎዳና በፍጥነት ማቅናት መቻሉን፤ አገራዊ ሉዓላዊነትን ከባዕድ ወረራ ለመግታት በጽናትና መስዋዕትነት የመቆም አስፈላጊነትን፤ የውጭ ጠላትን ከመጋፈጥ አስቀድሞ አገር ውስጥ ካሉ ተፎካካሪዎችም ሆነ ባላንጣዎች ጋር ልዩነትን አቻችሎና ተባብሮ አለመሥራት የሚያስከትለው መዘዝን፤ እንዲሁም የኅይል እና የጭካኔ አገዛዝ ጠቀሜታው ለጊዜው ብቻ እንጂ ዘላቂ አለመሆኑን ነው።
ችግርን ለመጋፈጥ የማይናወጥ ፅናትና ጥንካሬ እጅግ አስፈላጊ ቢሆንም ገደብ ያልተበጀለት አምባገነንነት የሚያመጣው አደጋ ደግሞ የትየለሌ ነውና፣ ከቀበሌ ጀምሮ እስከ ርዕሰ ብሔር ደረጃ ላይ ያሉ ባለሥልጣናት ልብ ሊሉት የሚገባ ተሞክሮ ነው።
የድርጊት ጥሪ
በመጪው ሚያዝያ ሰባት ቀን ለሚከበረው 156ኛው የመቅደላ ጦርነት መታሰቢያ በዓል እየተቃረብን ነው። እግረ መንገዳችንን አምባው እንደ ማሳዳ ሁሉ በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት እንዲመዘገብ የተባበሩ ጥሪ ቢደረግ ጠቀሜታው ከፍተኛ ነው። አንደኛ፣ የታሪካዊነቱን ፋይዳ ስፋትና ጥልቀት በእጅጉ ያልቀዋል። ሁለተኛ፣ ከቃጠሎ ተርፈው እንግሊዝ ውስጥ በብሪቲሽ ሙዚየምም ሆነ በሌሎች ስፍራዎች የሚገኙትን በመቶዎች የሚቆጠሩ የተዘረፉ የባህል ቅርሶችን አንድ በአንድ እየለመኑ በመቀበል ሳይሆን ሁሉንም ባንድነት ለማስመለስ የፈረጠመ ጫናን ይፈጥራል። (እዚህ ላይ በርካታ የተዘረፉ ቅርሶችን በማስመለስ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ግለሰቦችና ተቋማትን ሳንዘነጋ ነው)። ሶስተኛ፣ በአሁኑ ሰዓት መቅደላ ላይ በሚያሳዝን መልኩ በጥቂት የድንጋይ ካቦች ብቻ በምልክትነት የሚታየው የአጤ ቴዎድሮስ መቃብርም ሆነ ሌሎች ታሪካዊ ክንውን የተፈፀመባቸው ስፍራዎች ለጎብኚዎች በምቹ ሁኔታ ቢጎለብቱ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ሊገኝ የሚችለው ኢኮኖሚያዊ ትሩፋት ለአካባቢውም ሆነ ለሕዝቡ እድገት በጎ ሚና ይጫወታል።
የአጤ ቴዎድሮስ እና የመቅደላ አምባ ጀብድ በበርካታ ዕውቅ ቲያትሮችና ቱባ ተዋንያን፣ በታሪካዊ መጻሕፍት፣ በሥዕሎች፣ በዘፈኖች፣ በፖለቲካ ዲስኩሮች፣ ወዘተ ደምቀው መወደሳቸው የሚያስመሰግን ተግባር ነው። ነገር ግን ውዳሴና አድናቆቱ የላቀ ትርጉምና ጠቀሜታ የሚያስገኘው ጉዳዩ ወደ መሬት ወርዶ በስፍራው ላይ ሲታይና ሲጨበጥ ነው። ለዚህ ተግባር ደግሞ አምባውን በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የማስመዝገቡ ጥረት ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛል። ይህ ለነገ የሚባል ጉዳይ አይደለም፤ እስካሁን አለመደረጉ በእራሱ ዘግይቷልና።
***
ከአዘጋጁ፡-
* ዳንኤል ካሳሁን (ፒ ኤች ዲ) በተለያዩ ከባቢያዊ ነክ ጉዳዮች ዙሪያ በጂኦግራፊያዊ ምልከታና የጥንቅር ዘዴ ተመርኩዘው፣ መጣጥፎችን በተለያዩ የሕትመት ውጤቶች  ለኢትዮጵያውያን ያካፍላሉ። ጸሃፊውን በኢሜይል አድራሻቸው፡- This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. ማግኘት ይቻላል፡፡

የኢትዮ ሮቦ ሮቦቲክስ የትምህርትና ውድድር ማዕከል ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር

ለሶስት ቀናት በታዳጊዎች መካከል በተዘጋጀው ውድድር ማጠቃለያ ላይ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ድኤታ

ክቡር ባይሳ በዳዳ (PhD) ለአሸናፊዎች እውቅና ሲሰጡ:-

Saturday, 23 March 2024 20:53

ሣቅሽ እንደ ሀገሬው ...

ጥርስሽ የሌላ፥ ፈገግታሽም የተረታ፤
በሰው ጉዳይ፥ በሰው መቼት
‘ሚበረታ።
ትብታቡን ሳይበጥስ፥ ያደደሩበትን
ሳይቆረጥም፤
በአሟሟቱ የሚደመም።
ሲንዱት እየሣቀ፥
ሲያፈርሱት እየሣቀ፤
በቀብሩ ላይ የሚታደም።
(የአብፀጋ ተመስገን /maddbn/)




Saturday, 23 March 2024 20:51

ናፍቆቴ ዳርቻው

ዥው ብዬ
ወደ ታች እምዘገዘጋለሁ
በሀይል
ቁልቁል እወርዳለሁ
እናም ትንፋሽ አጥሮኝ
መሬት ርቆኝ
አለቅሁ ተሳቅቄ
ኧረ ናፍቆኛል መውደቄ፡፡
****




Saturday, 23 March 2024 20:49

ዱር ሃገሬ

ልቤን ጫካ አደረግሁት
ልቤን ዱር አደረግሁት
ይኸው ዛሬ
ስጎበኘው ተዟዙሬ
ሰፍሮበታል የአገር አውሬ፡፡
(ዳዊት ጸጋዬ፤ 2016)

አንድ የጣሊያን አፈ-ታሪክ እንዲህ ይላል።
አንድ የታወቀ ክራክ የሚባል ሌባ ነበር ይባላል። ይህንን ሌባ ማንም ሊይዘው አልቻለም። ይህ ክራክ የተባለው ሌባ ደግሞ ክሩክ የሚባለውን ሌላ ሌባ ለማግኘት ከፍተኛ ምኞት ነበረው።
አንድ ቀን ክራክ ምሳውን ሊበላ አንድ ሆቴል ገብቶ፣ ከአንድ ሌላ ተመጋቢ ራቅ ብሎ ይቀመጣል። ሰዓት ለማየት ወደ እጁ  ሲመለከት ሰዓቱ ተሰርቆበታል።
“እኔ ሳላውቅ ሰዓቴን ከእጄ ላይ አውልቆ ሊወስድ የሚችል ክሩክ መሆን አለበት” አለ በሆዱ።
በዚህ ቁጭት ብድግ ይልና ግራና ቀኝ ዘወር ዘወር ብሎ ምግብ እየበላ ወዳለው ሰው ተጠግቶ በከባድ ቅልጥፍና የሰውዬውን ቦርሳ ይመነትፈዋል።
እንግዳው ተመጋቢ ሂሳብ ሊከፍል ኪሱ ሲገባ ቦርሳው የለም። ያለምንም ማመንታት ወደ ክራክ ዘወር ብሎ፤
“አንተ ክራክ መሆን አለብህ” አለ።
“ትክክል ነህ” መለሰለት።
“እንግዲያው አብረን እንስራ?” አለው።
“መልካም” አለ ክሩክ።
ጊዜ ሳይፈጅባቸው ተስማሙና አብረው ወደ ከተማ አመሩ። ከዚያም ወደ ንጉሡ ሀብት ማከማቻ ካዝና ሄዱ። ካዝናው በበርካታ ዘቦች ተከቧል። ያም ሆኖ ሌቦቹ ምድር ለምድር መግቢያ ጎርጉረው ገቡ። ያለውን ሀብት ሁሉ ሰርቀው ወጡ።
ንጉሡ የሚያደርጉት ግራ ገባቸው። ሌቦቹ እነማን እንደሆኑ ለማወቅ ችግሯቸው ሰነበቱና ቀጥታ ወደ እስር ቤት አመሩ። አንድ በሌብነት የታሰረ ሰው ጋር ሄዱና፤
“ማን እንደሰረቀኝ ከነገርከኝ በነፃ እንድትለቀቅ አደርጋለሁ” አሉት።
እስረኛውም፤ “ያለጥርጥር  ወይ ክራክ ወይም ክሩክ ወይም ሁለቱም መሆን አለባቸው። እንዴት ሊይዟቸው እንደሚችሉ እነግርዎታለሁ። የስጋ ዋጋ ከዛሬ ጀምሮ በኪሎ 100 ብር ገብቷል ይበሉና ያውጁ። ያንን ከፍሎ የሚገዛ ያ የእርስዎ ሌባ ነው።”
ንጉሡ የሥጋ ዋጋ 100 ብር አስገቡ። ሥጋ የሚገዛ ሰው ጠፋ። ሲረፋፍድ ግን አንድ ቄስ እንደገዛ ወሬው ተሰማ።
ይሄኔ እስረኛው፤ ”በቃ ወይ ክራክ ወይ ክሩክ በቄስ ተመስለው ሥጋ ገዙ ማለት ነው። አሁን እኔ እንዳልታወቅ ተሸፋፍኜ በየቤቱ እየዞርኩ እለምናለሁ። ሥጋ የሚሰጠኝ ሰው ካገኘሁ በሩ ላይ ቀይ ምልክት አደርጋለሁ። የእርስዎ ዘቦች እንግዲህ ተከትለው ሌቦቹን ማሰር ነው” አለ።
እስረኛው በዘዴ ተጠቀመ። እንዳለው በክራክ ቤት ላይ ቀይ ቀለም ምልክት አደረገ። ዳሩ ምን ያደርጋል፤ ሌባው ክራክ ምልክቱን አየውና በከተማው ባሉ ቤቶች በሮች ላይ ሁሉ ቀይ ምልክት አደረገባቸው። በመካያው የክራክና የክሩክ መኖሪያ ቤት የት እንደሆነ ሳይታወቅ ቀረ።
እስረኛው አሁንም ሌላ ዘዴ ዘየደ። “እነዚህ ሌቦች መቸገራቸው አይቀርም። ስለዚህ እንደገና የእርስዎን ሀብት ሊሰርቁ መምጣታቸው አይቀርም። ከደረጃው ግርጌ የሚፈላ ውሃ ያስቀምጡ። ሌቦቹ በጨለማ ወደ ምድር ቤት እንወርዳለን ሲሉ ውሃ ውስጥ ይገባሉ” አላቸው።
ንጉሡ እንደተባለው አደረጉ።
ሌቦቹ እውነትም ሲቸግራቸው ወደ ንጉሡ ካዝና መጡ። ክሩክ ቀድሞ ገባ። ጨለማ ስለነበረ በቀጥታ የፈላ ውሃ ካለበት በርሜል ውስጥ ጥልቅ አለ። ጓደኛው ሊያወጣው ሲሞክር አልተሳካለትም። ስለዚህ የክሩክን አንገት ቆርጦ እዛው ሬሳውን ጥሎት ሄደ።
ንጉሡ በነጋታው ሄደው ሌባው መያዙን አዩ። ግን ጭንቅላቱ ተቆርጦ ስለተወሰደ ማንነቱ የማይለይ ሆነ። አሁንም እስረኛው ሌላ ዘዴ ነገራቸው። “ሬሳውን በከተማ መሃል በፈረሶች ያስጎትቱት። ሬሳውን አይቶ የሚያለቅስ ሰው ከሰሙ የሌባው ቤት እዛ ነው ማለት ነው።”
እውነትም የክሩክ ሚስት ሬሳውን ስታይ ጮኸች። ሆኖም ይሄ አደገኛ መሆኑን የተገነዘበው ክራክ፤ ሰሀንና የቤት እቃ እየወረወረ  ሴትየዋን እየደበደበ ቆየ። ዘቦቹ ድምጽ ወደሰሙበት ቤት ገቡ። ያገኙት ግን ሚስቱ የቤት እቃ በመስበሯ ምክንያት የሚደበድብ ባል ብቻ ነው።
በመጨረሻ፤ ንጉሡ ሲጨንቃቸው፤ ሀብቴን የዘረፈውን ሌባ እምረዋለሁ። ግን አንድ ነገር ማድረግ ከቻለ ነው። ይኸውም የምተኛበትን አንሶላ ከሰረቀ ነው። ክራክ ፊት ለፊት መጥቶ ”እኔ እችላለሁ፤” አለ።
ያን ማታ ንጉሡ ሽጉጣቸውን ይዘው አልጋቸው ውስጥ ገቡ። ክራክ ከመቃብር ቆፋሪዎች ዘንድ ሬሳ ይዞ መጣ። የራሱን ልብስ አልብሶ ቤተ-መንግስቱ ጣራ ላይ አንጠለጠለው። እኩለ-ሌሊት ከጣራው ወደ ንጉሡ መኝታ ቤት መስኮት ሬሳውን ላከው። ንጉሡ ክራክ ነው ብለው ሬሳውን ደበደቡት። መሬት ወደቀ። ተነስተው ከፎቅ ወርደው የወደቀውን የክራክ ሬሳ ሊያዩ ሄዱ። ይሄኔ ክራክ በመስኮቱ ገብቶ የንጉሡን አንሶላ ጠቅልሎ ውልቅ አለ።
ንጉሡ ምህረት አደረጉለት። ልጃቸውንም ዳሩለት። ክራክም ሁለተኛ ላይሰርቅ ቃል ገባ!
***
ሌቦች በችሎታ የሚፎካከሩባት ሀገር ያልታደለች ናት። ሌባ ለመፈለግ ሌባ ማማከር እርግማን ነው። ሌባውን ካገኘህልኝ በነጻ እለቅሃለሁ ማለት ደግሞ የከፋ እርግማን ነው። በየበሩ ላይ ቀይ ምልክት ከሚያደርግ ሌባ ይሰውረን። ጭንቅላቱ ተቆርጦ ማንነቱ የማይለይ  ሌባ አይጣልብን፡፡ የምንተኛበትን አንሶላ ጭምር ለሚሰርቅ ሌባ እድል የሚሰጥ አዋጅ፤ መመሪያ፣ ፖሊሲ አያምጣብን። ሌቦቻችንን መያዝ ከባድ ነው። ታክቲክ እየለዋወጡ ሌብነት የሚያጧጡፉ ሌቦችን በቁጥጥር ስር ማዋል ትልቅ ተግባር ነው። ሌብነትና አያሌ መልኮቹ የጥቅል ስማቸው ሙስና ነው። ዛሬም እንደ ትላንት እግር እስኪነቃ ሲሄዱ ቢውሉ በዚህም ሆነ በዚያ ዘዴ በሀገራችን ይህ አባዜ ያልተጠናወተው መ/ቤትና ተቋም አይገኝም፤ ብንል ከሀቁ አንርቅም። በተናጽሮ ሲታይ ጥንት “ደሞዙን 250፣ የሚኖረው ቪላ ቤት፣ የሚነዳው ውድ ውድ መኪና!” በሚል ምጸታዊ መፈክር ሙስናን ለመዋጋት፤ ይሳካም አይሳካም መሞከሩ አይዘነጋም። ዛሬም መሰል መፈክር ማስገር የሚያስፈልግበት ደረጃ የደረስን ይመስላል። ጥንትም የነበረው ችግር ዛሬም እንዴት ሊኖር ቻለ? “በሥራው አጋጣሚ በእጁ የገባውን የመንግስትና የህዝብ ገንዘብ የዘረፈው” የሚለው አባባል ትላንት ነበር፤ ዛሬም አለ። ነገሩ እንግሊዞች “Who judges the judges?” “ዳኞቹን ማን ይዳኛቸው?” የሚለው ቁልፍ ጥያቄ ዙሪያ ያጠነጠነ ነው። ተቆጣጣሪውን ማን ይቆጣጠረው? ገምጋሚውን ማን ይገምግመው? እንደማለት ነው። ሌላው መነሳት ያለበት አባባል፤ They shout at most against the vices they themselves are guilty of የሚለው ነው፡፡ በአማርኛ ሲታሰብ፤  “ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል” የሚል የሼክስፒር አባባል መሆኑ ነው።
ዛሬ አዲስ የሚሾሙ ባለስልጣኖች ስለማናቸውም ጉዳዮች ሲጠየቁ፤ “ከጥንት የወረስነው አሰራር”፣ “ያለፈው ስርዓት የጣለብን እዳ”፣ “ባለፈው ጊዜ የነበረው አሰራር ዝርክርክነት” ወዘተ የሚል ነው፤ የመልሳቸው መነሻ ሃረግ። ከቶውንም እንደ ሰንሰለት ተሳስሮ ባለው የቢሮክራሲ አውታር፣ ሰው የሰውን ኪስ እንደራሱ በሚያውቅበት የእከክልኝ ልከክልህ አገር፣ ከጎኑ አንድ ባለስልጣን ሲነሳ ወዲያውኑ “ያለፈው አሰራር፣ ያለፈው ስርዓት” የሚባለው እንዴት ነው? ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል የሚባለውን የቁርጥ ቀን ተረት አንርሳ እንጅ!
ሹም ሽረት በተደረገ ቁጥር አሮጌውን መኮነንና አዲሱን ጻድቅ ማድረግ የተለመደው የአገራችን ፈሊጥ ነው። ከዚህ መጠንቀቅ አለብን። ከዜሮ የሚጀምር ልማት የለም። መልካም ፍሬ ያላፈሩ፣ ውጤት ያላስመዘገቡ፣ ድርብ ስራ የሚሰሩና የተዘጉ፣ ብቃትና ስኬት የሌላቸው ወዘተ… የሚሉ ግምገማዎች ስንል ፈጠው የወጡትን ጉድለቶች አብሮ መመርመርና በአግባቡ መገምገም  ይኖርባቸዋል። ማመን ብቻ ሳይሆን መተማመን ያስፈልጋል። አሁንም ሙያ፤ ስነ-ምግባርና ልምድ ወሳኝ መሆን አለባቸው።
ዝውውሮች በተፈተሸ አቅም የተጤኑ፣ ከአንዱ ኃላፊነት ገለል ብሎ ይሂድ ብቻ የማይባልባቸው መሆን አለባቸው። የሁሉ መ/ቤቶችና ተቋማት ጤና የአገሪቱ አጠቃላይ ጤና ነው። የሰራ-አከላቷ በትክክል መንቀሳቀስ ነው ለደህንነቷ ዋስትና የሚሆነው። አለበለዚያ ቴዎድሮስ እንዳለው፤
“መች ትተርፊያለሽ ኢትዮጵያ፤ ህዋስሽ አብሮኝ ካልሰራ
አንገትሽ ብቻ መቅደላ፣ አፋፍ ወጥታ ብትበራ…”
(የቴዎድሮስ ስንብት ከመቅደላ)
ማለት እንዳይሆን የመጨረሻ ቃላችን፤ መጠንቀቅ ተገቢ ነው። “ላም ባንድ ጎኗ አትሰባ፤ ባንድ ጎኗ ጉፋያ አትሆን” ይሏል ይሄው ነው።

  የማይመልሱ ሰዎችን ፎቶና ማንነት በሚዲያ ይፋ አደርጋለሁ ብሏል
         - የራስ ያልሆነ ገንዘብ ህጋዊ ማድረግ እስከ 25 ዓመት እስራት ያስቀጣል
         - የአካውንቶች መታገድ ገንዘቡን ለመመለስ እንቅፋት ፈጥሯል ተብሏል


          የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አጋጠመኝ ባለው  የሲስተም ችግር ምክንያት ያለአግባብ  ገንዘብ ከባንኩ  የወሰዱ ወይም ወደ አካውንቶች  ያስተላለፉ ግለሰቦች የወሠዱትን ገንዘብ ለባንኩ እንዲመልሱ የሠጠው የጊዜ ገደብ ዛሬ ያበቃል።  በተሰጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ገንዘቡን  ካልመለሱ ፎቷቸውንና ማንነታቸውን በመገናኛ ብዙኃን ይፋ እንደሚያደርግም ገልጿል ።
ባንኩ መጋቢት 6 ቀን 2016 ዓ.ም በተፈጠረው የሲስተም ችግር ምክንያት ከባንኩ  ገንዘብ የወሰዱ ወይም ወደተለያዩ ሂሳቦች ያስተላለፉ ግለሰቦች ገንዘቡን ተመላሽ እንዲያደርጉ ተደጋጋሚ ጥሪ ያቀረበ መሆኑን አመልክቶ፤  የመጨረሻ  ያለውን ጥሪ ከትላንት በስቲያ  ሐሙስ መጋቢት 12 ቀን 2016 ዓ.ም.  አስተላልፏል። በዚህ ጥሪ መሠረትም ባንኩ ገንዘቡን ለማስመለስ የሠጠው የጊዜ ገደብ ዛሬ ይጠናቀቃል ።
ገንዘቡን ተመላሽ በማያደርጉ ሰዎች ላይ በሕጋዊ ሂደቱ ተገቢ ውሳኔ እስኪገኝ ድረስ ፎቶግራፋቸውንና ዝርዝር ማንነታቸውን የሚገልጹ መረጃዎች፤ ባንኩ በመረጠው የብዙኃን መገናኛ መንገድ ለሕዝብ ይፋ እንደሚያደርግም አስታውቋል። ከሕግ አካላት ጋር በመተባበር የግለሰቦችን ስም ዝርዝር በየቅርንጫፎችና እንደሁኔታው ግለሰቦቹ ሊታወቁ በሚችሉበት አካባቢ ይፋ በማድረግ ቀጣይ ሕጋዊ እርምጃዎችን እንደሚከተሉም  ገልጿል። በተጨማሪም “ከፍትህ አካላትና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በመተባበር ተገቢውን የወንጀል፣ የፍትሐ ብሔር እንዲሁም አስተዳደራዊ እርምጃዎች እንዲወሰዱ እንደሚያደርግም አሳስቧል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ ከንግድ ባንክ የራሳቸው ያልሆነ ገንዘብ ያንቀሳቀሱ ግለሰቦች የማይመልሱ ከሆነ፣ በህግ እንደሚጠየቁ የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት ከትላንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ በተፈጠረው ችግር ዙሪያ ከባንኩ ጋር በጋራ እየሰራ እንደሚገኝ የገለፀው የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎቱ፤ የራስ ያልሆነን ገንዘብ ህጋዊ ማድረግ እንደ ወንጀሉ ክብደት እስከ 25 ዓመት በሚደርስ እስራት እደሚያስቀጣ አሳስቧል፡፡
ባንኩ አርብ መጋቢት 6 ቀን 2016 ዓ.ም. ምሽት ላይ የሲስተም ችግር በገጠመው ወቅት የተወሰደበት ገንዘብ  መጠን ከባንኩ በይፋ ባይገለጽም ፣ በዕለቱ የተወሰደው የገንዘብ መጠን 2.4 ቢሊዮን ብር (40 ሚሊዮን ዶላር) መሆኑን አሶሺየትድ ፕሬስ  ዘግቧል።

  -  ባለፈው ዓመት 7 ሺህ የሚጠጉ የሳይበር ጥቃት ሙከራዎች ተደርገዋል
ኢትዮጵያ ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭነታቸው ከፍ ካሉ ሀገራት  መካከል አንዷ እንደሆነችና የሳይበር ጥቃቶቹ  የፋይናንስና የፀጥታ ተቋማትን፣ ባንኮችን፣ እንደ ቴሌኮምና መብራት ሃይል ያሉ  ተቋማትን፣ መሰረተ ልማቶችንና  ቁልፍ የመንግስት ተቋማትን  ኢላማ ያደረጉ እንደሆኑ  ታዋቂው የሳይበር ደህንነት ተቋም ሲዮን ገልጿል።
ተቋሙ ከትናንት በስቲያ  ይፋ ያደረገው መረጃ እንደሚያመለክተው፤  ዓለማችን በኢንተርኔት መተሳሰሯና በዲጂታል ቴክኖሎጂ ጥገኝነቷ በፍጥነት እያደገ መሄዱን ተከትሎ የሳይበር ጥቃትም ፈተና ሆኖባታል። ባለፈው የፈረንጆቹ አመት ከ340 ሚሊየን በላይ ሰዎችን ተጎጂ ያደረጉ የሳይበር ጥቃቶች ተፈጽመዋል ።
ግለሰቦችን፣ ተቋማትን እና የመንግስት መስሪያ ቤቶችን ኢላማ ባደረጉ የሳይበር ጥቃቶች፣ በ2023 ብቻ ከ8 ትሪሊየን ዶላር በላይ የሚገመት ጉዳት ደርሷል።
የሳይበር ጥቃት የትኛውንም ሀገር ወይም ተቋም ለይቶ እንደማይተው የሚገልጸው ታዋቂው የሳይበር ደህንነት ተቋም ሲዮን፥ ጠንካራ የሳይበር ደህንነት ህግና ቴክኖሎጂ ያላቸው ሀገራት አደጋውን መቀነስ መቻላቸውን ገልጿል።
በአንጻሩ ደካማ የሳይበር ደህንነት ህግ ያላቸው አልያም ከነጭራሹ የሌላቸውና ጥቃቶችን አስቀድሞ ለመመከት የሚጠቀሟቸው ቴክኖሎጂዎች ከፈጣኑ የዲጂታል አለም ጋር አብሮ በማይሄድባቸው ሀገራት አደጋው እንደሚከፋም ጠቁሟል።
በዚህም መሰረት ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭነታቸው ከፍ ያሉ ናቸው በሚል  በተቋሙ  ከተጠቀሱ ሀገራት መካከል  ኢትዮጵያ የምትገኝ ሲሆን፤ አገሪቱ  ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭ በመሆን ከአለማችን  በ8ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች  ብሏል።
ባለፉት ጥቂት አመታት በኢትዮጵያ የሳይበር ምህዳሩን የሚጠቀሙ ሰዎች ቁጥር መጨመርን ተከትሎ፣ በግለሰቦችና ተቋማት ላይ የሚሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶችን ጨምሮ በሀገሪቱ  ቁልፍ የመንግስት መሰረተ-ልማቶች ላይ እየደረሱ ያሉ ጥቃቶች የብሄራዊ ደህንነት ስጋት መሆናቸውን የኢንሳ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ  የሚታወስ ሲሆን፤  ባሳለፍነው ዓመት 2015 ዓ.ም  ከ 6 ሺ 959 በላይ  የሳይበር ጥቶች መፈጸማቸውንም ጠቁመዋል።
ከሳይበር ጥቃቶቹ ውስጥም 2 ሺ 559 ያህሉ በድረ ገጽ ላይ የተፈጸሙ ሲሆኑ፤ 1 ሺህ 295 ያህሉ ደግሞ የማልዌርና የፒሺግ መሆናቸው ተጠቁሟል። እንዲሁም 603 በመሰረተ ልማት ቅኝት፣ 1 ሺህ 493 መሰረት ልማት የማቋረጥ (አብዛኛው የፋይናንስ ተቋማትን ኢላማ ያደረገ)፣ 695 ሰርጎ የመግባት ሙከራ እና 145 ሌሎች የሳይበር ጥቃት ሙከራዎች ተደርገዋል።
የሳይበር ጥቃቶቹ የፋይናንስና የፀጥታ ተቋማትን፣ እንደ ቴሌኮምና መብራት ያሉ ቁልፍ ተቋማት መሰረተ ልማቶችንና  ቁልፍ የመንግስት ተቋማትን  ኢላማ ያደረጉ ነበሩ ተብሏል። በ2015 የተሰነዘሩ የሳይበር ጥቃት ሙከራዎችን መከላከል በመቻሉም፣ በሀገር ላይ ሊደርስ የነበረ 23.2 ቢሊየን ብር ኪሳራ ማዳን መቻሉን የኢንሳ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ ማስታወቃቸው አይዘነጋም ።

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ባጋጠመው የሲስተም ችግር ወቅት ገንዘብ የወሰዱ ወይም ያስተላለፉ ግለሰቦች እስከ መጪው ቅዳሜ መጋቢት 14 ቀን 2016 ዓ.ም. ድረስ ካልመለሱ ፎቷቸውንና ማንነታቸውን በመገናኛ ብዙኃን ይፋ እንደሚያደርግ አስታወቀ።

ባንኩ ገንዘቡን ተመላሽ በማያደርጉ ሰዎች ላይ በሕጋዊ ሂደቱ ተገቢ ውሳኔ እስኪገኝ ድረስ ፎቶግራፋቸውንና ዝርዝር ማንነታቸውን የሚገልጹ መረጃዎች “ባንኩ በመረጠው የብዙኃን መገናኛ መንገድ ለሕዝብ ይፋ አደርጋለሁ” ሲል አሳስቧል።

ገንዘብ የወሰዱ ወይም ወደተለያዩ ሂሳቦች ያስተላለፉ ግለሰቦች በአቅራቢያቸው ወደሚገኙ የባንኩ ቅርንጫፎች በመቅረብ እንዲመልሱም የመጨረሻ ጥሪውንው ዛሬ ሐሙስ መጋቢት 12 ቀን 2016 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስተላልፏል።

ነገር ግን ይህ ሳይሆን ገንዘቡን በተቀመጠው ጊዜ ገደብ ተመላሽ የማያደርጉ ግለሰቦች ላይ የተለያዩ እርምጃዎችን እወስዳለሁ ሲል አስጠንቅቋል።

የሚወስዳቸው እርምጃዎች ደረጃ በደረጃና በተከታታይ ጠንከር ያሉ እንደሚሆኑ የገለጸው ባንኩ፤ ለሕግ አካላት ማሳወቅ አንዱ እንደሚሆንም አስታውቋል።

“ከሕግ አካላት ጋር በመተባበር የግለሰቦችን ስም ዝርዝር በየቅርንጫፎችና እንደሁኔታው ግለሰቦቹ ሊታወቁ በሚችሉበት አካባቢ ይፋ በማድረግ ቀጣይ ሕጋዊ እርምጃዎችን” እንደሚከተሉ አስታውቋል።

በተጨማሪም “ከፍትህ አካላትና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በመተባበር ተገቢውን የወንጀል፣ የፍትሐ ብሔር እንዲሁም አስተዳደራዊ እርምጃዎች እንዲወሰዱ እንደሚያደርግም” አሳስቧል።

የባንኩ ፕሬዝዳንት አቤ ሳኖ ረቡዕ ዕለት ለቢቢሲ ኒውስ ዴይ፣ የራሳቸው ያልሆነን ገንዘብ የወሰዱ ደንበኞች እስከ ሳምንቱ መጨረሻ ድረስ ካልመለሱ ማንነታቸውን ለፖሊስ እንደሚያሳውቁ ተናግረው ነበር።

“ማዕከሉ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገባ 1ሺ ህፃናትን የመቀበል አቅም ይኖረዋል”
አርቲስት መቅደስ ፀጋዬ ወላጆቻቸውን በሞት ላጡ ህጻናት፣ "መቅደስ የልጆች አድማስ" የተሰኘ ማዕከል በ1 ቢሊዮን ብር ወጪ ልትገነባ መሆኑ ተገለጸ፡፡
አርቲስቷ የምታቋቁመውን የበጎ አድራጎት ድርጅት አስመልክቶ በዛሬው ዕለት በካፒታል ሆቴል ለጋዜጠኞች መግለጫ ተሰጥቷል፡፡
ድርጅቱን ለማቋቋም ሃሳቡ የተፀነሰው ከ6 ዓመታት በፊት እንደነበር አርቲስት መቅደስ ጸጋዬ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ተናግራለች፡፡
የድርጅቱ የቦርድ አባል ደራሲ ውድነህ ክፍሌ እንደገለጸው፤ ማዕከሉ በዋናነት ልዩ ትኩረትና ጥበቃ ለሚያስፈልጋቸው ወላጅ አልባ ህፃናት አስፈላጊውንና ሁሉን አቀፍ እንከብካቤ በመስጠት በቀጣይ የሕይወት ጉዟቸው ስኬታማ ይሆኑ ዘንድ ትኩረት አድርጎ የሚሰራ ነው፡፡
በማዕከሉ ውስጥ ለሚቆዩ ልጆች ደረጃውን የጠበቀ የመኖሪያ፣ የትምህርትና የጤና አገልግሎቶችን ከመስጠትና፣ የአካል ብቃት ማጎልመሻ ከማደራጀት ባሻገር፣ የማኅበራዊ ሕይወትና የአእምሮ ማበልፀጊያ ስልጠናዎችን በመስጠት ሙሉ ጤንነታቸው የተረጋገጠ፣ በአካላዊ እድገታቸው የበቁ፣ በሥነ ልቦና፣ በግልና በማሕበራዊ ሕይወታቸው ጠንካራ የሆኑ እንዲሁም በአእምሮአዊ የጠራ ችሎታቸው የተደነቁና በዕውቀት የዳበሩ ሆነው የመጪው ጊዜ ብሩህና ስኬታማ ዜጎችን እንዲሆኑ በትኩረት ይሰራል ተብሏል።
“መቅደስ የልጆች አድማስ” በማእከሉ የሚያድጉ ልጆች በሁሉም ረገድ ኢትዮጵያዊ እሴቶችን የተላበሱና አዎንታዊ ተፅዕኖ ፈጣሪዎች እንዲሆኑ ማድረግ ዋና ትኩረቱ እንደሆነ ተገልጿል።
በሃያ አንድ ሺ ካሬ ሜትር ላይ እንደሚያርፍ የተነገረለት ማዕከሉ፤ ሙሉ ለሙሉ ለመገንባትና በሙሉ አቅሙ ስራውን እንዲጀምር ለማድረግ እስከ አንድ ቢሊዮን ብር ይፈጃል ተብሏል፡፡
የበጎ አድራጎት ድርጅቱ የመጀመሪያ ማዕከሉን የሚገነባው በአዲስ አበባ ሲሆን፤ ቀስ በቀስም ወደ ከልሎች ቅርንጫፎቹን የሚያሰፋ እንደሚሆን ተነግሯል፡፡ ማዕከሉ በመጀመሪያው ዙር 200 ህፃናትን ከመላው ኢትዮጵያ የሚቀበል ሲሆን፤ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገባ ደግሞ 1000 ህፃናትን የመቀበል አቅም እንደሚኖረው ተጠቁሟል፡፡
ማእከሉን እውን ለማድረግ መጋቢት 26 ቀን 2016 ዓ.ም በስካይላይት ሆቴል በይፋ ገቢ በማሰባሰብ ወደ ስራ የሚገባበት ቀን ሲሆን፤ በዚህ መርሃ ግብር ላይ ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች፣ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች፣ ባለሃብቶች፣ የኤምባሲ ተወካዮች፣ ታዋቂ ግለሰቦችና ሃሳቡን የሚደግፉና ቀና ልብ ያላቸው ሰዎች ይታደሙበታል ተብሏል።
Page 1 of 696