Administrator

Administrator

በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት እየታየ በሚገኘው 28 ተከሳሾች ላይ ለቀረበ የአቃቤ ህግ የቪዲዮ ማስረጃ አስተርጓሚ እንዲመድብ የታዘዘው የኢትዮጵያ ሬድዮና ቴሌቪዥን ድርጅት፤ የፍ/ቤቱን ትዕዛዝ ተግባራዊ ባለማድረጉ ዋና ዳይሬክተሩ ፍ/ቤት ታስረው እንዲቀርቡ ታዘዘ፡፡
በእነ አማን አሠፋ መዝገብ በሚገኙ የሽብር ተጠርጣሪዎች ላይ አቃቤ ህግ የሰው ምስክሮችንና በሺዎች የሚቆጠሩ የሰነድ ማስረጃዎችን ለፍ/ቤቱ አቅርቦ ያጠናቀቀ ሲሆን በአረብኛና በኦሮሚኛ ቋንቋዎች ለቀረቡት የቪድዮ ማስረጃዎች ኢሬቴድ አስተርጓሚ እንዲመድብ ከፍ/ቤቱ የተላለፈውን ትዕዛዝ ተግባራዊ አላደረገም ተብሏል፡፡ በዚህም ዋና ዳይሬክተሩ አቶ ብርሃኑ ኪዳነማርያም ታስረው ፍ/ቤት እንዲቀርቡ ታዟል፡፡
ቀደም ሲል እነዚህን የሽብር ተጠርጣሪዎች አስመልክቶ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን “ጅሃዳዊ ሃረካት” የሚል ዶክመንተሪ ፊልም ተዘጋጅቶ መሰራጨቱ የሚታወስ ሲሆን አቃቤ ህግም በክስ ማመልከቻው፣ ተጠርጣሪዎች የአልቃይዳ ህዋስ ሆነው በአለማቀፍ የሽብር መዋቅር ውስጥ ተሳታፊ እንደነበሩ ማመልከቱ ይታወሳል፡፡

  • መሥፈርቱን የማያሟሉ ከሐምሌ 1 ጀምሮ እርምጃ ይወሰድባቸዋል  
  • በሥራ ላይ ካሉት ክሊኒኮች መስፈርቱን የሚያሟላ  አይኖርም ተብሏል
  • የግል ክሊኒኮች ማህበር በቂ የዝግጅት ጊዜ ሊሰጠን ይገባል አለ  


የመንግሥትና የግል የጤና ተቋማት አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችላቸውን መስፈርቶችና ደረጃዎች የሚወስን አዲስ መመሪያ ወጣ፡፡ የጤና ተቋማቱ በአዲሱ መስፈርት መሰረት ራሳቸውን እንዲያደራጁ እስከ ሰኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም ጊዜ የተሰጣቸው ሲሆን ከሐምሌ 1 ጀምሮ መሥፈርቱን ባላሟሉት ላይ እርምጃ ይወሰዳል ተብሏል፡፡
የኢትዮጵያ የምግብ የመድኃኒትና የህክምና መሳሪያዎች ቁጥጥር ባለስልጣን ያወጣውና በአገሪቱ የሚገኙ ሁሉንም የመንግስትና የግል የጤና ተቋማት ይመለከታል የተባለው አዲስ መመሪያ፤ ተቋማቱ ማሟላት የሚገባቸውን ዝርዝር ጉዳዮች ይፋ አድርጓል፡፡ በዚሁ መመሪያ ላይ እንደተገለፀው፤ ሆስፒታሎች የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል፣ አጠቃላይ ሆስፒታልና ስፔሻላይዝይድ ሆስፒታል ተብለው በ3 መደቦች የሚከፈሉ ሲሆን የጤና ማዕከላት፣ የጤና ጣቢያዎችና ልዩ ማዕከላትም በዘርፉ እንደሚጠቃለሉ ተጠቅሷል፡፡
መመሪያው ሆስፒታሎች እንደየደረጃቸው የተለያዩ አገልግሎቶችን መስጠት እንደሚገባቸው በዝርዘር የገለፀ ሲሆን የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታሎች ቢያንስ 35 አልጋዎች፣ አጠቃላይ ሆስፒታሎች 50 አልጋዎች እንዲሁም ስፔሻላይዝድ ሆስፒታሎች ከ300 የማያንሱ አልጋዎች እንዲኖራቸው ያስገድዳል። ሁሉም የጤና ተቋማት የማዋለድ አገልግሎት መስጠት እንደሚገባቸው የገለፀው መመሪያው፤ በክሊኒኮች ውስጥ አልጋ በማዘጋጀት ህሙማንን በመደበኛነት አስተኝቶ ማከም እንደማይቻልና መካከለኛ ክሊኒኮች ለድንገተኛ ህመምና ለማዋለድ አገልግሎት የሚሆኑ 10 አልጋዎች ብቻ ሊኖራቸው እንደሚገባ ይደነግጋል፡፡ ክሊኒኮችን በስም መሰየም እንደማይፈቀድም በዚሁ መመሪያ ላይ ተገልጿል፡፡
የኢትዮጵያ የምግብ የመድኃኒትና የህክምና መሣሪያዎች ቁጥጥር ባለስልጣን፣ የቁጥጥር አስተባባሪ ሲስተር የሺአለም በቀለ መመሪያውን ማውጣት ያስፈለገበትን ምክንያት ሲናገሩ፤ በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ በጤናው ዘርፍ ተሰማርተው ለህዝብ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙ የጤና ተቋማትን ለመቆጣጠርና ተቋማቱ በምን ደረጃ ላይ እንዳሉ ለማወቅ ባለመቻሉ፣ ይህንን ችግር በማስወገድ ተቋማቱ የሚሰጧቸው አገልግሎቶች ጥራታቸውን የጠበቁ እንዲሆኑ ለማድረግና ህብረተሰቡን ለአደጋ የሚያጋልጡ አሰራሮችን ለማስወገድ ነው ብለዋል። በጤናው ዘርፍ የሚታዩ ህገወጥ ተግባራትን በመቆጣጠር ለህብረተሰቡ ብቃት ያለው አገልግሎት እንዲሰጥ ለማድረግ እንደሆነም አክለው ገልፀዋል፡፡
ባለስልጣን መ/ቤቱ የጤና ተቋማቱ የሚተዳደሩበትን መመሪያና መስፈርት ህግ አድርጎ ከማፅደቁ በፊት ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሰፋ ያለ ውይይት ማድረጉን የጠቆሙት ሲስተር የሺዓለም፤ በመመሪያው ላይ የተካተቱና ለአሰራር እንቅፋት ይሆናሉ የሚባሉ ጉዳዮች ካሉ ማሻሻያዎችን ለማድረግ እንደሚቻል በተደጋጋሚ መገለፁን አስታውሰዋል፡፡ ይሁን እንጂ መመሪያው ሊያሰራን አይችልም የሚል ሃሳብ ከየትኛውም ወገን ባለመነሳቱ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ህግ ሆኖ እንዲፀድቅ መደረጉንም ገልፀዋል፡፡ በዘርፉ የተሰማሩ አካላት ድርጅቶቻቸውን በመመሪያው መሰረት እንዲያደራጁ እስከ ሰኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም ድረስ ጊዜ እንደተሰጣቸውና የጊዜ ገደቡ ሲጠናቀቅ ባለስልጣን መ/ቤቱ የራሱን እርምጃ እንደሚወስድ ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ የግል ክሊኒኮች ባለቤቶችና አሰሪዎች ማህበር ምክትል ሊቀመንበር አቶ አበበ ያለው በበኩላቸው፤ መመሪያው የአገሪቱን ወቅታዊ ሁኔታ ያላገናዘበና በዘርፉ የተሰማሩ በርካታ ባለሙያዎችን ከስራ ውጪ የሚያደርግ በመሆኑ ሊታሰብበት ይገባል ብለዋል፡፡ ህብረተሰቡ ጥራት ያለው የህክምና አገልገሎት እንዲያገኝና ዘርፉም ወደተሻለ ደረጃ ከፍ እንዲል ታስቦ የወጣውን መመሪያ እንደማይቃወሙ ምክትል ሊቀመንበሩ ገልፀው፤ሆኖም በአገሪቱ የተሰማሩ የጤና ተቋማትን ወቅታዊ ሁኔታ ያላገናዘበና ምንም የመፍትሔ ሃሳብ ያላቀረበ በመሆኑ ብዙዎችን ከስራ የሚያፈናቅል ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ከ500 በላይ አባላት ያሉት ማህበሩ፤ አዲሱን ህግና መመሪያ ተከትሎ በመስፈርቱ መሰረት በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ አገልግሎት መስጠት ይቻላል ብለው እንደማያስቡ ገልፀው መንግስት በቂ የዝግጅት ጊዜና የጤና ተቋም መገንቢያ ቦታ ሊሰጠንና የብድር አገልግሎት ሊያመቻችልን ይገባልም ብለዋል፡፡ “እንደዚያ ካልሆነ የምንሰራው ከግለሰቦች በተከራየናቸው ክሊኒኮች በመሆኑ መስፈርቱ የሚጠይቀውን ለማሟላት ስንል ማፍረስም ሆነ መቀየር አንችልም” ሲሉ ችግራቸውን ጠቁመዋል፡፡ መስፈርቱን ካላሟላችሁ መስራት አትችሉም ከተባለ ግን በርካታ ባለሙያዎች ከስራ እንደሚፈናቀሉና ህብረተሰቡም በቂ አገልግሎት ለማግኘት እንደሚቸገር መታወቅ ይገባዋል ብለዋል።
ሲስተር የሺዓለም በቀለ በበኩላቸው፤“በአገሪቱ ውስጥ በህጋዊ መንገድ ተመዝግበው አገልግሎት ከሚሰጡ የጤና ተቋማት መካከል አዲሱን መስፈርት በበቂ ሁኔታ የሚያሟሉ ተቋማት ስለመኖራቸው አፍን ሞልቶ መናገር አይቻልም” ይላሉ፡፡

እስካሁን ለ3ሺ ተማሪዎች ነፃ የትምህርት ዕድል ሰጥቷል

ሴንትራል ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በቅርቡ ከሳኡዲ ለተመለሱ 180 ያህል ኢትዮጵያዊያን ነፃ የትምህርት እድል መስጠቱን አስታወቀ፡፡ የዩኒቨርሲቲው መስራችና ፕሬዚዳንት ዶ/ር አብነት ግርማይ፣ በዩኒቨርሲቲው ሾላ ካምፓስ ከትላንት በስቲያ የትምህርት እድሉ የተሰጣቸው፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተወካይ፣ የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊና ጋዜጠኞች በተገኙበት በሰጡት መግለጫ፤ ዩኒቨርስቲያቸው ከዚህ ቀደም ከተለያዩ የመንግስትና የግል ተቋማት ለተመለመሉና ከፍለው መማር ለማይችሉ 3ሺህ ተማሪዎች ነፃ የትምህርት እድል መስጠቱን አስታውሰው፤ አሁን ደግሞ የትምህርት ሚኒስቴርን መስፈርት ላሟሉ የሳኡዲ ተመላሾች ተመሳሳይ እድል መስጠቱን ተናግረዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በአዲስ አበባ፣ በአዳማ፣ በሀዋሳና በባህርዳር በአጠቃላይ ስድስት ካምፓሶች ያሉት ሲሆን በእያንዳንዱ ካምፓስ 30 ተማሪዎች ገብተው እንዲማሩ መወሰኑ ተገልጿል፡፡
ተማሪዎቹን አስተምሮ ለማስመረቅ ከአራት ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚፈጅ የጠቆሙት ዶ/ር አብነት፤ ከሌቭል አንድ እስከ ዲግሪ ድረስ እንዲማሩ እድሉ መመቻቸቱን ገልፀዋል፡፡ የትምህርት አሰጣጡንና አጠቃላይ የዩኒቨርስቲውን ድባብ  በተመለከተ ተማሪዎቹ ገለፃ ከተደረገላቸው በኋላ የሚፈልጉትን የትምህርት አይነት፣ የት መማር እንደሚሹና የሚማሩበትን ሰዓት መምረጥ እንደሚችሉ ዶ/ር አብነት ተናግረዋል። “ትምህርታችሁን ጀምራችሁ እስክታጠናቅቁ ድረስ ራሳችሁን፣ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጁንና  የከተማ አስተዳደሩን የሚያስከብር ስርዓት እንድትከተሉ እጠይቃለሁ” ሲሉም ለተማሪዎቹ ምክርና ማሳሰቢያ ሰጥተዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ተወካይ በበኩላቸው፤ቢሯቸው ተማሪዎቹንና የትምህርት አቀባበል ሁኔታቸውን እንደሚከታተል ገልፀው፣ ለሁሉም መልካም እድል ተመኝተውላቸዋል፡፡ እድሉ የተሰጣቸው ተማሪዎችም ነፃ የትምህርት እድሉን በማግኘታቸው ከተማ አስተዳደሩንና ዩኒቨርሲቲውን አመስግነው ትምህርታቸውን በአግባቡ ለመከታተል ቃል ገብተዋል፡፡   


በዶክተር ብርሃኑ ደመላሽ የተፃፈውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተው የአባቴ ምክሮች ሀሳቦቼ መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል።
95 ገፆች ያሉት መጽሐፍ፤ የደራሲው የመጀመሪያ ስራ ሲሆን በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ እንደሚያጠነጥንም ተገልጧል፡፡ መፅሐፉ መታሰቢያነቱ ለደራሲው ወላጅ አባት እና በፖለቲካ ምክንያት ለተሰዉ ዜጎች ሆኗል፡፡
መፅሐፉ በ30 ብር ለሽያጭ ቀርቧል፡፡

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በአገራችን በተለያዩ ሆቴሎችና የመዝናኛ ስፍራዎች መከበር የጀመረው የፍቅረኛሞች ቀን (Valentine’s Day)፤ በዛሬው ዕለት በከተማዋ የተለያዩ ሥፍራዎች ይከበራል፡፡
በዓሉ ከሚከበርባቸው ሥፍራዎች መካከል ኢስተምቡል ሬስቶራንት፣ ዲ ኤች ገዳ ታወር፣ ሐርመኒ ሆቴልና ቬልቪው ሆቴሎች የሚገኙበት ሲሆን በዓሉ በአበባና የተለያዩ ስጦታዎች፣ በሙዚቃ ድግስ፣ በጣፋጭ ምግቦች ዝግጅትና በትዊስት እንደሚደምቅ አዘጋጆች አስታውቀዋል።
የኔታ ኢንተርቴይመንትና ዱም ሚዲያና ፕሮሞሽን በትብብር ባዘጋጁት “የፍቅረኛሞች ቀን” በተለያዩ የኪነጥበብ ዘርፎች የላቀ አስተዋጽዖ ያበረከቱ ባለሙያዎች እንደሚሸለሙ ታውቋል፡፡   

Monday, 17 February 2014 09:10

ስለት

…ሰናይት ይሏታል፡፡ እኔ ሰኒ እላታለሁ፡፡ ከተዋወቅን ያለፈው ሰኔ ሚካኤል 3ኛ አመታችንን ደፈንን፡፡ ዝም ብሎ መተዋወቅ እንዳይመስላችሁ፡፡ ከመላመዳችን የተነሳ ፊቷን አይቼ ምን እንደምታስብ መገመት ሳይሆን ማወቅ ጀምሬያለሁ፡፡
እወዳታለሁ፡፡
እሷም “እወድሃለሁ” ትለኛለች፡፡
3ኛ አመታችንን ባከበርን ማግስት እድል እጇን ዘረጋችላት፡፡ ስትዘረጋላት “ልጨብጣት ወይ?” ብላ አማከረችኝ፡፡ “ምን ይጠየቃል ጨብጫት እንጂ” አልኳት፡፡ “እንዴት እንዲህ ትለኛለህ? ያንተ እጅ እያለ ባትወደኝ ነው እንጂ…” ብላ አኮረፈችኝ፡፡
ቶሎ ታኮርፋለች፡፡ ጥቃቅን ነገሮች ሁሉ ያስኮርፏታል፡፡ ብስክስክ ናት፡፡ እኔም አመሏን ለምጀዋለሁ፡፡ እሷም አልፎ አልፎ ቱግ የምለውን ነገር ታውቅልኛለች፡፡ መቻቻል ማለት ይሄ አይደል…ቢሆንም ይሄ አመሏ አንዳንዴ ትዕግስቴን ይፈታተነኛል፡፡
ከሰኒ ጋር የት ተገናኘን?
ቡና ቤት! (ለማንም ግን አይነገርም፤ ምስጢር ነው፤ በተለይ በተለይ ቤተሰብ እንዳይሰማ!)
ስንላመድ ከቡና ቤት አውጥቼ መጀመሪያ ወደ ልቧ፣ ኋላም ወደ ቤቴ አስገባኋት፡፡ ስትረጋጋ ቤተሰቤን ልጠይቅ አለችኝ ፈቀድኩላት፡፡ ያኔ እግረ መንገዷን ከእድል ጋር ተገናኘች፡፡
ታድያስ የእድሏ በር የተከፈተው በኔ ምክንያት አይደለምን? በሩን ባልከፍተው ቁልፉን ያቀበልሁ እኔ አይደለሁምን?
ውጭ ሀገር መሰደድ እንደ ሎተሪ በሚታይባት ሀገር ውስጥ ከዚህ የበለጠ ምን ጥሩ እድል አለ ጃል? አለ እንዴ? የለም እኮ!!
መሄድ የለብሽም ብላት በጄ እንደማትል ልቦናዬ እያወቀው፣ አፌን ለምን አበላሻለሁ ብዬ “ይቅናሽ” ብላት በአትወደኝም ተተረጐመብኝና በለመድኩት ኩርፊያ ገረፈችኝ፡፡
ውጭ ሀገር ለመሄድ 1…2 …ማለት ተጀመረ፡፡ ግን “ፕሮሰሱ” እንደታሰበው እንደጥንቸል ሊሮጥ አልቻለም፡፡
አንድ ቀን ይሄን “ውጭ” የሚለውን ልቧን ወደ ውስጥ ለመሳብ በማሰብ፣ ሻይ ቡና ልበልሽ ብዬ አንድ እኔ ነኝ ያለ ካፍቴሪያ ውስጥ ቋጠርኳት፡፡ አንድ ሁለት እያልን ጨዋታችንን አደራነው፡፡ ልክ እንደጥንቱ…ከወትሮው ልማዳችን በሹካ መጐራረሱን ብቻ ትተን…ልክ እንደ ጥንቱ በደንብ አወጋን፡፡  
ምንጭ፡- (ባለ “ሚኒስከርቷ” የሥነግጥምና የአጫጭር ታሪኮች ስብስብ)

ሚሉቲን ሴርዶጄቪች (ከኡጋንዳ፤ ካምፓላ)
ከሩብ ምዕተ ዓመት ውድቀት በኋላ የኢትዮጵያ እግር ኳስ፣ ባለፉት ጥቂት አመታት ማንሰራራቱና በአፍሪካ የእግር ኳስ መድረክ ላይ ቤተኛ እየሆነ መምጣቱ አንድ እርምጃ ነው፡፡ ለዚህ አስተዋጽኦ ያደረጉ ተጫዋቾች፣ አሰልጣኞች፣ ክለቦች፣ ስፖንሰሮች፣ ደጋፊዎች እና የፌዴሬሽን አመራሮች እንደየድርሻቸው ምስጋና ይገባቸዋል፡፡ ነገር ግን በዚሁ አህጉራዊ መድረክ ጠንካራ ተፎካካሪ የመሆን ምኞታችን ገና አልተሳካም፡፡ ፈተናውም ከእስካሁኖቹ ሁሉ የከበደ ነው፡፡ ለዚህም ነው የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ምርጫ፤ የብዙዎች መነጋገሪያ መሆኑ የማይገርመው፡፡
ለዚህ ትልቅ ሃላፊነት የሚመጥንና የሚስማማ አሰልጣኝ ለመምረጥ በተጀመረው እንቅስቃሴ፤ የአገር ውስጥ እና የውጭ ባለሙያዎች በእጩነት ስማቸው እየተጠቀሰ ውይይት መሟሟቁም ተገቢ ነው፡፡ የተጀመረው ውይይትም፤ በቅንነት፣ በብስለት እና በእውቀት እየዳበረ መሄድ አለበት፡፡ ለዚህም ይረዳ ዘንድ ቀደም ሲል በኢትዮጵያና በሌሎች የምስራቅ አፍሪካ አገራትና በደቡብ አፍሪካ የታወቁ ክለቦችን ያሰለጠኑ፤ እንዲሁም አስቀድሞ የሩዋንዳ አሁን ደግሞ የዩጋንዳ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ የሆኑትን የ44 ዓመቱ ሰርቢያዊ ሚሉቲን “ሚቾ” ሴርዶጄቪች በአሰልጣኞች ምርጫ ዙሪያ አወያይተናቸዋል፡፡

እንደምታውቀው እኔ ፕሮፌሽናል አሰልጣኝ ነኝ። የትኛውም ፕሮፌሽናል አሰልጣኝ ደግሞ ስለደሞዙ በይፋ ለመናገር ፈቃደኛ አይሆንም፡፡ ስለዚህም ከመናገር እቆጠባለሁ፡፡ ምክንያቱም መቼም ቢሆን የኔ ሩጫ ገንዘብ ለማግኘት አይደለም፡፡ ይልቁንም የሁልጊዜ ፍላጎቴ፣ ራዕይ  ላለው ፕሮጀክት መስራት ነው፡፡ እውነት ለመናገር፤ በአሰልጣኝነት በሰራሁባቸው አገራት ሁሉ ከማገኘው ንዋይ ይልቅ የምሰጠው አገልግሎት እና በትጋት ሰርቼ የማልፈው ይበልጣል፡፡ ለዚህም ይመስለኛል፤ በአሁኑ ጊዜ ከውጭ አሰልጣኞች መካከል በምስራቅ አፍሪካ የእግር ኳስ መድረክ ለረጅም ጊዜ በመቆየት ቀዳሚውን ስፍራ ለመያዝ የበቃሁት፡፡ በምስራቅ አፍሪካ አገራት በ14 ዓመታት የስራ ጊዜ ከፍተኛ ልምድ አካብቻለሁ፡፡ ሁሉም የሚያውቀው ደግሞ ለ5 ዓመታት በኢትዮጵያ እግር ኳስ እንደታማኝ ወታደር አገልግያለሁ፡፡ እናም በአሰልጣኝነቴ ከገንዘብ ይልቅ በስራዬ ከፍ ያለ ስኬት እና የማይረሳ ታሪክ ትቼ ማለፉን በይበልጥ እፈልገዋለሁ፡፡
አሁን በስራ ላይ ለሚገኘው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ታላቅ አክብሮት አለኝ፡፡ በኢትዮጵያ ብቻ አይደለም፤ በስራዬ በኖርኩባቸው አገራት ውስጥ ከፌዴሬሽኖች እና ከእግር ኳስ ተቋማት ጋር ያለኝ ግንኙነት በመከባበር ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ ስለዚህም በፌደሬሽን ስራዎች ላይ ጣልቃ ገብቼ ይህን አሰልጣኝ በዚህ ምክንያት ቅጠሩ በማለት ምክር በመስጠት ክብር ለመጋፋት አልፈልግም፡፡ ዋናው ነገር ኢትዮጵያ በአስደናቂ የባህል ትውፊቶቿ፤ ታሪኳ እና የአኗኗር ዘይቤ ልዩ አገር ናት፡፡ ይህን ክብር በመጠበቅ እና በማክበር፤ ከአገሬውና ከህዝቡ ጋር ተዋህዶ ሊሰራ የሚችል ሰው ያስፈልጋታል። ብሄራዊ ቡድኑ ከፊታችን ለሚጠብቁት ውድድሮች ረዥም የዝግጅት ጊዜ የለውም፡፡ ለ2015 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ውድድር የሚደረገው  ከ8 ወራት በኋላ ነው፡፡ ይህ የማጣርያ ውድድር በመስከረም አካባቢ ተጀምሮ በ3 ወራት ውስጥ 6 ጨዋታዎች የሚደረጉበት ነው፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ይህን ከባድ ማጣርያ በከፍተኛ ዝግጅት በብቃት መወጣት እንዲችል በፍጥነት ውጤታማ አሰልጣኝ ያስፈልገዋል፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚሰሩ የእግር ኳስ አሰልጣኞች ጋር በታላቅ የስራ ፍቅር ተከባብሮ እና በጓደኝነት ተቀራርቦ የመስራት ልምድ አለኝ፡፡ ይህ ደግሞ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውንም ይጨምራል፡፡ የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆነው ለፈፀሟቸው ስኬታማ ተግባራት አድናቆት አለኝ፡፡ ሌሎችንም አደንቃለሁ ለጊዜው ግን፣ የአሰልጣኝ ምርጫ በሚካሄድበት ወቅት ከኢትዮጵያዊ አሰልጣኞች እገሌን ብዬ አድናቆቴን ብገልጽ ተገቢ አይሆንም፡፡ ግን እርግጠኛ ነኝ፤ በሙያችን የተዋወቅን አሰልጣኞች ሁሉ፤ ያለኝን ከበሬታ እና አድናቆት ያውቃሉ፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ አሰልጣኞች በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ በከፍተኛ ትጋት የሚሰሩ እና የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ እንዲያንሰራራ ሁሉም በላቀ ደረጃ አስተዋፅኦ እንደነበራቸው አስባለሁ፡፡ በአሰልጣኝነት ሙያዬ ከኢትዮጵያውያን ጋር በመስራቴ ብዙ ትምህርት እና ልምድ ተጋርቻለሁ፤ አጋርቻለሁ፡፡ ለዚህ ደግሞ ለሁሉም ያለኝን የከበረ ምስጋና እገልፃለሁ፡፡ ባለሙያዎችን በስም እየጠራሁ ያልዘረዘርኩት አሁን ጊዜው ስላልሆነ ነው፡፡   በቴክኒክ ጉዳዮች ላይ ግን የማስበውን ነገር ሁሉ በዝርዝር ለመናገር ወደኋላ አልልም፡፡
የውጭ አገር  አሰልጣኞችን በተመለከተ አሁን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ላለበት አጣዳፊ ሁኔታ የሚሆን ባለሙያ በተፈለገው መስፈርት እና ብቃት በቀላሉ ማግኘት የሚከብድ ይመስለኛል፡፡ እኔም ለዚህ ሃላፊነት የሚመጥንና የሚስማማ የውጭ አሰልጣኝ ማን ነው ብባል፤ አንድም ሰው በአዕምሮዬ ሊመጣ አይችልም። ጥሩ አሰልጣኝ ለማግኘት በቂ ጊዜ ወስዶ መስራት ያስፈልጋል። ለአዲሱ አሰልጣኝ ቅጥር የሚሰሩትን ሁሉ በስራቸው እግዚአብሔር ይርዳቸው ነው የምለው። አሰልጣኝ ምርጫ ቀላል ነገር አይደለም፡፡ አሁን እግር ኳሱ ባለበት የተነቃቃ መንፈስ ለተሻለ ለውጥና ለላቀ እድገት በብቃት ተስማምቶ የሚያገለግል ባለሙያ ያስፈልጋል፡፡ ኢትዮጵያውያን እግር ኳስ አፍቃሪዎች ካላቸው ትልቅ ስሜት ጋር የሚስተካከል ትልቅ ስኬት ለማስመዝገብ የሚሰራ አሰልጣኝ እንጂ የሚያጎድል ሰው መመረጥ የለበትም፡፡ ማንም ሰው ደጋፊዎችን የማስከፋት እና ተስፋ የማስቆረጥ መብት የለውም፡፡ ከዚህ ጥቅል አስተያየት ባሻገር፣ የአሰልጣኝ ምርጫን በተመለከተ ከላይ በጠቀስኳቸው ምክንያቶች የተነሳ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እገሌ  ብዬ ለመጠቆም አሁን አልችልም፡፡
ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝንት ከሚፈለጉ እጩዎች አንዱ ሆኜ ስሜ በመነሳቱ ብቻ ለእኔ ትልቅ ክብር ነው፡፡ ለአሰልጣኝነቴ ዋጋ የሰጠ እውቅና በመሆኑ ከልብ ያስደስተኛል፡፡ አንድ ባለሙያ፣ ከምንም ነገር በላይ ለሙያው እውቅና ሲሰጠው ነው እርካታ የሚሰማው፡፡ ቢሳካ፤ ህልሜ እውን እንደሆነ እቆጥረዋለሁ፡፡ ምክንያቱም ሁሉም  አሰልጣኞች ትልልቅ ብሄራዊ ቡድኖችን በሃላፊነት ለመምራት ይፈልጋሉ፡፡ ሃቁን ልንገርህ፡፡ ኢትዮጵያዊያን ለእግር ኳስ ያላቸውን ፍቅር እና ስሜት እንዲሁም ልዩ ብሄራዊ ክብራቸውን ለሚያውቅ ሰው፤ ይህን ትልቅ ሃላፊነት ሲያገኝ፣ የዘወትር  ህልሙ እውን ሆነ ማለት ነው፡፡ የእግር ኳስ አሰልጣኞች ትልቁ ሃይል፤ በሃላፊነታቸው ለህዝብ ደስታን መፍጠር ነው፡፡ ለ90 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን  ደስታ መፍጠር የሚቻልበት ሃላፊነትን ማግኘት እጅግ ያጓጓል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ታላቅ ክብር  ነው፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ፣ አሁን መስቀለኛ መንገድ ላይ ያለ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም ባለፉት ጥቂት ዓመታት የተፈጠሩ መነቃቃቶች እና ውጤቶች ወደኋላ እንዲያፈገፍጉ ማንም አይፈልግም፡፡ ለዚህም ነው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የአጭር እና የረጅም ጊዜ ውጤታማ እቅዶችን የያዘ ብቁ አሰልጣኝ የሚያስፈልገው። የአጭርጊዜ እቅዱ በ2015 በሞሮኮ የሚስተናገደው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ነው፡፡ የረጅም ጊዜ እቅዱ ደግሞ በ2018 ራሽያ የምታስተናግደው 21ኛው የዓለም ዋንጫ ነው፡፡ አዲሱ የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ እነዚህን አቅዶች ማሳካት የሚችል ፤ የተነቃቃውን ለውጥ በማስቀጠል ለላቀ እድገት የሚተጋ ሊሆን ይገባል፡፡ በምንኖርባት ፕላኔት ውስጥ፤ ለዚህ ሃላፊነት የሚስማማ፤ ይህን ከባድ ሃላፊነት በብቃት መወጣት እና መስራት የሚችል አንድ ባለሙያ አውቃለሁ፡፡ ግን እገሌ ብዬ ስሙንና ማንነቱን ለመንገር መብት የለኝም፡፡ ምክንያቱም ይህ ሰው፤ በሌላ አገር የኮንትራት ስራ ላይ ስለሚገኝ ነው፡፡
እንደሁልጊዜው ልባዊ መልካም ምኞቴን መግለጽ እፈልጋለሁ፡፡ ለአንተም ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብም፡፡ በርቱ፤ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ትክክለኛ ቦታው ከምርጦች ተርታ ነው፡፡ እዚያ ቦታ እንዲደርስ ሁላችሁም በህብረትና በትጋት ስሩ፡፡ ከስምንት አመት በፊት ከጋዜጣችሁ ባደረግነው ቃለምልልስ፣ የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ብትሆን በማለት መልካም ምኞትህን ገለጽህልኝ እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ የመሆን ልባዊ ምኞት እንዳለ ሆኖ፤ እኔ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆንኩ አልሆንኩ  ምንግዜም የዋልያዎቹ ቁርጠኛ ደጋፊ ሆኜ እቀጥላለሁ፡፡


በ2014 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌደሬሽን ካፕ  ደደቢት እና  መከላከያ በቅድመ ማጣርያ  የመልስ ጨዋታዎቻቸው የምስራቅ አፍሪካ ክለቦችን ጥሎ ለማለፍ ትንቅንቅ ያደርጋሉ፡፡ ከሳምንት በፊት ደደቢት በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የዛንዚባሩን ኬኤምኬኤም በሜዳው 3ለ0 ሲያሸንፍ ጎሎቹን ዳዊት ፍቃዱ፤ ሺመክት ታደሰ እና ማይክል ጆርጅ ከመረብ አሳርፈዋል፡፡ በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ  መከላከያ ከሊዮፓርድስ ከሜዳ ውጭ በተገናኘበት ጨዋታ 2ለ0 ተሸንፏል፡፡
በኬንያው ብሄራዊ ስታድዬም ናያዮ በተደረገው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ለሊዮፓርድስ ሁለቱን ጎሎች ያስቆጠሩት አምበሉ ማርቲን ኢምባላምቦሊ እና ጃኮብ ኬሊ ናቸው፡፡ ደደቢት ከኬኤምኬኤም ጋር ከሜዳው ውጭ በሚያደርገው የመልስ ጨዋታ ከ2ለ0 በታች መሸነፍ፤ አቻ መውጣትና በማናቸውም ውጤት ማሸነፍ ጥሎ ለማለፍ ይበቃዋል፡፡
መከላከያ ደግሞ የኬንያውን ኤኤፍሲ ሊዮፓርድስ በሜዳው አስተናግዶ 3ለ0 ከዚያም በላይ በማሸንፍ የማለፍ  እድሉን ይወስናል፡፡  በቅድመ ማጣርያው ከኢትዮጵያው ደደቢት እና ከዛንዚባሩ ኬኤምኬኤም ጥሎ ማለፍ የሚችለው ክለብ በአንደኛ ዙር የማጣርያ ምእራፍ የሚገናኘው ከቱኒዚያው ክለብ ሲኤስ ኤስፋክሲዬን ጋር ነው፡፡
በሌላ በኩል ከኢትዮጵያው መከላከያ እና ከኬንያው ኤኤፍሲ ሊዮፓርድስ ጥሎ የሚያልፈው በአንደኛ ዙር የማጣርያ ምእራፍ የሚገናኘው  ከደቡብ አፍሪካው ሱፕር ስፖርት ዩናይትድ ወይም ከቦትስዋናው ጋብሮኒ ዩናይትስድ አሸናፊ ጋር ይሆናል፡፡ ሱፕር ስፖርት ዩናይትድ በቅድመ ማጣርያው የመጀመርያ ጨዋታ ጋብሮኒ ዩናይትድስን 2ለ0 አሸንፎታል፡፡

ዛሬ በእንግሊዝ በርሚንግሃም በሚካሄደው የ2 ማይል የቤት ውስጥ ውድድር የ23 ዓመቷ አትሌት ገንዘቤ ዲባባ የውድድር ዘመኑን ሶስተኛ የዓለም ሪከርዷን ልታስመዘግብ እንደምትችል ግምት አገኘች፡፡ ገንዘቤ ባለፈው ሁለት ሳምንት በ3ሺ ሜትር እና በ1500 ሜትር የቤት ውስጥ ውድድሮች ሁለት አስደናቂ የዓለም ሪከርዶችን አስመዝግባለች ዛሬ በበርሚንግሃም “ሳልስበሪ ኢንዶር ግራንድፕሪ” የ2 ማይል ሩጫ  ከ5 ዓመት በፊት በመሰረት ደፋር የተመዘገበውን ክብረወሰን ገንዘቤ ዲባባ ለመስበር እንደምትችል ተዘግቧል፡፡ ከተሳካላት በውድድር ዘመኑ 3 የዓለም ሪከርዶችን ያስመዘገበች ምርጥ አትሌት እንደምትሆን መረጃዎች አውስተዋል፡፡ ገንዘቤ በ2014 የውድድር ዘመን ከገባ ወዲህ በማሳየት ላይ የምትገኘው አስደናቂ ብቃት ከወር በኋላ በፖላንዷ ከተማ ስፖት በሚደረገው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ላይ በ3ሺ እና በ1500 ለድርብ የወርቅ ሜዳልያ ድሎች ግንባር ቀደም እጩም አድርጓታል፡፡
ገንዘቤ ከሳምንት በፊት በስዊድን ስቶክሆልም በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫ  ያሸነፈችው ርቀቱን በ8 ደቂቃ ከ16.60 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በማጠናቀቅ አዲስ የዓለም ክብረወሰን አስመዝግባ ነበር፡፡ ይህ ሪከርድ አስቀድሞ በመሰረት ደፋር ተመዝግቦ የነበረውን የሰዓት ክብረወሰን በ7 ሰኮንዶች ያሻሻለ ሲሆን ከ1993 እኤአ ወዲህ በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫ ሊመዘገብ ፈጣን ሰዓት ተብሎ ከፍተኛ አድናቆት አግኝቷል፡፡ አትሌት ገንዘቤ ዲባባ ከዚሁ የ3ሺ ማይል አዲስ የዓለም ክብረወሰኗ 5 ቀናት በፊት ደግሞ በጀርመን ካርሉስርህ በተደረገ የ1500ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫ በሪከርድ ሰዓት አሸንፋ ነበር፡፡ በ1500 ሜትር የቤት ውስጥ ሩጫው አትሌት ገንዘቤ ያሸነፈችው ርቀቱን በ3 ደቂቃ ከ55፡17 ሰኮንዶች በማገባደድ ሲሆን አስቀድሞ በሩሲያዊ አትሌት ተይዞ የነበረውን ክብረወሰን በ3 ሰኮንዶች አሻሽላዋለች፡፡

የማህጸን በር ካንሰር፣
በማህጸን አካባቢ የሚፈጠር የቅማል ዘር በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት ከሚተላለፉ  መካከል ናቸው፡፡
ዶ/ር ሰሎሞን ኩምቢ (ተባባሪ ፕሮፌሰር) በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጽንስና ማህጸን ሕክምና ትምህርት አስተማሪ እና እስፔሻሊስት ናቸው፡፡ ዶ/ር ሶሎሞን በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎችን ምንነት እና መፍትሔያቸውን ለዚህ እትም ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
ጥ/    የግብረስጋ ግንኙነት ሲባል ምን ማለት ነው?
መ/    የግብረስጋ ግንኙነት ማለት በተለምዶ የወንድ ብልት በሴቷ ብልት ውስጥ ሲገባ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን እንደሰዎቹ ስምምነት የሚፈጸሙ ሌሎችም የግብረስጋ ግንኙነቶች አሉ?
ጥ/    በሰዎች ስምምነት የሚፈጸሙ ሲባል ምን አይነቶች ናቸው?
መ/    የግብረስጋ ግንኙነት እንደ ሰዎቹ ስምምነት ይፈጸማል ሲባል በእንግሊዝኛው (Oral & Anal) ማለትም አንዳንድ ጊዜ በአፍ እና በፊንጢጣም በኩል ይፈጸማል፡፡
ጥ/    በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎች ሲባል ምን አይነት ናቸው?
መ/    የሚከሰቱትን ችግሮች በግብረስጋ ምክንያት የሚከሰቱ አካላዊ ጠንቆች ቢባሉ የሚሻል ይመስለኛል፡፡ ችግሮቹ የተለያዩ ሲሆኑ በብዛት የሚታወቁት ግን የአባላዘር በሽታዎች ተብለው የሚጠቀሱት ናቸው፡፡ ከዚህ በተለየ ግን ለምሳሌ...
የማህጸን በር ካንሰር፣
የማህጸን በር ካንሰርን የሚያመጡት ቫይረሶች በመሆናቸው ከወንድ ወደሴት በሚተላለፉበት ወቅት ለበሽታው መከሰት እንደ አንድ ምክንያት ይቆጠራል፡፡ አንዲት ሴት የማህጸን በር ካንሰር እንዳይከሰትባት ለመከላከል ሲባል የሚሰጠው ክትባት የግብረስጋ ግንኙነት መፈጸም ከመጀመሩዋ በፊት ቢሆን የሚመረጥ መሆኑን የህክምናው ዘርፍ ባለሙያዎች ያስረዳለሉ፡፡  
በአስገድዶ መደፈር ወይንም በሰምምነት በሚደረግ ግንኙነት ምክንያት የሴቷ ብልት የውስጥ ክፍል መቀደድ፣
በማስገደድም ይሁን በስምምነት በሚፈጸም ግንኙነት ሳቢያ የሚከሰት የሽንት መቋጠር ችግር፣
በግብረስጋ ግንኙነት ጊዜ ከሚፈጠር አግባብ ያልሆነ የኃይል መጠቀም ወይንም የሰውነት አለመመጣጠን ሳቢያ የሚፈጸም ከሆነ በሴቷ ብልት አካባቢ የሚገኙትን አካላት ጭምር የሚያጠቃ ይሆናል፡፡
ማህጸን አካባቢ የሚፈጠር የቅማል ዘር፡-
በማህጸን አካባቢ የሚፈጠር የቅማል አይነት ከወንድ ወደ ሴት ወይንም ከሴት ወደ ወንድ ሲተላለፍ በሚፈጠረው የመራባት ሁኔታ ቅጫም ሊኖረው ሲችል ከዚያም ወደብብት እና ወደ አይን ፀጉር ጭምር ሊተላለፍ ይችላል፡፡ ስሜቱም በብልት ወይንም በብልት ጸጉር ላይ የማሳከክእና የማቃጠል ሊሆን ስለሚችል ሴትየዋ ወይንም ሰውየው እንደዚህ ያሉ ስሜቶች ከታዩባቸው ቶሎ መፍትሔ መውሰድ ይጠበቅባቸዋል፡፡   
የተለያዩ የቆዳ በሽታዎች በግብረ ስጋ ግንኙነት ምክንያት ሊተላለፉ ይችላሉ፡፡
ጥ/    ሁሉንም በሽታዎች በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ ማለት ይቻላል?
መ/    የሚተላለፉት …Sexually transmissible infectious… ተብለው የሚለዩት ናቸው፡፡ እነርሱም በአማርኛው ጨብጥ፣ ቂጥኝ፣ ውርዴ፣ አባኮዳ፣ ባምቡሌ፣ የሴቶችን ፈሳሽ የሚያመጣ ፕሮቶዝዋ፣ ካንዲዳ የሚባል የፈንገስ አይነት እና ሌሎችም በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ ተብለው የሚፈረጁ ሕመሞች አሉ፡፡ ነገር ግን በብዛት በማህጸን አካባቢ የማህጸኑ፣ የቱቦው እና የእጢው መቆሸሽ (Pelvic inflammatory disease) በሚባል የሚጠራውን ሕመም የሚያመጡት ጎኖሪያ (ጨብጥ)፣ ክላይሚድያ፣ ማይኮ ፕላዝማ እና ዩሪያፕላዝማ የሚባሉ የህዋስ አይነቶች ናቸው፡፡ ስለዚህ ከግብረስጋ ግንኙት ጋር የሚያያዝ ችግር ነው ብሎ መውሰድ ይቻላል፡፡
ጥ/    በተላላፊ በሽታዎቹ ምክንያት የሚከሰተው ሕመም ምን ይመስላል?
መ/    ከተላላፊ በሽታዎቹ ጋር ያሉት ጠንቆች ከማህጸን በላይ እርግዝና፣ ማህጸን ወይንም ብልት አካባቢ የሚኖር ሕመም፣ መካንነት ወይንም ልጅ አለመውለድ፣ በውስጥ አካል (ጉበት)፣ የሆድ እቃ አካባቢ መሰራጨት፣ የአእምሮ፣ የቆዳ፣ የልብ ኢንፌክሽን የማምጣት ...ወዘተ የመሳሰሉትን ሕመሞች ሊያስከትል ይችላል፡፡ ከተጠቀሱት ሕመሞች በተጨማሪም በአለም አቀፍ ደረጃ በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት በመተላለፍ በሽታ ከሚባሉት ውስጥ ኤችአይቪ ቫይረስም አንዱ ነው፡፡
ጥ/    ከግብረስጋ ግንኙነት ጋር ተያይዘው የሚመጡ የሰውነት ጠንቆች ሲባል ምን ማለት ነው?
መ/    ከግብረስጋ ግንኙነት ጋር ተያይዘው የሚመጡ የሰውነት ጠንቆች ሲባል ከላይ እንደገለጽኩት ግንኙነት የሚደረግበት የሴቷ ብልት መቀደድ፣ ፊስቱላ የመሳሰሉት ነገሮች ባህሪያቸው መተላለፍ ሳይሆን በግንኙነት ምክንያት የሚከሰቱ ጠንቆች ሊባሉ የሚችሉ ናቸው፡፡ የማህጸን በር ካሰርንም በቀጥታ ተላላፊ በሚል ከባድ ድምዳሜ መስጠት ባይቻልም ቀደም ሲል ካንሰሩ የነበረባት ሴትጋር በወሲብ የተገናኘ ሰው ወደሌላ ሴት ሲሄድ ቫይረሱን ሊያስተላልፍ ይችላል የሚሉ አስተያየቶች አሉ፡፡
ጥ/    ተላላፊ የተባሉት በሽታዎች በዚህ ዘመንም አሉ? ወይንስ?
መ/    በእርግጥ በግሌ በቅርብ ያጠናሁት ጥናት የለም፡፡ ነገር ግን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎችን ወይንም የአባላዘር በሽታዎችን በጤና ጣቢያ ደረጃ በቀላል እንዴት ማከም እንደሚቻል ለማሳየት መመሪያ ሲያወጣ የተሰራ ጥናት እንደሚያሳየው ጎኖሪያ፣ ክላሚድያ፣ ትሪኮሞኒያሲስ፣ ካንዲድያሲስ የተባሉት ሕመሞች አሁንም ያሉ ሲሆን እንዲያውም በመሪነት ደረጃ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡  ባጠቃላይ ግን ሕመሞቹ በሙሉ አሁንም አሉ ማለት ይቻላል፡፡
ጥ/    በተላላፊ በሽታዎች ምክንያት የሚፈጠሩ የማሳከክ ስሜቶችን ጨው በመሳሰለው ነገር በመጠቀም መታጠብ ምን ይህል ይረዳል?
መ/    አንዳንድ ሴቶች ውሀ በማፍላት በጨው የመታጠብ ወይንም የመዘፍዘፍ እርምጃን ይወስዳሉ፡፡ ይህ በሰዎች ዘንድ ጥሩ ስሜትን ሊፈጥር ይችላል፡፡ ጨው ተፈጥሮአዊ ነገር ስለሆነ ምናልባት የማቃጠል ስሜት ይኖረው እንደሆነ እንጂ ጉዳቱ ብዙም አይታየኝም፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ኬሚካሎችን እንደመታጠቢያ መውሰድ በቁስል ወይንም በተቆጣ ሰውነት ላይ ሌላ ችግር ሊያስከትል ስለሚችል አይመከርም፡፡ ጨው ግን ብዙም ጥቅሙ ባይታወቅም ጉዳት ግን የለውም፡፡
ጥ/    ሰዎች እንደመፍትሔ ሊወስዱት የሚገባ እርምጃ ምንድነው?
መ/    መፍትሔውን ስናስብ በቅድሚያ ትኩረት መደረግ ያለበት ጥንቃቄ የተሞላበት የግብረስጋ ግንኙነት ማድረግ ነው፡፡ ይህም ማለት መከላከል የሚቻልበትን ዘዴ መጠቀም ሲሆን ለዚህም አንዱ የሴቶችና የወንዶችን ኮንዶም መጠቀም ማለት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በተለይም ወጣቶች ከትዳር በፊት የግብረስጋ ግንኙነት ማድረግ እንደማይገባቸው ይመከራል፡፡ ይህ ሀይማኖታዊ ብቻ ሳይሆን በሳይንሱም መንገድ የሚመከር ነው፡፡ ለወጣቶቹ እንደአማራጭ የሚመከረው ፍቅራቸውን በመላፋት ወይንም በመሳሳም ደረጃ ገድበው እንዲይዙት ነው፡፡ ከዚህ በተረፈ የሰውነትን እምቅ የሆነ ስሜት ለማውጣት Masturbation መጠቀም አንዱ ሳይንሳዊ ምክር ነው፡፡ ሁኔታዎች ከዚህ በላይ የሚገፉ ከሆነ ግን ሁለቱም ፍቅረኛሞች ምርመራ አድርገው የጤንነት ሁኔታቸውን በማረጋገጥ ግንኙነት ማድረግ ይችላሉ፡፡ ይህ ምክር የሚሰጠው ለኤችአይቪ ብቻ ሳይሆን ለአባላዘር በሽታዎችም ነጻ መሆን አለመሆን ማረጋገጫነት የሚመከሩ ናቸው፡፡ ከምር መራው በሁዋላም ከዚያ ከሚያውቁት ሰው ጋር ብቻ ግንኙነት ማድረግ ይገባቸዋል፡፡ የአባላዘር በሽታ በወንዶች ላይ ቶሎ ሲገለጽ በሴቶች ላይ ግን በተፈጥሮ ምክንያት ቶሎ ላይታወቅ ይችላል፡፡ ስለሆነም ሕመሙም በጊዜው ስለማይደረስበት በሴቶች ላይ ይበረታል፡፡ ነገር ግን የአባላዘር በሽታዎች ሊታከሙ ወይንም ሕመማቸውን ለመቀነስ የሚ ችሉ ናቸው፡፡ ስለዚህም ባጠቃላይ የሚሰጠው ምክር...
ችግሩ ከመከሰቱ በፊት አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ
ችግሩ ከተከሰተ በግልጽ ከፍቅረኛ ወይንም ከትዳር ጉዋደኛ ጋር መመካከር
ችግሩ ከተከሰተ በአስቸኳይ ወደጤና ተቋም በመሄድ ማማከር ይገባል፡፡
    ሰዎች አስቀድመው አስፈላጊውን እርምጃ ከወሰዱ ቫይረሶቹ፣ ባክቴሪያዎቹ፣ ፈንገሶቹ እና የፕሮቶዞዋው እና ቅማሉን ጨምሮ የሚታከሙና ሊድኑ የሚችሉ ናቸው፡፡