Administrator

Administrator

    እናት የማስታወቂያ ድርጅት፤ “ትርጉም ያለው የንባብ ባህል ለወጣቶች ስኬታማነት” በሚል መርህ ዛሬ ረፋድ ላይ ተጀምሮ  ለግማሽ ቀን የሚዘልቅ ውይይት በብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መፃሐፍት ኤጀንሲ አዳራሽ እንደሚካሄድ አስታወቀ፡፡ደራሲ ዘነበ ወላ እና ፀጋአብ ለምለም ለውይይቱ የመነሻ ሃሳብ እንደሚያቀርቡ የታወቀ ሲሆን በውይይት መድረኩ ላይ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት፣ የስነ - ፅሁፍ ማህበራት ተወካዮች፣ ባለስልጣናት፣ ደራሲያን፣ የስነ ጽሑፍ ምሁራን፣ መጽሐፍት አሳታሚዎችና አከፋፋዮች እንደሚገኙ ተጠቁሟል፡፡

በዚህ መድረክ የንባብ ባህልን ለማሳደግ ፍላጐት ያለው ማንኛውም ሰው እንዲታደም ተጋብዟል፡፡ እናት የማስታወቂያ ድርጅት፤ ለንባብ ባህል መዳበር አስተዋጽኦ ባላቸው ስራዎች ላይ በማተኮር ላለፉት አምስት አመታት ሲንቀሳቀስ የቆየ ሲሆን በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ላይ ዘወትር እሁድ ከምሽቱ 2፡00 እስከ 4፡00 ሰዓት በሚያቀርበው “ብራና” የተሰኘ ፕሮግራሙና በአዲስ አበባና በክልሎች በሚያዘጋጃቸው የመፃህፍት አውደ ርዕዮች ይታወቃል፡፡

Charlie and the Chocolate Factory” በሚል በሮዋልድ ዳህል ተፅፎ “ቻርሊና የቼኮሌት ፋብሪካው” በሚል በጌታነህ አንተነህ ወደ አማርኛ ተተርጉሞ የተዘጋጀው አዲስ መፅሀፍ ሰሞኑን ገበያ ላይ ውሏል፡፡ መፅሀፉ በቻርሊ ቸኮሌት ፋብሪካ ዙሪያ የሚያጠነጥን ወጥ ተረት ሲሆን በ157 ገፆች የተቀነበበ ነው፡፡
 በኦላንድ አታሚዎችና አሳታሚዎች ድርጅት የታተመው መጽሐፉ፤ ለአገር ውስጥ በ40 ብር፣ ለውጭ አገር በ20 ዶላር ለገበያ እንደቀረበ ታውቋል፡፡

በተለያዩ የኪነጥበብ ስራዎች ላይ የተሰማራው የዶን ፊልሞች ፕሮዳክሽን የገጣሚ በአካል ንጉሴ የግጥም ስብስቦችን ያካተተውን “ፍላሎት” የተሰኘ የግጥም መጽሐፍ ባሳለፍነው ሳምንት አጋማሽ በጣይቱ ሆቴል ጃዝ አምባ አዳራሽ አስመርቋል፡፡
መጽሐፉ በማህበራዊ፣ ባህላዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ 68 ግጥሞችን ያካተተ ሲሆን በ91 ገፆች ተቀንብቦ በ25 ብር ለገበያ እንደቀረበ ታውቋል፡፡ በምርቃት ስነስርዓቱ ላይ ተፈሪ አለሙ፣ ኪሮስ ሃ/ስላሴ፣ ምስራቅ ተረፈና እምወድሽ በቀለ ከመጽሐፉ ላይ ግጥሞችን ለታዳሚው አቅርበዋል፡፡

የነፃ አርት ቪሌጅ መስራች አባልና ምክትል ስራ አስኪያጅ የሆነው የታምራት ገዛኸኝ “ፈለግ ከሀ እስከ…” የተሰኘ የስዕል አውደ ርዕይ ትናንት ምሽት በጉራማይሌ የስነጥበብ ማዕከል ተከተፈ፡፡
አውደ ርዕዩ፤ ሰዓሊው ላለፉት 15 ዓመታት ያለፈበትን የስነ - ጥበብ ጉዞ የሚያስቃኝና አሁን ለደረሰበት ስነ - ጥበባዊ ከፍታ አስተዋጽኦ ያላቸውን ዘመን ተሻጋሪ ሥራዎች የሚያስቃኝ ነው ተብሏል፡፡

Saturday, 08 November 2014 11:29

የቀልድ ጥግ

ጋዜጠኛው ወደ ኢትዮጵያ ለስራ የመጣ አንድ ቻይናዊ እያነጋገረ ነው፡፡
ጋዜጠኛ - ቻይና ውስጥ አንድ አምፑል ለመቀየር ስንት ቻይናውያን ያስፈልጋሉ?
ቻይናዊ - አንድ በቂ ነው፡፡
ጋዜጠኛ - ኢትዮጵያ ውስጥስ አንድ አምፑል ለመቀየር ስንት አበሾች ያስፈልጋሉ?
ቻይናዊ - አምስት፡፡ አንዱ አምፑል ለመቀየር፣ አንዱ ወንበር ለመያዝ፣ ሶስቱ ደግሞ   ቆመው ለመመልከት፡፡
ጋዜጠኛ - ኢትዮጵያ ውስጥ አንድ አምፑል ለመቀየር ስንት ቻይናውያን ያስፈልጋሉ?
ቻይናዊ - አምስት፡፡ አንዱ አምፑል ለመቀየር፣ አራቱ ቆመው የሚመለከቱትን አበሾች  ለማባረር፡፡
ጋዜጠኛ - ቻይና ውስጥ አንድ አምፑል ለመቀየር ስንት አበሻ ያስፈልጋል?
ቻይናዊ - አንድ አበሻና ሶስት ቻይናውያን፡፡
አበሻው አምፑሉን ለመቀየር፣ ሶስቱ ቻይናውያን ደግሞ ሃበሻው አምፑሉን ቀይሮ ሲጨርስ አገሬ አልመለስም  
   እንዳይል ለመጠበቅ፡፡

615 ሚ. ዶላር ወጥቶበታል፤ ተጨማሪ 85 ሚ. ፓውንድ ለማስፋፊያ ተመድቦለታል
ለፕሬዚዳንቱ ልዩ አውሮፕላን 115 ሚ. ፓውንድ ተከፍሏል
3 ሚ. ቱርካውያን ስራ አጦች ናቸው

           የቱርኩ ፕሬዚዳንት ሪሲፕ ጣይብ ኤርዶጋን፤ በ615 ሚሊዮን ዶላር ወጪ ያሰሩትና አንካራ ውስጥ በሚገኝ 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ስኩየር ጫማ ቦታ ላይ ያረፈው ግዙፉ ‘ነጩ ቤተ መንግስት’ በአገሪቱ ዜጎች ዘንድ ተቃውሞ ማስነሳቱን ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ለ12 አመታት አገሪቱን በጠቅላይ ሚኒስትርነት ያስተዳደሩትና በቅርቡ የፕሬዚዳንትነት ስልጣን የያዙት ኤርዶጋን፤ ከታዋቂዎቹ ዋይት ሃውስና ቤኪንግሃም ቤተመንግስቶች እንደሚበልጥ የተነገረለትን ይህን ቤተመንግስት ማሰራታቸው፣ በአገሪቱ ግብር ከፋይ ዜጎች ዘንድ አላግባብ ወጪ የወጣበት የቅንጦት ግንባታ በሚል ተቃውሞ ገጥሞታል፡፡
ከሳምንታት በፊት ግንባታው ተጠናቆ ስራ የጀመረውና “አክ ሳራይ” ተብሎ የሚጠራው ቤተ መንግስት፤ በከፍተኛ ወጪ ከመገንባቱ በተጨማሪ፣ በአረንጓዴ ቦታነት በተከለለ ስፍራ ላይ መሰራቱ በአካባቢ ጥበቃ ተቆርቋሪዎች ዘንድ ተቃውሞ እንዳስነሳ ዘገባው ጠቁሟል፡፡
“ፕሬዚዳንቱ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዛፎችን ጨፍጭፈው በከፍተኛ ወጪ የራሳቸውን የቅንጦት ቤት የገነቡት፣ 3 ሚሊዮን ዜጎቿ ስራ አጥ በሆኑባት አገር ላይ ነው” ብለዋል - “ሪፐብሊካን ፒፕልስ ፓርቲ” የተባለው የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ከማል ኪሊዳሮግሉ ለቴሌግራፍ ጋዜጣ በሰጡት ቃል፡፡
በአገሪቱ ቤተ መንግስት ለመገንባት ከተመደበው በጀት ከሁለት እጥፍ በላይ ገንዘብ ፈሶበታል የተባለው ቤተ መንግስቱ 1 ሺህ ክፍሎች ያሉት ሲሆን እጅግ ዘመናዊ የሆነ ጥብቅ የደህንነት መቆጣጠሪያ ሲስተም ተገጥሞለታል፡፡
 ቤተመንግስቱ እጅግ ውድ በሆኑ የግንባታ ቁሳቁሶች የተሰራ ነው ተብሏል፡፡
‘ነጩን ቤተ መንግስት’ በቀጣዩ አመት የበለጠ እንዲያምርና እንዲስፋፋ ለማድረግ ተጨማሪ 85 ሚሊዮን ፓውንድ በጀት መመደቡን የጠቆመው ዘገባው፤ ለፕሬዚዳንቱ ልዩ ኤርባስ አውሮፕላን ለመግዛት 115 ሚሊዮን ፓውንድ በጀት መመደቡንም ገልጿል፡፡

ስልጣኑን ካላስረከበ አገሪቱን ከህብረቱ አባልነት አግዳለሁ ብሏል
ፓርቲዎች እስከ 1 አመት የመንግስት ሽግግር ለማድረግ ተስማምተዋል

            ቡርኪናፋሶን ለ27 አመታት የመሩት ፕሬዚዳንት ብሌስ ኮምፓዎሬ በህዝብ አመፅ ከስልጣን መውረዳቸውን ተከትሎ የአገሪቱ የጦር ሃይል ስልጣን የያዘበት አካሄድ ህገ መንግስታዊ ስርዓትን የተከተለ አይደለም ሲል የተቃወመው የአፍሪካ ህብረት፤ ጦሩ በሁለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ለሲቪል መንግስት ስልጣን እንዲያስረክብ ቀነ ገደብ ማስቀመጡን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ባለፈው ማክሰኞ ከተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችና ከንቅናቄ መሪዎች ጋር ውይይት ያደረጉት የአገሪቱ የጦር ሃይል መሪ ሌ/ኮሎኔል አይዛክ ዚዳ በተቀመጠው ቀነ ገደብ ስልጣን እንደሚያስረክቡ ቃል ገብተዋል፡፡
የአፍሪካ ህብረት በበኩሉ፤ ጦሩ በተቀመጠለት የጊዜ ገደብ ስልጣኑን የማያስረክብ ከሆነ፣ ቡርኪናፋሶን ከህብረቱ አባልነት ከማገድ አንስቶ በጦር መኮንኖች ላይ የጉዞ ማዕቀብ እስከመጣል የሚደርስ እርምጃ እንደሚወስድ አስታውቋል፡፡
ድንገት የተቀሰቀሰው የቡርኪናፋሶ ህዝባዊ አመጽ ብሌስ ኮምፓዎሬን ከስልጣን ማውረዱን ተከትሎ፣ አገሪቱን የማስተዳደሩን ስልጣን የተረከበው የጦር ሃይል በአፋጣኝ ስልጣኑን ለተገቢው መሪ እንዲያስረክብ ሁኔታዎችን የማመቻቸት አላማ የያዘው የምዕራብ አፍሪካ አገራት መሪዎች የልኡካን ቡድን፣ ወደ አገሪቱ በማምራት በጉዳዩ ዙሪያ መምከሩን ዘገባው ገልጿል፡፡
ጦሩ ስልጣኑን በአፋጣኝ እንዲያስረክብ ለማግባባት ወደ ቡርኪናፋሶ ያመሩት የጋና፣ የናይጀሪያና የሴኔጋል መሪዎች ከትናንት በስቲያ ከጦር ሃይሉ መኮንኖች፣ ከሲቪል ማህበረሰብ አካላት፣ ከጎሳ መሪዎችና ከተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ጋር መወያየታቸውንና ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ በመጪው አመት ህዳር ወር ላይ እስከሚካሄድ የሽግግር መንግስት እንዲቋቋም ስምምነት ላይ መደረሱን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የአፍሪካ ህብረት የጸጥታው ምክር ቤትም በወሩ መጨረሻ በሚጠራው ስብሰባ አገሪቱን ከቀውስ ለማዳን በሚቻልበት ሁኔታ ዙሪያ እንደሚመክርም ዘገባው አክሎ ገልጿል፡፡
ፕሬዚዳንት ብሌስ ኮምፓዎሬ፤ ህገመንግስቱን በማሻሻል ያለ አግባብ በቀጣዩ የአገሪቱ ምርጫ ለመወዳደር መሞከራቸውን ተከትሎ፣ ባለፈው ሳምንት በአገሪቱ በተቀሰቀሰው የህዝብ ተቃውሞ ከስልጣን መውረዳቸው ይታወሳል፡፡

ታዋቂው የማህበራዊ ድረገጽ ፌስቡክ ከተለያዩ የአለማችን አገራት መንግስታት የተጠቃሚዎቹን የግል መረጃዎች አሳልፎ እንዲሰጣቸው የሚያቀርቡለት ጥያቄዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን አስታወቀ፡፡ከተለያዩ የአለም አገራት መንግስታት የሚቀርቡለት ተመሳሳይ ጥያቄዎች ባለፉት ስድስት ወራት በ25 በመቶ እንደጨመ በድረገጹ ላይ የገለጸው ፌስቡክ፣ በዚህ ጊዜ ውስጥ 34 ሺህ 946 የመረጃ ጥያቄዎች እንደቀረቡለት አስታውቋል፡፡
ድረገጹ እንዳለው፤ የተለያዩ አገራት መንግስታት በፌስቡክ ተጠቃሚዎች ላይ በተለያዩ ምክንያቶች ክትትልና ምርመራ ለማድረግ የሚያግዛቸውን መረጃዎች ለማግኘት ጥያቄ ማቅረባቸውን ቀጥለዋል፡፡መንግስታት የሚያቀርቡትን መሰል ጥያቄዎች በመቃወም በተደጋጋሚ በአሜሪካ ለሚገኝ አንድ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቤቱታ እያቀረበ እንደሚገኝ ያስታወቀው ፌስቡክ፣ ፍርድ ቤቱ የአሜሪካ መንግስት በህገወጥ መንገድ ያገኛቸውን የተጠቃሚዎቹነረ መረጃዎች እንዲያስመልስለት አቤት እያለ መሆኑንም ገልጿል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ ታዋቂው ድረገጽ ጎግልም፣ የተጠቃሚዎቹን መረጃዎች አሳልፈው እንዲሰጡት በተለያዩ አገራት መንግስታት የሚቀርቡለት ጥያቄዎች ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ በ15 በመቶ መጨመራቸውን ባለፈው ወር ማስታወቁን ሮይተርስ አስታውሷል፡፡
መንግስታት ለወንጀል ምርመራ የሚያቀርቡለት የመረጃ ጥያቄዎች ባለፉት አምስት አመታት በ150 በመቶ እንደጨመረ ነው ጎግል ያስታወቀው፡፡

ከአዲስ አበባ ከተማ የመልሶ ማልማት እንቅስቃሴ ጋር ተያይዞ የቅርስ ጥበቃ ጥያቄዎች ይነሳሉ፡፡ አንዳንድ ወገኖች የከተማዋ ቅርሶችና ታሪክ የልማቱ ሰለባ ሆነዋል በሚል ይተቻሉ፡፡ ለአንድ ከተማ የቅርስ ፋይዳ ምን ያህል ነው? በአሁኑ ወቅት ያለው የቅርስ አጠባበቅስ ምን ይመስላል? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት ዕቁባይ፤ በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን የአለም አቀፍ ቅርሶች ምዝገባ የቡድን መሪና በአለም አቀፍ ቅርሶች አስተዳደር ዕቅድ ዝግጅቶች ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑትን አቶ ኃይለመለኮት አግዘውን አነጋግራቸዋለች፡፡

አዲስ አበባ የቅርሶች ከተማ ናት ይባላል፡፡ እስቲ ያብራሩልኝ…
አዲስ አበባ ቅርሶች ያሏት ከተማ ናት፡፡ ስለ አዲስ አበባ ቅርሶች ስንናገር፣ በዘመን ከፍለን ብናየው፤ ለምሳሌ በአርኪኦሎጂ እንግሊዝ ኤምባሲ አካባቢ የሚገኘው የዋሻ ሚካኤል ተክለሃይማኖትን፤ በታሪክና በአርኪኦሎጂ ደግሞ የመናገሻ የደን ታሪክን መጥቀስ እንችላለን፡፡ በከተማዋ ውስጥ ከሚገኙት ቀደምት አብያተ ክርስቲያኖች የቀራኒዮ መድሃኒያለም ቤተክርስቲያንን ስንመለከት፣ በ1836 በንጉስ ሳህለ ስላሴ ዘመነ መንግስት የተሠራ ነው፡፡ የእንጦጦ ማርያም ቤተክርስቲያንና ኡራኤልን እንዲሁም ሌሎችንም ማንሳት እንችላለን፡፡ እነዚህ ከከተማዋ መቆርቆር ከ1879 በፊት የነበሩ ናቸው፤ ስለዚህ አዲስ አበባ ቅርስም ታሪክም ያላት ከተማ ነች፡፡
የአዲስ አበባ የቅርሶች ምዝገባ ምን ይመስላል?
የከተማዋ ከፍተኛ መሀንዲስ የነበሩት ዶክተር ወንድሙ የሚባሉ ባለሙያ በ1964 ዓ.ም በኢትዮጵያን ሄራልድ ጋዜጣ ላይ የ”አዲስ አበባ ቅርሶች ከየት እስከ የት” የሚል ጽሑፍ በእንግሊዝኛ አቅርበው ነበር፡፡ ሊሴ ገብረማርያም ት/ቤት ጋ የሚገኘውን የራስ ናደው ወሎ ቤት ወይም በተለምዶ “ዋይት ሃውስ” ተብሎ የሚጠራውን ቤት ፎቶ ጋዜጣው ይዞት ወጥቶ ነበር፡፡ ጥናቱን መሠረት በማድረግ የአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት አንዳንድ ስራዎችን ሲሰራ ነበር፡፡ እሳቸው በወቅቱ በጋዜጣ ላይ የፃፉት ስጋታቸውን ነው፡፡ ስለ አዲስ አበባ ከተማ የቅርስ ስጋት መፃፍ የተጀመረው ከዚህን ጊዜ ጀምሮ ነው ማለት ነው፡፡ በ1979 ዓ.ም አዲስ አበባ መቶኛ አመቷን ስታከብር፣ ከተማዋ ሙዚየም ያስፈልጋታል በመባሉ፣ ኤግዚቢሽን ማዕከል አጠገብ የሚገኘው የራስ ብሩ ወልደገብርኤል መኖሪያ ቤት ታድሶ፣ የአዲስ አበባ ከተማ ተንቀሳቃሽ ቅርሶች የከተማዋን ታሪክ ሊተርኩ በሚችል መልኩ ፊንፊኔ፣ እድገት፣ አድዋ ወዘተ የተባሉ አዳራሾች እንዲቀመጡ ተደረገ፡፡ ቤቱ ቀደምት የኪነጥበብ ህንፃ የሚታይበት ነው፡፡
ከ1979 እስከ 1983 ዓ.ም የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ የሙዚየሙ የበላይ ጠባቂ ስለነበሩ፣ ሙዚየሙ በጀትና የቅርብ ክትትል ነበረው፡፡ በ1983 የመንግስት ለውጥ ሲመጣ በፌደራል የሚገኘው የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሠራተኞች ዲሴንትራላይዝድ ሲሆኑ የቅርስ ሃላፊነት ሊኖራቸው የሚገቡ ሰዎች ለአዲስ አበባ ተመደቡ፡፡ መጀመሪያ የተዋቀረው የከተማዋ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ቡድን ነው፡፡ የከተማዋን ታሪካዊ ቤቶች ለመጀመሪያ ጊዜ የአዲስ አበባ ወጣቶች ማህበርን በማስተባበርና ከተመደቡት ባለሙያዎች ውስጥ የተወሰኑት ቤቶቹን ቆጥረው ከተሰበሰበው መረጃ ውስጥ ወደ 130 የሚሆኑ ታሪካዊ ቤቶች የአዲስ አበባ ማስተርፕላን ክለሳ በተሰራበት ወቅት እንዲካተቱ ተደርጓል፡፡ ቤቶቹ በእድሜያቸው መርዘም ምክንያት ብቻ የተመዘገቡ ነበሩ፡፡ ነገር ግን የአዲስ አበባ ቅርሶች በአፄ ምኒሊክ ዘመን የተሠሩ ቤቶች ብቻ ናቸው ማለት አይደለም፡፡ በወቅቱ የተመዘገቡ ቦታዎችም ነበሩ፡፡ ለምሳሌ መስቀል አደባባይ፣ ጃንሜዳና እንጦጦ ተጠቃሽ ናቸው፡፡
እነዚህ ቦታዎች እንዴት ነው የተመረጡት?
ህዝብ በብዛት ወጥቶ የተለያዩ ክንዋኔዎችን የሚያደርግባቸው ስለሆኑ ነው፡፡ ወደ አስራ ሰባት የሚጠጉ የከተማዋ ሀውልቶችና አደባባዮችም ተመዝግበዋል፡፡ ቀደምት የሆኑ አብያተ ክርስቲያናትም ተመዝግበዋል፡፡
አዲስ አበባ ልትናገራቸው የምትችላቸው የራሷ የእድገት ደረጃዎች ያላት ከተማ ናት፡፡ ከ1879 እስከ 1928 ዓ.ም የምኒልክ ዘመን ኪነ ህንፃን እናያለን፡፡ ይሄ ዘመን በተለይ መጀመሪያ ላይ ወደ ቤተመንግስቱ የመጡትን የአርመኖችና ህንዶች ኪነጥበብ ህንፃ ያሳያል፡፡ ለምሳሌ የአርመኖቹን ብናይ፣ የአዲስ አበባ ወጣቶች እና ስፖርት ህንፃ አጠገብ የቦጐሲያን ቤት ይገኛል፡፡ ይህ ቤት እስከ አሁን ድረስ ውበቱ እንደተጠበቀ ያለ ቤት ነው፡፡ ጐጆ ቤት ነው፤ እዚያ ቤት ውስጥ ነው የአፄ ምኒልክ የሬሳ ሳጥን የተገጣጠመውና የተሠራው፡፡ አዲስ አበባ ከተማ ስትጀመር የነበረውን ገፅታ ያሳያል፡፡ እነ ሰባ ደረጃና እነ አርባ ደረጃን የምናይበት ነው፡፡ ቀደም ብዬ እንዳልኩት ከላይ በተጠቀሰው ጊዜ፤ የአርመኖች፣ የህንዶችና የግሪኮች አሻራ ያረፈባቸው ኪነ ህንፃዎች እናያለን፡፡
ከ1928 እስከ 1933 ዓ.ም ደግሞ ጣሊያኖች የራሳቸውን አሻራ ጥለው አልፈዋል፡፡ እነ ቤላ፣ ፖፓላሬ፣ ካዛንቺስ እንዲሁም የጣሊያን እስር ቤትና ፖሊስ ማዘዣ የነበረውን ራስ ሆቴልና ኢሚግሬሽን፣ የጣሊያን ዘመንን የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ከጣሊያን መውጣት በኋላ ከ1933 እስከ 1966 ዓ.ም አዲስ አበባ ውስጥ የተለያዩ ህንፃዎች ተሠርተዋል፡፡ የአፍሪካ ህብረትን፣ ማዘጋጃ ቤቱን፣ ብሔራዊ ትያትር አካባቢ ያሉትን ህንፃዎች፡- መከላከያ ሚ/ር፣ ብሄራዊ ባንክን… መጥቀስ ይቻላል፡፡ እስከ አሁን ድረስ የከተማዋን ውበት የሚያደምቁ ህንፃዎች ናቸው፡፡ ከ1966 እስከ 1983 የደርግ ዘመን ማብቂያ ድረስ ደግሞ የራሺያና የቡልጋሪያ የኪነ-ህንፃ ባለሙያዎች ስራ የሆኑ ህንፃዎችን እናያለን፡፡ ለምሳሌ ሰሜን ኮሪያውያኖቹ የሠሩት ጥቁር አንበሳ ጋ ያለው ሀውልት፣ ከጀርባው ደግሞ የዩጐዝላቪያ ባለሙያዎች ያነፁትን የጥቁር አንበሳ ሆስፒታልን እናገኛለን፡፡ በቦሌ መስመር ላይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የሚኖሩበት አፓርታማዎች በራሺያዎች የተሠሩ ናቸው፡፡ ኢህአዴግ አገሪቷን ማስተዳደር ከጀመረ በኋላም አዲስ አበባ እጅግ በጣም ፈጣን የከተማ እድገት እያሳየች ነው፡፡
ከተማዋ በስፋትም ሆነ በነዋሪዋ ብዛት ከፍተኛ ለውጥ ያመጣችበት ጊዜ ነው፡፡ ከተማዋ እንደ ገርጂ፣ አያት፣ ላፍቶ፣ ገላን፣ አየር ጤና የተባሉ አዳዲስ ሰፈሮችን አካትታለች፡፡ መሀል ከተማዋ ውስጥ ከፍተኛ የግንባታ ስራ እየተሠራ ነው፡፡ እዚህ ላይ ትልቁ ጥያቄ፣ “አዲስ ስንሰራ መነሻችን የሆነውን እንዴት በማድረግ ነው?” የሚለው ነው፡፡ አዲስ የባቡር መስመር ዝርጋታ እየተካሄደ ነው፡፡ ነገር ግን የመጀመሪያው የባቡር ሀዲድ ታሪካዊነቱ ቦታ ተሠጥቶት ጥበቃ አልተደረገለትም፡፡ የከተማዋ ነዋሪ ሳይቀር አፈር እያለበሰ ቤት ሠርቶበታል፡፡ ኤርትራ ውስጥ ከአቆርዳት እስከ ምፅዋ ያለው የባቡር መስመር ለቱሪዝም ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረገ ነው፡፡ ልማቱ ሠለባ ያደረጋቸው ቅርሶች አሉ፡፡ የአልሜክ ስልጣኔን የሚያሳየውና ሜክሲኮ አደባባይ የነበረው የራስ ቅል የተነሳ ሲሆን ተመልሶ ይሠራል የሚል ቃል ተገብቷል፡፡
ከመልሶ ማልማቱ ጋር ተያይዘው የሚነሱ የቅርስ ጥበቃ ጉዳዮች በምን ሁኔታ ላይ ይገኛሉ?
ከተማዋ አማካሪ አላት ወይ? የሚያስብሉ ስህተቶች ተፈፅመዋል፡፡ ለምሳሌ የአራት ኪሎ ሀውልትን የሚሸፍን ድልድይ መስራት ተገቢ አልነበረም፡፡ መስቀል አደባባይ የተሠቀሉ ትልልቅ የማስታወቂያ ሠሌዳዎች የቦታውን ታሪካዊነት ጋርደውታል፡፡ አደባባዩን ባቡሩ ማቋረጡ በራሱ አካባቢውን ለውጦታል፡፡ በአጠቃላይ ስርአት ይመጣል፤ ስርአት ይሄዳል፡፡ ያለፈው የሚባለው ትውልድ ጥሎት የሄደው መቀመጥ አለበት፡፡ የአዲስ አበባን ልማት በተመለከተ ለመነጋገር ማነፃፀር ያስፈልጋል፡፡ የምናነፃጽረው የድሮውን አሳይተን ነው፡፡ ሠፈሮቹን፣ በየሠፈሩ ውስጥ የነበሩ መስተጋብሮችን፣ ማህበራዊ ግንኙነትንና ትስስሩን ማቆየት አለብን፡፡ ስልጣኔ ማለት ትስስሩን ማጥፋት አይደለም፡፡ የተለያየ ርዕዮተ አለም ያልበገራቸውን ትስስሮች መጠበቅ አለብን፡፡ የመጀመሪያው ሲኒማ ቤት ሰይጣን ቤት ይባላል፡፡ ለምን እንደዚያ እንደተባለ የአሁኑ ትውልድ ሊያውቀው በሚገባ መልኩ መተረክና እዛው ቤት ውስጥ መፃፍ አለባት፡፡ በአለም ላይ ሲኒማ ከተፈለሠፈ በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ ቴክኖሎጂው ከደረሳቸው አገሮች አንዷ ኢትዮጵያ ናት፡፡
የፊልም ኢንዱስትሪውን ለማነፃፀር፣ ያንን ቤት መጠበቅ አለብን፡፡ አዲስ አበባ ከተመሠረተች 125 አመቷ ነው ብለን፣ አዳዲስ ህንፃዎችን ብቻ የምናሳይባት ሳይሆን ዕድገቷን ራሷ ማሳየት የምትችል መሆን አለበት፡፡
ቅርሶች በማን ነው የሚያዙት?
ቅርሱን አድሰን እናስተዳድራለን ለሚሉ ወገኖች ይሰጣል፡፡ በግል የተያዙ ታሪካዊ ቤቶች እኮ አሉ፡፡ ልዕልት ማርያም፤ የመሐመድ አሊን ቤት “አዲስ ውበት” በሚባል ድርጅታቸው እንዲያድሱ ተደርጓል፡፡ ሞዴል ሊያ ከበደ፤ የደጃዝማች አያሌው ብሩን ቤት አድሳ ይዛዋለች፡፡ የቀድሞው የአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት የነበረው የቢትወደድ ሃይለጊዮርጊስ መኖርያ ቤት ለቅርስ ባለ አደራ ተላልፏል የሚባል ነገር አለ፡፡ ያ ቤት አሁን መታደስ አለበት፡፡
አቶ አሰፋ ተሰማ፤ የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ የነበሩ ሰው ናቸው፡፡ በአንድ ወቅት ሲናገሩ፤ “ከተሜነት ወሳኝ ነው፤ የአዲስ አበባ አብዛኛው ነዋሪ ከገጠር የመጣ ነው፡፡ የከተሜ የአኗኗር ባህል ሊኖር ይገባል፡፡ ይህ ደግሞ አመራሩ ላይ መንፀባረቅ ይኖርበታል፡፡ አመራሩ ከተሜ መሆን አለበት፡፡ ከተሜነት የግድ ከተማ መወለድ አይደለም፡፡ ከተሜነት ከተማዋ ሊኖራት የሚገባውን ደረጃ ማየት መቻል ነው፡፡ ለምሳሌ ከደብረ ዘይት መንገድ ወደ አዲስ አበባ የሚገባ ሰው መሃል አዲስ አበባ ከተማ መግባቱን እንዲያይ ተብሎ ነው መንገዱ ገለጥ ያለው፡፡ የአንበሳ ህንፃ ዲዛይንም መንገዱን ተከትሎ እንዲሠራ ተደርጐ ነበር…” ብለው ነበር፡፡ በከተማ ዕቅድ የታወቁ ከንቲባዎች የነበሯት ከተማ ናት፤ ለንደንን ዲዛይን ያደረጉ ሰዎች በአዲስ አበባ ማስተርፕላን ላይ ተሳትፎ አድርገዋል፡፡ የእነዚህን ሰዎች ግብአት መጠቀም አለብን፡፡ የግድ ሰዎች ይህ ቦታ ታሪካዊ ነው” እያሉ መጮህ የለባቸውም፡፡ ከተማው ራሱ መናገር አለበት፡፡ መርካቶ አሁን በህንፃ እየተሞላ፣ የቀድሞውን ታሪካዊ እሴት እያጣ ነው፡፡ የግድ ማፍረስ አይጠበቅም እኮ፡፡ ከተማዋ ሠፍታለች፤ ቅርሶቿንና ታሪኳን በማይነኩ ቦታዎች መጠቀም ይቻላል፡፡ ፀሐይ ሪል እስቴትን ማየት ይቻላል፡፡ በአለም ላይ አሮጌና አዲሱ ከተማ ያሉባቸው ቦታዎች አሉ፡፡ ካይሮ ጥሩ ምሳሌ ትሆናለች፡፡ አዲስ አበባንም እንደዚያ መስራት ይቻላል፡፡ “ሠፈሮቹ ያለፈው ስርአት ገዢ መደብ ወይም የነፍጠኛ መቀመጫ ስለነበሩ…” እያለ የሚያስብ ካለ ጤነኛ አይደለም፡፡ ይህ አይነት አስተሳሰብ ያላቸው ከአመራር መወገድ አለባቸው፡፡ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ቡድን ተቋቁሞ የቆየው እስከ 1995 ድረስ ነው፡፡ በ1995 መዋቅር ሲሰራ፣ የቅርስ አስተዳደር፣ ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ውስጥ ገብቶ ነበር፡፡ ብዙ ጥፋት የደረሰው ያን ጊዜ ነው፡፡
በአንተ ዕይታ ኢትዮጵያ ሆቴል አካባቢ ያሉት ህንፃዎች ከምን ይመደባሉ?
በኔ ዕይታ በአጠቃላይ ብሔራዊ ትያትርና አካባቢው ቅርስ ነው፤ ዘመን ተናጋሪ ህንፃዎች ናቸው፡፡ ብሔራዊ ትያትር ጋ ያለው አንበሳ የከተማዋ አርማ ነበር፡፡ በነገራችን ላይ ከንቲባ ዘውዴ በላይነህ ሀውልቱን ሲመርቁ፤ “ይህ አንበሳ አንበሳ ባይመስልም የወጣበት ወጪ ግን አንበሳ አድርጐታል” ማለታቸው ይነገራል፡፡ ሰዓሊ ደስታ ሃጐስም ለቱሪዝም “የ13 ወር ፀጋ”  የሚለውን ስትሰራ የአንበሳውን ፊት በመውሰድ አርማ አድርጋዋለች፡፡ ህንፃዎቹ ብቻ አይደሉም፤ ከፍል ውሃ እስከ ሜትሮሎጂ ጫፍ ያሉት ዛፎች ጭምር ቅርስ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ ሆቴል አጠገብ ምን አይነት ህንፃ ይሠራ ይሆን? ከባድ ነው፡፡ የህንፃው ርዝመትስ ከመከላከያ ሚ/ር አንፃር እንዴት ሊሆን ነው?
ቅርስ በዩኔስኮ ማስመዝገብ ፋሽን እየሆነ የመጣ ይመስላል፡፡ እስቲ ስለሱ ይንገሩኝ…
ብዙ ሰው ቅርሱ የሚጠበቀው ዩኔስኮ ስለመዘገበው ይመስለዋል፡፡ ሌላው ደግሞ ቅርስ ማስመዝገብን ክልሎች ፉክክር የያዙበት ይመስላል፡፡ “የትኛውን መስቀል ነው ያስመዘገባችሁት?” ብሎ የጠየቀ ሃላፊ አለ፡፡ የተመዘገበው አከባበሩ ነው፤ ዩኔስኮ ሃይማኖት አይመዘግብም፡፡ የሶፍኦመርና ድሬ ሼክ ሁሴንን ለማስመዝገብም ጥረት እየተደረገ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ በሺዎች የሚቆጠሩ ባህላዊ አመጋገቦች፣ ከእምነት ጋር የተያያዙ ባህሎች አሉ፡፡ ለነዚህ ሁሉ ዩኔስኮ መዝገቡን ከፍቶ ይጠብቃል ማለት አይደለም፡፡ እንደ ኦሎምፒክ ተወዳድሮ ነው የሚመዘገበው፡፡ ሚ/ር መ/ቤቱም ምዝገባውን በተመለከተ መመሪያዎችን እያወጣ ነው፡፡ ዩኔስኮ አንድን ቅርስ ሲመዘግብ ቅድመ ሁኔታዎች አሉት፡፡ ለምሳሌ ታንዛኒያ አንድ የሆነ ቦታን ቅርስ ብለው ካስመዘገቡ በኋላ፣ ቦታው ላይ ነዳጅ ተገኘ ተባለ፡፡ ነገር ግን ነዳጅ ማውጣት ተከልክለዋል፡፡
ቅርሶችን በዩኔስኮ ማስመዝገብ ምንድን ነው ጥቅሙ?
ቅርሱን ለመጠበቅ የተወሰኑ ዕገዛዎች ይደረጋል፡፡ እኛ አገር በአንዳንድ ቦታ ባህሉን ትተው ለቱሪዝሙ ከፍተኛ ትኩረት ይሰጣሉ፡፡ ለቱሪዝሙ ዋናው ነገር ባህሉ መሆኑን ይረሱታል፡፡
በቅርቡ ለመመዝገብ የደረሰ ቅርስ አለ?
አዎ፤ ደቡብ ክልል ውስጥ ብራይሌ/አንጐይታ በመባል የሚታወቅና በአሁኑ ወቅት ስምንት ሰዎች ብቻ የሚናገሩት ቋንቋ አለ፤ እሱን ለማስመዝገብ ጥያቄ አቅርበን፣ ማስተካከያዎች እንድናደርግ ወደኛ ተልኳል፡፡ የገዳ ስርአትንም ለማስመዝገብ በሂደት ላይ ነን፡፡  

አንዳንድ ታሪክ ጊዜው እጅግ ሲርቅ ተረት ይሆናል፡፡
በጥንት ዘመን አንድ ሮማዊ ጀግና ወታደር ነበር ይባላል፡፡ አያሌ ጦርነቶችን በአሸናፊነት ተወጥቷል፡፡ አብዛኛውን ህይወቱን በጦር ሜዳ ስላሳለፈ በአካል የሚያውቀው ሰው የለም፡፡ ዝናው ግን በሰፊው ይወራል፡፡
አንድ ጊዜ ታዲያ አጠቃላይ ምርጫ በሀገሪቱ ሲካሄድ ያ ጀግና ፖለቲካ ውስጥ መግባት አለብኝ ብሎ ወሰነ፡፡ ስለዚህም በምርጫው ለከፍተኛው የፓርላማ ቦታ ይወዳደር ጀመር፡፡ በዚያን ጊዜው የሮማውያን የምርጫ ባህል ጥሩ ዲስኩር (ንግግር) ማድረግ ግድ ነበር፡፡ ጀግናው ንግግሩን የጀመረው ለዓመታት ለሮማ ሲዋጋ በጥይት ብዙ ቦታ ቆስሎ ነበርና ገላው ላይ ጠባሳዎቹን በማሳየት ነበር፡፡ ህዝቡ ከንግግሩ ይልቅ ጠባሳዎቹን እያየ ዕንባ በዕንባ ተራጨ፡፡ የዚያ ጀግና በምርጫው አሸናፊነት ከሞላ ጐደል የተረጋገጠ መሰለ፡፡
ታዲያ የዋናው ምርጫ ቀን ያ ጀግና በመላው የፓርላማ አባላትና በመሳፍንቱና በመኳንንቱ ታጅቦ ወደ መድረኩ ብቅ አለ፡፡ ህዝቡ ግራ ተጋባ፡፡ “በእንዲህ ያለ የምርጫ ቀን ይሄ ሁሉ ጉራ ለምን አስፈለገ?” ይባባል ጀመር፡፡   ያ ጀግና ንግግር ሲያደርግ አጃቢዎችንና ሀብታሞችን የሚያወድስ፣ በትዕቢትና በጉራ የተሞላ፣ የጦር ሜዳ ድሎቹን እያሳቀለ ከኔ ወዲያ ጀግና ላሳር ነው ይል ጀመር፡፡ ተፎካካሪዎቹንም አንተና አንቺ እያለ ያዋርድ ገባ፡፡ ቀልድ አወራሁ ብሎ የሚናገራቸው ወጐች ራሳቸው የሰው ሞራል የሚነኩና ህዝቡን የሚያበሳጩ ሆኑ፡፡ “ለሮማም እስከዛሬ ታይቶ የማይታወቅ ልማትና ሀብት አመጣላታለሁ!” እያለ በከፍተኛ መወጣጠር መድረኩ ላይ ተንጐራደደ፡፡
ህዝቡም “ያ እንደዚያ ዝናው የተወራ የጦር ሜዳ ጀግና እንዲህ ያለ ቱሪናፋ ነው እንዴ?” አለ፡፡ ወሬው በአገሪቱ ሙሉ ወዲያው ተሰማ፡፡ “ይሄንንማ ፈፅሞ አንመርጥም፡፡ እንዳይመረጥም ላልሰማው ህዝብ መናገር አለብን”፤ አለ ህዝቡ፡፡ ጀግናው ድምፅ አጣ! ሳይመረጥ ቀረ፡፡ ወደ ጦር ሜዳው ተመለሰ፡፡ “ያልመረጠኝን ህዝብ አሳየዋለሁ፡፡ እበቀለዋለሁ!” ይል ጀመር፡፡
ከጥቂት ሳምንታት በኋላ ወደ ሮማ የእርዳታ እህል በመርከብ መጣ፡፡ ምክር ቤቱ በነፃ ይታደል አለ፡፡ ያ ጀግና “ይሄ እህል በነፃ መታደል የለበትም፡፡ እምቢ ካላችሁ ጦር ሜዳውን ትቼላችሁ እመለሳለሁ” እያለ ያስፈራራ ጀመር፡፡ ይሄን ወሬ ምክር ቤቱ ለህዝቡ ነገረ፡፡ ህዝቡ ተቆጣ፡፡ “ያ ጀግና እፊታችን ቀርቦ ያስረዳ” አለ፡፡ ጀግናው ደግሞ “ህዝብ ብሎ ነገር አላቅም፡፡ ዲሞክራሲም አልቀበልም፡፡ አልመጣም” አለ፡፡ ህዝብ አደባባይ ወጥቶ ጮኸ፡፡ ምክር ቤቱ ያን ጀግና የግዱን እንዲመጣ አደረገውና ሸንጐ መድረክ ላይ ቆሞ እንዲናገር ታዘዘ፡፡ ጀግናውም አሁንም በእልህና በትእቢት ሁሉንም መሳደቡን ቀጠለ፡፡ ህዝቡ በሆታ አስቆመው፡፡ ለፍርድ ይቅረብልን አለ፡፡ ምክር ቤቱ ምንም ምርጫ አልነበረውም፡፡ ለፍርድ አቀረበው፡፡ በዚያን ዘመን ወንጀለኛ ቀጣበት በነበረው፤ ከከፍተኛ ተራራ ወደ መሬት ይወርወር፤ የሚል ሀሳብ ቀረበ፡፡ ሆኖም አስተያየት ተደርጐ ቅጣቱ እድሜ ልክ ይሁንለት ተባለና ዘብጥያ ተወረወረ! ህዝቡ በሆታና በዕልልታ መንገዱን ሞላው፡፡
                                                           ***
ሰዎችን በንግግር እንማርካለን ብለን ብዙ በለፈለፍን ቁጥር ብዙ ከቁጥጥራችን የሚወጡ ነገሮች ይከሰታሉ፡፡ ጠንካራና ልባም ሰዎች ጥቂት ምርጥ ነገሮችን ብቻ በመናገር የሰውን ልብ ይነካሉ፡፡ ስለዚህ ከአንደበታችን በመቆጠብ፣ ትሁት በመሆን፣ ህዝብን ባለመናቅ፣ ለምንናገረው ነገር የቤት-ሥራችንን ጠንቅቀን በመስራትና ጉዳያችንን በማወቅ ነው ለውጥ ለማምጣት የምንችለው፡፡
ከሁሉም በላይ ተአብዮ አገርንና ህዝብን ይጐዳል፡፡ ከማንም በላይ ነኝ እና አምባገነንነት የተአብዮ (የእብሪት) ልጆች ናቸው፡፡ ንቀት፣ ሰው-ጤፉነት፣ ሁሉን አውቃለሁ ባይነት፣ ቆይ-አሳይሃለሁ - ባይነት፤ ብቆጣም እመታሻለሁ ብትቆጪም እመታሻለሁ ማለት፤ የማታ ማታ ከላይ የተጠቀሰውን የጦር-ሜዳ ጀግና ዕጣ-ፈንታ የሚያሰጠን መሆኑ አሌ አይባልም፡፡ ከበደ ሚካኤል፤
“ኩራትና ትእቢት፣ የሞሉት አናት
ሰይፍና ጐራዴ፣ የመቱት አንገት
አይገላገሉም እንዲህ በቀላሉ
እመሬት ላይ ወድቀው ሳይንከባለሉ”
የሚሉን ለዚህ ነው፡፡
ከልክ ያለፈ ውዳሴና ማሞካሸትም ከጥቅሙ ጉዳቱ ነው የሚያመዝነው፡፡ ተወዳሹ እስኪታዘበን ድረስ ብናሳቅለው ለማንም የማይበጅ ንግግር እንዳቀረብን ነው የሚቆጠረው፡፡
ፀጋዬ ገብረመድህን፤
“ጅላጅል ምላስ ብቻ ናት
ማሞካሸት የማይደክማት”
የሚለን ለዚህ ነው፡፡
እናስተውል፡፡ ብዙ እዩኝ እዩኝ ደብቁኝ ደብቁኝን እንደሚያስከትል አንርሳ፡፡ ብዙ በተናገርን ቁጥር አልባሌና ዝቅ የሚያደርጉንን ጥፋቶች ለመስራት በር እንከፍታለን፡፡ ታዋቂው ሳይንቲስትና የጥበብ ሰው ሊዮናርዶ ዳቬንቺ፤
“ኦይስተሮች (Oysters) ጨረቃ ሙሉ በሆነች ሰዓት አፋቸውን ሙሉ በሙሉ ይከፍታሉ፡፡ ይሄኔ ክራቦች (Crabs) የባህር አረምን ኦይስተሮቹ አፍ ውስጥ ይሰገሰጋሉ፡፡ አፋቸው መንቀሳቀስ ያቅተዋል፡፡ ከዚያ የክራቦቹ ምግብ ይሆናሉ፡፡ አፉን ያለልክ የሚከፍት የማንም ሰው ዕጣ-ፈንታ ይሄው ነው፡፡ የአድማጩ ሰለባ ይሆናል” ይለናል፡፡
ባልባለቀ አእምሮና ባልበሰለ አንደበት ስንቶችን ልናስቀይም እንደምንችል እናጢን፡፡ “እዛም ቤት እሳት አለ” የሚለውን ተረት ከልቦናችን አንለይ፡፡ ከቶውንም እኔ አውቃለሁን ስንፈክር ሌላውም ያውቃልን አንርሳ፡፡ ባደባንበት ሊደባብን እንደሚችል፣ ደባ ራሱን ስለት ድጉሱን መሆኑን፣ ሥራ ለሰሪው እሾክ ላጣሪው እንደሚሆን አንዘንጋ፡፡ የወላይታው ተረት - “የኛ ቤት ጠማማነት እኛን ይጨርሳል፤ አለ እንጨት” የሚለን ይሄንኑ ነው!