አሚጎስ የገንዘብ'ና ብድር ህብረት ስራ ማህበር ለ4ኛ ዙር ስልሳ ዘጠኝ ዘመናዊ መኪኖችን በአሮጌ ላዳ ታክሲዎች ለማህበሩ ቆጣቢዎች'ና ብድር ተጠቃሚዎች ቀይሯል።
ይህ የገንዘብና ቁጠባ ብድር ህብረት ስራ ማህበር ላለፉት አስር ዓመታት ከሰባት ሺ በላይ አካላትን በማቀፍ እንዲሁም ለሶስት ሺ ሰዎች የብድር አገልግሎት በመስጠት በርካቶች ራሳቸውን'ና ቤተሰቦቻቸውን ወደ ተሻለ ህይወት እንዲቀይሩ የድርሻውን የተወጣ ማህበር ነው።
አሚጎስ በአዋጅ ቁጥር 147/91 እና ይሄንን አዋጅ ለማሻሻል በወጣ አዋጅ ቁጥር 402/96 መሰረት ተመዝግቦ የሚንቀሳቀስ ሲሆን ፤ዛሬ በጎልደን ቱሊፕ ሆቴል ስልሳ ዘጠኝ ዘመናዊ የታክሲ አገልግሎት የሚሰጡ መኪኖችን የሚዲያ አካላት በተገኙበት ለተጠቃሚዎች አስረክቧል።
የአሚጎስ መስራች'ና የኮርፖሬት ሴልስ ኃላፊ የሆኑት አቶ እንዳልካቸው በሀይሉ እንደተናገሩት ከሆነ፡ድርጅታቸው አሁን ላይ ለግለሰቦች እስከ አስር ሚሊዮን ብር የሚደርስ ብድር የማቅረብ አቅም አለው ያሉ ሲሆን ፤በእስካሁኑ የስራ ቆይታቸውም አራት ቢሊዮን ብር ብድር እንዳቀረቡና አንድ ሺ አምስት መቶ መኪኖችንም በብድር መያዣቸውን አብራርተዋል።
ከስድስት ወር እስከ አስር ዓመት ድረስ ሊቆይ በሚችል የብድር አከፋፈል ስርዓት ማንኛውም ግለሰብ ሆነ ማህበራት ለመኪናም ሆነ ለቤት ግዥ የሚሆን የብድር አገልግሎት ከአንድ ወር እስከ ሶስት ወር ባለ ጊዜ ውስጥ ብድር ማግኘት ይችላል ብለዋል።
አሚጎስ ኦክሎክ ጀነራል ትሬዲንግ የሚያስመጣቸውን መኪኖች በብድር ተጠቃሚ ያደረጋቸው የታክሲ ማህበራት ፡አዲስ ምቾት ፡ሀገሬ የታክሲ ማህበር ፡ገፅታ የተሰኙ ሲሆን ሌሎች ማህበራትም የዚህ እድል ተጠቃሚ እንደሆኑ ጥሪ አቅርቧል።
Published in
ዜና