Saturday, 14 February 2015 12:58

መኢአድ እና አንድነት እጩዎችን አስመዝግበዋል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)
  • “ሠማያዊ ፓርቲ የኔን መዋቅር ተጠቅሞ ነው እጩ ያስመዘገበው” አንድነት ፓርቲ  
  • -“እጩዎቻችንን ለማስመዝገብ ከቦርዱ አስፈፃሚዎች ተግዳሮት ገጥሞናል” ሰማያዊ ፓርቲ

      በቅርቡ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በአቶ ትዕግስቱ አወሉ እየተመራ ወደ ምርጫ እንዲገባ የወሰነለት እና በአቶ አበባው መሃሪ እንዲመራ የተወሰነው መኢአድ በምርጫው ለመወዳደር እጩዎቻቸውን ማስመዝገባቸውን ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተገኘው መረጃ ጠቁሟል፡፡
አንድት ፓርቲ ከ200 በላይ እጩዎች ማስመዝገቡን ያስታወቀ ሲሆን መኢአድ በበኩሉ፤ መረጃዎቹ ተጠናቅረው አልደረሱኝም ብሏል፡፡ ከብሄራዊ ምርጫ ቦርድም ፓርቲዎቹ ያስመዘገቧቸው እጩዎችን ብዛትን በተመለከተ ማረጋገጫ ማግኘት አልተቻለም፡፡  
የአንድነት ፕሬዚዳንት አቶ ትዕግስቱ አወሉ፤ ቦርዱ ፓርቲውን እንዲመሩ ከወሰነ ጊዜ አንስቶ ከቢሮ መረካከብ ጋር በተፈጠረው የጊዜ መጓተት ምክንያት በ5 ቀናት ውስጥ ብቻ በአዲስ አበባ ሃያ ሶስቱም የምርጫ ክልሎች ጨምሮ ከሱማሌ፣ ጋምቤላና ትግራይ በስተቀር በሌሎች ክልሎች 201 እጩዎችን ማስመዝገብ መቻላቸውን ገልፀዋል፡፡
ለሌሎች ፓርቲዎች የተሠጠው 49 ቀን ሲሆን ለእነሱ 7 ቀን ብቻ እንደተሰጠና ፓርቲው በ5 ቀን ብቻ እጩዎቹን ለማስመዝገብ መገደዱ የፈለገውን ያህል እጩ ማቅረብ እንዳላስቻለው የጠቀሱት አቶ ትዕግስቱ፤ በማስመዝገብ ሂደቱ ፓርቲው በውዝግብ ውስጥ ማለፉ ተግዳሮት እንደፈጠረባቸው ተናግረዋል፡፡
የተፈጠረውን ውዝግብ ተከትሎም አባላት ወደ ሠማያዊ ፓርቲ መቀላቀላቸው፣ ሠማያዊ ፓርቲ የኛን መዋቅር ተጠቅሞ እጩዎቹን ለማበራከት አስችሎታል ያሉት አቶ ትዕግስቱ፤ የአንድነትን አባላት ማስመዝገቡ የተገቢነት ጥያቄ ያስነሳል ነው ብለዋል፡፡ “ሠማያዊ ፓርቲ በተለይ በደቡብ፣ በኦሮሚያ እና በአማራ የተለያዩ ቦታዎች ላይ የአንድነት አባላትን አስመዝግቧል” ያሉት የአንድነት ሊ/መንበር፤ ይህም ፓርቲው ቀደም ሲል በአካባቢዎቹ መዋቅር እንዳልነበረውና አጋጣሚውን እንደተጠቀመ ያመለክታል ብለዋል፡፡ “የኛ ሰዎች ባይኖሩ ሠማያዊ ፓርቲ ምን ያስመዘግብ ነበር?” ሲሉ አቶ ትዕግስቱ ጠይቀዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን የሠጡን የሠማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ በበኩላቸው፤ እንኳን ከአንድነት ወደ ሠማያዊ የተቀላቀሉትን ቀርቶ የፓርቲውን ነባር አባላት እንኳ ለማስመዝገብ ችግር ገጥማቸው እንደነበር ጠቅሰው በተለይ ጐጃም ውስጥ ለፓርላማ 10 እጩዎችን እንዳናስመዘግብ ተደርገናል ብለዋል፡፡ ደቡብ እና ኦሮሚያ ላይ በግልጽ ሠማያዊ ፓርቲን የተቀላቀሉ የአንድነት አባላት መኖራቸውን የጠቆሙት አቶ ዮናታን፤ አዲስ አበባ ላይም ከ23 ቦታዎች በ4ቱ የአንድነት አባላት የነበሩት ይወዳደራሉ ብለዋል፡፡
ሠማያዊ ፓርቲ ከመነሻው 380 መቀመጫ ለማሸነፍ አልሞ 400 እጩዎችን እንደሚያቀርብ አረጋግጦ ወደ ምርጫው እንቅስቃሴ መግባቱን የጠቆሙት አቶ ዮናታን፤ የአንድነት አባላት የነበሩት በፖለቲካ ትግሉ ያበረከቱት አስተዋጽኦ እየተመዘነ ለቦታዎቹ ታጭተው የነበሩ የሠማያዊ ፓርቲ አባላትን በመተካት እንዲገቡ ተደርጓል እንጂ ሠማያዊ የእጩ ችግር የለበትም ብለዋል፡፡ ለአንድነት የተመዘገቡ እጩዎች ሣይቀሩ ከአንድነት ለቀው ለሠማያዊ የመመዝገብ መብትም እንዳላቸው ሊታወቅ ይገባል ብለዋል አቶ ዮናታን፤ የመኢአድ የምርጫ አስተባባሪ በበኩላቸው፤ ፓርቲው በተሰጠው አጭር ጊዜ ውስጥ እጩዎቹን ለማስመዝገብ መሞከሩን ጠቅሰው ምን ያህል እጩዎች ተቀባይነት አግኝተው ተመዘገቡ የሚለውን ለማወቅ ገና ጥረት እያደረጉ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

Read 1505 times