Saturday, 29 November 2014 10:44

ለኢቦላ ዘመቻ 1100 ኢትዮጵያውያን በጐ ፈቃደኞች ተመዝግበዋል

Written by  መታሰቢያ ካሣዬ
Rate this item
(8 votes)

የኢቦላ በሽታን ለመቆጣጠር ለሚደረገው ዘመቻ 1100 በጐ ፈቃደኛ ኢትዮጵያውያን መመዝገባቸውንና ከእነዚህ መካከል 210 የሚሆኑት በያዝነው ወር መጨረሻ ላይ በሸታው ወደሚኝባቸው የምዕራብ አፍሪካ አገራት እንደሚሄዱ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
የሚኒስቴሩ የሥራ ኃላፊዎች ከትናንት በስቲያ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት የአፍሪካ ህብረት ባቀረበው ጥሪ መሰረት ኢትዮጵያ በጐ ፈቃደኛ የጤና ባለሙያዎችን በሽታው ወደሚገኝባቸው አገራት ለመላክ እንቅስቃሴ ስታደርግ ቆይታለች፡፡ በዚህ መሰረትም በአገሪቱ ለሚገኙ የጤና ባለሙያዎች በቀረበው ጥሪ መሰረት 1100 የሚሆኑ በጐ ፈቃደኛ የጤና ባሙያዎች ማለትም ዶክተሮች፣ የህብረተሰብ ጤና መኮንኖች፣ ነርሶች፣ ፊልድ ኢፒዶሞሎጂስቶች፣ ሳይካትሪስቶች፣ ሳይኮሎጂስቶች፣ የአካባቢ ጤና፣ የጤና ትምህርት፣ የላብራቶሪና የፋርማሲ ባለሙያዎች ተመዝግበዋል፡፡ ከእነዚህ ተመዝጋቢዎች መካከልም 210 የሚሆኑት ተመርጠው ወደስፍራው እንዲሄዱ ተወስኗል፡፡ እነዚህ ተጓዦች ወደ ስፍራው ከመንቀሳቀሳቸው በፊት በቂ ስልጠናና ትምህርት የተሰጣቸው ሲሆን በሽታው ወደሚገኝባቸው የምዕራብ አፍሪካ ሶስት አገራት ማለትም ላይቤሪያ፣ ሴራሊዮንና ጊኒ እንደሚጓዙም ኃላፊዎቹ ተናግረዋል፡፡
የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ቴክኒካል አማካሪ ዶ/ር መርሃዊ ይርዳው እና የሚኒስቴር መ/ቤቱ ህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አህመድ አሚኖ በጋራ በሰጡት በዚሁ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት አገሪቱ ከህብረቱ የቀረበላትን ጥሪ ተቀብላ በግንባር ቀደምትነት አጋርነቷን ለማሳየት የምታደርገውን ጥረት በመደገፍ ወደ ስፍራው ለመጓዝ በርካታ ቁጥር ያላቸው በጐ ፈቃደኛ ኢተዮጵያውያን ተመዝግበዋል፡፡ አገሪቱ ባለሙያዎችን ወደ ስፍራው ከመላኳም በተጨማሪ 500ሺ የአሜካን ዶላር በሽታው ለመቆጣጠር ለሚደረገው ጥረት ድጋፍ ታደርጋለች፡፡
በጐ ፈቃደኛ የጤና ባለሙያዎቹ በተባበሩት መንግስታት ስታንዳርድ መሰረት የሚከፈላቸው መሆኑንና የክፍያው መጠንም ወደፊት እንደሚገለፅ ተናግሯል፡፡ የበጐ ፈቃድ ተጓዦቹ በያዝነው ወር መጨረሻ ወደ ስፍራው እንደሚጓዙም ኃላፊዎቹ በጋዜጣዊ መግለጫቸው ላይ ተናግረዋል፡፡

Read 1979 times