Monday, 03 November 2014 07:34

ትውልደ ኢትዮጵያዊው በቦስተን የቦንብ ጥቃት ተከስሶ ጥፋተኛ ተባለ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

እስከ 16 አመት የሚደርስ እስር ሊፈረድበት ይችላል

የ21 አመቱ ትውልደ ኢትዮጵያዊ ወጣት ሮቤል ፊሊጶስ፤ የአሜሪካ ፖሊስ ባለፈው ሚያዝያ ወር በቦስተን ማራቶን ውድድር ላይ በተከሰተው የቦንብ ጥቃት ዙሪያ በሚያደርገው ምርመራ ሃሰተኛ መረጃ ሰጥቷል፤ ምርመራውን ሆን ብሎ አስተጓጉሏል በሚሉ ሁለት ክሶች ባለፈው ማክሰኞ በቦስተን ፌደራል ፍርድ ቤት ቀርቦ ጥፋተኛ መባሉ ተዘገበ።
ፍንዳታው ከደረሰ ከሶስት ቀናት በኋላ፣ የቦንብ ጥቃቱ ፈጻሚ ነው ተብሎ በሚጠረጠረው ዞካር ሳርኔይ የተባለ ግለሰብ ክፍል ውስጥ የነበሩ ማስረጃዎችን አሽሽተዋል ከተባሉ ሶስት ሰዎች ጋር እንደነበር የተጠረጠረውና የግለሰቡ ጓደኛ የሆነው ወጣት ሮቤል ፊሊጶስ፣ በመጭው ጥር ወር መጨረሻ በቀረቡበት ክሶች በእያንዳንዳቸው እስከ ስምንት አመት የሚደርስ የእስራት ቅጣት ሊጣልበት እንደሚችል ተነግሯል፡፡
ሮቤል በወቅቱ አደንዛዥ ዕጽ ተጠቅሞ ስለነበር፣ በክፍሉ ውስጥ ስለተፈጠረው ነገር ማስታወስ ባለመቻሉ እንጂ ሆን ብሎ አልዋሸም ያሉት የሮቤል ጠበቆች፣ ይግባኝ እንደሚጠይቁ ተናግረዋል፡፡
ሶስት ሰዎችን ለሞት፣ ከ260 በላይ ሰዎችንም ለመቁሰል አደጋ የዳረገውን የቦንብ ጥቃት ፈጽሟል ተብሎ የተጠረጠረው ዞካር ሳርኔይ፣ በመጪው ጥር ፍርድ ቤት እንደሚቀርብ የጠቆመው ዘገባው፤ ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘ እስከ ሞት የሚደርስ  ቅጣት ሊጣልበት እንደሚችል ታውቋል፡፡

Read 1205 times