Administrator

Administrator

 ሁዋዌ ስመጥር የስዊዝ ዲዛይን ስሪትና የስማርት ቴክኖሎጂን በማጣመር የተፈበረከ፣ የላቀ የስክሪን ጥራት ያለው ዘመናዊ የእጅ ሰዓት ለገበያ አቀረበ፡፡
ዓይንን በሚስብ ገፅታ በዘርፉ አንጋፋ በሆኑ ባለሙያዎች በጥንቃቄ የተፈበረከው ሁዋዌ የእጅ ሰዓት፤ በአዳዲስ የሰዓት ቴክኖሎጂዎችና ከፍተኛ አቅም ባላቸው ጥሬ ዕቃዎች ተሰርቶ ለገበያ የቀረበ ሲሆን የነባሩን የእጅ ሰዓት አሰራር በአዲስ ቴክኖሎጂ በማራቀቅ ዘመኑን የሚወክል ምርት ነው ተብሏል፡፡
የሁዋዌ አዲሱ የእጅ ሰዓት የዕለት እንቅስቃሴዎን ማገዝ በሚችሉ ቴክኖሎጂዎች የተሞላ ሲሆን ተጠቃሚዎች እጅ ላይ በማሰር በማንኛውም እንቅስቃሴ ወቅት ሊጠቀሙበት የሚችሉት ነው፡፡ በተገጠመለት እንቅስቃሴን የሚለይ ቴክኖሎጂ አማካኝነት ተጠቃሚዎች በሚራመዱበት፣ በሚሮጡበት አልያም ተራራ በሚወጡበት ጊዜ የሰውነት እንቅስቃሴ መለየት እንደሚያስችልም ተነግሯል፡፡
ሁዋዌ የእጅ ሰዓት የአንድሮይድ ቴክኖሎጂን የሚጠቀም ሲሆን ተጠቃሚዎች የሚሹትን ወቅታዊ መረጃዎች የሚያገኙበት እንደሆነ ታውቋል፡፡ የእጅ ሰዓቱ ሙዚቃ፣ አፕሊኬሽኖችንና ጎግልን ጭምር መጠቀም የሚያስችል ቴክኖሎጂ አለው ተብሏል፡፡

ሽልማቱን ያሸነፈ የመጀመሪያው የዘፈን ግጥም ደራሲ ነው

የ75 ዓመቱ የሮክ ሙዚቃ አቀንቃኝ አሜሪካዊው ቦብ ዳይላን በዘፈን ግጥሞች ደራሲነቱ የ2016 የሥነ ፅሁፍ የኖቤል ሽልማት አሸናፊ ሆነ፡፡ “በታላቁ የአሜሪካውያን የዘፈን ባህል ውስጥ አዲስ ቅኔያዊ አገላለፅ በመፍጠሩ ነው” ለሽልማቱ የበቃው ተብሏል።
እ.ኤ.አ በ1993 ዓ.ም የረዥም ልብ ወለድ ደራሲው ቶኒ ሞሪሰን የሥነ ፅሁፍ የኖቤል ሽልማት ከወሰደ በኋላ ይሄን ሽልማት ያሸነፈ የመጀመሪያው አሜሪካዊ ሆኗል፤ ቦብ ዳይላን፡፡ ይሄን እጅግ የተከበረ ሽልማት ያሸነፈ የመጀመሪያው የዘፈን ግጥም ደራሲም ነው ተብሏል፡፡
ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ሽልማቱን በተመለከተ በሰጡት አስተያየት፤ “በጣም ይገባዋል›› ብለዋል። “ከምወዳቸው ገጣሚያን አንዱ የሆንከው ገጣሚ፣ እንኳን ደስ ያለህ” ሲሉ በትዊተራቸው ላይ አስፍረዋል - ኦባማ፡፡ የስዊዲሽ አካዳሚ ዋና ፀሐፊ ሳራ ዳኒዩስ፤ ቦብ ዳይላን ለሽልማቱ የተመረጠው “በእንግሊዝኛ ተናጋሪው ማህበረሰብ ዘንድ ታላቅ ገጣሚ ስለነበር ነው” ብለዋል፡፡
“ለ54 ዓመት ያህል በሙያው ውስጥ ራሱን ሲፈጥር ኖሯል፤ ያለማቋረጥ አዲስ ማንነት በመፍጠር” ሲሉ ሳራ ዳኒዩስ፤ ለሪፖርተሮች ተናግረዋል፡፡

“የስልጣን ፍላጎት የሌለው አካል መቋቋም አለበት”
አቶ ወንድወሰን ተሾመ (የኢዴፓ አመራር)
የነዚህ ቀውሶች መነሻ ምክንያቶች በርካታ ናቸው፡፡ ወደ መፍትሄው ለመሄድ ከተፈለገ ግን የፖለቲካ ስልጣን ፍላጎት የሌለው አካል መቋቋም አለበት፡፡ ውይይቶች በስፋት ከተደረጉ ብዙ ችግሮች ሊፈቱ ይችላሉ፡፡ መንግስት አሁን ባለው ሁኔታ በመደበኛ ተግባሩ ላይ ቀጥሎ ሂደቱ መካሄድ አለበት እንጂ የሽግግር መንግስት ምናምን የሚለው የማያስኬድ ነው፡፡ ለስልጣን ፍላጎት የሌለው ገለልተኛ አካል ተቋቁሞ፣ ብሄራዊ እርቅ ላይ ጠንከር ተብሎ መሰራት አለበት፡፡ “መንግስት የመፍትሄው አካል መሆን የለበትም፣ የሽግግር መንግስት ይቋቋም” በሚለው ሃሳብ አልስማማም፡፡ የሽግግር መንግስት ይቋቋም ቢባል ማን ነው የሚያቋቁመው? ስለዚህ አንድ ነፃ አካል የግዴታ መቋቋምና ሃሳቦች የሚንሸራሸሩበትን እድል መክፈት ያሻል እንጂ ይህ ስርአት እንደወደቀ አድርጎ የሽግግር መንግስት መቋቋም አለበት የሚለው እኔ ብዙም አይታየኝም፡፡

===========================

“ተቃውሞ የሚገታው ጥያቄዎችን በመመለስ ነው”

በላይ ማናዬ (ጋዜጠኛና ጦማሪ)
በኔ ግምት የተቃውሞዎቹ መነሻ የመብት ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ህዝቡ የመብት ጥያቄ ማንሳቱ ደግሞ የተነፈጉ መብቶች መኖራቸውን ነው የሚያመለክተው፡፡ ጥያቄዎቹ በሰላማዊ መንገድ ነበር የተጀመሩት፡፡ መንግስትም ህገ መንግስታዊ ናቸው ብሎ ያመነበት ሁኔታ ነበር፡፡ በተለይ የማስተር ፕላኑን ጉዳይ በተመለከተ በአግባቡ እያወያዩ ለህዝቡ ምላሽ በመስጠት ረገድ የታየው ዳተኝነት የችግሩ መነሻ እንደነበር መንግስት ራሱ ሲገልፅ ነበር፡፡ ስለዚህ በኔ እምነት የእነዚህ ሁሉ ተቃውሞዎች መነሻ ህዝቡ የተነጠቀው መብት መኖሩ ይመስለኛል።
መንግስት ለነዚህ ተቃውሞዎች ምላሽ የሰጠበት መንገድ አጥጋቢ ነው ብዬ አላስብም፡፡ በተለይ በሰለጠነ መንገድ ይበልጥ ውይይቶችን እየፈቀደ፣ የህዝብን ጥያቄ ለመመለስ ያደረገው ጥረት ዝቅተኛ ነው፡፡ ለዚያም ነው ተቃውሞዎቹ እየበረቱ የሄዱት። የህዝቡ ተቃውሞ አሁን በያዘው ቅርፅና መልክ ወደተለያዩ ቦታዎች ሳይዳረስና ሳይስፋፋ፣ከህዝቡ ጋር በሰፊው ተነጋግሮ መፍትሄ ለመስጠት ይቻል ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡ በእርግጥ የተቃውሞ ድምፆች በፓርላማው ሊኖር ይገባ ነበር፡፡ የህዝብ መተንፈሻ መኖር ነበረበት፡፡  ይህ በሌለበት ሁኔታ የታመቀ ነገር ይኖራል፡፡ የታመቀ ነገር ደግሞ ይፈነዳል፡፡ አሁን እያየን ያለነው እንዲህ ያለውን ነገር ነው፡፡
የዘገዩ ነገሮች እንዳሉ ባምንም አሁንም ቢሆን በትልቁ መፍትሄውን ማሰብ እንችላለን፡፡ ሁሉን አቀፍ ለውጥ የሚያመጣ መድረክ አዘጋጅቶ በውይይት መቀራረብ ያሻል፡፡
መንግስት ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ተነጋግሮ መፍትሄ ሊያበጅ ይችላል። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ረጅም ጊዜን ይወስዳል። በነዚህ ጊዜያት መንግስት የበለጠ ከህዝቡ ጋር መወያየትና ህዝቡን አዳምጦ ተገቢ ምላሾችን ሊሰጥ ይገባል፡፡ የተቃውሞዎቹ መግቻ ነው ብዬ የማምነው፣ከስር ከስር ጥያቄዎችን እየመለሱ መሄድ ነው፡፡  

============================

“የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁም ወደ መፍትሄው የሚወስደን መሆን አለበት”
ጁሃድ ሳዲቅ  (የጋዜጣ አምደኛ)

በእኔ እይታ አሁን ያለው ተቃውሞ ዋናው መንስኤ የዲሞክራሲ እጦት ነው፡፡ የመናገር፣ ሃሳብን የመግለፅ የመሳሰሉት መብቶች በሚገባ  በተግባር ላይ አልዋሉም፡፡ የፕሬስ ነፃነቱም በሚገባ አልተተገበረም። ዲሞክራሲ ሳይኖር ደግሞ ሰላምና መረጋጋት ሊኖር አይችልም፡፡ የሁሉም ነገር ዋና ማዕከል ዲሞክራሲ ነው፡፡ መንግስት ዲሞክራሲን ረስቶታል ማለት እንችላለን፡፡ ሁልጊዜ ስለ ልማት ብቻ ነው የሚነሳው፡፡ እርግጥ ልማትን ሁሉም ይደግፈዋል፤ ለሀገራችን እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ ትልቁ ክፍተት ዲሞክራሲን ከልማት ጋር በሚገባ ማያያዝ አለመቻሉ ነው፡፡ መንግስት ለዚህ ቶሎ መፍትሄ መስጠት አለበት፡፡ ሌላው የፕሬስ ነፃነትን የተመለከተ ነው፡፡ በቅርቡ ሶሻል ሚዲያውን ዘግቷል። ያሉት ፕሬሶች መንግስት የሚገልፀውን ብቻ ዋቢ አድርገው የሚጠቀሙ ናቸው፤ ራሳቸው አጀንዳ ቀርፀው አይሰሩም። ህብረተሰቡ ከነሱ ያጣውን ለማግኘት ወደ ማህበራዊ ሚዲያው አዘንብሏል፡፡ የትኛውም ሰው ሃሳቡን የሚገልጽበት ነፃ መድረክ ሆኗል፡፡ ውጭ ሀገር ሆነው የሚፅፉ ሰዎች አሉ፡፡ ሰው የነሱን ሀሳብ ይከተላል፡፡ ለዚህ መፍትሄው መንግስት ፕሬሱን በሰፊው መክፈት ነው፡፡
በሌላ በኩል የምርጫ ስርአት መስተካከል አለበት። ተቃዋሚዎች የህዝብ ወኪልና ጆሮ እንደመሆናቸው ህዝባቸውን የሚወክሉበት በቂ ቦታ ማግኘት አለባቸው፡፡ አለበለዚያ የወሰዱት የህጋዊነት ፍቃድ የግድግዳ ላይ ጌጥ ይሆናል ማለት ነው፡፡ አሁንም መንግስት ወደ ድርድርና ንግግር መምጣት አለበት፡፡ ለተቃዋሚ ፖለቲከኞች ሰፊ መድረክ መስጠት አለበት፡፡ ለሀገር ውስጥ ተቃዋሚ ቦታ የማይሰጥ ከሆነ፣ ማህበረሰቡ ውጭ ወዳለው ተቃዋሚ ያዘነብላል፡፡ ውጭ ሀገር ያለው የፖለቲካ ቡድን ሀገር ውስጥ ካለው ጋር ብዙ ግጭቶች አሉበት፡፡ ህዝቡ ግን አማራጭ ሲያጣ ወደነሱ ይሄዳል፡፡ ስለዚህ ተቃዋሚዎችን በሚገባ አቅርቦ መወያያት አለበት፡፡
ሌላው ተቃውሞዎቹ በሙሉ የመንግስት የመልካም አስተዳደር ችግሮች ነፀብራቅ ናቸው። ከሙስሊሙ ማህበረሰብ ጥያቄ ጀምሮ እስካሁን ያለውን ችግር በጠረጴዛ ዙሪያ መፍታት እየተቻለ ወደ ሌላ አቅጣጫ ነው የተመሩት፡፡ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ሃላፊዎችም እርስ በእርሱ የተምታታ መረጃ ነበር ለህዝቡ ሲያስተላልፉ የነበሩት። በኦሮሚያ ኦፌኮ በተደጋጋሚ ማስተር ፕላኑን በተመለከተ እንወያይ የሚል ጥሪ አድርጓል፤መንግስት ግን ምላሽ ሳይሰጥ ቆይቶ በመጨረሻ ነው ማስተር ፕላኑን ሰርዣለሁ ያለው። ይሄን ካለ በኋላ ደግሞ በወቅቱ ከዚሁ ጉዳይ ጋር በተያያዘ የታሰሩት መፈታት ነበረባቸው። እነዚህ ሰዎች ማስተር ፕላኑን ነበር የተቃወሙት፤ ስለዚህ ሊፈቱ ይገባ ነበር፡፡ ለሟች ቤተሰቦችና ንብረት ለወደመባቸው ካሳ መክፈል ነበረበት፡፡ መንግስት ይቅርታ የጠየቀባቸውን ነገሮች በሚገባ ማስተካከል ሲገባው ዳተኝነት አሳይቷል፡፡  
አሁንም ከዚህ በኋላ ገዥውም ተቃዋሚውም ግልፅ ፖለቲካን ያራምዱ፡፡ የህብረተሰቡን ችግር ይስሙ፣ ይረዱ፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ አገራችን ሙሉ ሰላም ያገኘችበት የታሪክ አጋጣሚ የለም፤ ይሄ ያሳዝናል። ባለንበት ዘመን ይሄ መለወጥ አለበት፡፡ በውይይትና በምክክር ችግሮችን የመፍታት ባህል መዳበር አለበት። ሰው በመረጃ መበልፀግ አለበት። የተበላሸው የሚዲያ ምህዳር መስተካከል አለበት። መንግስት ችግሩን ብቻውን ለመፍታት መታገል የለበትም፡፡
ሁሉም የመፍትሄ አካል መሆን አለበት። ህዝቡ ስለሃገሩ ሁኔታ የማወቅ፣የመቆርቆር መብቱ ሊከበርለት ይገባል፡፡
ተቃዋሚዎች ወደ ፓርላማ የሚገቡበት ሁኔታ መኖር አለበት፡፡ መንግስት፤ ህዝብ ዝም ቢልም እየታዘበው መሆኑን ማወቅ አለበት፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁም በሚገባ ወደ መፍትሄው የሚወስደን መሆን አለበት እንጂ ይበልጥ የሚያፍን መሆን የለበትም፡፡

- “በየግላችን ስልጡን አስተሳሰብ በማዳበር፣ ስልጡን ባህል እንፍጠር” ብለን አፍረጥርጠን የምንነጋገረው መቼ ይሆን?
- በነባር አስተሳሰብና በነባር ባህል ውስጥ ሆነን፣ እድሜ ልክ ተመሳሳይ የፖለቲካ አዙሪት ውስጥ መዘፈቅና መተራመስ ብቻ!

በአገራችን ስናየው የከረምነው ቀውስ፤... ራቅ አድርገን የመንግስትን የሚመለከት የፖለቲካ ጉዳይ ልናስመስለው እንችላለን። ለምሳሌ ለአመታት እየተጓተቱ ብዙ ቢሊዮን ብር የባከነባቸው የመንግስት ፕሮጀክቶች ከአገሪቱ ቀውስ ጋር የተያያዙ ናቸው ብለን  ብንናገር ስህተት አይሆንም። ፕሬዚዳንት ተሾመ ሙላቱ ሰኞ እለት ለፓርላማ ባቀረቡት ንግግርም፤ የመንግስት ፕሮጀክቶች ብክነትን መጓተትን ለማስተካከል እርምጃ እንደሚወሰድ ገልፀዋል፡፡ ጥሩ ነው፡፡
ግን፣ ከአመታት በፊት መደረግ አልነበረበትም ወይ ብለን መጠየቅ እንችላለን፡፡ “ፕሮጀክቶቹ በታቀደላቸው ጊዜ እየተከናወኑ ናቸው” የሚል የቲቪ ዜና በማሰራጨት እውነታውን መካድ እንደማያዛልቅ፤ ከአራትና ከአምስት አመት በፊት በዚሁ ጋዜጣ በተደጋጋሚ ተዘግቧልኮ፡፡ “ፕሮጀክቶቹ፤ በታቀደላቸው አቅጣጫ እየተከናወኑ ነው” ብሎ ማድበስበስ እንደማያዋጣም፣ ገና ድሮ መታወቅ ነበረበት።
ቢሆንም፤ ከአመታት በኋላ፣ እውነታውን መካድና ማድበስበስ እንደማያዋጣ በመገንዘብ፣... ፕሮጀክቶቹ የመጓተትና የብክነት አዙሪት ውስጥ መግባታቸውን መንግስት ማመኑ... አንድ ቁምነገር ነው።
እንዲህ... ስናወራው፣ የሩቅ ጉዳይ እንጂ፤ በቀጥታ የሚመለከተን የቅርብ ጉዳያችን አይመስልም።
እዚያው በሩቁ እንጨርሰው ካልን፤ “ለመሆኑ፣ ለፕሮጀክቶቹ ምን አይነት መፍትሄ ተበጀላቸው?” በሚል ጥያቄ መቀጠል እንችላለን።
አዎ፤ መንግስት፣ ችግሩን አምኖ መፍትሄ እንደሚያበጅላቸው ቢገልፅም፣ መፍትሄው ምን እንደሆነ አልተናገረም።
በተቻለ መጠን መንግስት ቢዝነስ ውስጥ እንዳይገባ ማድረግ፣ የተጀመሩትን ፕሮጀክቶች ቀስ በቀስ ወደ ግል ኢንቨስትመንት ለማዛወር መሞከር፣ እስከዚያው ግን፤ የፕሮጀክቶቹ ግንባታ፣ በጨረታ በግል ኩባንያዎች እንዲከናወን ማድረግ አንድ መፍትሄ ነው። በጨረታ በተለያዩ ኩባንያዎች የተገነቡ የኤሌክትሪክ ማመንጫ ግድቦችን ማየት ይቻላል - በአብዛኛው አልተጓተቱም፤ ብዙ ቢሊዮን ብሮች በከንቱ አልባከነባቸውም። መንግስት የሚገነባቸው የመስኖ ግድቦች፣ ከአስር አመታት በላይ ያለ ውጤት መጓተታቸውን ደግሞ መመልከት ይቻላል - ብዙ ቢሊዮን ብሮችን በከንቱ አባክነዋል።
ስለዚህ፣ የፕሮጀክት ግንባታዎችን በጨረታ ለኩባንያዎች መስጠት፣ ጥሩ ጊዜያዊ መፍትሄ ነው።
ለዘለቄታው ግን፣ የመንግስት ፕሮጀክቶች፣ መቼም ቢሆን፣ አነሰም በዛ፣ ከብክነትና ከመጓተት እንደማያመልጡ፣ ከታሪክ በመማር፣ እድገት የሚመጣው በግል ኢንቨስትመንት መሆኑን በመገንዘብ፣ ሁነኛ የመፍትሄ ለውጥ መፍጠር ያስፈልጋል። ይሄ ግን፣ በአንድ የአዋጅ ለውጥ ብቻ እውን ሊሆን አይችልም። ከእለት እለት፣ ከአመት አመት፣ በፅናት የሚቀጥል የረዥም ጊዜ ጥረትን ይጠይቃል - የሀሳብና የተግባር ብቻ ሳይሆን፣ ጠቅላላ የአስተሳሰብና የባህል ለውጥን የሚጠይቅ ነውና። እንዴት?
የጥረት ስኬትን የሚያደንቅና የግል ንብረትን የሚያከብር ስልጡን አስተሳሰብና ስልጡን ባህል ለመፍጠር መጣጣር ያስፈልጋላ።
አዎ፤ ይሄ ጥረትንና አለማዊ ስኬትን፤ ብልፅግናንና የግል ንብረትን የሚያስከብር ስልጡን አስተሳሰብ፣ በዛሬው ዘመን በአለም ዙሪያ ቸል እየተባለ ወይም እየተብጠለጠለ ሲደበዝዝ እናይ ይሆናል። ግን፤ ይህንን የዘመኑን የጥፋት አቅጣጫ በመከተል፣ የምናገኘው ትርፍ የለም - ከድህነትና ከትርምስ በቀር። የአለም መንግስታት ምንም ይበሉ ምን፤ ከብዙ አገራት የብዙ ዘመናት ታሪክ፣ ከራሳችን የቅርብ ጊዜ ታሪክ እንዲሁም አሁን በገሃድ ከምናየው እውነታ መገንዘብ እንችላለን ስልጡን አስተሳሰብንና ስልጡን ባህል ቸል ከተባለ፤ ከጥፋት ውጪ ምንም ውጤት አይገኝም።
እናም፣ ከጊዜያዊ መፍትሄዎች ባሻገር፣ ለወደፊትም ስልጡን አስተሳሰብና፣  ስልጡን ባህል ለመፍጠር፣ … በዚህ ደልዳላ መሰረት ላይም፤ ለግል ንብረት ዋስትና የሚያረጋግጥ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚን ለማስፋፋት በፅናት መጣጣር ያስፈልጋል የማያወላውል የካፒታሊዝም ስርዓትን ለማስፈን፡፡
በእርግጥ፣ ይሄ ዘላቂ መፍትሄ፣ በአንድ ውሳኔና በአንድ ወር ይቅርና በደርዘን ውሳኔዎችና አመታትም ሙሉ ለሙሉ እውን ይሆናል ማለት አይደለም። ግን ሌላ አማራጭ የለም፡፡ መጀመር አለበት፡፡ ይህንን ጉዞ … መንግስት፣ ቀሽም ስህተቶቹን በማረም መጀመር ይችላል... ባለሃብትን “ኪራይ ሰብሳቢ” እያለ ከማንቋሸሽ፣ በብር ህትመት ሳቢያ የዋጋ ንረት በተፈጠረ ቁጥር በባለሃብትና በነጋዴዎች ላይ ከማሳበብ መቆጠብ፣ “የነጋዴዎች ፍላጎት፣ ትርፍን ማግኘት ብቻ ነው” እያለ እንደ ወንጀልና እንደ ሃጥያት ከመኮነን መታቀብ አለበት። የግል ጥረትን፣ የግል ብቃትንና የግል ስኬትን ማድነቅ …. ማክበር ካልጀመረ፣ የሚያዛልቅ መፍትሄ ማግኘት አይችልም። እያየነው ነውኮ።
መንግስት የግል ጥረትንና ስኬትን ሳያከብር፣ ሌሎች ሰዎች በተለይም ወጣቶች … ህይወታቸውን በጥረት እንዲያሻሽሉና ስራ ፈጣሪ እንዲሆኑ ቢጠብቅ፣ ከንቱ ጥበቃ ነው። መንግስት የግል ንብረትን ከመንካት ሳይቆጠብ፣ ሌሎች ሰዎች በተለይም ወጣቶች፣ የሰውን ንብረት እንዲያከብሩ ቢጠብቅ፣ ሞኝነት ነው። ይሄውና ስንት ህይወትና ንብረት ጠፋ! መንግስት፣ ከእስካሁኑ ጥፋቶች ተምሮ፣ ቀሽም ስህተቶችን በማረም ከጀመረ፣ ሌሎቻችንስ?
ያው፣ ምሁራንና ዜጎችም፣ ለሰው ህይወትና ለግል ንብረት ዋጋ ሳንሰጥ፣ መንግስት ህይወታችንና ንብረታችንን እንዲያከብርልን ብንጠብቅ ሞኝነት ነው፤ አልያም ግብዝነት፤ አልያም ቅጥፈት።
በፅሁፌ መግቢያ ላይ እንደገለፅኩት፤ … ይሄውና ጉዳዩ በጣም ቅርብ የግል ጉዳያችን እንደሆነ ማሳየት እየጀመርኩ ነው፡፡ ለብዙ ሰዎች፣ ፖለቲካ ማለት፣ በቃ … ሁሉንም ነገር በመንግስት ላይ የማላከክ ጨዋታ ይመስላቸዋል፡፡ አገሪቱ ፖለቲካ፣ ከዘመን ዘመን፣ ብዙም ነገር ሳይሻሻል የሚቀጥለውም በዚህ ምክንያት ነው፡፡ እንዴት በሉ፡፡
የእውነት... የምር... በሃሰት ያልቆሸሸ አእምሮንና ሃሳብን የምንፈልግ ከሆነ፣ ስልጡን አኗኗርን... ስኬትንና የጥረት ብልፅግናን የምንፈልግ ከሆነ... ክቡር ሰብእናን፣ በራስ የመተማመን እርካታን የምንፈልግ ከሆነ... አዎ፣ እነዚህን የምንፈልግ ከሆነ፣ … “ከመንግስት ፕሮፓጋንዳና አፈና መላቀቅ፣ ከመንግስት በደልና ዝርፊያ መዳን፣ ከመንግስት የዘፈቀደ ፍረጃ መገላገል” … በሚል ዲስኩር ነገሩን ሁሉ መንግስት ላይ ከምረን፣ ከኃላፊነት የምንሸሽት ጉዳይ ሊሆን አይችልም።
ከመንግስት ውጭ፣ ሌላ ሰው... ሌላ ቡድን... ሌላ ፓርቲ... በአሉባልታ ላይ እየተማመነ በዝምታ እንድንቀበል ለማስፈራራት ሲሞክር፣ የጥረት ስኬትን ሲያንቋሽሽና የግል ንብረት ላይ ዘመቻ ሲያውጅ፣ ሰዎችን በጅምላ እየፈረጀ በዘር ወይም በሃይማኖት ተከታይነት ለማቧደን ሲሞክርም... ‘አልቀበልም’ ማለት ያስፈልጋል። ቢያንስ ቢያንስ ደግሞ፣ በየግላችን፣ በአሉባልታ ፕሮፓጋንዳ ላይ ከመተማመን በመቆጠብ፣ ሌሎችን በዛቻ ለማፈን ከመሞከር በመራቅ፣ እያንዳንዱን ሰው በዘር በተወላጅነት ሳይሆን፤ በግል ብቃቱ፣ በተግባሩና በባህርይው የምንመዝንበት የእውነትን ጉዞ መጀመር እንችላለን - በስልጣኔ ጎዳና። የሰዎችን የጥረት ስኬት ከማንቋሸሽና የግል ንብረት ላይ ጥላቻ ከመቀስቀስ በመቆጠብ... የስልጡን አኗኗር አቅጣጫን መያዝ እንችላለን።
በጣም ሩቅ ሃሳቦች ሊመስሉ ይችላል። ግን ሌላ ምን የተሻለ አማርጭ አለ? በዚያ ላይ ደግሞ፤ ብዙ ኑሯችን የተመሰረተው በዚህ ቀና አስተሳሰብ ላይ ነው። ሀሰትንና እውነትን፣ የሀብት ፈጠራንና የሀብት ዝርፊያን ወይም ውድመትን፣ ታታሪነትንና ማምታታትን ለይተን ማወቅ ያቅተናል እንዴ? ብቃት ያለውና ብቃት የሌለውን ሰው መለየትም እንችላለን። መጥፎ ተግባር የፈፀመና ድንቅ ተግባር የፈፀመ ሰውን ለይተን የማወቅ አቅምም አናጣም፡፡ ክፉ እና መልካም የሰው ባህርይን መለየት እንችላለን። ነገርዬው፣ የዘር ወይም የሃይማኖት ተከታይነት ጉዳይ እንዳልሆነኮ ግልፅ ነው፡፡ ሩቅ ሳንሄድ በአንድ ቤተሰብ ውስጥ እንኳ፣ የብቃትና የባህርይ ልዩነት እንዳለ እናውቃለን - አንዱ ታታሪ፣ አንዱ ሌባ... አንዱ ቀና፣ አንዱ አስመሳይ፣ አንዱ መልካም አንዱ ክፉ።
በየጊዜው የምናስተውለው ይህንን የዘወትር እውነታ፣ ይህንን ግልፅ እውቀት... አንቅበረው። አንካደው። ሁሌም፣ መተማመኛችን እንዲሆን በክብር እንያዘው፣ እንጠብቀው፣ እናጠንክረው። ያኔ፣ የማንኛውም መንግስት ወይም የሌሎች ፖለቲከኞች መጫወቻ ላለመሆን በሙሉ ልብ መከላከል እንችላለን። ቀስ በቀስም እንደማያዋጣቸው ይገነዘባሉ። መጫወቻ የሚያደርጉን፣ መጫወቻ ለመሆን ስለምንመቻቸው ነው።
ለእውነት ክብር ከሌለን፤ በሰበብ በአስባቡ እውነትን የምንክድ ከሆነ፤... በፕሮፓጋንዳና በአሉባልታ፣ በአፈናና በስድብ እንዲያጣድፉን የልብ ልብ እንሰጣቸዋለን - እውነትን እያዋረድን፣ እውነትን አክብሩ ብለን ለመከራከር፣ ውስጣዊ ሃይል አይኖረንማ።
ለጥረትና ለስኬት፤ ለግል ንብረትና ለብልፅግና ክብር ከሌለን፣ እንዳሻቸው በኑሯችንና በንብረታችን ላይ እንዲዘምቱ ፈቃድ ሰጠናቸው ማለት ነው።
ግን ስህተታችንን የማረም እድል የለንም ማለት አይደለም። ለእውነት፣ ለጥረት፣ ለስኬት፣ ለግል ብቃትና ለግል ማንነት ትልቁን ክብር በመስጠት፣ የስልጡን ጎዳና ጉዞን መጀመር እንችላለን።
ያኔ፣ ማንኛውም መንግስትም ሆነ ሌሎች አጥፊዎች፣ እንዳሻቸው የመፈንጨት ጉልበታቸው ይቀንሳል። ለነገሩ ባይቀንስ እንኳ፣ እነሱ ይዋሻሉ ብለን፣ የላቀ ውሸታም በመሆን ልናሸንፋቸው ከሞከርን... ከጅምሩ ተሸነፍን ማለት ነው። ደግሞስ፣ ፕሮፓጋንዳና አሉባልታ መጥፎ ከሆነ፤ የላቀ ፕሮፓጋንዳና የላቀ አሉባልታ፣... በአንዳች ተአምር፣ “ጥሩ” ሊሆን አይችልም። በሰው ኑሮና ንብረት ላይ መቀለድ ወይም መዝረፍ፣.. ‘መጥፎ’ ከሆነ፤ ከዚህ የላቀ አዲስ የዝርፊያ ወይም የጥፋት ሪከርድ ማስመዝገብ፣... በአንዳች ተአምር፣... ‘ጥሩ’ ሊሆን አይችልም።
ይችላል እንዴ?
የዚያኛው ጎራ ፕሮፓጋንዳ፣ ‘ለመጥፎ አላማ’ ነው። የዚህኛው ጎራ አሉባልታ ግን፣ ‘ለበጎ አላማ’ ነው... ብለው ራሳቸውን የሚያታልሉ ሰዎች ጥቂት አይደሉም።
“ለበጎ አላማ እስከሆነ ድረስ”... እውነትን መካድና መዋሸት፣ አገሬውን በፕሮፓጋንዳ ማጥለቅለቅ፣ መንግስት በሰዎች ኑሮ ላይ አድራጊ ፈጣሪ እንዲሆን መፍቀድ፣ ተቃዋሚ ነኝ በሚል ሰበብ የሰውን ንብረት መዝረፍና ማጥፋት፣ የብሄር ብሄረሰብ ፖለቲካን ማስፋፋት፣ ይህንን እቃወማለሁ በሚል ሰበብ ሰዎችን በጅምላ እየፈረጁ በዘር ወይም በሃይማኖት ማቧደን... እነዚህ የሃሰት፣ የጥፋትና የክፋት መንገዶች በሙሉ... “ለበጎ አላማ እስከሆነ ድረስ”...  ይፈቀዳሉ? ለዛሬ ብቻ! ለነገ ብቻ! ለዚህኛውና ለዚያኛው ጉዳይ ብቻ! እገሌን ለመደገፍና እንቶኔን ለማጥቃት ብቻ! ከዚያ በኋላ፣ ወደ እውነት፣ ወደ ቀናው መንገድ፣ ወደ መልካም ጎዳና እንመለሳለን? … እንዲህ ዓይነት ጨዋታ እንደማያዋጣ እንደገና ዘንድሮም አየነው፡፡
ሰዎች! ራሳችንን አናታልል። በመሰረታዊ ሃሳቦች ላይ፣ ‘ለዛሬ ብቻ’፣ ‘ለዚህኛው ጉዳይ ብቻ’፣ ‘ለእገሌ ብቻ’ የሚባል ነገር የለም። የተሳሳቱ፣ አጥፊና ክፉ ሃሳቦች፣ ‘በአላርም’ ለተወሰነ ጊዜ ብቻ የሚያገለግሉ፣ ወይም በአድራሻ የሚላኩ ወይም በፋይል የሚከደኑ ቁንፅል ቁሶች አይደሉም።... እውነትን፣ የግል ንብረትን፣ የግል ማንነትን በማንቋሸሽ... አገርን ለመምራት የሚያስብ ባለስልጣን ወይም ሰዎችን ለመቀስቀስ የሚሞክር ተቃዋሚ... የሃሰት፣ የጥፋትና የክፋት ማዕበል እንዳይፈጠር መግታት አይችልም።
ሃሳቦች፣ ሃያል ናቸው... በድንበር፣ በጊዜና በዘበኛ ታጥረው አይቀመጡም። ለዛሬ፣ ለእንትን፣ ለእገሌ... ተብሎ የሚገደብ መሰረታዊ ሃሳብ የለም። መንግስትም ሆነ ተቃዋሚ፤... በአንዳች ማመካኛ፣ ሰዎችን በዘር ለማቧደን ወይም የዘረኝነት ስሜትን ለመቀስቀስ ከሞከረ፣ ነገርዬዋ እዚያው ተገድባ አትቀርም። እዚህም እዚያም፣ በዚህና በዚያ በኩል፣ ለመሰንበቻውና ለከርሞ፣ ስፍር ቁጥር የሌለው መዘዝ ታስከትላለች። ለዚህም ነው፤ የመንግስት ባለስልጣናትም ሆኑ የተቃዋሚ ፖለቲከኞች፣ በየጊዜው የሚጀምሩት ነገር ከቁጥጥር ውጭ ሲሆንባቸው የምንመለከተው።
እሺ። ግን፣ የሃሰት፣ የጥፋትና የክፋት ጎዳና የተጀመረው፣... ለበጎ አላማ ከሆነስ? አዎ፣ እንዲህ አይነት ማመካኛ እየደረደሩ ራሳቸውን የሚያታልሉ ሰዎች ብዙ ናቸው። ደግሞም አስቡት።
በይፋ፣ “ለክፉ አላማ” በማሰብ፣ ኑሯችሁን አጠፋለሁ፣ ንብረታችሁን እዘርፋለሁ” የሚል ፖለቲከኛም ሆነ መንግስት፣ ገዢም ሆነ ተቃዋሚ የትም አይኖርም። ሁሉም አምባገነኖችና ነውጠኞች፣ ጥፋትና ዝርፊያ የሚፈፅሙት፣ “ለበጎ አላማ” በሚል ማመካኛ ነው።
“ለበጎ አላማ ራሳችሁን መስዋዕት አድርጉ” በማለት ይሰብካሉ። መስዋዕትነትን በእሺታ ተቀብለን እናጨበጭባለን። ከዚያስ? ከዚያማ … ‘ለበጎ አላማ’፤ ኑሯችሁን እንደ በግ ለእርድ፣ እንደ ቁራጭ እንጨት ለማገዶ ይወረውሩታል። ይሄ የመስዋዕትነት አምልኮ፣ በጭራሽ... ፈፅሞ... ‘በጎ አላማ’ ሊሆን አይችልም። ከበጎ አላማ ጋርም ጤናማ ግንኙነት ሊኖረው አይችልም። ‘በጎ አላማ’ን የሚያጠፋ ክፉ በሽታ ነው - የመስዋዕትነት አምልኮ።
ይልቅስ፣ ከመስዋዕት አምልኮ በተቃራኒ፤... የሰውን ኑሮ፣ የጥረት ስኬትንና የግል ንብረትን ማክበር ነው - ‘በጎ አላማ’። ይሄ፣ ያን ያህልም ውስብስብ ሃሳብ አይደለም። ነገር ግን፣ ምንም ሳይሸራረፍና ሳይበረዝ፣ በፅናት ለመተግበር ብዙም ሙከራ አይታይም። ለምን? ለዘመናት ስር በሰደደ ‘የመስዋዕት አምልኮ’ ሳቢያ!!  በሌላ አነጋገር፣ ጉዳዩ መንግስትን ብቻ የሚመለከት ጉዳይ አይደለም፡፡ ለእያንዳንዳችን … የግል ጉዳያችን ነው፡፡ ለእውነትና ለግል አዕምሯችን፣ … ለጥረትና ለግል ንብረት፣ … ለግል ብቃትና ለግል ማንነት … ክብር የሚሰጥ ስልጡን አስተሳሰብ በየግላችን ለማዳበር እንጣር፡፡ በዚህም ስልጡን ባህል እንፈጥራለን፡፡

  በአንድ የአጫጭር ተረቶች ስብስብ ውስጥ የሚከተለው ተረት ይገኝበታል፡፡
በአንድ ድርጅት ውስጥ ከዕለታት በአንድ ቀን አስገራሚ ሁኔታ ይከሰታል፡፡ ሰራተኞቹ እስከ ምሳ ሰዓት ድረስ ስራቸውን ሲያከናውኑ ቆይተው ለምሳ ይወጣሉ፡፡
ምሳ በልተው የተመለሱት ሁሉም አንድ ላይ አልነበረም፡፡ ከምሳ በኋላ ቡናና ሻይ የሚጠጡት ዘገዩ። ምሳቸውን አቀላጥፈው የተመለሱት ደግሞ ቀድመው ደረሱ፡፡ ሆኖም የውጪው በር ላይ የተለጠፈው ማስታወቂያ, የሁሉንም ቀልብ በመሳቡ, ሰራተኞቹ በሩ ጋ ቆመው ማስታወቂያውን ያነባሉ፡፡ እንዲህ የሚል ነው ማስታወቂያው፡-
“በእዚህ ድርጅት ውስጥ ለረጅም ጊዜ ስራችሁን ስታከናውኑ ዕድገታችሁን እንዳታገኙ እንቅፋት ሆኖባችሁ የነበረው ሰው፤ በትላንትናው ዕለት ሌሊት ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡ ስለሆነም ዛሬ ከዘጠኝ ሰዓት ጀምሮ በድርጅቱ መሰብሰቢያ አዳራሽ በመገኘት, አስከሬኑን በክብር መሰናበት የምትችሉ መሆኑን እንገልፃለን”
                          ድርጅቱ
አንብበው እንደጨረሱ፡-
“ማን ይሆን እባካችሁ?” አለ አንደኛው በሀዘን፡፡
“አሳዛኝ ነው፡፡ ሆኖም ማን እንደሆነ ለማወቅ ጓጉቻለሁ” አለ ሌላኛው፡፡
አብዛኛው ሰው በየውስጡ፤
“ማነው ዕድገቴን ሲያሰናክል የነበረው?” እያለ በየሆዱ ነገር ማብሰልሰል ይዟል፡፡
የታሰበው ሰዓት ደረሰ፡፡ ሁሉም በየተራ እየመጡ, በሬሳ ሳጥን ውስጥ ያለውን ሰው ማየት ጀመሩ፡፡ ሁሉም ያዩትን ባለማመንና በድንጋጤ አፋቸውን እየያዙ በቆሙበት ደርቀው ቀሩ፡፡ በሳጥኑ ውስጥ ያዩት ሰው መንፈሳቸውን ሰቅዞ ይዞታል፡፡
የሬሳ ሳጥኑ ውስጥ አንድ ሰፊ መስተዋት ኖሯል ለካ፡፡ ወደ ሳጥኑ የተመለከተ ሰው ሁሉ መልሶ የራሱን ፊት ነበር የሚያየው፡፡ ከራሱ ምስል በታችም የሚከተለው ፅሁፍ በጉልህ ይነበባል፡-
“ዕድገትህን ሊያሰናክል የሚችል አንድ ሰው ብቻ ነው፡፡ እሱም አንተው ራስህ ነህ!”
“አንተ ብቻ ነህ ህይወትህን ከሥሩ መለወጥ የምትችለው፡፡
“አንተ ብቻ ነህ በደስታህ፣ በስኬትህ፣ በአስተሳሰብህና በአመለካከትህ ላይ አዎንታዊ ተፅዕኖ ማሳደር የምትችለው”
“አንተ ብቻ ነህ ራስህን ማገዝ፣ ከውድቀት ማንሳት የምትችለው፡፡
“የበላይ ጓደኛህ፣ አለቃህ፣ ወላጆችህ፣ አገርህ፣ ጓደኛህ ሲለወጥ መጠነኛ ተፅዕኖ ባንተ ላይ ሊያሳድር ይችል ይሆናል፡፡ ህይወትህ ሙሉ በሙሉ የምትለወጠው ግን አንተ ራስህ ስትለወጥ ብቻ ነው!
ከነዛ ጎታችና አጋች ዕምነቶችህና አስተሳሰቦችህ ስትላቀቅና ለህይወትህ ኃላፊነት ያለብህ አንተና አንተ ብቻ መሆንህን ስታውቅ በእርግጥ ህይወትህ ትለወጣlች!››
                                                   *   *   *
ለውጥ ለማምጣት የራስ መለወጥ ግድ ነው፡፡ ሌላውን እንለውጣለን ተብሎ ሲታሰብ  ‹‹እኔ ተለውጫለሁ?›› `ከጥንት አስተሳሰቤስ ተላቅቄያለሁን?›› ብሎ ራስን መጠየቅ፣ ራስን መፈተሽ ዋና ነገር ነው። ሊቁ ኮንፊሽየስ፤ ካንተ ያነሱትን ሰዎች ይበልጡኛል ስትል ትሰማለህ፡፡፡ ግን ደግሞ ያንተ ደቀመዝሙሮች ናቸው፡፡ ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል? ተብሎ ሲጠየቅ፤ የደቀመዛሙርቱን ስም እየጠቀሰ፤
‹‹እገሌ፤ ቀጥተኛ ነው እንጂ እንደ ሁኔታው መለዋወጥን አይችልም (Flexibility እንዲሉ) እገሌ፣ ነገሮችን ማብራራት ይችላል እንጂ አዎ ወይም አይደለም ብሎ እቅጩን መናገርና ቀላል መልስ መስጠት አይችልም! እገሌ ደግሞ ደፋር ነው፤ ግን ጥንቁቅ አይደለም፡፡ ድፍረት አለጥንቃቄ ዋጋ የለውም፡፡ በመጨረሻም ሌላው ተማሪዬ ግርማ ሞገስ አለው፡፡ ይህ እንዴት እንደሚሳካ ያውቃል፡፡ ግን እንዴት ትሁት መሆን እንዳለበት አያውቅም፡፡ እኔ እነሱ ያልቻሏቸውን በማወቄ፣ ደቀ- መዛሙርቴ እንዲሆኑ ሆነዋል›› ሲል መለሰ ይባላል፡፡
ከላይ የጠቀስነው ስብስብ ‹‹ወዴት እያመራን ነው?›› በሚል ርዕስ የተቀነበበ ሲሆን፤ ዋና ዋና ነጥቦቹ አገራችንን ያሳዩናል፡፡ እነሆ፡-
‹‹ረጃጅም ህንፃዎች፣ ትናንሽ ትእግስቶች፣ ሰፋፊ መንገዶች፣ ጠባብ አመለካከቶች፣ የምናወጣው ብዙ፣ የሚኖረን ጥቂት፤ ብዙ እንገዛለን፤ ጥቂት እንደሰታለን፡፡
… ብዙ ዲግሪ፣ ትንሽ ማመዛዘን /ግንዛቤ… ብዙ አዋቂዎች፣ ብዙ ችግሮች፣ ብዙ መድሀኒት፣ ትንሽ ጤንነት… ጥቂት እናነባለን፣ ብዙ ቴሌቪዥን እንመለከታለን፣ አልፎ አልፎ እንፀልያለን፡፡
.. ብዙ እናወራለን፣ ትንሽ እናፈቅራለን፣ አብዝተን እንጠላለን!... ለህይወት ዕድሜ ጨምረንላታል፣ ለዕድሜ ግን ህይወት አልጨመርንላትም፡፡ ስልጣንን ለማገልገል ሳይሆን ሆድ ለመሙላት ተጠቀምንበት፡፡ ሆድ ተንዘርጥጦ አዕምሮ ግን ኮሰመነ፡፡
መከባበር በመናናቅ፣ መተዛዘን በመጠፋፋት፤ህሊና በሆድ ተተኩ፡፡ ጨረቃ ላይ ደርሰን ተመለስን፣ ግድግዳ የሚለየውን አዲስ ጎረቤታችንን መተዋወቅ ግን አቀበት ሆነብን፡፡ ከምድራችን የሚገኘውን ትንሽ ቦታ ግን አልተቆጣጠርንም፡፡… አቶምን ሰነጠቅን፣ መሰረተ-ቢስ ጥላቻዎችንንና ቅራኔዎቻችንን ግን አልፈታንም።
ብዙ እናነባለን፣ ትንሽ እንለወጣለን፤ ብዙ እናቅዳለን፣ ጥቂት እናሳካለን፡፡ መቸኮልን እንጂ መጠበቅን አልተማርንም፡፡ የተሻለ ገቢ እንጂ ያደገ ሥነ ምግባር የለንም፡፡
ብዙ መረጃ የሚይዝና ብዙ ሥራ ባጭር ጊዜ የሚያከናወን ኮምፒዩተር ፈጠርን እንጂ በመካከላችን ግን ብዙ ተግባቦት አልፈጠርንም፤ በብዛት ብዙ ሄደናል፤ በጥራት ግን ወደ ኋላ ተጎትተናል፡፡
ጊዜው እንዲህ ሆነ፡- ሰው በሁለት ገቢ የሚተዳደርበት፣ ትዳር ግን የሚበተንበት፣ የተሰነጣጠቁ ቤቴሰቦች የሚኖሩባቸው ግን የተዋቡ መኖሪያዎች፡፡
ወቅቱ ፈጣን ጉዞ የሚደረግበት፣ ለአንድ ሌሊት ትዳር የሚወጣበትና ግብረ-ገብነት ተሽቀንጥሮ የተጣለበት ዘመን…. ወዴት እያመራን ነው?!››
ከላይ የተጠቀሱትን በከፊል እንኳ ብናሟላ ‹‹ላሜ ወለደች ነው፡፡ በተደጋጋሚ ብለን ብለን ያልተሰሙ ዛሬ ቦታ ያገኙ ጉዳዮች ያስደስቱናል፡፡ የህዝብን ጥያቄ አንደሰማም ነበር- አዎ፡፡ መቶ ፐርሰንት አሸነፍን ማለት ራስን ማታለል ነበር- አዎን፡፡ ጠባብነት፣ ትምክህተኝነት፣ ኪራይ ሰብሳቢነት፣ የመልካም-አስተዳደር እንከኖች ወዘተ የእኛው የቤት ጣጣ ነበሩ-አዎ፡፡ እነዚህ ሁሉ ተደራርበው ዛሬ ለደረስንበት ሁኔታ ከዳረጉን፤ እንደመፍትሔ፡- ጥፋተኞችን ለይቶ እርምጃ መውሰድ በጎ ነገር ነው፡፡ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ለግርግሮች መረጋጋት መፍትሄ መሻት አማራጭ የሌለው ነው - ትክክል፡፡ በአዋጁ አፈፃፀም ሳቢያ ሊከሰቱ የሚችሉ አግባብ የለሽ ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶችን ከወዲሁ ተጨንቆ ተጠቦ ለመግታት መዘጋጀት በጎ ነገር ነው! የሲቪክ ማህበረሰብን መኖር ማበረታታትና ማጠናከር - ዱሮ ተብሏል - ዛሬም ግድ ሆኗል!
የአገር ሽማግሌዎች በየቱም መልክ ተሰባስበው ሀሳባቸውን እንዲሰነዝሩ ከልብ ፍቃደኛ መሆን የባህላዊ ዲሞክራሲ ብሎም የዘመነው ዲሞክራሲ መሰረት ነው! ሙስናን መቃወም የዚሁ አካል ነው! ተቃዋሚዎች ቦታ እንዲያገኙ የምርጫውን ህግ እስከመለወጥ ሁኔታዎችን ማመቻቸት፤ እሰየው ነው፡፡ “በህዝብ ፊት ቃል ከገባህ ትልቅ ነገር አደረግህ! ካልፈፀምከው ግን ትልቅ ስህተት ላይ ወደቅህ ወዮልህ!” የሚለውን አባባል መቼም አለመርሳት ነው! “ሰው - ፊት ቃል ከገባህ በኋላ “ፉርሽ - ባትሉኝ”፣ ማለት አይቻልም” የሚለው አባባል መሰረቱ ይሄው ነው!!

(ወ/ሮ ሂክማ ኬይረዲን፤ የደቡብ ክልል መንግሥት ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት ኃላፊ)

   የችግሩ ምክንያት በዲላ የንግዱ ማኅበረሰብና የጌዴኦ ዞን ሕብረት ሥራ ዩኒየን መካከል የቦታ ይገባኛል ክርክር ነበር፡፡ ባለፉት ጊዜያት ፍ/ቤቱ አክራክሮ ውሳኔም አስተሳልፎ ወደ አፈፃፀም ሂደት ሊገባ ነበር፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ ቦታው ለዩኒየኑ ይገባል በሚል የተወሰኑ አካላት ማኅበረሰቡን አነሳስተው በንግዱ ማኅበረሰብ ላይ ጉዳት ደርሷል። የፍ/ቤቱን ውሳኔ መነሻ አድርጎ ነው ግጭቱ የተከሰተው፡፡ ከግጭቱ ጋር በተያያዘ የሰው ሕይወት ጠፍቷል፣ ንብረትም ወድሟል፡፡ 23 ሰዎች ሞተዋል፤ ቤት ንብረት የተቃጠለባቸውና የወደመባቸው አሉ፤ ጉዳቱ ሰፊ ነው፡፡
በዚሁ ሂደት መካከል ችግሩ ሲከሰት ደንግጦ ከቤቱ የወጣ፤ ቤትንብረቱ ሲቃጠል ከቤቱ የወጣ  ሰው አለ፡፡ አንዳንድ ሰዎች የብሔር ግጭት ነው ይላሉ፡፡ ግን አይደለም፡፡ ጉዳቱ የደረሰው ከአካባቢው ብሔረሰብ ውጭ ብቻ አይደለም፡፡ ከአካባቢው ተወላጅ ሕይወቱ ያለፈ አለ፡፡ ስለዚህ ከሁሉም ኢትዮጵያዊ ብለን ነው መውሰድ የሚቻለው፡፡ የንግዱ ማኅበረሰብ ውስጥም የአካባቢው ተወላጆች አሉ፡፡ ንብረታቸው የወደመው የሁሉም ነው፡፡ ስለዚህ ግጭቱ የተወሰነ ብሔረሰብ ላይ በፍፁም ያነጣጠረ አይደለም፡፡
ለተጠቂዎቹ ቀድሞ የደረሰላቸውና ሕይወታቸውን የታደገው የአካባቢው ማኅበረሰብ ነው፡፡ አንዳንዶቹ የሃይመናት ተቋማት ውስጥ ተጠልለው ነው ያመለጡት፡፡ ሌሎቹ ደግሞ በአርሶ አደሩ ጓሮ ነው የተጠለሉት፡፡ ቤቱን በማጋራት ከቤቱ በላይ ሲሆንበት የአካባቢውን ማኅበረሰብ አስተባብሮ ድንኳን በመደኮን፤ ውሃ፣ ምግብ፤ በማቅረብ ቀድሞ የደረሰላቸው የአካባቢ ማኅበረሰብ ነው፡፡ ከቤት ንብረቱ የተፈናቀለ ሰው ከ20-25ሺህ ይደርሳል፡፡ መንግሥት ችግሩ ከዞኑ አቅም በላይ መሆኑን ካረጋገጠ በኋላ የፀጥታው ኃይል ገብቶ ሰላም የመፍጠርና የማረጋጋት ሥራ ሰርቷል፡፡ በመቀጠል ደግሞ ለተፈናቀሉ የማኅበረሰብ ክፍሎች የሚያስፈልጉ ነገሮችን ከለየ በኋላ ቁሳቁሶች ገዝቶ እያሰራጨ ነው፡፡ አብዛኛው ሕዝብ ደርሶታል፤ ያልደረሳቸውም ያሉ ይመስለኛል፡፡
በመሠረቱ ችግሩ ይህን ያህል ይሆናል ተብሎ አልተጠበቀም፡፡ ሲነሳ በተደራጀ መልኩ ቀደም ብሎ የተሠራበት አይደለም፡፡ ለንግዱ ማኅበረሰብ ተወስኗል የሚል ነገር ነው ለኅብረተሰቡ ተሰራጨው። አብዛኞቹ የኅብረት ሥራ ዩኒየኑ አባላት በአርሶ አደሩ መሃከል ያሉ ናቸው ወሬውን ያሰራጩት፡፡ ውሳኔው ተላላፊ እንጂ ወደ አፈጻጸም አልተገባም፡፡ የዞኑ አመራርም በአንድ ጊዜ ችግሩ በዚህን ያህል ይሰፋል፤ ኅብረተሰቡ በአንድ ጊዜ ይህን ውሳኔ ይሰማል የሚል ግንዛቤ አልነበረውም። ጥፋቱ ከአካባቢ አካባቢ ይለያል፡፡ ዲላ በስፋት ተጎድቷል። ወናጎ ላይና ይርጋጨፌ ላይ በጣም በስፋት ጉዳት ደርሷል፡፡ ሌሎች ወረዳዎች ላይ መጠነኛና ቀላል ነበር፡፡ መነካካቱ አለ፡፡ ግን ችግሩ አጠቃላይ ነው ብሎ መውሰድ አይቻልም፡፡
በአሁኑ ወቅት ይህንን ችግር ፈጥረዋል የተባሉ የተጠረጠሩ ሰዎች ተይዘዋል፡፡ የሕግ ሂደት መጠበቅ ስላለበት እነዚህ ሰዎች ናቸው ብሎ መደምደም አይቻልም፡፡ ከኅብረተሰቡ ጋር ስለጉዳዩ ውይይት ሲደረግ እነዚህ እነዚህ ናቸው ብሎ የሰጣቸው ሰዎች አሉ፡፡ ቁጥራቸው ሊጨምርም ሊቀንስም ይችላል፡፡
ከዝግጅት ክፍሉ
የይርጋጨፌ ወረዳ አስተዳዳሪ ስለጉዳዩ ለመጠየቅ ደውለንላቸው ሞባይሉ አይሰማም፣ በቢሮ ስልክ ደውሉ ብለውን ቁጥር ሰጡን። ስንደውል አይነሳም፡፡ መልሰን ደውለን ስልኩ አይነሳም አልናቸው፡፡ ቆይ እኔ እደውላለሁ ብለው ሳይደውሉ ቀሩ፡፡ ዞኑ አስተዳዳሪ ጋ ደውለን ስለጉዳዩ ልናናግራቸው መፈለጋችንን ስንነግራቸው አሁን አልችልም ስብሰባ ላየ ነኝ አሉን፡፡

- የወህኒ ቤቱ ጠባቂዎች እስረኞቹ እንዲያመልጡ ትብብር አድርገውላችዋል

    በህገ ወጥ መንገድ ድንበር ጥሰው ገብተዋል በሚል በደቡባዊ የመን በሚገኝ እስር ቤት ውስጥ ታስረው የነበሩ 1 ሺህ ህገወጥ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ባለፈው ረቡዕ ሌሊት አምልጠው መጥፋታቸውን አንድ የአገሪቱ የደህንነት ሃላፊ ማስታወቃቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
በህገወጥ መንገድ ወደ የመን ገብተዋል በሚል ሻባዋ በተባለቺው የአገሪቱ ግዛት ውስጥ ታስረው ከነበሩትና ወደ አገራቸው ሊመለሱ ከተዘጋጁት 1 ሺህ 400 ያህል ኢትዮጵያውያን ስደተኞች መካከል አንድ ሺህ የሚሆኑት ባለፈው ረቡዕ ሌሊት እስር ቤቱን ሰብረው በመውጣት መጥፋታቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡
የእስር ቤቱ ጠባቂዎች ስደተኞቹ እንዲያመልጡ ትብብር እንዳደረጉላቸው ተረጋግጧል ያለው ዘገባው፤ ስደተኞቹ በተቀናበረ መንገድ ካመለጡ በኋላም በተዘጋጀላቸው መኪና በቡድን በቡድን እየሆኑ በአቅራቢያ ወደሚገኙት ማሪብ እና ባይዳ የተሰኙ ግዛቶች መሄዳቸውን አስታውቋል፡፡ የየመን መንግስት ባለፈው ወር ብቻ በህገ ወጥ መንገድ ድንበር ጥሰው ገብተዋል በሚል ከ220 በላይ አፍሪካውያን ስደተኞችን በቁጥጥር ስር በማዋል ወደ አገራቸው እንደመለሰ ያስታወሰው ዘገባው፤ከእነዚህም መካከል አብዛኞቹ ኢትዮጵያውያን እንደነበሩ ጠቁሟል፡፡

 አላስፈላጊ ብክነትን መቀነስ የሚል ዘመቻ የጀመረው የናይጀሪያ መንግስት፤ የአገሪቱ መሪ ሙሃመድ ቡሃሪ ከሚጠቀሙባቸው 11 ልዩ አውሮፕላኖች ውስጥ ሁለቱን ለመሸጥ መወሰኑን የፕሬዚዳንቱ ቃል አቀባይ ባለፈው ረቡዕ አስታወቁ።
የአገሪቱ መንግስት ፋልከን ሰቭንኤክስ እና ሃከር 4000 የሚል መጠሪያ ያላቸውን የፕሬዚዳንቱ ልዩ አውሮፕላኖችን እንደሚሸጥ የሚገልጽ ማስታወቂያ በጋዜጣ ላይ ማውጣቱን ቃል አቀባዩ ጋርባ ሼሁ መግለጻቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ መንግስት ለፕሬዚዳንታዊ በረራዎች የሚደረጉ ወጪዎችን ለመቀነስ ሁለቱን አውሮፕላኖች ለመሸጥ ከመወሰኑ ባሻገር  ከተቀሩት የፕሬዚዳንቱ አውሮፕላኖች የተወሰኑትን ለአገሪቱ አየር ሃይል እንደሚሰጥም ቃል አቀባዩ አስታውቀዋል፡፡ ናይጀሪያ በነዳጅ ዋጋ መቀነስና በውጭ ምንዛሬ እጥረት ሳቢያ የከፋ የኢኮኖሚ ድቀት ውስጥ መግባቷንና መንግስትም ይህንን ችግር ለመፍታት በማሰብ ከጀመራቸው እርምጃዎች ውስጥ፣ አላስፈላጊ ወጪዎችን መቀነስ አንዱ እንደሆነም ዘገባው ያስረዳል፡፡

 10 ሚሊዮን ሚስጥራዊ መረጃዎች እንዳሉት አስታውቋል

      የመንግስታትንና የታላላቅ ተቋማትን ጥብቅ ሚስጥሮች ፈልፍሎ በማውጣትና በማጋለጥ የሚታወቀው የዊኪሊክስ ድረገጽ መስራች ጁሊያን አሳንጄ፣ የአሜሪካን ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የተመለከተ ጥብቅ ሚስጥር በቅርቡ ይፋ አደርጋለሁ ማለቱን ዩኤስኤ ቱዴይ ዘገበ፡፡
አሳንጄ የዊክሊክስን 10ኛ አመት የምስረታ በዓል በማስመልከት በቪዲዮ ሊንክ ባስተላለፈው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ መጪው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ከሚከናወንበት ከህዳር ወር መጀመሪያ በፊት ከምርጫው ጋር የተያያዙ ሚስጥራዊ መረጃዎችን ለአለም ይፋ እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡ ዊክሊክስ ከዚህ በተጨማሪም በመጪዎቹ አስር ሳምንታት ውስጥ ከጦር መሳሪያዎች፣ ከጦርነቶች፣ ከጎግል ኩባንያና ከሌሎች ጉዳዮች ጋር የተያያዙ አዳዲስ ጥብቅ ሚስጥሮችን በየሳምንቱ እንደሚዘከዝክና ይፋ የሚያደርጋቸው 10 ሚሊዮን ያህል ጥብቅ ሚስጥራዊ መረጃዎች እንዳሉት አሳንጄ ተናግሯል፡፡
ከሰሞኑ ዊኪሊክስ ከሂላሪ ክሊንተን ጋር በተያያዘ ጥብቅ መረጃ ያወጣል ተብሎ ቢጠበቅም ምንም ነገር አለማውጣቱን የጠቆመው ዘገባው፣በሌላ በኩል አሳንጄ የሄላሪ ክሊንተንን የምርጫ ቅስቀሳ ለማደናቀፍ አሲሯል በሚል የሚናፈስበትን ሰሞንኛ መረጃ በዚሁ መግለጫው አስተባብሏል፡፡ አሳንጄ በቀረቡበት ክሶች ለስዊድን ተላልፎ እንዳይሰጥ በመስጋት፣ ከ2012 አንስቶ ለንደን ውስጥ በሚገኘው የኢኳዶር ኤምባሴ በጥገኝነት ተጠልሎ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡

    ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ታላቅ ንጉሥ ሰፊ ግዛት እያስተዳደረ ይኖር ነበር፡፡ ዕድሜው እየገፋ  ሲሄድ ሶስቱን ልጆች በተራ ወደ አልጋው እየጠራ፣ አንድ ጥያቄ ይጠይቃቸዋል፡፡ በመጀመሪያ  ትልቁንና ጉልበተኛውን ልጁን ጠርቶ፤  ‹‹ልጄ፤ አሁን እኔ ህመምተኛ እየሆንኩ መጥቻለሁ፡፡ ስለዚህም አልጋዬን ለእናንተ መተው አለብኝ፡፡
ለመሆኑ ግዛቴን ለማስተዳደር ትችላለህ? ዝግጁ ነህ?››
ትልቁ ልጅም፤
‹‹መጠርጠሩስ! በደምብ እችላለሁ››
ንጉሡ፤
‹‹በምን ተማምነህ እንዲህ አልክ?››
ትልቁ ልጅ፤
‹‹በራሴ ስለምተማመን፡፡ ደግሞምኮ እንኳን እኔ ጎልማሳው፣ አንተም ሽማግሌው ስታስተዳድር
ነበር!›› ሲል መለሰ፡፡
‹‹እሺ ሂድ፡፡ መካከለኛውን ወንድምህን ጥራው››
መካከለኛው ወንድም ተጠርቶ መጣ፡፡
ንጉሡ፤
‹‹እንኳን ደህና መጣህ፡፡ ልጄ፤ አሁን እኔ እያረጀሁና ህመምተኛ እየሆንኩ መጥቻለሁ፡፡ ስለዚህም አልጋዬን ለናንተ ማውረስ አለብኝ፡፡ ለመሆኑ ግዛቴን ለማስተዳደር ዝግጁ ነህ?›› መካከለኛው ልጅ፤
‹‹እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ ግን ካወረስከኝ ወንድሞቼን እያማከርኩ ለማስተዳደር እሞክራለሁ››
ንጉሥ፤
‹‹እሺ ሂድ፡፡ ታናሽ ወንድምህን ጥራው›› አለና ሸኘው፡፡
በመጨረሻ ታናሽየው ተጠርቶ ንጉሡ ፊት ቀረበ፡፡
ንጉሥ፤
‹‹ እንኳን ደህና መጣህ፡፡ ያስጠራሁህ አንድ ችግር ገጥሞኝ ነው፡፡ አየህ ልጄ፤ አሁን እኔ እያረጀሁና
ህመምተኛ እየሆንኩ መጥቻለሁ፡፡ ስለዚህም አልጋዬን ለናንተ ማውረስ አለብኝ፡፡ ለመሆኑ ግዛቴን
ለማስተዳደር ዝግጁ ነህ?›› ሲል ጠየቀው፡፡
ታናሽ ወንድምም፤
‹‹ማስተዳደር የምችል ይመስለኛል››
ንጉሥ፤
‹‹በምን ተማምነህ እንዲህ ልትል ደፈርክ?›› አለው፡፡
ታናሽ ወንድምም፤
‹‹ሦስት ዓይነት አቅም እንዳለኝ እተማመናለሁ፡፡
1ኛ/ የአንተን ምክር አዳምጣለሁ
2ኛ/ ከወንድሞቼ ጋር እመካከራለሁ
3ኛ ከአገሬው ጋር እወያያለሁ፡፡ የአገር ሽማግሌዎችን ጠርቼ ‹‹ምን ይበጃል?›› ብዬ እጠይቃለሁ፡፡
ሲል መለሰለት፡፡
ንጉሡ በጣም ተደሰተና፤
‹‹አገርና ሥልጣን የገባህ አንተ ነህ፡፡ ስለሆነም ግዛተ-መንግሥቴን መውረስ ያለብህ አንተ ነህ፡፡
ወንድሞችህን ጥራቸው›› አለው፡፡
ወንድሞቹን ሄዶ ጠራቸውና ሶስቱም ንጉሡ ፊት ቆሙ፡፡
ንጉሡም፤
‹‹አያችሁ ልጆቼ፤ ከሦስታችሁ ብልህ ሆኖ ያገኘሁት ትንሹን ወንድማችሁን ነው፡፡ የአገር አስተዳዳሪ  ብልህ መሆን አለበት፡፡ ይሄ ወንድማችሁ ብልህ በመሆኑ እኔንም አልተወ፤ እናንተንም አልተወ፤ ህዝቡንም አልተወ፡፡ እኔ ትላንት ነኝ፡፡ እናንተ ዛሬ ናችሁ፡፡ ህዝቡ ነገና ዘለዓለም ነው፡፡ ስለዚህም ሁላችንም በጊዜ ላይ ሠንሠለት ሰርተን አገርን አገር እናደርጋለን፡፡ ትንሹን ወንድማችሁን ውደዱት፡፡ ታዘዙት፡፡ ተግባብታችሁ ኑሩ!›› አላቸው፡፡
*  *  *
አገርን አገር ለማድረግ ሁላችንም መኖር አለብን፡፡ ታሪክን መርሳት የለብንም፡፡ ዛሬ ላይ ቆመንም  ነገን መገንባት እንዳለብን ማሰብ ይገባል፡፡ አገሬውን የያዘ አገርን በአግባቡ ይመራል፡፡ ከአገሬው የመከረ ከአገር መከረ ማለት ነው። ልባዊ መወያየትን መፍራት የለብንም፡፡ ሥነስርዓትን መፍራት የለብንም፡፡ አሮጌው ማለፉን አዲሱ ማሸነፉን (The new is invincible ይሏልና) ጭራሽ መዘንጋት የለብንም፡፡ መወራረስ መኖሩን፣ መለዋወጥ አይቀሬነቱን፣ ቋሚውና ቀሪ ህዝብን አገር መሆኑን ለአንድ አፍታም አለመርሳት እጅግ ይበጃል፡፡ ህዝብ ችግር ላይ ከወደቀ ሆድ እንደሚብሰው አለመዘንጋት ነው፡፡ ፕሮፌሰር ሽብሩ ተድላ፤ ‹‹በጎጃም በገንዘብ ወዳድነታቸው ብዙ ችግር ፈጥረዋል›› ያሏቸውን ራስ ኃይሉን የገለፁበት መንገድ ለእኛም ይጠቅመናል፡- (ከ‹‹ጎሬዛም ማሪያም እስከ አዲስ አበባ›› ከሚለው መጽሐፍ)
‹‹እንደሚወሳው፤ በጢስ የሚባል የግብር ሥነስርዓት ዘርግተዋል፡፡ ስለሆነም ጢስ የሚጤስበት ጎጆ ሁሉ ግብር እንዲጣልበት ተወሰነ፡፡ ገበሬው የተጣለበትን ግብር መክፈል ስላልቻለ፣ ብዙ ቤተሰቦች ቤቶቻቸውን እየለቀቁ፣ እየተዳበሉ፣ አንድ ጎጆ ውስጥ መኖር ጀመሩ፣ በዚህም ድርጊት ጢስ የሚጤስባቸው ጉጆዎች ቁጥር ቀነሰ፡፡ የተዳበሉ ቤተሰቦች፣ አንድ ቤት ቢኖሩም ቅሉ፤ ምግባቸውን የሚያበስሉ በተለያዩ ምድጃዎች ላይ ስለነበር፣ ራስ ኃይሉ ይህን ሲረዱ፣ በጉልቻ ቁጥር ላይ የተመሰረተ አዲስ ግብር ጣሉ፡፡ ባላገር ችግሩን ለማቃለል በወሰደው እርምጃ አንፃር፣ ራስ አዳዲስ ህግና ደንብ እያወጡ፤ አራሹ     ከችግሩ መላቀቅ ተሳነው፡፡
በዚህን ጊዜ አንድ አንጀቷ ያረረ፣ የተማረረች የሚከተለውን ገጠመች፡-
መሶቤን ወሰዱ፣
ድስቴንም ወሰዱ፤
ራስ የቀረዎ ትንሽ አማርኛ፣
ሆዴን በወሰዷት አርፌ እንድተኛ፡፡”
የኢኮኖሚ ችግሮች ሲያመረቅዙ ፖለቲካዊ ባህሪን ይወልዳሉና ሰብሰብ፣ ጠንቀቅ ብሎ ማየትን ይጠይቃል፡፡ (politics is the concentrated form of economics ይሏልና) የህዝብ ኢኮኖሚያዊ ምሬት ምላሽ እንደሚሻ ሁሉ በመድብለ ገፁ ፖለቲካዊ ቁጣ ሲሆንም አስቸኳይ ምላሽ መሻቱን ቢያንስ ዛሬ በይፋ አውቀናል፡፡ በይፋ ሰምተናል። ቁጣው ስርዓተ አልበኛነትን እንዳይወልድ በጊዜ የአስተዋይ መፍትሄ መስጠት ወሳኝ ነው፡፡ ከስሩ ያልተነቀለ ችግር ዳግም ማቆጥቆጡ አሌ አይባልም፡፡ የዛሬውን ተገላገልኩት ብሎ መተኛት መፍትሄ አይሆንም፡፡ ሰላም የራሱ ሂደት አለው፡፡ “ካያያዝ ይቀደዳል” የሚለውን ብሂል አንርሳ፡፡ ቀውጢ ቀውጢንና ጥላቻን እንጂ መረጋጋትን አይወልድምና ረጋ ብሎ “የረጋ ወተት ቅቤ ይወጣዋልን” ማሰብ ነው! ሁሉም
የህብረተሰብ ክፍል የነውጡ - ቀውስ ገፈት ቀማሽ ነው። ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የደረሰው ሀዘን ሀዘንተኛ ነው፡፡ ሁላችንም፣ ለአንዲት ነብስ ማለፍ የምንቆረቆር ሁሉ ሀዘንተኞች ነን!ዛሬ እንደድሮው ዘመን “… ወይ እረሱ፣ ወይ መንኩሱ፣ ወይ ተኩሱ” አይባል ነገር 21ኛው ክፍለ
ዘመን ነው፡፡ (አገር፤ አንድ አራሽ፣ አንድ ቀዳሽ፣ አንድ ተኳሽ ያስፈልጋታል እንዲል መጽሐፍ፡፡)
ይልቁንም ሰላምን ዓላማ ማድረግ ዋና ጉዳያችን ነው፡፡ የምናርሰውና የምንቀድሰው ሰላም ሲኖር ነው፡፡ ሁከት፣ ነውጥ፣ ትርምስ፣ ዓላማ ቢስ ዘረፋ፣ ሲቀጣጠል የብዙ ህይወት፣ የብዙ ንብረት፣ የብዙ ሞራል ጥፋት ሊያስከትል እንደሚችል ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ሁሉም “ከአያያዝ ይቀደዳል” ነው፤ መላ-ጨመቁ!
ከትውልዶች መወራረስና ከትውልድ ቅብብል የምናተርፈው፤ ካለፈው የምንማረው ምንም ይሁን
ምን አንዳች ነገር አይጠፋም፡፡ ፕሮፌሰር ሽብሩ ተድላ፤ “የቅብብሎሽ ሩጫ” በሚለው ግጥማቸው
ታላቅ ምክር ለግሰውናል፡- ከሰማን፡፡
አባቶቻችን እጅ፣ ትንታግ ተቀብለን፤
ርስ - በርስ ሽኩቻ፣ እሳቱን አዳፍነን፤
ጨለማ ውስጥ ነን፤
አትበሉ!
እጁን የዘረጋው፣ ይህ አዲሱ ትውልድ፣
ከከሰለ ችቦ፤ የቱን ብርሃን ሊወስድ፤
አትበሉ፤
መልካሙን ነው ማየት፣
ውቡን ነው መመኘት፣
ብርሃን ይከሰታል፣ ከተዳፈነ እሳት፡፡
ከአገሬው መምከር፣ ወደ ራስ ማየት፣ የሚነገረውን ማዳመጥ፣ ከአገር ሽማግሌዎች መማር፣ ልባዊ ውይይት ማድረግ፣ ጥፋትን በወግ በወጉ መዳኘት፣ ክስተቶች የምን ነፀብራቅ እንደሆኑ መመርመር፣ ብሶትን በአግባቡ መቀየድ፣ የግርግር ተጠቃሚዎችን ለይቶ ማየት፤ ደንብሮ አለማስደንበር፤ ሌላውን ለማይቀደዳል!”