Administrator

Administrator

ግሪን ዌቭ አሊያንስ ከኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ጋር በአረንጓዴ ልማት ዙሪያ ለመሥራት የሚያስችለውን ስምምነት በዛሬው ዕለት  ረፋዱ ላይ ፈጸመ፡፡

ስምምነቱን የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ም/ ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ፍሬነሽ መኩሪያና የግሪን ዌቭ አሊያንስ ዋና ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ ረድኤት ያዘው በባለሥልጣኑ መ/ቤት አዳራሽ ተፈራርመዋል፡፡

የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ም/ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ፍሬነሽ መኩሪያ በፊርማ ሥነስርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ በጠ/ሚኒስትሩ ሃሳብ አመንጪነት የተጀመረውን አረንጓዴ ልማት ለማስቀጠል መንግሥታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት አጋርነት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፤ በዚህ ረገድ የዛሬው ስምምነት ፋይዳው የላቀ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ባለሥልጣን መ/ቤቱ  ከመጋቢት 20 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ የአየር፣ የውሀ፣ የአፈርና የድምጽ  ብክለትን ለመቀነስ የሚያስችል የ6 ወራት ዘመቻ መጀመሩን የገለጹት ወ/ሮ ፍሬነሽ፤ በአጋርነት መሥራት ዘመቻውን ውጤታማ ያደርገዋል ብለዋል፡፡

የግሪን ዌቭ አሊያንስ መሥራችና የቦርድ ሰብሳቢ አርቲስት ሚኪያስ ነጋሳ በበኩላቸው ባደረጉት ንግግር፤ የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን የሚያከናውናቸው ሥራዎች ሰፊ ከመሆናቸው አንጻር መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት አጋርነት ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፤ ዛሬ የተከናወነው ስምምነት የአረንጓዴ ልማት እንቅስቃሴውን ወደላቀ ደረጃ ለማሸጋገር የሚረዳ ነው ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት የዓባይ ግድብ 13ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ ያዘጋጀዉን የመታሰቢያ ቴምብር በዓሉን በማስመልከት በተዘጋጀዉ የፓናል ዉይይት መድረክ ላይ ይፋ አደረገ።
የአባይ ግድብ የመታሰቢያ ቴምብሩን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተመስገን ጥሩነህ፣የዉሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ እና የአባይ ግድብ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ሀላፊ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር) በጋራ መርቀዋል።
የመታሰቢያ ቴምብሩ ከዛሬ ጀምሮ ለ192 የአለም አገራት እንደሚሠራጭ ተገልጿል።

የደራሲና ጋዜጠኛ አበራ ለማ "የዓለማችን ምስጢራት" የተሰኘ አዲስ መጽሐፍ ከሰሞኑ ለአንባቢያን ቀርቧል።

ይህ አዲስ መጽሐፍ የፊታችን መጋቢት 28 2016 ዓ.ም በወመዘክር አዳራሽም ይመረቃል ተብሏል።

"ግጥም ሲጥም "ለሁሉም ክፍት የሆነ የኪነጥበብ  መድረክ ተመልሷል። በዚህም ሳምንትም የቦታ ለወጥ አድርጎ ነገ ረቡዕ መጋቢት 25 2016 ዓ.ም ከምሽቱ 12:00 ጀምሮ ገርጂ በሚገኘው ደስክ አዲስ ውስጥ ይካሄዳል ተብሏል።

"እንዲህ ያለም የለ"መጽሐፍ ረቡዕ ይመረቃል

የገጣሚ ሀብታሙ ሀደራ "እንዲህ ያለም የለ" የተሰኘ የግጥም ስብስብ መጽሐፍ የፊታችን ረቡዕ መጋቢት 25 2016 ዓ.ም ከ10:30 ጀምሮ በወመዘክር አዳራሽ ይመረቃል።

  • • ጎሳዬ ተስፋዬ፣ ሳሚ ዳንና ጃኪ ጎሲ ይሳተፉበታል

           ታዋቂ የኢትዮጵያ ድምፃዊያን የሚሳተፉበት “የኢትዮጵያ ሙዚቃ ቀን” በእስራኤል ቴላቪቭ እንደሚካሄድ  አፍሮ ስታይል ኢንተርቴይመንት አስታወቀ፡፡  
    የእስራኤል የነፃነት ቀንን ምክንያት በማድረግ፣ ግንቦት 5 ቀን 2016 ዓ፣ም የኢትዮጵያ የሙዚቃ ቀን በቴላቪቭ የሚካሄድ ሲሆን፤ አፍሮ ስታይል ኢንተርቴይመንት ባዘጋጀው በዚህ  ኮንሰርት ላይ ጎሳዬ ተስፋዬ፤ ሳሚ ዳንና ጃኪ ጎሲ እንደሚጫወቱ ተገልጿል። ታዋቂ የጃማይካ ዳንስሆል አርቲስትም በኮንሰርቱ ላይ  እንደሚሳተፍ  ተጠቁሟል።
    የኢትዮጵያ የሙዚቃ ቀንን ለማክበር የተሰናዳው መርሐግብር ከሚያዚያ 29 እስከ ግንቦት 10 ቀን 2016 ዓ.ም  የሚቆይ ሲሆን፤ በተለያዩ የሙዚቃ ዝግጅቶችና በእስራኤል ከተሞች በሚካሄዱ ጉብኝቶች የሚታጀብ ይሆናል ተብሏል።
    ከሚያዚያ 29 እስከ ግንቦት 4 ቀን 2016 ዓ.ም በእየሩሳሌም ከተማ ጉብኝቶች የተዘጋጁ ሲሆን፤ ግንቦት 5  በሃንገር 09 አዳራሽ ቴላቪቭ ላይ የኢትዮጵያ ሙዚቃ ቀን ልዩ  ኮንሰርት እንደሚካሄድ ተጠቁሟል፡፡  በተመሳሳይ ቀን የቴላቪቭ ከተማን ለማስጎብኘትም ታቅዷል።  ግንቦት 8 ቀን 2016 ዓ.ም በሚር ያቆብ አዘጋጅነት በቴላቪቭ ሐንገር 09 አዳራሽ፣ የሬጌ ሙዚቃ ዝግጅትና ዳንስ እንደሚቀርብም ታውቋል።


ይህ ተከታታይ ድራማ 42 ክፍሎች ያሉት ሲሆን በሳምንት ሁለት ቀናት ማለትም ቅዳሜና እሁድ ከምሽቱ አንድ ሰዓት ለተመልካቾች ይቀርባል።

"ዕንቁ ሴት፣ ንቁ ሴት፣ ዝግጁ ሴት"

"ዕንቁ ሴት፣ ንቁ ሴት፣ ዝግጁ ሴት"የተሰኘ  ቅዳሜ መጋቢት 21 2016 ዓ.ም ከቀኑ 10:00 ጀምሮ ሰንጋተራ በሚገኙ ፐርፐር ብላክ አዳራሽ ውስጥ ይካሄዳል።

በዕለቱም ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠ ፣ አርቲስት መቅደስ ፀጋዬ ፣ ሲሰተር ዘቢደር ዘውዴ ጭምሮ የተለያዩ እንግዶች ሀሳቦቻቸውን ያቀርባሉ ተብሏል።

ሃያኛው የባለአክሲዮኖች አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤውን መጋቢት 14 ቀን 2014 ዓ.ም በሚሊኒየም አዳራሽ ያካሄደው ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ፣ የተከፈለ ካፒታሉን ወደ 20 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ ውሳኔ አሳለፈ፡፡    
የባንኩ አዲሱ የዲሬክተሮች ቦርድ ሊቀመንበር አቶ ሺሰማ ሸዋነካ በጉባኤው ላይ ባደረጉት ንግግር፣ ንብ ኢንተርናሽናል ባንክን ወደ ቀድሞ ከፍታው ለመመለስና ላቅ ወዳለ ደረጃ ለማድረስ በሚያስችል ጉዞ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።
“ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ በበርካታ ደንበኞች በተለይም በንግዱ ማኅበረሰብ ዘንድ ተወዳጅ ባንክ ነው’’ ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ባለአክሲዮኖች ከምንጊዜውም በበለጠ ድጋፋቸውን እንዲያረጋግጡለት ጠይቀዋል።
ቀደም ሲል እንደ አገርም ሆነ በዘርፉ እንዳሉ ሌሎች ተቋማት ሁሉ ያጋጠሙ የገንዘብ አከል ችግሮች በንብ ባንክ ደረጃ በባሰ መልኩ መስተዋላቸውን በመጥቀስ፣ አሁን ግን አዲስ የተመረጠው የዲሬክተሮች ቦርድ ችግሮችን እያቃለለ መምጣቱን ጠቁመዋል፡፡
ባንኩ፣ “በአዲስ መንፈስ፣ ለላቀ ከፍታ!” በሚል መሪ ቃል ያስጀመረውን የማርኬቲንግ ንቅናቄ ተከትሎም፣ በሂደት የባንኩ ቅርንጫፎች ምንም አይነት የስንቅ ችግር እንዳያጋጥማቸው መሠራቱን ተናግረዋል፡፡ ደንበኞች ከቼክ ምንዛሪ ጋር በተገናኘም ስጋት እንዳይገባቸው መልዕክት አስተላልፈዋል።
ባንኩ በምንጊዜም ባለውለታነት ሊጠቀሱ የሚችሉ የረጅም አመታት ባለአክሲዮኖችና ደንበኞች ያሉት መሆኑን የጠቀሱት ሊቀመንበሩ፤ አሁን ላይ ሁሉም ገንዘባቸውን ሲያስወጡም ሆነ ሲያስገቡ በንብ ኢንተርናሽናል ባንክ እንዲሆን ጠይቀዋል፡፡
የደንበኞቹን እምነት መልሶ ለመገንባት የተለያዩ ሥራዎችን እያከናወነ የሚገኘው ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ፤ አስቸጋሪ ባለው የሥራ ወቅት የተከፉ ደንበኞቹን በይፋ ይቅርታ በመጠየቅ በጀመረው አገራዊ የማርኬቲንግ ንቅናቄ መልካም ለውጦችን እያመጣ መሆኑን የቦርድ ሊቀመንበሩ አቶ ሺሰማ አስታውቀዋል።
በቀጣይም ወደ ትግበራ በገባው የዘጠና ቀናት ፍኖተ ካርታ ዕቅድ መሠረት በሁሉም የባንክ አገልግሎቶች ፈጣን ለውጦችን በማምጣት ንብ ባንክን ወደነበረበትና ከዚያም ላቅ ወዳለ ደረጃ ለማሸጋገር ትልቅ ቁርጠኝነት መኖሩን በአስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤው ለተገኙ ባለአክሲዮኖች ገልጸዋል፡፡
አዲሱ ቦርድ ወደ ሥራ ከገባበት አጭር ጊዜ አኳያ ጥሩ ውጤት ለማስመዝገብ የሚያስችሉ እንቅስቃሴዎችን እያደረገ መሆኑን መገንዘባቸውን የገለጹት የጉባኤው ተሳታፊ ባለአክሲዮኖችም፤ ቦርዱ ባንኩን ከግል ባንኮች ዘርፍ ከፊት ለማሰለፍ የሚያደርገውን ጥረት በመደገፍ ከጎኑ እንደሚቆሙ በሰጡት ቃል አረጋግጠዋል።
በጉባኤው ከተነሱ አጀንዳዎች መካከል አንዱ፣ እ.ኤ.አ በ2022 የተገኘውና ያልተወሰነበት የትርፍ ድርሻ ክፍፍል ላይ ውይይት በማድረግ ገንዘቡ ለባንኩ ካፒታል ማሳደጊያነት እንዲውል የባለአክሲዮኖች ጉባኤ በአብላጫ ድምፅ ወስኗል።
በባንኩ በ18ኛ አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤ የተወሰነውን የካፒታል ማሳደጊያ ጊዜ እንዲሻሻል በተደረገው ውይይትም፣ እስከ ሰኔ 30 ቀን 2016 ዓ.ም ተጠናቅቆ እንዲከፈል መወሰኑን ከባንኩ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

በአማራ ክልልና በትግራይጊዜያዊ አስተዳደር መካከል የተከሰተው ውዝግብ ተባብሶ ቀጥሏል። ሁለቱም ወገኖች በየፊናቸው ማስጠንቀቂያና መግለጫ እያወጡ ነው፡፡
የአማራ ክልል  ትናንት ባወጣው መግለጫ፤ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ሀገሪቱን ና ሁለቱን ክልሎች ወደ ቀውስ ከሚያስገቡ ተግባራቱ  እንዲቆጠብ አስጠንቅቋል። የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር  ያወጣው መግለጫ ጠብ አጫሪ  እንደሆነም ገልጿል። ክልሉ ባወጣው በዚሁ መግለጫው፤  “የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር  መጋቢት 18 ቀን 2016 ዓ.ም የራያ አላማጣ ወረዳ ቀበሌዎችን በመያዝ  የአካባቢው ነዋሪዎችን በመግደልና በማሰቃየት ላይ ይገኛል” ሲል ከስሷል።
የአማራ ክልል በመግለጫው፤ “የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ካቢኔ መጋቢት 16 ቀን 2016 ዓ.ም ከመማሪያ መጽሐፍ ካርታ ጋር በተያያዘ በአማራ ክልል ላይ ጥቃት ከመፈጸም የማይመለስ መሆኑን የሚገልጽ የጠብ አጫሪ መግለጫ ማውጣቱ ካለፉት ድርብርብ ውድቀቶች ትምህርት አለመውሰድን ከማሳየት የዘለለ ፋይዳ አይኖረውም” ብሏል።
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ለሀገሪቱ ቋሚ ቀውስ ምንጭ ከሚያደርጉት ተግባራት እንዲታቀብና ሀገሪቱንና ሁለቱን ክልሎች ወደ ቀውስ ከሚያስገቡ ተግባራት እንዲቆጠብም የአማራ ክልል መንግስትአስጠንቅቋል።  በተጨማሪም ጊዜያዊ አስተዳደሩ ከለመደው አጓጉል የካርታ ፖለቲካ ጨዋታ እንዲወጣና የህዝብን ፍላጎት ማዕከል ባደረጉ ውይይቶች ላይ እንዲያተኩር ክልሉ  መክሯል።
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ካቢኔ በበኩሉ ሰሞኑን ባወጣው መግለጫው፤ “የአማራ ክልል መንግሥት የትግራይ መሬቶችን የግዛቱ አካል በማድረግ፣ በክልሉ ካርታ ላይ አስፍሯል፤ የትግራይ ክልል መሬቶች የሰፈሩበትን ካርታ በትምህርት ካሪኩለሙ በማካተት እያስተማረበት እንደሚገኝ ተረድቻለሁ” ብሏል።
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ካቢኔ፣ የአማራ ክልል በመማሪያ መጽሐፍት ላይ ያወጣውን የተሳሳተ ካርታ በአስቸኳይ ማስተካከያ እንዲያደርግ በመግለጫው  ያስጠነቀቀ ሲሆን፤ ይህ የማይሆን ከሆነ ግን “ይህን ተከትሎ ለሚመጣው ነገር ሁሉ ሃላፊነቱን የሚወስደው የአማራ ክልል መሆኑን ልናሳውቅ እንወዳለን” ብሏል።


Page 6 of 703