Administrator

Administrator

“የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች ሁሉ ተባበሩ”
ካርል ማርክስ “የዓለም ሠራተኞች ተባበሩ፤ ከሰንሰለቱ በስተቀር የሚቀርባችሁ ነገር የለም ብሎ ነበር”፤ እኔም እላለሁ፤ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች ሁሉ ተባበሩ፣ ከእስራት ሰንሰለቱ በስተቀር የሚቀርባችሁ ምንም ነገር የለም፡፡ (All Ethiopian oppositions Unite! You have nothing to lose but your chains) ማርክስን መጥቀሴ ማርክስሲት ሆኜ አይደለም፤ አባባሉ እውነትነት ያለው ሆኖ ስለአገኘሁት እንጂ! ለነገሩ ማርክስን በደንብ ሳያውቁ ማርክሲስትም ሆነ ፀረ-ማርክስሲት መሆን አይቻልም።
28 የተቃውሞ ፖለቲካ ፓርቲዎች የፖለቲካ ምኅዳሩ እንዲሰፋ፣ ምርጫው ፍትሐዊና ገለልተኛ እንዲሆን ያቀረቧቸው ጥያቄዎች በአግባቡ ሳይመለሱ ወደ ምርጫው እንደማይገቡ በሙሉ ድምፅ ወስነዋል። ይህ ትብብር ቀጣይነት የሚኖረው ከሆነ በእውነቱ በጣም ታሪካዊ ሊባል የሚችል ነው። የዛሬው ጽሑፌ በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ የሚያተኩር ሆኖ በቀጣይ ቢደረጉ መልካም ነው ብዬ በማስባቸው ነገሮች ላይ የራሴን ሐሳብ ለመሰንዘር ነው።
ኻያ ስምንት ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች “ምንም ውጤት በሌለው ምርጫ አንሳተፍም፣ የአገር ሀብትም በማባከኑ ወንጀል ላይ ተሳታፊ አንሆንም” ብለው ራሳቸውን ከምርጫው ማግለላቸው በራሱ ትልቅ ነገር ነው።

በእኔ እይታ ከዚህ ረብ የለሽ የምርጫ ሂደት ራስን ማግለል ከሰላማዊ ዐመፅ - አልቦ ትግል አማራጮች አንዱ ነው - ከዐምባገነን መንግሥት ጋር አለመተባበር! ይህ በራሱ ግን በቀጣይ እርምጃዎች እስካልተደገፈ ድረስ ውጤቱ “ምንም” የውሳኔ አማራጭ ሊሆን ይችላል። ማርክስ “የፕሮግራም ጋጋታ ብቻውን ለውጥ አያመጣም” ብሏል።

ይህ ሐቅ አሁንም ይሠራል። ወደ ውጤት የማይቀየር ዘጠና ዐይነት ፕሮግራም መኖሩ ምንም አይፈይድም። ትግሉን ለማካሄድ መሠረታዊ በሆኑ ተጨባጭ አጀንዳዎች ላይ ብቻ ተመርኩዞ፣ ባለው ላይ እየተደመረ የሚሄድ የተመረጠ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ መኖር አለበት። ወደ ምርጫ መግባት አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ተመራጭ የትግል ስልት አይደለም። ከዚህ አንጻር አሁን ወደ ምርጫ አለመግባቱ ቀዳሚው ተመራጭ ስልት ሆኖ ተገኝቷል ማለት ነው። ከዚህ በኋላስ ምን እናድርግ የሚል ጥያቄ መምጣቱ የሚጠበቅ ነው። በተስፋ መቁረጥ፣ አንገት ደፍቶ መቀመጥ “ፖለቲካዊ ለውጥ ለማምጣት ተሰልፈናል” ከሚሉ ኅይሎች የሚጠበቅ ነገር አይደለም። በዚህ ጊዜ ትክክለኛው አማራጭ የሚሆነው ሰላማዊ፣ ዐመፅ አልቦ ትግል ለማካሄድ መነሣት ነው።
ይህ ሰላማዊ፣ ዐመፅ አልቦ ትግል ጄን ሻርፕ “ከዐምባገነንነት ወደ ዴሞክራሲ” በሚለው መጽሐፉ ላይ እንዳስቀመጠው 198 ደረጃዎች አሉት። ሰሞኑን በጋራ በተደረሰበት ውሳኔ አንዱን ብቻ ነው በተወሰነ መልኩ የተጠቀምነው፤ ገና 197 ደረጃዎች ይቀራሉ ማለት ነው። እንግዲህ ተግቶ ደረጃ በደረጃ አንድ በአንድ መተግበር ያስፈልጋል።
ይህ ትግል ጥብቅ ዲሲፒሊን የሚጠይቅ፣ ነገሮች ባልታሰበ ኹኔታ ወደ ዐመፅና ብጥብጥ እንዳያመሩ መጠንቀቅን የግድ የሚል፣ ሐላፊነት የሚሰማቸው ሰዎች ብቻ ሊያደርጉት የሚችሉት ነገር ነው። እንደ ማኅተመ ጋንዲ ያለ የሞራል ልዕልና ያለው መሪ፣ እንደ ሕንዶች ያለ ሥርዐት ያለውና በአንድ ላይ ያለልዩነት የሚሰለፍ ሕዝብ መፈጠር ይኖርበታል። ይህ እንዲኾን ከተፈለገ በመጀመሪያ እንደ ሕዝብ ያሉብንን ልዩነቶች ለማጥበብና ለማመቻመች ጠንክሮ መሥራት ያስፈልጋል።
ቀጥሎ መሠራት ያለበት ስለሰላማዊ ዐመፅ አልቦ ትግል በስፋትና በጥልቀት ማስተማር፣ ለዚህ መርሕ በተግባር መገዛት እንዲቻል ማለማመድ ያስፈልጋል። በዚህ ዙሪያ ሙስሊም ወንድሞቻችን እስካሁን እያሳዩት ያለው ሰላማዊ ተቃውሞ የሚደነቅ ነው። አገር በቀል የሰላማዊ ትግል ስልት በመሆኑ ለእኛ ጥሩ ትምህርትና ሞዴል ሊሆን የሚችል ነው። ይህ በራሱ የሚያሳየው ነገር አለ፤ ሕዝባችን በአግባቡ የሚመራውና አምኖ ሊከተለው የሚችል መሪ ድርጅት ካገኘ ሰላማዊ ትግል ለማካሄድ አያዳግተውም።
እዚህ ላይ መሠመር ያለበት አንድ ዋና ነጥብ ግን አለ፤ ይህ ዐይነቱ የፖለቲካ ትግል እርስ በርስ ለስድብና ለዱላ የሚገባበዙ የፖለቲካ መሪዎች የሚመሩት ሊሆን አይችልም። በትምህርት ብዛት ወይም በፖለቲካው ብዙ ዘመን በማስቆጠርም አይደለም። “እገሌ ወደ ፓርላማ የገባው ኢሕአዴግ ስለደገፈው ነው፤ እገሌ ደግሞ የኢሕአዴግ ተለጣፊና ተቀላቢ ነው” እያሉ በማውራትና በማስወራትም የሚሳካ አይደለም። ተጨባጭ አጀንዳዎችና የፖለቲካ ስትራቴጂዎች ላይ የተመሠረተ፤ ሊታይ የሚችል ተጨባጭ እንቅስቃሴ ማድረግ ግድ የሚል ነው።
ትርጉም የሌለው ስብሰባ በየጊዜው በማካሄድም አይደለም። ስብሰባ በራሱ ቁም ነገር አስገኝቶ አያውቅም። ፖለቲካዊ ትግል ማካሄድ ማለት በየጊዜው ስብሰባ ማካሄድ ማለት አይደለምና። የፖለቲካ አመራሮቹ፣ ፖለቲካውን በተገቢው ሁኔታ ለመምራት ወገባቸውን ጠበቅ፣ ምራቃቸውን ዋጥ አድርገው መነሣት ይኖርባቸዋል።
ሕገ መንግሥቱን ለማስከበር በሚደረገው ትግል ሐላፊነት ወስደው ለመምራት፣ መታሰርም ካለ ለመታሰር ዝግጁ መሆን ያስፈልጋል። “እኔ ሜዳ ሜዳውን ነው መታገል የምፈልገው እንጂ መታሰር እፈራለሁ” የሚል የፖለቲካ መሪ ካለ አቋሙን መመርመር፣ ካልኾነም ራሱን ከአሁኑ ከፖለቲካው ማግለል አለበት። ከዚህ በኋላ በፖለቲካው የሚኖሩና ለፖለቲካው የሚኖሩ ሰዎች መንገዳቸው አንድ ላይ መሆን የለበትም። ሕገ መንግሥቱን የሚጥስ መንግሥት ባለበት አገር፣ ሕገ መንግሥቱን ለማስከበር መነሣት በራሱ ወንጀል ሆኖ እስር ቤት ሊያስወርድ እንደሚችል ምንም ጥርጥር የለውም።
ራሳቸውን ከምርጫው ያገለሉት ፓርቲዎች ቀጣይ ርምጃ መሆን ያለበት፣ ሕዝቡን ሰብስቦ ማነጋገር ነው። በምርጫው ላይ ለመሳተፍ “የምርጫው ሜዳ ይስተካከል፣ ምርጫ ቦርድም ገለልተኛ ይሁን” ብለን የጠየቅነው ጥያቄ፣ የኢሕአዴግ መንግሥትና ምርጫ ቦርድ የዝሆን ጆሮ ሰጥተውታል። ይህ ጥያቄአችን ተቀባይነት አግኝቶ ተፈጻሚ እስኪኾን ድረስ ሕዝቡ ሰላማዊ ትግል እንዲያካሂድ መጥራትና መምራት ያስፈልጋል። ፓርቲዎቹ አባሎቻቸውንና ደጋፊዎቻቸውን ይዘው ሰልፍ መውጣት፣ አመራሮቹም ለተቃውሞ መንገድ ላይ ተኝቶ ማደርና መቀመጥ መጀመር ይኖርባቸዋል። ሕዝቡ የፓርቲዎቹን ቁርጠኝነት ሲገነዘብ በልበ ሙሉነት ለመደገፍ ይነሣል፤ መብቱን ለማስከበርም በጽናት መቆም ይጀምራል።
የፓርቲዎቹ አመራሮች እንዲህ በሚያደርጉበት ጊዜ ሊታሰሩ ስለሚችሉ ሌላ ተጠባበቂ አመራር ማዘጋጀት፣ እንደገና ያ አመራር ሲታሰር ደግሞ እንደዚሁ ሌላ እየተተካ ጥያቄው እስኪመለስ ድረስ መቀጠል ያስፈልጋል። አንድ እውነት አለ፤ ሁላችንም ለመታሰርና ለመሞት እስከተዘጋጀን ድረስ፣ ኢሕአዴግ ሁሉንም ማሰር፣ ሁሉንም መግደል ፈጽሞ አይችልም። እነ አንዷለም እና እነ በቀለ ገርባ የታሰሩት ሌሎቻችን ዝም በማለታችን ነው። ይህ ሥርዐት የመለወጡ ቁርጠኝነት በሁላችን ዘንድ እስከሌለ ድረስ በተወሰኑ ሰዎች ትግል ብቻ ለውጥ ይመጣል ማለት የዋህነት ነው።
ኢሕአዴግ ሁኔታዎች አስገድደውት ካልሆነ በስተቀር በእኩልነት ሜዳ፣ በገለልተኛ ዳኛ ሥር ሆኖ በምርጫ አይወዳደርም። በማያጠራጥር ሁኔታ ቢሸነፍም ሥልጣኑን በሰላም አያስረክብም። እነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች ማለትም እኩል የመወዳደሪያ ሜዳና ገለልተኛ ምርጫ ቦርድ በትክክል እስኪኖር ድረስ በምርጫ የመሳተፉ ጉዳይ መታሰብ የለበትም። በዚህ ጉዳይ ላይ ፓርቲዎቹ ቁርጠኛ አቋም ከያዙ ገዥው ፓርቲ በምርጫ ቦርድ በኩል “በምርጫ ስላልተሳተፋችሁ” ብሎ የፓርቲዎቹን ሕጋዊ ሰርተፊኬት ወደ መቀማቱ እንደሚገባ ምንም ጥርጥር የለውም።
በዚህ ጊዜም ቢሆን ትግሉ ወደ ህዝባዊ ንቅናቄ እንዲሸጋገር ተግቶ መሥራት እንጂ መደናገጥ አያስፈልግም። የግብጽ ሙስሊም ወንድማማች ፓርቲ ሕጋዊ ዕውቅናውን በሙባረክ መንግሥት በኩል ቢያጣም እውነተኛውን ህልውናውን ግን አላጣም ነበር። ሌላው ቀርቶ አባላቱ በግል እየተወዳደሩ የፓርላማውን አሥራ አምስት በመቶ መቀመጫ እስከመያዝ የደረሱበት ጊዜ ሁሉ ነበር።
ከዚህ የምንረዳው አንድ የፖለቲካ ፓርቲ የምስክር ወረቀቱ ሲቀማ የሚጠፋ ከሆነ ሲጀመር የፖለቲካ ፓርቲ አልነበረም ማለት ነው። የአንድ ፖለቲካ ፓርቲ ህልውና በጠንካራ ሕዝባዊ መሠረት ላይ እንጂ በሰርተፊኬት ላይ መቆም የለበትም። ስለዚህ ህልውናውን አላግባብ በሚያጣበት ወቅትም ቢሆን ትግሉ ባለው ሕዝባዊ መሠረት መቀጠል የሚችል፣ ከሰርተፊኬት በላይ የሆነ አቅም ያለው ኅይል መሆን መቻል ይኖርበታል። አንድ ፖለቲካዊ ፓርቲ ጽኑ ሕዝባዊ መሠረት፣ ጠንካራ አደረጃጀትና አመራር ከሌለው በስለላ፣ በጦር፣ በኢኮኖሚና በመዋቅር በደንብ የተደራጀን መንግሥት ማሸነፍና ሥርዐት መለወጥ አይችልም።
ከሁሉም በላይ በእኛ አገር ያለውን ተጨባጭ ፖለቲካዊ ሁኔታ በደንብ ማጤን ያስፈልጋል። የአገራችን ችግር የሥልጣን ጥያቄ ብቻ አይደለም። ትግሉ የርእዮተ ዓለም ትግል መሆኑንም መረዳት ያስፈልጋል። ሁለት አብረው ሊሄዱና ሊታረቁ የማይችሉ የአብዮታዊ ዴሞክራሲና የሊበራል ዴሞክራሲ ትግል ነው እየተካሄደ ያለው።
ኢሕአዴግ መሠረቱ ማርክስሲት ድርጅት ስለሆነ ይህን ቅራኔ በሚገባ ይረዳዋል። ዋናው ነጥብ ኢህአዴግ በትክክል በሁሉም ነገር እስካልተሸነፈ ድረስ በምርጫ ስለተሸነፈ ብቻ ሥልጣኑን ያስረክባል ማለት እንዳልሆነ በደንብ መታወቅ አለበት። ኢሕአዴግ ሁልጊዜ በምርጫ የሚወዳደረው እንደሚያሸንፍ እርግጠኛ ሆኖ ነው። እንደሚሸነፍ ቢያውቅ፣ ማወቅ ሳይሆን ቢጠረጥር እንኳ ወደ ምርጫ ውድድር አይገባም።
ስለዚህ ከገዢው ፓርቲ ጋር በምርጫ ለመወዳደር የሚቻለው በመጀመሪያ ነፃና ገለልተኛ ምርጫ ቦርድ እንዲሁም እኩል የውድድር ሜዳ ሲፈጠር ብቻ ነው። ኢህአዴግ ይህን አምኖ እስኪቀበል ድረስ ግን ሰላማዊ ትግሉን ብቻ አጠናክረን መቀጠል ይኖርብናል። ኢሕአዴግን ወደዚህ ደረጃ ሳያመጡ ከእርሱ ጋር በምርጫ መወዳደር እርሱን ከማጀብ፣ የእርሱን ድል ከማድመቅ ውጪ ትርጉም አይኖረውም። በማጀቡ ሂደት ከአሁን በፊት እንደታየው የተወሰኑ የተቃዋሚ ፓርቲ ተመራጮችን ወደ ፓርላማ ማስገባት ይቻል ይሆናል። የሥርዐት ለውጥ ግን በዚህ መንገድ አይመጣም ፤ እስከአሁን የተጓዝንበት ልምድ የሚያሳየውም ይሄንኑ ነው።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ስነጽሑፍ ትምህርት ክፍል ለረጅም አመታት በመምህርነት ያገለገሉት ዶ/ር ዮናስ አድማሱ በተወለዱ በ69 ዓመታቸው በትላንትናው ዕለት ከዚህ አለም በሞት ተለዩ፡፡
ህዳር 6 ቀን1935 ዓ.ም ከእናታቸው ከወ/ሮ ጌጤነሽ (ውባለ ጐንደር) ቸኮል እና ከአባታቸው ከቶ አድማሱ ሃዳስ ማርያም በአዲስ አበባ ደጃች ውቤ ሠፈር የተወለዱት ዶ/ር ዮናስብቻቸውን በሚኖሩበት ቤታቸው ውስጥ ህይወታቸው አልፎ እንደተገኙ ምንጮ ጠቁመዋል፡፡ ፖሊስ አስከሬኑን ለምርመራ ወደ ሆስፒታል ሊወስድ እንደወሰደ የጠቆሙ ምንጮች፤ የቀብር ስነስርአታቸው የሚፈፀምበት ቀን እንደተወሰነ ገልፀዋል፡፡

ትዳር ያልመሰረቱትና ልጆች የሌላቸው ዶ/ር ዮናስ፤ በቅርቡ በህይወት በሌለው በታናሽ ወንድማቸው በዶ/ር ዮሐንስ አድማሱ የተዘጋጀውን የዮፍታሔ ንጉሴ የህይወት ታሪክ ጥናታዊ ጽሑፍ አርመው በመጽሐፍ መልክ እንዲታተም በማድረግ ለምርቃቱ በመዘጋጀት ላይ እንደነበሩ ታውቋል፡፡ 

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ የታተመው መጽሐፉ፤ የካቲት 13 ቀን 2005 ዓ.ም ለምርቃት ስነስርዓቱ ቀጠሮ ተይዞለት እንደነበር ተገልጿል፡፡
በቋንቋና ስነጽሑፍ መምህርነታቸው የሚታወቁት ዶ/ር ዮናስ፤ ከ5 አመት እስከ 9 አመት ባለው የልጅነት ጊዜያቸው የቤተክህነት ትምህርትን፣ ከዚያም በኮከበ ጽብሃ የቀዳማዊ ሃይለስላሴ አንደኛ ደረጃ ት/ቤት የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ተከታትለዋል፡፡
አጭር የመምህርነት ስልጠና ከወሰዱ በኋላም ለአንድ አመት በቀድሞ የወለጋ ክ/ሀገር በአንደኛ ደረጃ መምህርነት እንዳገለገሉ የህይወታ ታሪካቸው ያስረዳል፡፡
በኋላም አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በመግባት በኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ስነጽሑፍ የትምህርት ክፍል የመጀመሪያ ድግሪያቸውን በ1959 ዓ.ም አግኝተዋል፡፡ ከ1960 ጀምሮ ለአንድ ዓመት በዲፓርትመንቱ በመምህርነት ሲያገለግሉ ከቆዩ በኋላ በ1962 ዓ.ም የትምህርት እድል አግኝተው ወደ አሜሪካ በመጓዝ በሎስአንጀለስ ዩኒቨርሲቲ ሁለተኛ ድግሪያቸውን በእንግሊዝኛ ቋንቋ ወስደዋል፡፡ ከዚያም ወደ ሃገር ውስጥ ተመልሰው በሙያቸው ማገልገል ቢጀምሩም በ1970 ዓ.ም በቀይ ሽብር ምክንያት በድጋሚ ተሠደው ወደ አሜሪካ በማቅናት እዚያው የዶክትሬት ድግሪ ትምህርታቸውን ተከታትለው ከደርግ ውድቀት በኋላ በ1988 ዓ.ም ወደ ሀገር ውስጥ በመመለስ እስከ ህልፈተ ጊዜያቸው ድረስ በመምህርነት ሲያገለግሉ መቆየታቸውን የህይወት ታሪካቸው ያስረዳል፡፡

 

ከአገራችን ተረቶች አንዱ እንዲህ ይላል፡፡ አንድ ቁራ የሚበላው አጥቶ ከቦታ ቦታ ይዘዋወራል፡፡ አየር ላይ ሲንከራተት አንድ አሞራ ያጋጥመዋል፡፡ አሞራ፤ “አያ ቁራ ወዴት እየሄድክ ነው?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ቁራም፤ “የምበላው ነገር ባገኝ ብዬ ብዙ ዞርኩኝ፤ ግን እስካሁን አላገኘሁም” ሲል ይመልሳል፡፡ አሞራ፤ “እዚያ ማዶ በሬ አርደው ቅርጫ ሲያደርጉ ተመልክቻለሁ፡፡ እሰቲ ሂድና አካባቢው ላይ አንዣብ፡፡” ቁራ፤ “እግዚሃር ይስጥህ ወደዚያው ሄጄ የእለት ጉርሴን ብፈልግ ይሻላል፡፡” ቁራ አንደተነገረው በሬ ወደታረደበት መንደር ይሄዳል፡፡ በአየር ላይ ሆኖ ያንቋርራል፡፡ ቅርጫ የሚካፈሉት ሰዎች ያዩትና ድንጋይ እያነሱ እየወረወሩ ያባርሩታል፡፡ ቁራው ይሸሽና ዞሮ ዞሮ መጥቶ ደሞ ዛፍ ላይ ያርፋል፡፡

ሰዎቹ ያዩትና በቅዝምዝም ዱላ ሊመቱት ያምዘገዝጉበታል፡፡ የድንጋይ እሩምታ ይለቁበታል፡፡ ሸሽቶ ወደ አየር ይበራል፡፡ ይሄኔ አሞራ ያገኘዋል፡፡ አሞራ፤ “አያ ቁራ ጠግበህ በላህ?” ይለዋል፡፡ ቁራ፤ “ምን እበላለሁ ሰዎቹ አይናቸውን እኔ ላይ ተክለው በየትኛውም መንገድ ብሞክር ድርሽ አላስደርግ አሉኝ!” አሞራ፤ “እንግዲያው እንዲህ እናድርግ፡፡ አንተ በድንጋይ ቢወረውሩ የማያገኙህ ቦታ ሁንና ጩህባቸው፡፡ አንተን ለመምታት ወዳንተ ዞረው ሲያተኩሩ እኔ አካባቢው ላይ አድፍጬ እቆይና በአሳቻ ሰዓት ደህናውን ብልት መንትፌ እሮጣለሁ፡፡

ከዚያ እንካፈላለን!” ቁራ በዚህ ይስማማና ከፍ ብሎ በአየር ላይ ሆኖ ጩኸቱን ያቀልጠዋል፡፡ አሞራ እንደገመተው ሰዎቹ እየተሯሯጡ ድንጋይም፣ እንጨትም፣ እያነሱ ወደ አየር እያጐኑ መከላከል ቀጠሉ፡፡ ትርምስ ሆነ፡፡ አሞራ ሆዬ አስቀድሞ በቅርጫው አቅራቢያ ሣር የሚግጡ በጐች ዘንድ ይመጣና አንዱ በግ ላይ አርፎ ድምፁን ፀጥ አድርጐ ይጠብቅ ኖሯል፡፡ በጉ መናገርም፤ ከላዬ ላይ ውረድም፤ ለማለት ባለመቻሉ ዝም ብሎ ሣሩን ይግጣል፡፡ አሞራ ትርምሱ በጣም የተጧጧፈበትን አሳቻ ሰዓት ጠብቆ እንዳለው አንዱን ደህና ሙዳ መንትፎ ክንፌ አውጪኝ ይላል፡፡ ቁራ አሁንም ጩኸቱን ቀጥሏል፡፡ አሞራ ወደማይደረስበት አቅጣጫ በረረ፡፡ ቁራ እንዳንቋረረ ቀረ! “ጩኸትን ለቁራ፣ መብልን ለአሞራ” ይሏል ይሄው ነው፡፡ *** የእለት ሳሩን አቀርቅሮ የሚግጥ በግ ሆኖ የአሞራ መቀመጫ ከመሆን ያድነን፡፡

ቀና ብለን ውረድ ለማለት የማንችለው፣ ገፍተን የማናባርረው፤ ሮጠን የማናመልጠው ባላጋራ፣ መረማመጃ ከመሆን ያውጣን፡፡ እንደ ቁራ ከመጮህ፣ እንደባለቅርጫ ህዝብ ሙዳችንን ከመመንተፍ ያትርፈን፡፡ ከሚዲያ ጩኸትና ዘራፌዋ፣ ከማይናከስ አንበሳ አበሳ፣ ሁኔታዎችን ሳያመዛዝን ጥልቅ ከሚል አድር - ባይ ይሰውረን፡፡ “ቅንዝንዝንና፣ የቀን ጐባጣን ስቀህ አሳልፈው፣ ቢያምርህ ሰው መሆን” የሚለውን የሻምበል ዮሐንስ አፈወርቅን ግጥም ልብ እንል ዘንድ ልብ ይስጠን፡፡ የሀገራችን የመማር ማስተማር ሂደት አሳሳቢ ነው፡፡ የራስ እድገት፣ ሀገራዊ እድገትና ሙያዊ እድገት ነው የመማር-መማማር አላማ፡፡ ይህ በእርግጥ እየሆነ ነወይ፤ ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ በተለይ የሳይንስ ነክና ሂሳብ ነክ ትምህርቶች ስምረት አስፈሪ ነው፡፡ በፍላጐት መመደብ ቅንጦት ከሆነ ሰንብቷል፡፡

የተማሪ ሁኔታ ተስፋ ያስቆረጠው መምህር ቁጥር ጥቂት አይባልም፡፡ ከናካቴው ማስተማሩን ለመተው ያኮበኮበው መምህር በቋፍ ያለ መሆኑን ማስረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ “ዝናቡ የትጋ ስንደርስ ነው የመታን?” ብለን እንደ ቹኒአቸቤ የምንጠይቅበት ሰዓት ነው፡፡ ትምህርት አስቀያሚ የሆነው ከመቼ ጀምሮ ነው? በምን ምክንያት? የትውልድ መሰረት የሆነው ትምህርት ቅጥ ካጣ ነገ ምን መሳይ ሊሆን ነው? ብዛት ነው ጥራት የሚያዋጣን? (Academic excellence or mass production? እንዲል ፈረንጅ፡፡

በጌቶች የሚሠራ ወጥ ወይስ ለብዙሃኑ ታዳሚ የሚሰራ የድግስ ወጥ ነው የሚያዋጣን? እንደማለት ነው፡፡ ተምረን ምን ልንሆን ነው? የኮብል - ስቶን ትውልድ እያልን የምንሳለቀው እስከመቼ ነው? ተማሪና አስተማሪ አንድ ገበያ እየዋለ ምን አይነት ሥነምግባራዊ ግንኙነት ሊኖር ነው? የተማሪ አስተማሪ ግምገማ በት/ቤት አዋጣን ወይስ አላዋጣንም? ይሄ ሁሉ ሆኖ ዛሬ የት ደርሰናል? ሃይማኖትና ትምህርት ለየቅል አይደሉም ወይ? በቅን ልቦና ያልተወያየንባቸው ጥያቄዎች አቤት ብዛታቸው? ያም ሆኖ አሁንም አልመሸም፡፡ ብንወያይበትና እውነቱን ፍርጥ ብናደርገው ይበጀናል፡፡ ጥናት ቢቀርብበት ፍሬ እናገኝበታለን፡፡ አለበለዚያ ሥጋቱና ዋስትና ማጣቱ ይገድለናል! “ሰዎች ሁሉ ስጋትና ዋስትና - ማጣት አላቸው፡፡ በዚህ ዋስትና - ማጣታቸው ላይ ከተጫወትክ ታሸንፋለህ፡፡ ሆኖም ሥልጣንን በተመለከተ ሁሉም ነገር የደረጃ ጉዳይ ነው፡፡

በጣም ትልቅ ሥልጣን ያለው ሰዉ የበለጠ ዋስትና - ማጣት የሚሰማውና የባሰበት ሥጉ ሰው ነው፡፡ ስለዚህም ሌሎችን የሚያጠቃውና አደገኛ የሚሆንባቸው በበለጠና በከፋ ደረጃ ነው፡፡ ስለዚህ ከእንዲህ ያለው ሰው ጋር ስትጫወት ስስ ብልት አይተህ ሊሆን ይገባዋል፡፡ ጥቂት ጥቃት እጅግ በጣም ይሰማዋል! ይህንን አትርሳ” ይለናል ሮበርት ግሪን፡፡ አሞራ፤ ቁራ መጮህ እንደሚቀናው አውቋልና እሱን እያስጮኸ ሙዳውን ይወስዳል፡፡ “የኛ ተግባር መማር መማር መማር!” የሚለውን አሮጌ መፈክር ባንዘነጋው መልካም ነው፡፡ከት/ቤትም መማር፣ ከኑሮም መማር ይጠብቅብናል፡፡ በመምረጥና በማጽደቅ መካከል ልዩነት መኖሩን እንማር፡፡ የኳስ ቲፎዞ በመሆንና የፖለቲካ ቲፎዞ መሆን መካከል ልዩነት መኖሩን እንማር፡፡ “ትላንትማ ቤትህ ደጃፍ ላይ እንቅፋት የመታህ ድንጋይ ዛሬም ከመታህ ድንጋዩ አንተ ነህ፤ የሚለውን የቻይኖች አባባል አንዘንጋ፡፡

በሀገራችን ብዙ ነገሮችን ለመተግበር ከጥናትና እቅድ ይልቅ በዘመቻ ማመናችን የቆየ ባህል ነው፡፡ የዘመቻ ሥራ ደግሞ ያንድ ሰሞን ሆይሆይታ ነው፡፡ ዘራፍ ይበዛዋል፡፡ ስለሆነም “የእነ ቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንበሌጥ መሆኑ አይታበሌ ነው! ለሚዲያ ፍጆታ፣ አሊያም ለውጪ መንግሥታት ተቋማት ጆሮ-ገብነት ብለን በአንድ ወቅት እንደቁራ የምንጮኸውን ጩኸት፣ ነገ ደግመን የማንሰማው ከሆነ፤ የጊዜ፤ የሰው ኃይልና የአቅም ብክነት ብቻ ነው የሚሆነው፡፡ የምንጮኸውን ከልባችን እንጩህ! የምንሰራውን ከልባችን እንሥራ! ይሄን አቀድኩ ይሄን እስካሁን ፈፀምኩ ለማለት ብቻ የምንጣደፍበት ደርዝ-አልባ ጉዞ ከንቱ ነው፡፡ “በችኮላ ቅቤ ያንቃል፤ ቀስ በቀስ ድንጋይ ይዋጣል” የምንለው ያለነገር አይደለም፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የስድስተኛው ፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ÷ ካህናት እና ምእመናን ስድስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባት ሊኾን ይገባል የሚሉትን ዕጩ በመጠቆም እንዲሳተፉ ጠየቀ፡፡ አስመራጭ ኮሚቴው፣ ስለ ስድስተኛው ፓትርያሪክ የምርጫ ሂደትና የተመረጡት ፓትርያሪክ ስለሚሾሙበት ቀን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ካህናትና ምእመናን ግልጽ ለማድረግ ከትላንት በስቲያ በጽ/ቤቱ በሰጠው መግለጫ ባስተላለፈው ጥሪ÷ በሀገር ውስጥ ያሉ ካህናት÷ አገልጋዮች መኾናቸውን፣ ምእመናንና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ደግሞ የአጥቢያው ቤተ ክርስቲያን አባላት መኾናቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ በመያዝ በአስመራጭ ኮሚቴው ጽ/ቤት በአካል በመቅረብ፣ ከሀገር ውጭ የሚገኙትም በፋክስ ቁጥር 011 - 1567711 እና 011-1580540 ከየካቲት 1 - 8 ቀን 2005 ዓ.ም ድረስ ዕጩአቸውን እንዲጠቁሙ ጠይቋል፡፡

አራት ሊቃነ ጳጳሳትን፣ ሁለት የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎችን፣ ሁለት የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎችን፣ አንድ የሰንበት ት/ቤት፣ አንድ የማኅበረ ቅዱሳንና ሦስት የምእመናን ተወካዮችን በአጠቃላይ 13 አስፈጻሚዎችን በአባልነት በያዘውና ታኅሣሥ 10 ቀን 2005 ዓ.ም በቅ/ሲኖዶስ በተቋቋመው አስመራጭ ኮሚቴ ወጥቶ በቋሚ ቅ/ሲኖዶሱ መጽደቁ በተገለጸው መሪ ዕቅድ እንደሚያመለክተው÷ የስድስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ ሂደት የሚጀምረው ለአንድ ሱባኤ/ሳምንት በሚቆይ የጸሎት ጊዜ ነው፡፡ ከትላንት የካቲት 1 ቀን እስከ የካቲት 8 ቀን 2005 ዓ.ም በሚዘልቀው በዚህ የጸሎት ሱባኤ÷ ቤተ ክርስቲያኒቱ ቅን/ርቱዕ መሪ እንድታገኝ፣ እግዚአብሔር የወደደውንና የፈቀደውን በመንበሩ ያስቀምጥ ዘንድ ካህናቷና ምእመናንዋ አምላካቸውን በጸሎት እንዲማፀኑ በዐዋጅ ታዝዘዋል፡፡በምርጫው ለመሳተፍ የሚችሉት መራጮች÷ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች፣ የጥንታውያን ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ካህናት፣ ምእመናን፣ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች እና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ናቸው፡፡

ታኅሣሥ 8 ቀን 2005 ዓ.ም ቅ/ሲኖዶሱ ባጸደቀው የፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንብ አንቀጽ 7 ንኡስ አንቀጽ 1 - 7 ላይ በተዘረዘረው የመራጮች ማንነት÷ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በሙሉ፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ም/ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያና የድርጅት ሓላፊዎች፣ የየሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች፣ በሀገር ውስጥና በውጭ አገር የሚገኙ ገዳማት አበምኔቶች፣ እመምኔቶች እና የታላላቅ አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ከየሀገረ ስብከቱ ሰበካ ጉባኤያት የተወከሉ አራት የካህናት፣ አራት የምእመናንና አራት የሰንበት ት/ቤት ተወካዮች ጠቅላላ ብዛታቸው ከእያንዳንዱ ሀገረ ስብከት 12 ሰዎች፣ የመንፈሳዊ ኮሌጆች መምህራንና ተማሪዎች ተወካዮች ከየኮሌጆቹ ሁለት ሁለት ሰው፣ ቤተ ክርስቲያን ሕጋዊ ዕውቅና የሰጠቻቸውና ከቤተ ክርስቲያኗ ጋራ አብረው በመሥራት ላይ የሚገኙ ማኅበራት ተወካዮች ከየማኅበራቱ አንድ አንድ ሰው እንደኾኑ ተደንግጓል፡፡

በዚህ ድንጋጌ መሠረት በስድስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ የሚሳተፉ መራጮች አጠቃላይ ቁጥር 800 ሲሆን ይህም ባለፉት አምስት ፓትርያሪኮች ከተሳተፉት መራጮች ብዛት ጋራ ሲነጻጸር ‹‹በእጅጉ የላቀ ነው›› ተብሏል፡፡ በሀገር ውስጥ በሚገኙት የ53ቱ አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት ሰብሳቢነት በሚመራ የአስተዳደር ጉባኤ ውሳኔ የሚለዩት መራጮች ዝርዝር እስከ የካቲት 16 ቀን ለአስመራጭ ኮሚቴው እንዲላክ፣ መራጮቹም እስከ የካቲት 19 ቀን 2005 ዓ.ም አዲስ አበባ እንዲገቡ መታዘዙን የኮሚቴው መግለጫ ጠቅሷል፡፡

በፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንቡ እንደተደነገገው፣ ምርጫው ታዛቢዎች ይኖሩታል፡፡ እኒህም÷ ከአራቱ አኀት አብያተ ክርስቲያናት (ግብጽ፣ አርመን፣ ሕንድ እና ሶርያ) ከእያንዳንዳቸው አንድ አንድ ሰው፣ ከዓለም አብያተ ክርስቲያናት ማኅበር አንድ፣ ከአፍሪቃ አብያተ ክርስቲያናት ም/ቤት አንድ፣ በቋሚ ቅ/ሲኖዶስ ከቤተ ክርስቲያኗ ምእመናን የሚመረጡ ታዋቂ የአገር ሽማግሌዎች ሦስት፣ በመንግሥት የሚወከሉ ሦስት ሰዎች እንደኾኑ ተገልጧል፡፡አስመራጭ ኮሚቴው እስከ የካቲት 16 ቀን 2005 ዓ.ም በፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንብ የዕጩዎች መመዘኛ መሠረት አጣርቶ ለምርጫ የሚያቀርባቸውን ዕጩ ፓትርያሪኮች ማሳወቅ ይጠበቅበታል፤ ለምርጫ የሚቀርቡት ዕጩዎች ብዛትም አምስት ነው፡፡

ለዕጩ ፓትርያሪክነት የሚጠቆመው ሊቀ ጳጳስ፣ ጳጳስ ወይም ኤጶስ ቆጶስ÷ ዜግነቱ ኢትዮጵያዊ የኾነ፣ የውጭ አገር ዜግነት ካለውም የውጭ ዜግነቱን ሰርዞ ወደ ኢትዮጵያዊነቱ የተመለሰ፣ ዕድሜው ከ50 ዓመት ያላነሰ ከ70 ዓመት ያልበለጠ፣ ከቤተ ክርስቲያኒቱ የአብነት ትምህርቶች ቢያንስ በአንድ ጉባኤ የተመረቀ ቢቻል ሁለገብ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ያለው ኾኖ ከከፍተኛ የመንፈሳዊ ትምህርት ተቋማት ወይም በዘመናዊ ትምህርት ቢያንስ ዲፕሎማ ወይም ዲግሪ ያለው፣ ሙሉ አካል ያለውና ጤንነቱ የተሟላ፣ የቤተ ክርስቲያኗ ቋንቋ የኾነውን ግእዝን የሚያውቅ ኾኖ ቢቻል ከዓለም አቀፍ ቋንቋዎች አንዱን የሚያውቅ፣ በቅድስና ሕይወቱና በግብረ ገብነቱ የተመሰገነ፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በመፈጸም በቂ የአስተዳደር ችሎታና ልምድ ያለው መኾን እንደሚገባው በፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንቡ ላይ በሰፈረው መመዘኛ ተደንግጓል፡፡ ከአምስቱ ዕጩዎች መካከል ለዕጩ ፓትርያሪክነት ይኹንታ የሚሰጣቸውን አባቶች ለመወሰን የመጨረሻ ሥልጣን ያለው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ነው፡፡ ምልአተ ጉባኤው ከየካቲት 16 ቀን ጀምሮ ተሰብስቦ ከተወያየ በኋላ የካቲት 19 ቀን 2005 ዓ.ም አምስቱን ዕጩ ፓትርያሪኮች ለሕዝቡ ይፋ እንደሚያደርግ በኮሚቴው መግለጫ ላይ ተጠቅሷል፡፡

የ፮ኛው ፓትርያሪክ ምርጫ የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም እንደሚከናወን፣ ለፓትርያሪክነት የተመረጠው አባት በዓለ ሢመት ደግሞ የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም እንደሚፈጸም ኮሚቴው ያስታወቀ ሲኾን ምርጫው ኀሙስ፣ የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም ተካሂዶ በዚሁ ዕለት ከምሽቱ 12፡00 ላይ የተመረጠው አባት በብዙኀን መገናኛ አማካይነት ለሕዝብ ይፋ እንደሚኾን ገልጧል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በራሷ ሲኖዶስ መመራት ከጀመረችበት ከ1951 ዓ.ም ወዲህ ስድስተኛ ፓትርያሪክ በመኾን ለመንበረ ተክለ ሃይማኖት የሚመረጠው አባት ሹመት (በዓለ ሢመት) የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም ኮሚቴው አስታውቋል፡፡ በዓለ ሢመተ ፕትርክናውም የሚከናወነው ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የልዩ ልዩ አብያተ ክርስቲያን መሪዎች፣ የሃይማኖት ተቋማት ተወካዮች፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ካህናትና ምእመናን በተገኙበት እንደሚኾን በመግለጫው ላይ ተመልክቷል፡፡

አንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ (አንድነት) በማተሚያ ቤት ዕጦት ምክንያት ለተቋረጠው የፓርቲው ልሳን ዘላቂ መፍትሄ ለመስጠት የተለያዩ የገቢ ማስገኛ ዝግጅቶች እና እርዳታዎችን አሰባስቦ የማተሚያ ማሽን ለመግዛት ማቀዱን አስታወቀ፡፡ ፓርቲው በትናንትናው ዕለት በጠራው ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳስታወቀው፤ ለአንድ ዓመት ከሁለት ወር ያህል የመንግሥት በሆነው ብርሀንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት እየታተመ በየሣምንቱ ማክሰኞ ለገበያ ይቀርብ የነበረውን “ፍኖተ ነፃነት” የተባለ የፓርቲው ጋዜጣ ወደ አንባቢው ለመመለስ በውጭ እና በአገር ውስጥ ከሚገኙ ደጋፊዎቹ በአራት ወር ጊዜ ውስጥ ገንዘብ በማሰባሰብ አንድ ሚሊዮን ብር የሚያወጣ የማተሚያ ማሽን ለመግዛት አቅዷል፡፡

በዕለቱ የፓርቲው ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ እንደተናገሩት፤ በሕጋዊ መንገድ የተቋቋመ ማንኛውም ፓርቲ የራሱን ልሣን የማሳተም መብት እንዳለው ሕጉ ቢደነግግም፤ መንግሥት ማተሚያ ቤቶች ላይ በሚያደርገው የተለያዩ ጫናዎች ምክንያት በተፈጠረ ፍርሀት ጋዜጣ ብቻ ሳይሆን ደረሰኝ ማሳተም እንደተቸገሩ ተናግረዋል፡፡

በማተሚያ ቤት ዕጦትም ለአባላቱና ለኅብረተሰቡ መረጃ በመስጠት የሚገለገሉበትን ጋዜጣ ማተም እንደተቸገሩ ገልጸዋል፡፡ በማተሚያ ቤት ምክንያት ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ላይ የተጣለውን እገዳ ለመታገል የማተሚያ ማሽኑን መግዛት እና የሕትመት ውጤቱን ማስቀጠል አስፈላጊ መሆኑን የተናገሩት ዶ/ር ነጋሶ፤ ከአስፈላጊነቱ ዓላማ በመነሳት የተለያዩ ጥናቶችን ሲያካሂዱ ቆይተው ማሽኑ ከአጋዥ መሣሪያዎቹ ጋር አንድ ሚሊዮን ብር እንደሚያወጣ እንደተረዱ ገልጸዋል፡፡

ማሽኑን ለመግዛት ከአቅራቢ ድርጅቶች ጋር መነጋገር መጀመራቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህንን የፓርቲውን ዓላማ እና ፍላጎት ለማሳካት የሚደረገውን የገቢ ማሰባሰብ ፕሮጀክት ለማከናወን ሦስት ኮሚቴዎች መቋቋማቸውን የገለፀው ‹‹የፍኖተ ነፃነት›› ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ነብዩ ኃይሉ ስለ ገቢ ማሰባሰቢያ እቅዱ እንዳብራሩት፤ መጽሐፍትን በመሸጥ፣ ከ30 ብር እስከ 1ሺሕ ብር ለሚለግሱ ኩፖን፣ ከተጠቀሰው ገንዘብ በላይ መለገስ ለሚፈልጉ የቃል ኪዳን ሰነድ መዘጋጀቱን እና ዓላማውን የሚደግፍ ማንኛውም ሰው በባንክ ሂሳብ ቁጥራቸው ገቢ ማድረግ እንደሚችል ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም በኢንተርኔት ኦን ላይን ከዛሬ ጀምሮ እስከ ሚቀጥሉት አራት ወራት የገቢ ማሰባሰቡን ሥራ እንደሚቀጥሉ ጠቁሟል፡፡

ዶ/ር ነጋሶ በበኩላቸው፤ “ፍኖተ-ነፃነት” ለአባላቱና ለህብረተሰቡ ብቻ ሳይሆን ኢህአዴግም ቢሆን ሃሳቡን ማስተላለፍ ከፈለገ ሊገለገልበት እንደሚችል ተናግረዋል፡፡ ፓርቲዎች በማተም ሥራ ላይ ሲሠማሩ ቀረጥ መክፈል እንደሌለባቸውም በህጉ ማስቀመጡን ገልፀው፤ ማሽኑ የሌላ ሰው የህትመት ሥራ እንደማይሠራና “ከፍኖተ-ነፃነት” በተጨማሪም በኦሮምኛና በሌሎች የአገሪቱ ቋንቋዎች የሚሠራጩ የራሱን ኒውስሌተሮች የመስራት ሃሳብ እንዳለው ዶ/ሩ ገልፀዋል፡፡ የገቢ ማሰባሰቡ ከዛሬ ጀምሮ ለቀጣዮቹ አራት ወራት እንደሚቀጥልም ለማወቅ ተችሏል፡፡

በተያያዘ ዜና የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊና የቋንቋ ምሑር ዶ/ር ኃይሉ አርአያ “ቋንቋና የቋንቋ ፖሊሲ” በሚል ርእስ ነገ ረፋድ ላይ በአንድነት ጽ/ቤት ጥናት እንደሚያቀርቡና ውይይት እንደሚካሄድ የተገለፀ ሲሆን ህብረተሰቡ በውይይቱ ተካፋይ እንዲሆን ግብዣ ቀርቧል፡፡

“... እንግዲህ የእናቶች ጤና ሲባል በቅድሚያ እናቶችን ለጉዳት የሚዳርጋቸው የእናቶቹ ወደ ሆስፒታል ያለመምጣት ችግር ነው፡፡ ይህ ምክንያቱ የተለያየ ሲሆን አሁን አሁን ግን መንግስት የጤና ኤክስንሽን ሰራተኞችን ለህብረተሰቡ ቅርብ በሆነ ሁኔታ እያሰማራ እና እናቶቹም ስለጤናቸው እንዲማሩ እየተደረገ ስለሆነ የተሻለ ነገር አለ ማለት ይቻላል፡፡ ነገር ግን አሁንም ብዙ መስተካከል የሚገባቸው ነገሮች እንዳሉ አይካድም፡፡ እናቶች ለህክምና ወደሆስፒታል ሲመጡም አገልግሎት የሚሰጥባቸው መሳሪያዎች በበቂ ሁኔታ መገኘት ይገባቸዋል፡፡ የህክምናው ባለሙያ ክህሎትና የመሳሰሉት ሁሉ የእናቶችን ጤንነት ለመጠበቅ አንዱም ሳይዛባ በተሟላ መንገድ መገኘት ይገባቸዋል፡፡ ... የጤና ባለሙያው በቂ የሆነ ችሎታ ኖሮት በበቂ መሳሪያ እየታገዘ ህክምናውን እንዲሰጥ ሁኔታዎች መሟላት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህ ካልሆነ የእናቶች ወደሆስፒታል መምጣት አለመምጣት ምንም ልዩነት የለውም፡፡ ምናልባት ልዩነት ሊባል የሚችለው ወደሐኪም ሳይሄዱ ከእቤት መሞት ወይንም ሐኪም ቤት ሄዶ መሞት በሚል ሊገለጽ የሚችል ብቻ ነው...” ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ /የጽንስና ማህጸን ሕምና እስፔሻሊስት የእናቶችና ሕጻናትን ሞት በመቀነስ ረገድ የደብረማርቆስ ሆስፒታል ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር እየሰራ መሆኑን ዶ/ር አብነት ሲሳይ በደብረማርቆስ ሆስፒታል የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ገለጹ፡፡

እንደ ዶ/ር አብነት ገለጻ የደብረማርቆስ ሆስፒታል ከኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ጋር ከሚሰራው ስራ በተጨማሪ አይክ ኢትዮጵያ ከሚባል ግብረሰናይ ድርጅት ጋር በመተባበር የእናቶችን እና ሕጻናትን ጤንነት በሚመለከት ለሚሰራው ስራ ከተመረጡ ሁለት ሆስፒታሎች አንዱ ሆኖአል፡፡ ደብረማርቆስ ከአማራ ክልል ከትግራይ ደግሞ አድዋ ሆስፒታል ተመርጠው ከተወሰኑ ወራት ወዲህ ስራ የጀመሩ ሲሆን ከሕብረተሰቡ ጋር በተቀናጀ ሁኔታ መስራት አስፈላጊ በመሆኑ ንቃተ ህሊናን የማዳበር ስራ ተሰርቶአል፡፡ በጤና ተቋም ወይንም ወደ ሆስፒታል በመቅረብ የሚወልዱ እናቶች ቁጥር 20ኀ የማይሞላ በመሆኑ ይበልጡኑ እናቶችን ለማዳን ወደ ህብረተሰቡ መውረድ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቶአል፡፡ ወደህብረተሰቡ ለመድረስ ደግሞ የጤና ኤክስንሽን ሰራተኞች ዋናዎቹ ድልድዮች በመሆናቸው በደብረማርቆስ ዙሪያ ያሉትን ሙያተኞች ጠርተን የፕሮግራሙን አላማ ከማስረዳት ጀምሮ የጤና ኤክስንሽን ሰራተኞቹ እናቶችን ከጤና ኬላ ወደ ጤና ጣብያ እንዲያስተላልፉ ከዚያም ከፍ ወዳለ ሆስፒታል የመቀባበልን ሁኔታ በተቀናጀና ስርአት ባለው መንገድ እንዲሰራ አስፈላጊ መሆኑን እንዲገነዘቡ በማድረግ ስራው ተጀምሮአል፡፡

እናቶች ብዙውን ጊዜ በእርግዝና ጊዜ ክትትል ሲያደርጉ ቢቆዩም ለመውለድ ወደሆስፒታል ወይንም ክትትል ሲያደርጉ ወደቆዩበት ጤና ተቋም የሚሄዱት በጣም ጥቂቶች የመሆናቸው ጉዳይ አሳሳቢ በመሆኑ ይህንን ሁኔታ መልኩን በመቀየር እናቶች በወሊድ ጊዜ ወደሆስፒታል ለመሄድ የሚያስችላቸውን ቅድመ ዝግጅት እንዲያደርጉ የሚያስችላቸውን ዘዴ መምከር ተገቢ ይሆናል፡፡ ይህንንም በተገቢው ለማስፈጸም እንዲያስችል ከኢሶግ እንዲሁም ከአይክ ጋር የሚሰራው ስራ የእርግዝና ክትትል ስታደርግ የቆየች እናት በመሀከል ብትሰወር ወደየት እንደደረሰች ፣ወልዳ ይሁን ወይንስ? በምን ምክንያት ? የሚለውን ለይቶ ማወቅና እናቶች ያሉበትን ሁኔታ በሚገባ ተረድተው ቅድመ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ለማስቻል የሚደረግ ክትትልን ይጨምራል፡፡ የደብረማርቆስ ሆስፒታል ከኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ጋር በመተባበር 5/ጤናጣቢያዎችን ባካተተ መልኩ የእናቶችንና የጨቅላዎችን ሞትና ደህንነት ሁኔታ በክትትል ይመዘግባል ፡፡ በዚህም መሰረት ከአንድ ወር በፊት ስለነበረው አሰራር በዶ/ር... ያለምወርቅ እንደቀረበው ሪፖርት ከሆነ በጤናጣቢያዎቹ ለሚኖረው አገልግሎት አንድ አምቡላንስ ተመድቦ አስፈላጊ በሆነበት ቦታና ሰአት እናቶችን ወደሆስፒታል ማመላለስ ተጀምሮአል፡፡ ሆስፒታሉ በየወሩ ከየጤናጣብያዎቹ ጋር በየወሩ በስብሰባ የሚገናኝ ሲሆን ችግሮችንም ከስር ከስሩ እየተከታተሉ መፍታት የሚያስችል አሰራር ተዘርግቶአል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ጤናጣብያዎቹ ለእናቶች ማበርከት ያለባቸውን አገልግሎት ጠንቅቀው እንዲያውቁና እንዲተገብሩ ለማስቻል ድጋፍ ይደረግላቸዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በየወሩ በሚኖረው ዳሰሳ የእናቶችን እና ጨቅላዎችን ሞት በተመለከተ በማዋለጃ አካባቢ ብቻ ሳይሆን በሆስፒታሉ በተለያዩ ክፍሎችም ያለው ሁኔታ በሪፖርት እንዲካተት ይደረጋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የእናቶችንና ጨቅላዎችን ሞት በመመዝገቡ ረገድ በሆስፒታሎችና በጤና ጣቢያዎች ያለውን ብቻም ሳይሆን እናቶች በቤታቸው እንዳሉ የተከሰተ ነገርም ካለ በቀበሌና በኤክስንሽን ሰራተኞች አማካኝነት እንዲመዘገብ የሚያስችል አሰራር ተዘርግቶአል፡፡ በደብረማርቆስ ሆስፒታል እንደውጭው አቆጣጠር በኦክቶበር ወር 150/አንድ መቶ ሀምሳ እናቶች የወለዱ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ ከጤና ጣብያዎች እስከ ሰማንያ ኪሎ ሜትር ከሚደርስ እርቀት በቅብብል የመጡና እራሳቸውም ወደ ሆስፒታሉ የመጡ ይገኙበታል፡፡ በአጠቃላይ ወደ 27 የሚሆኑ እናቶች ወደሞት አፋፍ ደርሰው የነበሩ ሲሆን ነገር ግን በሆስፒታሉ የተመዘገበ የእናቶች ሞት የለም፡፡ ለሞት አፋፍ እንዲደርሱ ከሚዳርጉዋቸው ምክንያቶችም አንዱ ደም መፍሰስ ሲሆን ሁለት እናቶች የማህጸን መተርተር የደረሰባቸው ናቸው፡፡ ሁለት እናቶች ደግሞ ከማህጸን ውጭ ያረገዙ ሲሆን ውርጃም የሚጠቀስ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ እናቶች ከወለዱ በሁዋላ የሚከሰት የደም መፍሰስ አብዛኛውን ለሞት አፋፍ የመድረስ ሁኔታ ማለትም 25 በመቶ የሚሆነውን ድርሻ ይይዛል፡፡ ከእርግዝና ጋር ተያይዞ የሚከሰት የደም ግፊትም ያጋጠመ ሲሆን አስፈላጊውን ሕክምና በማግኘታቸው ከሞት ተርፈዋል፡፡ ከዚህ ውጭ የትራንስፖርት፣ የምግብ እጥረት እና የቤተሰብ እቅድ ዘዴን ባለመጠቀም ምክንያት እና ብዙ የወለዱ እናቶችም ለከፋ አደጋ ተጋልጠው ተገኝተዋል፡፡ ወደ ሀያ የሚሆኑ እናቶች በልጅነታቸው ግርዘት የተፈጸመባቸው ሲሆን በጎጂ ልማዳዊ ድርጊት ምክንያት በምጥ ጊዜ ለሚከሰቱ ሕመሞች የተጋለጡም አሉ ፡፡

ለሞት አፋፍ የደረሱ እናቶች እድሜ ከ20-40 የሚደርሱ ሲሆኑ የልጅነት ጋብቻም ለችግር ከሚያጋልጡ መካከል ናቸው፡፡ ከላይ የተጠቀሱትን ችግሮች ለመቅረፍም ህብረተሰቡን በማስተማሩ ረገድ በአቅራቢያው ያሉት የጤና ባለሙያዎች የበኩላቸውን ድርሻ ተወጥተዋል፡፡ በደብረማርቆስ ሆስፒታል የእናቶችን እና የጨቅላ ሕጻናትን ሞት ምክንያት ለማወቅ በሚደረገው አሰራር ያጋጠሙ ችግሮችን በሚመለከት የሕመምተኞች የቅብብል ሁኔታ አንዱ ሲሆን ሌላው የኤሌክትሪክ መስመር አለመኖር ነው፡፡ በማዋለድ ረገድ አንዳንድ ተጨማሪ መሳሪያዎች እንደቫኪዩም የመሳሰሉ ማለት ነው እጥረቱ እንዳለ ተገንዝበናል፡፡ ነገር ግን መፍትሔውን በሚመለከት አንዳንድ ጤና ጣቢያዎች ያለባቸውን የቅጽ እጥረት እራሳቸው በመፍጠር ተገቢውን መረጃ አያይዞ ወደሆስፒታል የመላክ አሰራር ተጀምሮአል፡፡ የኤሌትሪክ አገልግሎትንም በሚመለከት ለአንዳንድ ጤና ጣቢያዎች በቻርጀር የሚሰራ መብራት ለመስጠት ሁኔታዎች ተመቻችተዋል፡፡ የህክምና መርጃ መሳሪያዎችም በተቻለ መጠን በጎደለበት ቦታ እንዲሰጥ ሆስፒታሉ የራሱን መፍትሔ ዘርግቶአል፡፡ በአጠቃላይም ከጤናጣቢያዎቹ ጋር በወር አንድ ጊዜ አጠቃላይ ስብሰባ የሚደረግ ሲሆን በሆስፒታሉ ከሰራው ጋር የሚገኛኙት የሚመለከታቸው ባለሙያዎች በሙሉ ወደጤናጣቢያዎች እየወረዱ የጎደለውን ነገር የማየት ስራ እንዲሰራ ከስምምነት ተደርሶአል፡፡ ከሆስፒታሉ ጋር በትብብር የሚሰሩ ሳላይት ጤና ጣቢያዎችን በምን መንገድ ማጠናከር እንደሚገባ እና ያለውን ክፍተት ማሟላት እንዲሁም ምላሾችን በተገቢው በመመርመር አስፈላጊውን ማድረግ በሆስፒታሉ የተዋቀረው ቡድን ስራ መሆኑ የታመነበት ስለሆነ የእናቶችንና ጨቅላዎችን ሞት ምክንያት ከማወቅ አንጻር የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ እሙን ነው እንደ ዶ/ር ያለምወርቅ፡፡

የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ከአለምአቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ጋር በመተባበር በሚያደርገው እገዛ በኢትዮጵያ ከ9/መንግስታዊ ሆስፒታሎችና 45/ ጤና ጣብያዎች ጋር በመተባበር የእናቶችን ሞት ሁኔታ ለማወቅ ለሚሰራው ስራ እንዲረዳ በየሆስፒታሎች መረጃ ለመሰብሰብ እንዲያስችል አንዳንድ ኮምፒዩተር ገዝቶ አከፋፍሎአል፡፡ ዶ/ር አብነት ሲሳይ ከደብረማርቆስ ሆስፒታል የኮምፒዩተሩን አገልግሎት ሲገልጹ ከአሁን ቀደም ባለው አሰራር የህመምተኞች ካርድ በአካል የሚቀመጥ ሲሆን ከቦታ ጥበት የተነሳ ከተወሰነ ጊዜ በሁዋላ እንዲቃጠል ይደረጋል፡፡ አሁን ግን ኮምፒዩተሩን በማግኘታችን ...ለምሳሌ የዛሬ ሶስት አመት አንዲት እናት ታክማ የነበረ እና ሐኪሙዋ በሌለበት እንደገና ለሕክምና ብትመለስ በኮምፒዩተር የተያዘ መረጃ ካለ በቀላሉ ችግርዋን ለመረዳት እና በወቅቱ ባለው ሐኪም ለመረዳት ትችላለች፡፡ ስለዚህ የህሙማኑን መረጃ በተሙዋላ መንገድ ለረጅም ጊዜ ለማስቀመጥ የሚረዳ በመሆኑ ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያውያን ስደተኞችና እግር ኳስ በደቡብ አፍሪካ
በደቡብ አፍሪካ በስደት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በርካታ ናቸው። የ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ድል እንዲቀናው ስታዲየም ገብተው ድጋፋቸውን በመስጠት ከፍተኛ እንቅስቃሴ አድርገዋል፡፡ ድጋፍ አሰጣጣቸውም ከጨዋታው ቀጥሎ የዓለም አቀፍ ብዙሃን መገናኛውን ቀልብ ከሳበ ጉዳይ አንዱ ሆኖ አልፏል፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጣ የስፖርት አምድ አዘጋጅ ግሩም ሰይፉ በደቡብ አፍሪካ ጨዋታዎቹ በተካሄዱበት ስታዲየም ተገኝቶ ከጥቂቶቹ ኢትዮጵያውያን ጋር እንዴት ደቡብ አፍሪካ እንደገቡ፣ ስለሚገኙበት ሁኔታ እና ስለሰጡት ድጋፍ ጠይቋቸው እንደሚከተለው መልሰዋል፡፡
“ኤርትራዊ ብሆንም ዋልያዎቹን ደግፌአለሁ”
ሰናይ ነጋ

የተወለድኩት በደሌ የሚባል ስፍራ ኢሊባቡር ውስጥ ነው፡፡ከልጅነቴ ጀምሮ ኳስ ስለምወድ እጫወትም ነበር፡፡የአንደኛ ደረጃ ትምህርቴን እዚያው ኢሊባቡር ውስጥ ተማርኩ፡፡ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን ደግሞ በአየር ጤና እና በቦሌ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተከታትያለሁ፡፡በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል በተነሳው ግጭት ኤርትራዊ በመሆኔ ከቤተሰብ ጋር ወደ ኤርትራ ሄድኩ፡፡ኤርትራ የገባሁት የ23 ዓመት ወጣት ሆኜ ነበር፡፡ በኤርትራ ለ11 ዓመታት በውትድርና ቆየሁ፡፡
የውትድርና ህይወት ሲያማርረኝ በሽሬ በኩል አቋርጬ ወደ ኢትዮጵያ ተመለስኩ፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ እህቴ ስለነበረች እርሷ ጋር ለ15 ቀናት ቆየሁ፡፡
ከዚያ በኋላ በሞያሌ አድርጌ ናይሮቢ ገባሁ፡፡ከሁለት ዓመት የናይሮቢ ቆይታ በኋላ በአውሮፕላን ደቡብ አፍሪካ ገብቼ እዚህ ከነበሩ ቤተሰቦቼ እና ጓደኞቼ ጋር ተቀላቀልኩ፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ በንግድ ሥራ ተሰማርቼ እየሠራሁ ነው፡፡ኳስ ጨዋታ ብዙም አልከታተልም ነበር፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ወደ ደቡብ አፍሪካ ሲመጣ ግን እዚህ ካሉ ኢትዮጵያውያን ጋር ስለምሠራ፣ የነበረው መንፈስ ግጥሚያቸውን እንዳይና ቡድኑን ለመደገፍ አነሳሳኝ፡፡ዜግነቴ ኤርትራዊ ቢሆንም የተወለድኩበት ያደግኩበት እና የተማርኩበት አገር ኢትዮጵያ ስለሆነች “ዋልያዎቹን” ደስ ብሎኝ ደግፌአለሁ፡፡

* “Conversation with God” የሚለው መፅሃፍ “እግዚአብሄር ፖለቲከኛ ነው” ይላል * ምርጫ ቦርድ “ሆደሰፊ” እየሆንኩ ነው ብሏል (እንመነው እንዴ?) ዛሬ ከናንተ ምን እንደምፈልግ ታውቃላችሁ? የኢህአዴግን “ትዕግስት” እና የምርጫ ቦርድን “ሆደሰፊነት” ብቻ! (ራሳቸው ሲናገሩ ሰምቼ እኮ ነው!) ሁለቱ አለን የምትሉ ከሆነ ግን በነፃነት ማውጋት፤ አዳዲስ ምስጢሮችን መለዋወጥ፤ ፖለቲከኞችን ማማት፤ ባለሥልጣናትን “መቦጨቅ” (ማስረጃ ባይኖረንም በመረጃ) እንችላለን፡፡ እንዳልኳችሁ እናንተ ብቻ ትዕግስቱና ሆደ ሰፊነቱ ይኑራችሁ፡፡ እኔ የምለው ግን--- ሰሞኑን ምርጫ ቦርድ “ሆደሰፊነቱን” በኢቴቪ ሲናገር ሰምታችኋል? (የአበሻ ይሉኝታ አያውቅም ልበል?) ከኢህአዴግ ጋር የፓርቲዎች ምክር ቤት አባል የሆኑ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የእጩዎች ማስመዝገቢያ ጊዜ እንዲራዘምላቸው ጠይቀው፤ በአስር ቀን አራዘምኩ ብሎ እኮ ነው “ሆደ ሰፊ ነኝ” ያለው (ሆደ ሰፊ አያውቅም ማለት ነው!) ባለፈው ሳምንት የኢህአዴግ ፅ/ቤት ሃላፊ የሆኑት አቶ ሬድዋን ሁሴን ከምርጫው ጋር በተገናኘ ስለተቃዋሚዎች ያሉትን ሰምታችኋል አይደል? (ኢህአዴግ ግን አሳዘነኝ!) በምርጫው ይሸነፋል ብዬ እንዳይመስላችሁ! (መታሰቡስ!) በነገራችሁ ላይ አንድ ፖለቲከኛ ወዳጅ አለኝ --- ሁሌ ምርጫ ሲቃረብ “አስማተኛ ፓርቲዎች ካልተፈጠሩ በስተቀር ኢህአዴግ በምርጫ አይሸነፍም!” ይለኛል (የሚያውቀው ነገር ቢኖር ነው) አስማቱን ትተን ወደ ነባራዊው እውነታ ስንመጣ --- አቶ ሬድዋን ምን ነበር ያሉት? “የተቃዋሚዎች በምርጫው መሳተፍና አለመሳተፍ ትርፍም ኪሳራም የለውም” በዚህ አነጋገራቸው የበሸቀ ሌላ ወዳጄ “የሳቸውም ንግግር ያው ነው!” አለኝ - በንዴት ጨሶ (ትርፍም ኪሳራም የለውም ማለቱ እኮ ነው!) አንድ ታዋቂ የአገር ውስጥ የፖለቲካ ተንታኝ በሰጡት አስተያየት ደግሞ “ንግግሩ ለሃያ አንድ ዓመት በሥልጣን ላይ ለቆየ ፓርቲ አይመጥንም” ብለዋል፡፡

ደግነቱ ይሄን አስተያየት በሰጡ ማግስት ነፃ የትምህርት እድል አግኝተው ወደ አሜሪካ መብረራቸውን ሰምቻለሁ (አሜሪካ የመሸጉ ፖለቲከኞቻችን ስንት ደረሱ ይሆን?) እኔ የምለው ግን--- ኢህአዴግ መቼ ይሆን ዲፕሎማት የሚዋጣለት? (ከዚህ በኋላማ ተስፋ የለውም-- አረጀ እኮ!) አሁን እንግዲህ ለየት ወዳለው የዛሬ አጀንዳችን ብወስዳችሁ ሳይሻል አይቀርም፡፡ ሰሞኑን እጄ ገብቶ ያነበብኩት መፅሃፍ በአንድ አሜሪካዊ ደራሲ የተፃፈ ነው፡፡ እሱ ግን እኔ አልፃፍኩትም ባይ ነው፡፡ (ከደሙ ንፁህ ነኝ ለማለት ይመስላል) እንዴት ሲባል----እግዚአብሄር የነገረኝን በወረቀት ላይ ከማስፈር ውጭ ሌላ ሚና የለኝም ይላል፡፡ ኒል ዶናልድ ዋልሽ የተባለው አሜሪካዊ ደራሲ ከእግዚአብሔር ጋር ያደረግሁት ንግግር ነው ያለው መፅሃፍ ባለ ሦስት ጥራዞች ሲሆን ርዕሱም Conversation with God ይላል፡፡ (ከእግዚአብሔር ጋር የተደረገ ወግ ወይም ጨዋታ ልትሉት ትችላላችሁ) ምልልሳቸውን ስታነቡት ግን ምኑም ጨዋታ አይመስልም፡፡ የጦፈ Hard talk ነው፡፡ በነገራችሁ ላይ ደራሲው ከእግዚአብሄር ጋር ንግግር የጀመረው ድንገት ነው - ሳያውቀው፡፡ በፈረንጆቹ 1993 የፋሲካ በዓል አካባቢ በህይወቴ አስደናቂ ክስተት ተከሰተ ይላል - ደራሲው፡፡ በወቅቱ በግል ህይወቱ፣ በሙያውና በሥነልቦናው ደስተኛ አልነበረም፡፡ ህይወቴ ሁሉ የከሸፈ ይመስለኝ ነበር (እንደኢትዮጵያ ታሪክ ይሆን?) የሚለው ደራሲው፣ የተሰማውን ስሜት በደብዳቤ ላይ እያሰፈረ የማስቀመጥ የዓመታት ልማድ እንደነበረው ገልጿል አንድ ቀን ግን (ሳይመረው አልቀረም ) የተለየ ደብዳቤ መፃፍ ጀመረ - በቀጥታ ለእግዚአብሄር፡፡ ደብዳቤው የቁጣ፣ የምሬት፣ የንዴት፣ የመወነባበድና የወቀሳ ነበር፡፡ ልክ የሚፅፈውን ሁሉ ፅፎ ሲጨርስ ነው ከእግዚአብሄር ጋር ግንኙነት የጀመረው - በመፅሃፉ መግቢያ ላይ እንደገለፀው፡፡ መጀመርያ ላይ መደነጋገጥና መደነጋገር እንደተፈጠረበት ደራሲው ባይካድም፣ በኋላ ግን እንደጓደኞች ያወሩ እንደነበር ይናገራል - ለአንድ ቀን ሳይሆን ለሶስት ዓመት፡፡ እውነት ለመናገር ወጋቸው ፈፅሞ እኮ የፈጣሪና የሰው አይመስልም፡፡

ሰውና ሰው የሚተጋተግ እንጂ ፡፡ የእግዚአብሔርም ምላሽ የማይታመን ነው፡፡ ተጠራጥሬው ነበር ይለናል - ደራሲው፡፡ ወዲያው ግን ራሱ እግዚአብሄር መሆኑን ተረድቼ ሶስት ዓመት አብረን ዘለቅን፡፡ እኔ እጠይቃለሁ፣ እሱ ይመልስልኛል፡፡ የውይይታቸውም ውጤት Conversation with God የሚለውን መፅሃፍ ወለደ፡፡ መፅሃፉ ታትሞ ለገበያ ሲቀርብም ተወዳጅ በመሆን እንደተቸበቸበ ይናገራል - ኒል ዶናልድ ዋልሽ፡፡ የኒውዮርክ ታይምስ Bestseller ነበር፡፡ በነገራችሁ ላይ እግዚአብሔር ከአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ጆርጅ ቡሽን፣ ቢል ክሊንተንና ጂሚ ካርተንን እንደሚያደንቃቸው ለደራሲው ነግሮታል - Conversation with God በተሰኘው መፅሃፍ፡፡ ያለምክንያት ግን አይደለም፡፡ ለአገራቸውና ለዓለም ባከናወኑት ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ሥራዎቻቸው እንደሆነ አስረድቶታል፡፡ እግዚአብሔር ሌላው የሚያደንቀው መሪ ማን መሰላችሁ? የሶቭየቱ ሚኻኤል ጐርባቾቭ! ለምን? ቀዝቃዛውን ጦርነት ማስቆም የቻሉና ብቸኛው ኮሙኒስት የሰላም የኖቤል ተሸላሚ ሲል አድንቋቸዋል - እግዚአብሔር በመፅሃፉ ላይ፡፡ ለነገሩ ትክክለኛው የዓለም ስርዓት ኮሙኒዝም ነው ብሏል ለደራሲው ሲያወጋው - ነገር ግን አተገባበር ላይ ችግር አለ ባይ ነው (የሰው ልጅና ኮሙኒዝም አልተግባቡም እንደማለት) የእግዚአብሄርን ኮሙኒስትነት አስረግጦ መናገር ባይቻል እንኳን ካፒታሊስት እንዳልሆነ በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል፡፡ እንዴት ቢሉ---- በውይይታቸው ላይ የዓለም ሃብት እኩል መከፋፈል አለበት የሚል ሃሳብ ይሰነዝራል - እግዚአብሄር፡፡ እንዳልኳችሁ በመፅሃፉ ውስጥ ደራሲውና እግዚአብሔር ያላነሱትና ያልተከራከሩበት ጉዳይ የለም፡፡ ስለ ትዳር፣ ፍቅር፣ ወላጅነት፣ ታክስ፣ ስለሰይጣንና ሲኦል (ሰይጣንና ሲኦል የሰው ልጅ ፈጠራዎች ናቸው ብሏል) ከሞት በኋላ ስላለው ህይወት፣ ወዘተ በዝርዝር ተወያይተዋል፡፡

የአሁኑ ዘመን ትውልድ ራሱ ከልጅነት ሳይወጣ ልጅ አሳዳጊ መሆኑን ይወቅስና፣ የሰው ልጅ 40 ዓመት ሳይሞላው በፊት ወላጅ መሆን አይገባውም በማለት ልጆችን ማሳደግ የሚገባቸው አያቶች እንደሆኑ ይጠቁማል፡፡ ዓለም ጦርነት የሌለባት ሰላማዊ ፕላኔት ትሆን ዘንድ ምን ይደረግ ለሚለውም ሰፊ መልስ ይሰጣል - እግዚአብሄር፡፡ እስቲ የደራሲውና የእግዚአብሄር ውይይት ምን እንደሚመስል ለማየት ትችሉ ዘንድ አለፍ አለፍ እያልኩ ላስነብባችሁ፡፡ ደራሲ -እባክህ --- አገራት ከአገራት ጋር ሰላም የሚያወርዱበትንና ጦርነት ከነአካቴው የሚገታበትን መንገድ ንገረኝ --- እግዚአብሔር - በአገራት መካከል ሁልጊዜም አለመስማማት መኖሩ አይቀርም፡፡ አለመስማማት ችግር የለውም፡፡ እያንዳንዱ አገር ልዩ መሆኑን የሚያሳይ ጤናማ ምልክት ነው፡፡ አለመስማማትን በኃይል መፍታት ግን ከፍተኛ ያለመብሰል ምልክት ነው፡፡ በዓለም ላይ የሃይል መፍትሄ የማይወገድበት ምክንያት የለም፣ አገራቱ ለማስወገድ ፈቃደኛ እስከሆኑ ድረስ ነው ታዲያ፡፡ አንዳንዶች በገፍ የሚሞቱት ሰዎችና የሚጠፋው ህይወት ይሄንን ፈቃደኝነት ለማምጣት በቂ ነው ብለው ሊያስቡ ይችላሉ፡፡ ኋላ ቀር ባህል ለሰፈነበት እንዳንተ ያለው አገር ግን ነገሩ እነሱ እንደሚያስቡት አይደለም፡፡ ሙግት ማሸነፍ እችላለሁ ብለህ እስካሰብክ ድረስ መሟገትህ አይቀርም፡፡ በጦርነት ማሸነፍ እችላለሁ ብለህ እስካሰብክ ድረስም ትዋጋለህ፡፡ ደራሲ - ለዚህ ታዲያ መፍትሄው ምንድነው? እግዚአብሔር - መፍትሄ የለኝም፡፡ ምልከታ እንጂ! --- የአጭር ጊዜ መፍትሄ የሚሆነው አንድ የዓለም መንግስት መመስረት ነው - አለመግባባቶችን የሚፈታ የዓለም ፍርድ ቤት ያለው! (አሁን እንዳለው ዓለማቀፍ ፍ/ቤት ውሳኔው ችላ የማይባል መሆን ግን አለበት) የትኛውም አገር የቱንም ያህል ጉልበት ቢኖረውና ተፅዕኖ ማሳረፍ ቢችልም ሌላው አገር ላይ ጥቃት እንዳይሰነዝር ዋስትና የሚሆን አንድ የዓለም ሰላም አስከባሪ ኃይል ሊመሰረት ይችላል፡፡

… በዚህ መንገድ ብቻ ነው በዓለም ላይ ሰላም ሊሰፍን የሚችለው፡፡ ያኔ --- የትናንሽ አገራት ዕጣ ፈንታ በትላልቅ አገራት መልካም ፈቃድ ላይ የተመረኮዘ መሆኑ ይቀራል፡፡ በራሳቸው ሃብት ላይ መደራደራቸው ያቆማል፡፡ ቁልፍ መሬታቸውን ለውጭ ወታደራዊ ሃይል (ቤዝ) አሳልፈው አይሰጡም፡፡ … አንድ አገር ብትወረር 160ዎቹም የዓለም አገራት በተቃውሞ ይነሳሉ፡፡ --- ትላልቅ አገራት የዓለምን የሃብት ክምችት ለብቻቸው መቆጣጠርና ማከማቸታቸውም ይቀራል፡፡ ይልቁንም ሃብቱን ለሌሎች አገራት እኩል እንዲያካፍሉ---ይገደዳሉ፡፡ የመላው ዓለም መንግስትም የጨዋታውን ሜዳ ለሁሉም እኩል ያደላድላል፡፡ (ደራሲውና እግዚአብሄር ስለዘመኑ የትምህርት ሥርዓትም የጦፈ ክርክር አድርገዋል፡፡ ቀንጨብ አድርጌ ላስነብባችሁ! ) ደራሲ - ስለትምህርት ልትነግርኝ ትፈቅዳለህ? እግዚአብሔር -- እንዴታ! አብዛኞቻችሁ የትምህርትን ትርጉም፣ ዓላማና ጥቅም በትክክል አልተረዳችሁትም፡፡ የትምህርት አሰጣጥ ሂደትንማ ባናነሳው ይሻላል፡፡ ---- አብዛኛው የሰው ዘር የትምህርት ትርጉምና ዓላማ እንዲሁም ጥቅም ዕውቀት ማስተላለፍ ነው ብሎ ደምድሟል፡፡ አንድን ሰው ማስተማር ማለት - የአንድን ቤተሰብ፣ ጐሳ፣ ህብረተሰብ፣ አገር፣ ዓለም የተከማቸ ዕውቀት መስጠት ሆኗል! ሆኖም ትምህርት ከዕውቀት ጋር እምብዛም የሚያገናኘው ነገር የለም፡፡ ደራሲ -ትምህርት ከዕውቀት ጋር ካልተገናኘ ከምን ጋር ነው የሚገናኘው ታዲያ? እግዚአብሔር - ከጥበብ፣ ከብልሃት ደራሲ-ልዩነታቸው ምንድነው? እግዚአብሔር- ጥበብ ወደ ኑሮ የተቀየረ እለት በእለት የተቀየረ ዕውቀት ነው፡፡ -- ለልጆቻችሁ ዕውቀት ስትሰጧቸው ምን ማሰብ እንዳለባቸው እየነገራችኋቸው ነው፡፡ ማወቅ ያለባቸውን ነው የምትነግሯቸው፤ እውነትን ነው እንዲረዱ የምትፈልጉት፡፡ ጥበብ ስትሰጧቸው ግን ማወቅ ያለባቸውን ወይም እውነቱን አይደለም የምትነግሯቸው፡፡ ይልቁንም የራሳቸውን እውነት እንዴት እንደሚያገኙ ታስተምሯቸዋላችሁ፡፡ ደራሲ -ግን እኮ ያለ ዕውቀት ጥበብ ሊኖር አይችልም፡፡ እግዚአብሔር - እስማማለሁ፡፡

ለዚህ እኮ ነው ጥበብ ሰጥታችሁ ዕውቀትን መዘንጋት የለባችሁም ያልኩት፡፡ የተወሰነ መጠን ዕውቀት ከአንደኛው ትውልድ ወደ ቀጣዩ መተላለፍ አለበት፡፡ በተቻለ መጠን ግን ትንሽ ቢሆን ይመረጣል፡፡ የቀረውን ህፃኑ ፈልጐ ያግኘው፡፡ ዕውቀት ይረሳል፤ ጥበብ ግን ፈፅሞ የሚረሳ አይደለም፡፡ ደራሲ - ስለዚህ ት/ቤቶቻችን ትንሽ ትንሽ ማስተማር ነው ያለባቸው ማለት ነው? እግዚአብሔር - ት/ቤቶቻችሁ አትኩሮታቸውን መለወጥ አለባቸው፡፡ አሁን በእጅጉ ያተኮሩት ዕውቀት ላይ ነው፡፡ ለጥበብ ትንሽ የተቆጠበች ትኩረት በመስጠት፡፡ በትንታኔያዊ አስተሳሰብ፣ በችግር መፍታትና በሎጂክ ዙርያ የሚሰጡ ትምህርቶች ለብዙ ወላጆች አስፈሪ ናቸው፡፡ እንዲህ ዓይነቶቹ ትምህርቶች ከካሪኩለሙ እንዲወጡ ይሻሉ፡፡ እንዲህ የሚያደርጉት የራሳቸውን የአኗኗር ዘይቤ ጠብቀው ለማቆየት ነው፡፡ እንዴት ቢሉ … የራሳቸውን ሳይንሳዊ የአስተሳሰብ ስልት እንዲያዳብሩ የተፈቀደላቸው ህፃናት የወላጆቻቸውን ሥነ ምግባርና አጠቃላይ የኑሮ ዘይቤ መከተል አይፈልጉም፡፡ የአኗኗር ዘይቤያችሁን ጠብቃችሁ ለማቆየት ስትሉ የትምህርት ስርዓታችሁ የህፃናትን ችሎታ ሳይሆን ትውስታቸውን ብቻ እንዲያዳብር አድርጋችሁ ነው የቀረፃችሁት፡፡ እንግዲህ የቀረውን መፅሃፉን ፈልጋችሁ አንብቡት፡፡ እኔ ግን አንድ ነገር በጣም ተመኘሁ--- እንደዚህ አሜሪካዊ ደራሲ ከእግዚአብሄር ጋር የመወያየት እድል ባገኝ አልኩ ለራሴ፡፡ ስለአገሬ ፖለቲከኞች ብዙ ብዙ የምጠይቀው ነገር ስላለኝ እኮ ነው፡፡ የዘመናት የፖለቲካ እንቆቅልሻችን እንዴት እንደሚፈታ ብልሃቱን ይሰጠኝ ዘንድም መወትወቴ አይቀርም ነበር፡፡ የእኛ የፖለቲካ ችግር ሰው ሰራሽ ቢሆንም መፍትሄው በሰው አቅምና ችሎታ የማይገኝ መሆኑን አይተነዋላ!

ሺጉሜን የተባለው የጃፓን ንጉሥ ቻ-ኖ-ዩ የተባለው የሻይ ስነስርዓት በጣም ደስ ይለው ነበር፡፡ በችሎቱ ላይ ዳኛ ሆኖ ሲቀመጥ እንኳ ሻዩን እያደቀቀ ይፈጭ ነበር ይባላል፡፡ ምክንያቱ የሚከተለው ነው፡- 

ከዕለታት አንድ ቀን የሻይ ነጋዴ የነበረ ወዳጁን
“ህዝቡ ስለ እኔ ምን ያስባል?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ነጋዴውም፤
“ማስረጃቸውን በግልፅ የማያቀርቡ ሰዎችን ትቆጣለህ፡፡ ሙልጭ አድርገህም ትሳደባለህ የሚል አስተያየት ነው ያለው፡፡ በዚህ ምክንያትም ህዝቡ እውነተኛውን ህጋዊ ማንነቱንና ጉዳዩን ወደ አንተ ለማቅረብ ስለሚፈራ እውነቱ በግልፅ አይታወቅም” ሲል ይነግረዋል፡፡
ንጉሡም፤
“አመሰግናለሁ! እንኳን ነገርከኝ፡፡ እኔ እስከዛሬ፤ ለሰዎች እቅጩን የመናገር ልማድ ነበረኝ፡፡ ስለዚህም ትሁቶቹና በድፍረት በአደባባይ የመናገር ድፈረት የሌላቸው ጨዋ ሰዎች እውነቱን ፍርጥ አድርገው አይገልፁም፡፡ ወደፊት ጠባዬን ማረም ይኖርብኛል” ይላል፡፡
ከዚህ በኋላ ንጉሡ ዙፋን ችሎት በሚቀመጥበት ጊዜ ሁሉ፤ አንድ የሚያስገርም ነገር ማድረግ ጀመረ ይባላል፡፡ በጨርቅ ተሸፍኖ የሻይ መውቀጫው/መፍጫው ከስሩ እንዲቀመጥለት ያዛል፡፡ በሀር ጨርቅ ተሸፍኖ ጥዋ መስሎ ይቀመጥለታል፡፡ ከዚያም አቤቱታ አቅራቢው ህዝብ አቤቱታውን ሲያሰማ እሱ ሻዩን እየወቀጠ ትኩረቱን ወደ ሙቀጫው በማድረግ ቁጣውን ይቆጣጠራል፡፡
ቀጥሎም የፈጨውን ሻይ በትክክል መድቀቅ አለመድቀቁን በእጁ እየነካ ያየዋል፡፡ ያረጋግጣል፡፡ ሻዩ በትክክል ከተፈጨ መንፈሱ የረጋና ሚዛናዊ መሆኑን ያስባል፡፡ በትክክልም አቤቱታ ማዳመጡን ያምናል፡፡ ሻዩ ያላግባብ የተወቀጠ ከሆነ ግን የተረበሸና ቁጠኛ ስሜት እንደነበረው ያውቃል፡፡
በረጋ መንፈስ የተፈጨው ሻይ፤ ፍርድ በትክክል መስጠቱንና አቤት ባዮቹም ረክተው መሄዳቸውን ይነግረዋል፡፡ ይሄኔ፤
“ተመስገን! ህዝቤ ሳያዝንብኝ፤ ረክቶና ደስ ብሎት ሄዷል ማለት ነው” ብሎ ፈገግ ይላል፡፡
* * *
ለህዝብ የሚቆረቆር ዕውነተኛ መሪ የህዝብን ብሶት ማዳመጥ፤ አቤቱታውን መስማት ያረካዋል። ህዝብ የልቡን ዕውነት የሚደብቅ ከሆነ ትክክለኛ አስተዳደር አለ ለማለት ያዳግታል፡፡ ዐይና - ውጣው በአደባባይ እንደልቡ ሲናገር፤ ጭምቱና ፈሪው ሃሳቡን ሳይገልጽ ይቀራልና ሥርዓቱ ሁሉንም ያስተናግዳል ለማለት አያስደፍርም፡፡ ሃሳቡን የሚገልጽ ህዝብ የዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ምሰሶ ነው። በዚህ ረገድ በጥሞና የህዝብን የልብ ትርታ ለማዳመጥ የሚችል ጆሮ ያለው መሪ ያስፈልጋል፡፡ የመሥሪያ ቤት አለቃ፣ የማህበር መሪም ሆነ የፖለቲካ መሪ አስተዋይ አዕምሮ፣ ሆደ - ሰፊ አመራርና “ወደፊት ይህን ይህን ጠባዬን ማረም ይኖርብኛል” የማለት ድፍረት ሊኖረው ያሻል፡፡ ያን ካገኘን ታድለናል፡፡
የአንድ ሀገር ህዝብ እንደዜጋ የተፃፈን ጽሑፍ በነፃነት፣ በጥሞናና በጥንቃቄ አንብቦ የሚመረምር፤ ያሻውን ዓይነት የፖለቲካ ሥርዓት የሚከተል፣ በነፃነት አገዛዙን የሚቃወም፣ የሚተችና ሲያስፈልግ አይሻኝም የማለት መብቱን የሚያውቅ ሊሆን ይገባል፡፡ እንደአራሽ እንደላብ - አደርም የአቅሙን ያህል ማምረትና የኢኮኖሚ ህልውናውን ሊያጠናክር ይጠበቅበታል፡፡ እንደዜጋም ሆነ እንደሠራተኛ በአገሩ ይኖር ዘንድ የሚያሠራው፣ የሚያሳትፈው ሥርዓትና ህግ ሊያገኝም የግድ ነው፡፡
“ባገር እኖር ብዬ
ልጅ አሳድግ ብዬ
ከብት እነዳ ብዬ፤
ለባሻ ዳርኩለት ሚስቴን እቴ ብዬ”
እያለ የሚያለቅስ ባላገር በምንም ዓይነት ማየት የለብንም፡፡ ጊዜውም ቦታውም አይፈቅድምም። በፖለቲካ የተገፋ፣ በኢኮኖሚ የደቀቀ፣ ማህበራዊ ድርና ማጉ ውሉ የጠፋ ህብረተሰብ እንዳይኖር ነው የስትራቴጂያችን ዒላማ! ውሃ ጋ ከሆን አሣ፣ ግጦሽጋ ከሆን ሥጋ መብላትን ልናውቅበት ወቅቱ ያስገድደናል፡፡
አንድ የገዛ በሬው ሊወጋው የሚያሳድደው ባለበሬ ለአንድ የሰፈር አዛውንት፤ “እረ ይሄ በሬ እያሳደደ አስቸገረኝ“ ቢላቸው፤ “የት ነው የምትተኛው?” ብለው ጠየቁት አሉ፡፡ ባለበሬውም፤ “ቤቴ። ሣር ፍራሼ ላይ!” ይላቸዋል፡፡ ሽማግሌውም፤
“ታዲያ ቀለቡ ላይ እየተኛህ ዱሮስ ላያባርርህ ኖሯል እንዴ?” አሉት ይባላል፡፡ ሰውንም ቀለቡ ላይ ተኝተን ነፃነት አለህ ብንለው የለበጣ ነው የሚሆነው፡፡ ነፃነቱን ከኢኮኖሚ ጥቅሙ የሚያስተሳስር ሥርዓት መፍጠር ተገቢ ነው፡፡ ለተገቢ ሥርዓት ክሳቴ የሚታገሉ ሁሉ ጊዜን መሠረት ያደረገ ስትራቴጂ ይኖራቸው ዘንድ ወቅቱ ይጠይቃቸዋል፡፡
“ፊት የበቀለን ወፍ ይበላዋል” የሚለውን ተረት ሳንረሳ “የዘገየ ፍርድ ካልተፈረደ አንድ ነው”ን እያውጠነጠንን፤ ትክክለኛው ጊዜ ሲደርስ ግን “የሚሥማሩን አናት መምታት”ና አጋጣሚን በአግባቡ መጠቀም ወሳኝ መሆኑን ልናሰምርበት ይገባል፡፡ በወቅቱ ያልዘራም በወቅቱ ያልሰበሰበም ሁለቱም ከመራብና ከማስራብ አይድኑም - “ንገሥ ቢሉት ዛሬ ሰምበት ነው አለ” የሚለው የጉራጊኛ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው!!

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በድጋሚ ተቀጠረ

በዓዲ ኀትመትና ማስታወቂያ ሓላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ስም እየታተመ የሚወጣው “አዲስ ታይምስ” መጽሔት፤ ከብሮድካስት ባለሥልጣን የሞያ ብቃት ማረጋገጫ ምስክር ወረቀት እድሳት በመከልከሉ ከኅትመት ውጪ ሆነ፡፡ አሳታሚው ለዝግጅት ክፍላችን እንደገለጸው፤ የአገሪቱ የፕሬስ ሕግ በሚያዘው መሠረት የመጽሔቱን ዓመታዊ ፈቃድ ለማሳደስ ከድርጅቱ የሚጠበቁትን መስፈርቶች ሙሉ በሙሉ ቢያሟላም የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን ጥር 2 ቀን 2005 በላከው ደብዳቤ ለመጽሔቱ የሞያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት እድሳት እንደማያደርግ አስታውቋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን እድሳቱን እንደማያደርግ ለአሣታሚው በላከው ደብዳቤ ያመለከተው ሦስት ዋና ዋና ምክንያቶችን በመጥቀስ ነው። እነዚህም የአክስዮን ባለቤቶችና የአድራሻ ለውጥ ሲደረግ በ15 ቀን ውስጥ ለባለሥልጣኑ ማሳወቅ አለመቻል፣ ለኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት መወዘክር የዐሥራ አምስት ቀን እትም አለማስገባት እንዲሁም መፅሔቱ “በሕጋዊ ባለቤቶቹ ሳይሆን ምንጩ በማይታወቅ ገንዘብ ነው የሚተዳደረው የሚሉት ናቸው፡፡ የ“አዲስ ታይምስ” መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ተመስገን በበኩላቸው፤ የአክስዮን ባለቤትነት እና የአድራሻ ለውጥ ሲያደርጉ በጊዜው በደብዳቤ ማሳወቃቸውን፣ በየዐሥራ አምስት ቀኑ ለኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ሁለት ሁለት ኮፒ ያስገቡበትን ደረሰኝ ለባለሥልጣኑ ማቅረባቸውን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ማንነቱ በማይታወቅ የገንዘብ ምንጭ ነው የሚንቀሳቀሰው›› የሚለውን የባለሥልጣኑን ምክንያት ደግሞ “በጥንቆላ ላይ የተመሠረተ መረጃ ነው” ሲሉ አጣጥለውታል፡፡ “ጉዳዩን ይዘን ወደ ፍርድ ቤት እናመራለን” ያሉት አቶ ተመስገን፤ የመጽሔቱ መታገድ ‹‹የአቶ ኀይለማርያም መንግሥት የመለስን ራዕይ እናስቀጥላለን ሲል የነበረውን በተግባር እያረጋገጠ መሆኑን ያመለክታል” ብለዋል፡፡ የአራት ወራት ዕድሜ ያስቆጠረው “አዲስ ታይምስ” መጽሔት ከ35 ሺሕ ኮፒ በላይ እየታተመ በየሁለት ሳምንቱ ይሠራጭ እንደነበር፣ ይህም በአገሪቱ ካሉ መጽሔቶች በኅትመት፣ ብዛትና በተደራሽነት ቀዳሚ እንደሚያደርገው አቶ ተመስገን ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡

በኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን የሕዝብ ግንኙነት ተጠባባቂ ሓላፊ የሆኑት አቶ ወርቅነህ ጣፋ በበኩላቸው፤ ባለሥልጣኑ የእድሳት ክልከላውን ከማድረጉ በፊት ከባለአክሲዮኖቹ ጋር የአድራሻ ቅየራ እና የአክሲዮን ድርሻ ለውጥ ሲደረግ አለማወቃቸው እንዲሁም በቤተ መጻሕፍት ወመዘክር የመጽሔቱ ቅጂዎች እየደረሱ እንዳልሆኑ ተወያይተንባቸው ችግሩ እንዳለ አምነው ተቀብለው ነበር ብለዋል፡፡ የመጽሔቱ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ተመስገን ደሳለኝ፤ የአክስዮኑ 93 በመቶ ድርሻ ባለቤት አገር ውስጥ እንዳልሆኑና ሰባት በመቶ ድርሻ ያላቸው ግለሰብ ብቻ አገር ውስጥ መኖራቸውን በመግለፅ አገር ውስጥ ያሉትን ብቻ አነጋግሮ እዚህ ድምዳሜ ላይ መድረስ እንደማይቻል ተናግረዋል፡፡ አቶ ወርቅነህ የፋይናንስ ምንጩን በተመለከተ ሲናገሩ፤ ‹‹አሁን በግልፅ ይፋ ባናደርግም መረጃው አለን” ብለዋል፡፡ ይህ በዚህ እንዳለ የሕዝብን ሐሳብ ማናወጥ፣ ሕዝቡን በሕገ - መንግሥቱ ላይ ማነሣሣትና የመንግሥትን ስም ማጥፋት የሚሉ ሦስት ክሦች የተመሰረተባቸውና ነሐሴ 17 ቀን 2004 ዓ.ም በቃሊቲ ማረሚያ ቤት ለስድስት ቀናት ከታሰረ በኋላ ክሱ ተቋርጦ በነጻ የተለቀቁት የቀድሞው የፍትሕ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ አቶ ተመስገን ደሳለኝ፤ ከሦስት ወር በኋላ ክሱ በዐቃቤ ሕግ ተንቀሳቅሶ በ50ሺሕ ብር ዋስ መለቀቃቸው ይታወሳል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት 16ኛ ወንጀል ችሎት ትእዛዝ ታኅሣሥ 27 ቀን 2005 ዓ.ም ቀርበው ተለዋጭ ቀጠሮ የተሰጣቸው የድርጅቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ማስተዋል ብርሃኑ እና የጋዜጣው ዋና አዘጋጅ አቶ ተመስገን ደሳለኝ ትላንት ጥር 23 ቀን 2005 ዓ.ም ቢቀርቡም “መዝገቡን አልመረመርነውም” በሚል ብይኑ ሳይሰማ የቀረ ሲሆን ችሎቱ ለየካቲት 1 ቀን 2005 ዓ.ም እንዲቀርቡ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡