Administrator

Administrator

Saturday, 23 March 2013 14:32

ኮፍያው

ነገሩ የተጀመረው በኮፍያ ነው - ለምሳ ቤት መጥቶ ሲወጣ፣ በሩ አካባቢ ባገኘው ኮፍያ - ጥልፍልፍ የቴኒስ መጫወቻ (የራኬት) ምስል በላዩ ላይ ያለበት ኮፍያ፡፡ ኮፍያውን አንስቶ መኪናው ውስጥ ከተተውና ወጣ፡፡ ወደ ቢሮው ከገባ በኋላ የኮፍያውን ነገር ሊረሳው አልቻለም፡፡ “የማን ኮፍያ ነው?” የሚል ጥያቄ በአእምሮው ውስጥ አንቃጨለ፡፡ “አንድ ወንድ ጥሎት የሄደው ነው” … የሚል ምላሽ ከአእምሮው ስርቻ መልሶ አስተጋባ፡፡ ሀሳቡን ለማባረር ራሱን በሥራ ለመጥመድ ሞከረና አቃተው፡፡ ሥራ መሥራት ሲያቅተው ወደ ሚስቱ ደወለ፡፡ ሚስቱ፣ ቤት ነው የምትውለው፡፡ ከተጋቡ ገና አራት ወራቸው ነው፡፡ ስሟ ሶፊ ቢሆንም “ምጥን!” ይላታል፤ ሲያቆላምጣት - በዚህ አጠራሩ እሷ ባትስማማም፡፡ ምጥን ያለች ናት፤ አይኗ የተመጠነ፣ እጆቿ የተመጠኑ ውበቷ የተመጠነ፡፡ ትርፍ የሚባል ነገር የላትም፡፡ ጥርሷ ያምራል ግን ትንሽ አፍንጫዋ … የሚሏት አይነት አይደለችም፡፡ ሁሉ ነገሯ ያምራል፡፡

ስልኩን አነሳች፡፡ ትንሽ አወሩ፡፡ “ዛሬ፣ ቤት ማን መጥቶ ነበር?” አላት ባለቤቷ አበራ - እንደዘበት፡፡ ለአፍታ ዝም አለች፡፡ “ዛሬ … ዛሬ … ማንም አልመጣም … እኔ ምልህ …” ብላ ወደ ሌላ ወሬ አመራች፡፡ “ኮፍያው የማን ነው?” ሊላት ፈለገ፤ ግን ቃላቱ ከአንደበቱ ሊወጡለት አልቻሉም፡፡ እየዋሸችኝ ነው? ለምን ትዋሸኛለች? ሰውነቱን አንዳች ነገር ሲወረው ተሰማው፡፡ ትንሽ አውርተው ስልኩ ተዘጋ፡፡ ቢሮው ውስጥ እንዳለ ፈዞ ቆመ፡፡ እሱና እሷ ብቻ በሚኖሩበት ቤት ውስጥ አንድ ኮፍያ እንዴት ሊገኝ ይችላል? ኮፍያ መቼም እግር የለው፣ የሰው ግቢ ውስጥ ዘሎ የሚገባው! የአንድ ሰው … የአንድ ወንድ ጭንቅላት ላይ ሆኖ መግባት አለበት ወደ ግቢው፡፡ ያንን ኮፍያ ያደረገው ጭንቅላት የማነው? የብዙ ሰዎች ምክር በአእምሮው መጣ፡፡

ለምን አታገባም? በልጅነትህ እናትህ አንተን እና አባትህ ጥላችሁ ስለሔደች ነው? እናትህ ምን አይነት ጨካኝ ብትሆን ነው በገዛ ጓደኛው አባትህን ከድታው የሄደችው? አባትህ ግን ምን አይነት ሞኝ ቢሆን ነው? እድሜ ዘመኑን ሲሰማው የነበረ ንግግር፣ ምክር እና ጥያቄ፡፡ በመጨረሻ ሶፊን ሲያገኝ የሴት ጥላቻው እንደጉም በኖ፣ ትዳር መያዙን የሰሙ ሁሉ ማመን አልቻሉም ነበር፡፡ “ምን አስነክታው ነው?!” ብለው ነበር ያዳነቁት፡፡ ከሶፊ ጋር በትዳር ሲኖሩ ለጥርጣሬ የሚያበቃ አንዳችም ድርጊት አይቶባት አያውቅም፡፡ ሁሌም ግን እንደሰለላት ነው፡፡ … ሁሌም አይኖቹ ለጥርጣሬ የሚሆን ነገር ለማግኘት በንቃት ይቃብዛሉ፡፡ ሶፊ ላይ ግን ምንም ነገር አግኝቶ አያውቅም - ኮፍያውን ግቢው ውስጥ ወድቆ እስኪያገኝ ድረስ፡፡ ኮፍያውን ካገኘ በኋላ ነው ስጋት እንደደራሽ ያዋከበው - የፈራው ደርሶ በነፍሰ ስጋው እየተጫወተች እንዳይሆን ሰጋ፡፡ ምን ነበር አባቱ የሚለው? “አጥንት ቢሰበር ወጌሻ ይጠግነዋል፡፡ የተሰበረን ልብ ግን ከሞት በቀር የሚያድነው የለም! በተለይ በሴት የተሰበረ ልብ …” ነበር የሚለው፡፡

ልቡ በሴት እንዳይሰበር ስንት አመት ነበር የተጠነቀቀው? እናቱ ከውሽማዋ ጋር ስትሔድ የአባቱ ብቻ ሳይሆን የእሱም ልብ ነበር የታመመው፡፡ ስቃዩን ያውቀዋል! እና ሶፊ … ከቢሮው ተስፈንጥሮ ወጣና ሲበር ወደ መኪናው ሔዶ ኮፍያውን አወጣው፡፡ የማን ኮፍያ ነው!? ወደ አፍንጫው አስጠጋው፡፡ የወዝ ሽታ አፍንጫውን ሰነፈጠው፡፡ አሽቀንጥሮ ከጋቢናው ወንበር ላይ ጣለው፡፡ “ጎረምሳ ይሆናል፣ ወይ ደግሞ መላጣ! መላጣ ነው በዚህ የሙቀት ወር ኮፍያ የሚያደርገው - መላጣውን ለመሸፈን፡፡ ለዚህ ነው የኮፍያው አስቀያሚ የወዝ ሽታ ያልጠፋው፡፡ ከኔ ግን በምን አባቱ በልጦባት ነው?”… የኮፍያውን ባለቤት አሰበው፡፡ መላጣ … ምናልባትም ቴኒስ ተጫዋች፡፡ “ወይኔ!” ብሎ የመኪናውን ኮፈን በቡጢ ነረተው፡፡

“ቀደም ብዬ ለምሳ ቤት በመሔዴ ደርሼባቸው ያ መላጣ ተደናግጦ ይሆናል ኮፍያውን ጥሎ የፈረጠጠው፡፡ ይኼ መላጣ!” አለ በንዴት፡፡ “ግን ለምን መላጣ መረጠች? ስንት ባለጎፈሬ ሞልቶላት! ምናልባትም እኮ መላጣነቱን ይሆናል የወደደችው!” በሆዱ ወፈ ሰማይ ጥያቄ ፈለፈለ፡፡ ለሶስት ቀን እያደባ፣ ሰአት እየቀያየረ ባለኮፍያውን በአሳቻ ሰአት ሊያጠምደው ሞከረ፤ አልቻለም! ሌሊት እየተነሳ ከቤቱ ጓሮ ዞሮ አካባቢውን መረመረ፡፡ መላጣው ሰውዬ አጥር እየዘለለ ሊሆን ይችላል የሚገባው፡፡ የአጥር ጥግ ሁሉ አሰሰ - አንድም ዱካ የለም፡፡ “መላጣ ሰው እንዴት እንደምጠላ!” … ሰው መሰላችሁ!?” ይል ጀመር ለጓደኞቹ፡፡ ጓደኞቹ የጋራ አለቃቸውን በሾርኒ እያማው ስለሚመስላቸው ይስቃሉ፡፡ አለቃቸው መላጣ ነው፡፡ “ከአስር መላጣ አንድ ሾጣጣ!” አለ አንድ ቀን አፉ እንዳመጣለት፡፡ መላጣና ሾጣጣ ምን እንደሚያገናኛቸው ጓደኞቹ አልጠየቁትም - ዝም ብለው ሳቁ የጋራ አለቃቸውን እያሰቡ፡፡

በነጋታው አለቃው ጉዳዩን ሰምቶ የፅሁፍ ማስጠንቀቂያ ሰጠው፡፡ መላጦችን የሚጠላበት አንድ ተጨማሪ ምክንያት አገኘ፡፡ ከሶስት ቀን በኋላ ሚስቱ በእንቅልፍ ልቧ ስትዘባርቅ ሊሰማት ወስኖ ለተከታታይ ሁለት ቀናት አጠገቧ ተገትሮ አደረ፡፡ በሁለተኛው ቀን አጠገቧ እንደቆመ ነቃች፡፡ “ምነው!” አለችው በእጁ የያዘውን አውራ ጣቷን እያየች፡፡ ደንግጦ ለቀቃት፡፡ “አውራ ጣቱን የተያዘ ሰው፣ ሲያዝ ቀን የሰራው ይዘከዝካል” ብለው ሰዎች እንደመከሩት አልነገራትም፡፡ ኮፍያውን ባገኘ በአምስተኛው ቀን፡ ከአምስት ቀን በኋላ ለምሳ መጥቶ ማዕድ ቀርቦ እየበሉ ሳለ ጥያቄ አነሳላት፡፡ “ስለ መላጣ ሰው ምን አስተያየት አለሽ?” አላት እንደዘበት፡፡ ጥያቄው ግራ ያጋባት ይመስል አይኗን እያስለመለመች አየችው፡፡ “ስለመላጣ ነው ስለሰላጣ?” … ጠየቀችው ለምሳ የቀረበውን ሰላጣ እያየች፡፡ “ስለ መ.ላ.ጣ?... ማለቴ እኔ አሁን መላጣ ሰዎችን እጠላለሁ…” አላት ሳቀች፡፡ “እኔ ደሞ መላጣ ሰው እወዳለሁ! አባቴ እኮ መላጣ ነበር፡፡ አንተም ቶሎ ብትመለጥ ደስ ይለኛል፡፡ የመላጣው ሰውዬ ባለቤት ብባል ደስ ይለኛል … ኸኸኸኸኸኸኸኸኸኸኸ” አስረዝማ ሳቀች ሶፊ፡፡ “እና አባትሽን እንዲያስታውስልሽ ነው መላጣ የጠበስሽው?” በሆዱ አጎረምርሞ ዝም አለ፡፡ ያ መላጣ እዚሁ ሰፈር ውስጥ ይሆናል እኮ የሚኖረው! ጎረቤቶቹን አሰባቸው፡፡ መላጣ ከመካከላቸው አለ እንዴ? ከቤታቸው ፊት ለፊት ያሉትን ሰውዬ አሰባቸው፡፡ እሳተ ጎመራ እንደቦደሰው ተራራ፣ መሀል አናታቸው ላይ ብቻ ነው ጸጉር የሌለው፡፡

እሳቸው ደሞ ኮፍያ አያደርጉም! ሌሎቹ ጎረቤቶቹ ደሞ አርቴፊሻል ፀጉር ካልተጠቀሙ በስተቀር ከመከም ጎፈሬ ናቸው፡፡ ቴኒስ የሚጫወት ከመካከላቸው አሰበ፤ ማንም ሊመጣለት አልቻለም፡፡ ጎረቤቶቹ ከሜዳ ቴኒስ ይልቅ ለፈረስ ጉግስ የቀረቡ ናቸው፡፡ ኮፍያውን ባገኘ በስድስተኛው ቀን፡ ፀጉር ቤት ሔዶ “አንድ ዘመድ ሞቶብኛል!” ብሎ ፀጉሩን ተላጨ፡፡ መላጣ ሆኖ የዛን ቀን ወደቤት ቢገባም ሚስቱ ሶፊ ግን የተለየ ስሜት አልሰጣትም፡፡ “እሷ የምትወደው የተፈጥሮውን ራሰ በራ ይሆናል!” ብሎ ተናዶ ራቱን ሳይበላ ተኛ፡፡ ኮፍያውን ባገኘ በሰባተኛው ቀን፡ ጓደኛውን ማትያስን ደውሎ ጠራው፡፡ ከሶፊ ጋር ሲጋቡ አንደኛ ሚዜው ነበር፡፡ ራሰ በራ ባይሆንም በቅርቡ ራሰ በረሀ የመሆን እድል አለው ሲል አሰበ፡፡ ራሰ በራ በሆነ ሰው ብቻ ሳይሆን በእጩ ራሰ-በራዎች መቅናት ጀምሯል፡፡ “ማቲያስ እንቢ የማትለኝ አንድ ነገር እንድታደርግልኝ እፈልጋለሁ!” ብሎ እግሩ ስር ወደቀ፡፡

ማቲያስን በግድ እሺ ካሰኘ በኋላ ከእግሩ ስር ተነሳ፡፡ “ሚስቴን ላምናት አልቻልኩም፡፡ በኔ ላይ የደረበችብኝ ይመስለኛል፡፡ ለዚህ ደግሞ ፍንጭ አግኝቻለሁ፡፡ ሰውዬው መላጣ ይመስለኛል…” ብሎ ስለኮፍያው ነገረው፡፡ “እና አንተ ሌላ ፍላጐት እንዳለው ሰው ሆነህ ቅረባት፡፡ ማለቴ… በቃ ልታወጣት እንደምትፈልግ…” አለው ማትያስን በመለማመጥ፡፡ ማትያስ በንዴት ጥሎት ሄደ! ኮፍያውን ባገኘ በስምንተኛው ቀን፡ ማትያስን አፈላልጐ አገኘው፡፡ እንባ አውጥቶ ለመነው፡፡ “የአባቴን ቁስል እያወክ!” በግድ…በግድ አሳመነው፡፡ እቅድ ነደፉ፡፡ እሱ ለመስክ ሥራ እወጣለሁ ብሎ ሊሄድ፤ ማትያስ ደሞ የእሱን መውጣት ተከትሎ እሷን ሊፈታተን፡፡

ኮፍያውን ባገኘ በሃያኛው ቀን፡ ማትያስ “ዝም ብለህ ነው! ሚስትህ ንፁህ ናት! ይኸው ሁለት ሳምንት ለሚጠጋ ጊዜ እቤታችሁ እያመሸሁ ተፈታተንኳት፡፡ እሷ ግን እንዴት ክብሯን የምትጠብቅ መሰለችህ?” አበራ፤ “አይምሰልህ ሴቶችን አንተ ስለማታውቃቸው ነው፡፡ ውጪ ራት ጋብዛት፡፡ ለኔ እንዳትነግረኝ አደራ ብለህ ንገራት!” ኮፍያውን ባገኘ በሃያ ስድስተኛው ቀን፡ ሶፊ ስልክ ደውላ “አቤ…ቆየህ እኮ በጣም… ዛሬ ጓደኛህ ማትያስ ራት እንብላ አለኝ፡፡ እኔ ግን ደስ አላለኝም፡፡ አበራ ልቡ እየመታ “ሶፊ ደሞ ምን ማለትሽ ነው? ማትያስ ማለት እኔ ማለት ነው እያልኩሽ፡፡ እራት በልታችሁ መመለስ ነው፡፡

ምን ችግር አለው?…” ነዘነዛት፡፡ ተስማማች፡፡ ኮፍያውን ባገኘ በሃያ ሰባተኛው ቀን፡ ማትያስ፣ “አበራ ሚስትህ በጣም ታማኝ ናት! አንተ በሰጠኸኝ ገንዘብ እራት ጋብዣት እስከ ስምንት ሰአት ድረስ አብረን አመሸን፡፡ ግን… እኔንጃ በህይወቷ ሙሉ እንዳንተ የምትወደው ሰው እንደሌለ አረጋግጫሁ!” አበራ ንድድ አለው፡፡ በቃ የሴቶችን ልብ ማግኘት ከባድ ነው ማለት ነው? አባቱም እናቱን ታማኝ ናት ብሎ በደመደመበት ሰአት ነበር ጥላው የጠፋችው፡፡ አእምሮው የእናቱን ድርጊት እንደፊልም ማጠንጠን ጀመረ፡፡ ሶፊማ በፍፁም ልታታልለኝ አትችልም! “እና ካሁን በኋላ ተልእኮዬን ጨርሻለሁ?” አለ ማትያስ፡፡ “አንድ የመጨረሻ እድል ማቲ…” ለመነው ኮፍያውን ባገኘ በሃያ ስምንተኛው ቀን፡ ማትያስ ሶፊ ቤት ሲጫወት አመሸ - የሰአቱ መንጐድ እንዳልተገነዘበ መስሎ፡፡ እኩለ ሌሊት ተጠጋ፡፡

በቤቱ ወስጥ እሱና ሶፊ ብቻ ናቸው ያሉት፡፡ በጣም መምሸቱን ሲያረጋግጥ “በጣም ስለመሸ እዚሁ ባድር…” የሚል ሰበብ አቀረበ፡፡ ኮፍያውን ባገኘ ሃያ ዘጠነኛው ቀን፡ አበራ ራሱ ለማትያስ ደወለ፡፡ “እሺ?” አለ አበራ “ምን እሺ አለ?” ማትያስ ቀዝቀዝ አለ፡፡ የሆነ ነገር ተፈጥሯል ማለት ነው፡፡ አበራ ልቡ መታ፡፡ በአንድ በኩል ሚስቱ ስታታልለው ስለያዛት ደስታ፣ በሌላ በኩል ክህደቷ እንደወላፈን ገረፈው፡፡ “እኔ እኮ ነግሬሃለሁ! ሴቶች ከሀዲ ናቸው! ያ መላጣን ማውጣቷ ሳያንስ አንተንም! የማላውቃቸውን ስንት ወንዶች… ስንት ወንዶች…” የአበራ ድምፅ በለቅሶ ሻከረ፡፡ “ባክህ ዝም በል! ምንም የሆነ ነገር የለም! ትላንትና ማታ ሚስትህ ባለጌ ብሆንባትም አክብራ ሶፋ ላይ አስተኝታ፣ መኝታ ቤቷን ቆልፋ ነው የተኛችው!” ማትያስ ስልኩን ጆሮው ላይ ዘጋው፡፡

አበራ እልህ በልቡ ተንተከተከ፡፡ ከማትያስ ጋር እንደተመሳጠሩ ወይ ጠርጥራ በነፍሰ ስጋው እየተጫወተች ነው እንጂ… አእምሮው ውስጥ ያሉ ድምፆች አስተጋቡ - “የሴቶችን ልብ ማመን አትችልም! ልባቸውን ወንድ ያኘዋል ማለት ዘበት!” ሲፈራ ሲቸር ማቲያስ ጋር ደወለ፡፡ ያሳለፈውን ህይወት እየተረከ ማትያስ እንዳያዝንለት አደረገ፡፡ ማትያስ በጣም ተጨነቀ፡፡ “እሺ አሁን ምን አድርግ ነው የምትለኝ?” “ሚስቴን ማመን እፈልጋለሁ! ያን ለማድረግ የመጨረሻ! የመጨረሻ! አንድ ነገር ብቻ ተባበረኝ! ከዛ በኋላ አላስቸግርህም ማትያስ አማራጭ አልነበረውም “የተቆለፈ ልብ በአልኮል ይከፈታል! ያኔ የተደበቀ ማንነት ይወጣል!” አለ አበራ ኮፍያውን ባገኘ በሰላሳኛው ቀን፡ ማትያስ ሁለት ሰአት ላይ ወደ ሶፊ መጣ፡፡ ራት በልተው ሲጨርሱ ይዞ የመጣውን ሻምፓኝ ከፈተ፡፡ ሶፊ አልጠጣም አሻፈረኝ አለች፡፡ ማትያስ ለአበራ ደውሎ ነገረው፡፡ አበራ ለሶፊ መልሶ ደወለ “ሶፊዬ ማትያስ ማለት እኔ ማለት ነው፡፡ እሱ እኮ ብቸኝነት እንዳይሰማሽ ነው፡፡ ለኔ ስትይ እሺ በይው…” ለመናት፡፡

ሶፊ አንደኛውን የሻምፓኝ ብርጭቆ ተቀብላ ተጐነጨች… ደገመች… ኮፍያውን ባገኘ ሰላሳ አንደኛው ቀን ጠዋት፡ አበራ ጠዋት ወደ ቤቱ መጣ፡፡ በሩን ከፍቶ ሊገባ ሲል የግቢውን ቆሻሻ የሚደፋው ልጅ ከበሩ መግቢያ ላይ አገኘው፡፡ እድሜው ከዘጠኝ አመት አይበልጥም፡፡ “ጋሼ፤ ቆሻሻ አለ?” “የለም!” ብሎት አልፎት ሊገባ ሲል፣ ልጁ እየተቅለሰለሰ ጠጋ አለው፡፡” “ጋሼ ይቅርታ! ባለፈው ቆሻሻ ልወስድ ስገባ ያቺን ኬፕ… ማለቴ ኮፍያ ግቢ ውስጥ ረስቻት ወጣሁ፡፡ ባለፈው መኪና ውስጥ አይቻት ልጠይቅዎት ስል ሄዱ፡፡ በኋላ ፊልድ ሄደዋል አሉኝ…” አበራ አናቱን በዱላ የተመታ ያህል ደነገጠ፡፡

“ያንተ ነው?” አለ ልጁ ላይ እያፈጠጠ፡፡ ልጁ በድንጋጤ እንደተዋጠ ጭንቅላቱን ላይ ታች ወዘወዘ፡፡ “እና መላጣ ምናምን ስል የበረው በራሴ ፈጥሬ ነው?” አለ አበራ ሳይታወቀው እየጮኸ “ምናሉኝ ጋሼ?” ልጁ ግራ ተጋብቶ ጠየቀው፡፡ ልጁን ችላ ብሎ ወደ ግቢው ሲገባ ማትያስ አይኑ እንደቀላ ወደ በሩ ሲመጣ አየው፡፡ ቆሞ ጠበቀው፡፡ “ያው ደስ ይበልህ! ያሰብከው ሁሉ ሆነልህ! በመጠጥ አደንዝዘህ የምትፈልገውን ፈፅመናል!...” ማትያስ በንዴት ባሩድ የተቃጠሉ ቃላቶቹን እንደጥይት ተኮሳቸው፡፡ “ከሌላ ወንድ ጋር እስክታያት መቼም ቢሆን አርፈህ እንደማትቀመጥ እርግጠኛ ነበርኩ! ሚስት ያገባነው ለበቀል ነበር!” ብሎት ሄደ፡፡ ሚስቱን እጅ ከፍንጅ በመያዙ እርካታን ጠብቆ ነበር፡፡ እርካታ የለም! ፈፅሞ እርካታ ውስጡ የለም! ንፁህነቷ እየጐላ የእሱ መሰሪነት እየገዘፈ መጣበት፡፡

ቤት ሲገባ የሶፊ ሻንጣ ለጉዞ ተዘጋጅቶ ተቀምጧል፡፡ አንገቷን ደፍታ ከሶፋው ላይ ተቀምጣለች፡፡ ቀጭን እንባ በፊቷ ላይ ይወርዳል፡፡ በቆመበት ቁልቁል አያት! መግቢያ ቀዳዳ አጥታ ስትሽቆጠቆጥ በእርካታ ተሞልቶ እንደሚያስተውላት ነበር ያሰበው፡፡ መሳሳቱ ወለል ብሎ ታየው! እንደ አልማዝ የጠነከረ ታማኝነቷን እሳት ሆኖ ማቅለጥ ቢያቅተው፤ በውሃ ሸርሽሮ በድን አካሏ ቃል ኪዳን እንዲሰብር ማድረጉ መልሶ አንገበገበው…

ባለ 18 ፎቅ ሆቴል በክልል ከተሞች ቀርቶ በአዲስ አበባም አልተለመደም፡፡ ጣና ሐይቅን ከጀርባው አድርጐ የተሠራው ባለ 5 ኮከቡ ሆቴል ለባህርዳር ከተማ ተጨማሪ ውበት ሆኗታል፡፡ የሆቴሉ ባለቤት ትልቅሰው ገዳሙ ወደ ኮንስትራክሽን ቢዝነስ የገቡት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ቢሆንም የሆቴሉን ግንባታ በአጭር ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ ችለዋል - ፈተናዎችን እየተጋፈጡ፡፡ በጐጃም ውስጥ በገጠር አካባቢ የተወለዱት ወ/ሮ ትልቅሰው፤ ከአምስት አመት በላይ በባሌ እና በአዲስ አበባ በአስተማሪነት ከሰሩ በኋላ ነው ወደ ቢዝነስ የገቡት፡፡ ከትንሽ ንግድ ተነስተው፣ አንዱን ቢዝነስ ለሌላ ትልቅ ቢዝነስ መሰላል እያደረጉ ዛሬ ከ300 ሚሊዮን ብር በላይ የፈጀ ሆቴል ሰርተዋል፡፡ ከወ/ሮ ትልቅሰው ጋር ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው ያደረገችውን ቃለ-ምልልስ እነሆ! የትልቁ ሆቴል ግንባታ እየተጠናቀቀ ነው… ባህርዳር ከተማ ባለ አምስት ኮኮብ ሆቴል “G+18” ፎቅ እየሰራሁ ነው።

በከተማውና በክልሉ ሆቴል ኢንቨስትመንት ትልቁና የመጀመሪያው ይሆናል ብዬ እገምታለሁ። 150 ክፍሎች፣ አምስት ሬስቶራንት፣ መዋኛ፣ ሳውና፣ ስቲም፣ ጃኩዚ... የባለ አምስት ኮኮብ ሆቴል ደረጃዎችን የሚያሟላ ነው። የፊታችን ሐምሌ ወር ላይ በ“ሶፍት ኦፕኒንግ” ስራ ለማስጀመርና በ2006 ዓ.ም. ለማስመረቅ እቅድ አለኝ። 24 ሰዓት እየተሰራ ነው። ዘጠና ፐርሰንት ተጠናቋል። ሻምፑና ኮንድሽነር፣ ሹካና ማንኪያ ካልሆነ በስተቀር... ሁሉም ነገሮች ገብተዋል።

ማኔጅመንቱ ፍሬንቻይዝድ ነው፤ ነጮች ናቸው የሚያስተዳድሩት። እግዚአብሄር ከፈቀደ ብዙ ነው አላማዬ። ሄሊኮፕተር ገዝቼ እንግዶቼን ለማስጎበኝበት ህልም አለኝ። ለምሳሌ ከአዲስ አበባ እንግዶችን ተቀብለናቸው ደብረ ማርቆስ እናሳርፋቸዋለን። ከዛ ባህርዳር እኛ ሆቴል፤ ከዚያም ላሊበላ ጎንደር እያልን ለማስጎብኘት በቅብብሎሽ መስራት ነው ቅድመ ዝግጅታችን። የሄሊኮፕተር ጊዥውን አጥንተን ጨርሰናል። ሆቴሉ ስራ ሲጀምር አስር ማርቼዲስ፤ አራት ላንድ ክሩዘር፤ ሶስት ጀልባዎች ይኖሩታል። ሶስቱ ጀልባዎች ከጀርመን ታዘው እየመጡ ነው። አንደኛው ጀልባ 45 ሰዎችን ማስተናገድ የሚችልና የባህር ላይ እራት የሚዘጋጅበት ነው። ሶስት መኝታ ቤቶችና አንድ ሻወር ያለው ጀልባ ነው። ሁለቱ 25 ሰው የሚጭኑ ትናንሽ ጀት ስክኒች ናቸው። ሆቴሉ የሚከፈተው ይሄ ሁሉ ተሟልቶ ነው። የየት ሀገር ባለሞያዎች ናቸው ሆቴሉን የሚስተዳድሩት? ማኔጅመንቱን እኔ መያዝ አልፈልግም። ከአለም አቀፍ የሆቴል ማኔጅመንት ጋር እየተነጋገርን ነው። ገና አልተፈራረምንም። ግን ፍራንቻይዝ ነው የሚሆነው።

ከ400 በላይ ሰራተኞች ይኖሩታል። የሆቴሉ ስም ምን ተባለ-- በፍራንቻይዝ ስለሚሰራ፣ የሆቴሉን አስተዳደር በሚመራው ኩባንያ የሚወሰን ይሆናል። ምናልባት ከእነሱ ጋር ካልተስማማሁ “ግራንድ ባህርዳር” እለዋለሁ። በባህርዳር ላይ እየተሰራ ያለው ባለ አምስት ኮኮብ ሆቴል መጀመሪያ ላይ ባለ 18 ፎቅ እንዲሆን አልታሰበም ነበር ሲባል ሰምቻለሁ። ደግሞም፤ የህንፃ አርኪቴክቶችና ዲዛይነሮችን እየተከታተልሽ ትፈታተኚያቸዋለሽ ይባላል? እውነት ነው። የሆቴሉ ቁመት ወደ ላይ ረጅም እንዲሆን የፈለኩት እኔ ነኝ፡፡ ክልሉ የሰጠኝ ቦታ ቆንጆ ነው። ታወር ነበር፤ ዲዛይን አቀረብኩላቸውና “አስራ አራት አድርጊው” ሲሉኝ “አስራ አራት ከደረስኩ፤ አስራ ስምንት ለምን አይሆንም” ብዬ አስራ ስምንት አድርጌ ሰራሁት። ከዲዛይነሮች ጋር እኩል ነው የምራመደው። እኩል ነው ቻሌንጅ የማደርጋቸው። ኤክስፓዠሩ አለኛ! ዓለም ላይ ብዙ አገር እዞራለሁ።

ሆን ብዬ ባለ አምስት ኮኮብ ሆቴሎች ነው የማርፈው። ይህቺ ግድግዳ፣ ጣሪያ ምን ትመስላለች? ፍሪጅዋ ምን ላይ ተቀመጠች? እያልኩ የሚሉትን ነገሮች በደንብ እመለከታለሁ። ካሜራዬ ውስጥ ብታይ የሰው ፎቶ አታይም። የመፀዳጃ ቤት፣ የመታጠቢያ ገንዳ፣ የአልጋ ዓይነት፣ የሆቴሉ ክፍሎች፣ የግድግዳና የጣሪያ ቀለማቸው፣ የሬስቶራንት ዕቃ አቀማመጥ ፎቶ ነው የምታይው። አርክቴክቶች ከእኔ ፈቃድ ውጪ አይሰሩም። እያንዳንዱዋን ነገር እኔ ማየት አለብኝ፤ መተማመን አለብን። ለእኔ ሳያሳዩ ያደረጉት ነገር ካለ፣ ቀስ ብለን እናሳምናታለን ብለው ነው የሚሰሩት፡፡ የሚመቸኝንና የሚሆነውን ነው የማሰራቸው።

ከዱባይ ኤሚሬት ኮንኮርድ፣ ግራንድ አይነት ሬስቶራንት እኔ ጋ እንዲደገም አድርጌዋለሁ። ውስጡ ምን ይመስላል? የሚለው በሙሉ የእኔ ምርጫና ፍላጎት ነው፡፡ አልጋ፣ የአልጋው ቀለም፣ የቤቱ ግድግዳ ቀለም “ይሄ የራሴ ስራ መሆን አለበት” ብያቸው ሙሉ በሙሉ የእኔ የእጅ ስራ ውጤት ነው። ከሠራተኞቼ ጋር እኩል ቱታ ለብሼ፣ ኮፍያ አድርጌ አንዱን ሳነሳ አንዱን ስጥል ነው የምውለው። በጣም ደስተኛ ነኝ። ኤስያ፣ ቻይና ሌሎች በሆቴልና ቱሪዝም ትልልቅ ስም ያላቸው አገሮችን ጎብኝቻለሁ። አምስት ኮኮብ ሆቴል አርፌ አይቻቸዋለሁ። ብቻዬን ሳይሆን አርክቴክቸሮቼንም ይዤ፣ በዓለም ላይ ያልተጓዝኩበት አገር የለም። እንግሊዝ አገር ብቻ ነው የሚቀረኝ። ሌላ የት የት ከተማ ነው ሆቴሎች የሠራሽው? ምዕራብና ምስራቅ ጎጃም ፈረስ ቤት፣ ደብረ ማርቆስ፣ አሁን ደግሞ ትልቁና ባለ አምስት ኮኮብ ሆቴሉ የባህር ዳሩ ነው። በሆቴል ኢንዱስትሪ ውስጥ ደግሞ ሰፊ ስራ ጀምሪያለሁ።

በተለያዩ ክልሎች ስራዬን ማስፋፋት እፈልጋለሁ። በርግጥ ደክሞኛል.. ግን ባለኝ የተፈጥሮ ባህሪ ከስራ ርቄ መኖር አልችልም። ቱሪዝሙን ተከትዬ የምሰራ ይመስለኛል። በደብረማርቆስ ከተማ በጥሩ መስተንግዶ የሚታወቀው “ትልቅ ሆቴል” የሚባል ባለ ሶስት ኮኮብ ሆቴል አለኝ። 50 የመኝታ ክፍሎች፣ ሳውና፣ ስቲም፣ መጠነኛ የስብሰባ አዳራሽ አለው። አምስት ሺ ካሬ ሜትር ማስፋፊያ ቦታ ሰጥተውኛል። አሁን ደግሞ አስፋፍቼ የተለያዩ ነገሮችን ለመስራት ዲዛይኑ ተሰርቶ ግንባታ ላይ ነው። በማህበረሰባችንም በቤተሰብም ሴት ልጁ በተለያየ ስኬትና ኃላፊነት ለማጨት ያለው ውስንነት ደፍሮ ለመውጣት ፈተናዎችንና ችግሮችን ለመጋፈጥ ያለውን አስተሳሰብ በመስበር ምን ሰራሁ ትያለሽ--- “ሴት” የሚለው ቋንቋ እኔን አይገልፀኝም።

ወንድ ሊያደርግ የሚችለውን ነገር ሁሉ ማድረግ እችላለሁ። መማታት ቢኖርብኝ፤ እማታለሁ(ሳቅ)። ግፍና በደል እንኳን የደረሰብኝ የለም። በእምነት በኩል ያጎደልኩት ነገር የለም። ባንኩም ሰዉም “ትልቅሰው ትሰራለች፣ ተበድራ ትከፍላለች” ይላል እንጂ፣ በጥርጣሬም ሆነ በሌላ ስሜት የሚያየኝ የለም። ስራዎቼን አይተው አድንቀው ከጨረሱ በኋላ፣ “አይገርምም ሴት አኮ ናት” ብለው የሚናገሩ አሉ። ይኼ በጣም የሚያናድደኝ ቋንቋ ነው፡፡ “እና ሴት ብሆንስ ማድረግ አልችልም?” ነው የእኔ ጥያቄ። ወንድ ከእኔ የተሻለ አእምሮ አለው? እሱ ሊያስብ የሚችለውን ያህል እኔም አስባለሁ። እንዲያውም ከወንዱ የተሻለ ዲሲፕሊን የሚታየው በሴቶች ላይ ነው። ለ”ኮሚትመንት” ተገዢ በመሆንም ሴቶች ይበልጣሉ። በቃላችን ለመገኘት እንበረታለን።

ገንዘብ አናባክንም፣ ሴቶች ጥንቁቅ ነን። ዕዳና ብድር ብዙ አንደፍርም። ብዙ መስራትና መሄድ እችል ነበር። ወደ ጠንቃቃነት እናደላለን ብዬ አምናለሁ። ቤተሰብም ላልሽው የሰጡኝ ነገር ሲኖር ገንዘባቸውን እንዳላባክንባቸው ሊሆን ይችላል። እኔ ጥሬ ግሬ ያመጣሁት ገንዘብ ነው። ማንም በእኔ ህይወት ጣልቃ ሊገባ የሚፈልግ የለም። የምፈልገውን እሸጣለሁ፤ የምፈልገውን አጠፋለሁ። ይሄ መንገድ ልክ አይደለም የሚለኝ ሰው የለም። በርግጥ ቤተሰቦቼ የገጠር ሰው ናቸው። አስተማሪነትን ስለቅ በጣም ተሰምቷቸዋል። ኑሮዬን ያበላሸሁ መስሎ ስለታያቸው። ኑሮዬ በየጊዜው እየተቀየረ ሲያዩ ግን በጣም ያደንቁኝ ጀመር።

ካልሽስ፣ አንድ ጊዜ ወደ ባህርዳር በአውሮፕላን እየተጓዝኩ ሳለ ከአንዲት የባህርዳር ዩኒቨርሲቲ የሁለተኛ ዓመት ተማሪ ጋር እያወራን ነበር፡፡ እኔን አታውቀኝም። ስለ እኔ እያደነቀች ለኔ ታወራለች። “አንድ ሴት ጀግና፤ በጣም ጎበዝ…” እያለች ስታወራልኝ፣ ዝም ብዬ አዳምጣታለሁ። መጨረሻ ላይ፤ እኔ መሆኔን ስነግራት፣ ተነስታ ተጠመጠመችብኝ። በክልሌ እንደብርቅ ነው የሚያዩኝ። በጣም ያከብሩኛል። ህዝቡ የባህርዳሩን አዲሱን ሆቴሌን ወደ ላይ ቆሞ ሲቆጥር፣ ሲያደንቅ፣ መተዋወቅ ሲፈልግ ነው የማየው። የልጅነት ህልምሽ ምን ነበር? ነጋዴ፣ የቢዝነስ ሰው የመሆን ምኞት ነበረሽ? በእንጨት የተሰራ ትንሽ ሳጥን “ባንክ” እያልሽ ሳንቲም ማስቀመጥ… “የእንቁጣጣሽ” ሳንቲም ማጠራቀም… የገጠር ልጆች ነኝ።

ሳንቲም አላውቅም ነበር ንግድ ምን እንደሆነ አላውቅም። የአካባቢዬ ልጆችና ወንድሞቼ እንዳጋጣሚ ወደ ቢዝነስ ገብተው ውጤታማ የሆኑበት ጊዜ ነበር። እነሱን ተከትዬ ነው የገባሁት እንጂ ቢዝነስ ምን እንደሆነ እንኳን አላውቅም ነበር። የት ነው የተወለድሽው፣ ያደግሽው? ጎጃም ቆላ/ደጋ ዳሞት የሚባል አውራጃ ደጋዳሞት ውስጥ አሁን ምዕራብ ጎጃም ፈረስ ቤት ነው የተወለድኩት። ትምህርቴንም ያጠናቀቁት እዛው ፈረስ ቤት ነው። ከዛም መምህራን ማሰልጠኛ ባሌ ገባሁ። ሁለት ዓመት ሰርቻለሁ። አዲስ አበባ አምስት ዓመት ሰርቻለሁ። ከባሌ ወደ አዲስ አበባ ስቀየር ያኔ አዲስ አበባ ክልል አልነበረም። በጊዜው ዝውውር የለም። አዲስ አበባ እየሰራሁ ደሞወዛችንን ክልል ይከፍለን ነበር። ባሌ ክ/ሀገር ማለት ነው።

በኋላ ክልል ሲመደብ “ይሄንን ዓይነት ዝውውር አናስተናግድም” ብሎ አዲስ አበባ ላይ ማስታወቂያ ሲያወጣ፤ ወደ ባሌ ተመለሽ ተባልኩኝ.. ከ5ዓመት በኋላ ማለት ነው። አንድ ጓደኛዬ “አትሄጅም፤ እኛ ጋ ትሰሪያለሽ” አለኝ። ያኔ ነው አሰተማሪነቱን የተውኩት። መጀመሪያ ወደ ንግዱ ስትገቢ ገንዘብ ከየት አመጣሽ? ሰው ብር ሰጥቶኝ በብድር? እረ! ስጦታ ነው። ምን ያህል ገንዘብ--- 18 ሺህ ብር የመጀመሪያው የንግድ ስራሽ ምን ነበር? በጣም ትንሽ የሸቀጣሸቀጥ ሱቅ ነው የከፈትኩት። ትንሽ ዓመት ሰራሁና ወደ ግሮሰሪ አሳደኩት። ከትንሽ ተነስቶ የማደግ ምሳሌ ነኝ። እንደ ጓደኞቼ ማደግ፤ ሰው መርዳት፣ አገሬ ላይ መስራት እፈልግ ነበር። እግዚአብሄር ይመስገን የተመኘሁትን ሁሉ አድርጌያለሁ።

ነገ ደግሞ የተሻለ ሰው እንደምሆን አውቃለሁ። የሸቀጣሸቀጥ ሱቁና ግሮሰሪው አሁንም አሉ? አይ የሉም። ወደያው የውጭ ንግድ ጀመርኩ። ከዛ ደግሞ አድጌ ወደ ትራንስፓርት ንግድ ገባሁ። ትራንስፓርቱ ስራ አሁንም ድረስ አለ። የውጭ ንግድ ስትይ ---? የዛሬ 16 ዓመት ወደ ቻይና፣ ወደ ዱባይ አገር ሄጄ ጨርቃጨርቅና ኮርያ ብርድ ልብስ አመጣ ነበር። በጅምላ ልብስ አከፋፍል ነበር። ስራው ደስ ስላላለኝ ነው እንጂ አድካሚ ነበረ፡፡ ጉምሩክ ላይ ያለው ጣጣ “ኤስ ጂ ኤስ” የሚባል መስሪያ ቤት ነበር። እዚያ ሄዶ መዞሩና መግዛቱ ፈተናውና ድካሙ ከባድ ነው። ብዙ ስላልወደድኩት ወደ ትራንስፖርት ገባሁ። በተፈጥሮዬ አንድ ስራ ላይ ሙጭጭ ብዬ መቆየት አልወድም። የተወሰነ ነገር በተወሰነ ጊዜ ነው በፍቅር የምሰራው።

ከዚያ በኋላ መገልበጥ ወደ ሌላ ነገር መሄድ እፈልጋለሁ። ለሆነ ጊዜ ያህል ከሰራሁ በኋላ ቁጭ ብዬ ገንዘብ መቁጠር አይደለም። ለምሳሌ ሆቴል ሰርቼ ገንዘብ መሰብሰቡ ላይ አይደለም የማተኩረው። ደብረ ማርቆስ ያለውን ንግዴን ትንሽ ወንድሜ ነው የሚሰራበት። ፈረስ ቤት ያለውን ሆቴል፤ ትልቅ ወንድሜ ማኔጅ እንዲያደርገው ሰጥቸዋለሁ። የትራንስፓርት ስራውስ? አገር አቋራጭ ሦስት የህዝብ አውቶብሶች ገዛሁ። ከዛ ደግሞ ሶስት ቦቴዎችን። ስሰራ ቆይቼ፤ እንደገና ሶስት ቦቴዎች ጨመርኩ። ወደ ደረቅ ጭነት ትራንስፖርትም ገባሁበት፣ 27 የደረቅ ጭነት መኪኖች ነበሩኝ። ከዚያ ደግሞ፤ አርባ ገልባጭ መኪኖችን በአንድ ጊዜ አስገባሁ። ከባድ ስራ ነው፡፡ ሾፌር፣ ረዳት፣ ጥገና... ከባድ ነው። ከጊዜ በኋላ ወደ ግንባታው አዘነበልኩ።

አሁን የተወሰኑት መኪኖች ተሸጥዋል። የተወሰኑት አሉ፤ የትራንስፓርት ድርጅቱ እየሰራ ነው። የትራንስፓርት ድርጅትሽ ስም ምን ይባላል? “ቻኩ ትራንስፓርት” ይባላል። የደረቅ ጭነትና የፈሳሽ ጭነት መኪኖች፣ ገልባጮችና ሌሎች የኮንስትራክሽን መሳሪያዎችን እያሰማራ ሲሰራ ነው የቆየው። ገልባጮቹን ቀስ በቀስ ሸጥኳቸው። አሁን ደረቅ ጭነቱ ይሰራል። ለንግድ ስኬታማነትሽ አይነተኛ ሰው ለአንቺ ማን ነው? ወንድሞቼንና የአካባቢ ልጆቼን አይቼ ነው ወደ ንግድ የገባሁት ብየሽ የለ? በጣም የምወደው ወንድሜና ጓደኛዬ፣ እንደ ራሴ የማየው፣ ‹‹ጥላሁን ደስታ›› ይባላል። ዛሬ ለእኔ ብር ማግኘት ቀላል ነው። 4 እና 5 ሚሊዮን ብር መበደር እችላለሁ። ከሆነ ሰው ሄጄ መቀበል እችላለሁ። ያን ጊዜ ማንም በማያውቀኝ ሰዓት፤ ማንም በማይሰጠኝ ሰዓት ”አበድረኝ” ብዬ አይደለም የምጠይቀው። “ብር እፈልጋለሁ” ብዬ ነው የምጠይቀው። በተለይ የማልረሳው አንድ ጊዜ 425 ሺ ብር ነበር እዚህ አዲስ አበባ ውስጥ የመኖሪያ ቤቴን የገዛሁት። እኔ የነበረኝ 300 ሺ ብር ብቻ ነበር። ቀብድ ከፈልኩና በቀጥታ ደውዬ፣ “125 ሺህ ብር እፈልጋለሁ” አልኩት።

“ቢያንስ ተዘጋጅ እንኳን አትይኝም ወይ?” ሲለኝ፤ “በቃ፤ እፈልጋለሁ፣ እፈልጋለሁ” አልኩት። እንዳለውና እንደሚሰጠኝ አውቃለሁ። እቁብ ብንገባ ቅድሚያ የሚሰጠኝ ለእኔ ነው። ጓደኞቹን ይሰበስብና ተጣጥለው ለእኔ ነው የሚሰጠኝ። ጠንካራ እንድሆን ነው የሚለፋው። ችግር እንኳን ቢኖርብሽ፣ “ሰው አለኝ፤ እገሌ አለኝ” የምትይው አለኝታ ሲኖር፤ ጠንካራና ደፋር ትሆኛለሽ። ለዚህ ሁሉ ስኬት ያበቃኝ፣ ጥላሁን ደስታ ይባላል። እሱ ነው ለእኔ አይነተኛው ሰው። እኔም የወሰድኩትን ያህል ገንዘብ ብወስድ፣ ባልኩት ሰዓትና ጊዜ ሳላዛንፍ ነው የምመልሰው። ከትራንስፓርቱ ቀጥሎ ንግድሽ ወደ ምን አደገ? ኤምባሲ የተከራያቸው ቤቶች አሉኝ። ነዳጅ ማደያ አለኝ። ኧረ ተይኝ፣ መዘርዘሩ ሳይሆን መስራት ደስታን ይሰጠኛል። ዕድሜሽ ስንት ነው? ለቤተሰብሽ ስንተኛ ልጅ ነሽ? መስከረም 21 ቀን 2005 ዓ.ም. 40 አመቴን አክብሬአለሁ፡፡

አምስተኛ ልጅ ነኝ። ከእኔ ላይ አራት፣ ከእኔ ታች አራት አሉ ዘጠኝ ነን። አንድ እህቴ አለች፤ እኔ ነኝ አሳድጌ የዳርኳት፤ ጥሩ ህይወት አላት ባሏም ጎበዝ ነው፡፡ ሌሎችም አሉ ጥሩ የሚያግዙኝ - እግዚአብሄር ይመስገን። አባቴ በህይወት የለም፤ እናቴ አለች። በሆቴልና ቱሪዝም ኢንዱስትሪው በስፋት ለመስራት ስትነሳሺ ወደ ፊት እንደ ዕቅድ የያዝሻቸው ነገሮች ምንድን ናቸው? ክልሎች ላይ ለመስራት እፈልጋለሁ። በቅርብ እንኳን የማስበው አዋሳ፣ ላሊበላ፣ ጎንደር መስራት እፈልጋለሁ። በምን ያህል ካፒታል ተገነባ የደብረ ማርቆሱም፣ የባህር ዳሩም? የደብረ ማርቆሱን ስሰራ ሁሉም ነገር ርካሽ ነበር። ምን ያህል እንዳወጣሁ አሁን በትክክል አላስተውሰውም። ምናልባት ከ16 እስከ 20 ሚሊዮን ብር ይሆናል። የባህርዳሩ ግን ተይው። በጣም ሁሉ ነገር ያበደበት ጊዜ ነው። ግን አንድም ቀን ስራውን ለማቆም አልፈለግኩም። አንድም ቀን አንድም ሰዓት ስራው አልቆመም። ከተጀመረ ሦስት ዓመቱ ነው። በ2,540 ካሬ ላይ ነው ያረፈው። 350 ሚሊዬን ብር ድረስ ይጨርሳል ተብሎ ይገመታል። ከባንክ ተበደርሽ? ወይም ዛሬም ጓደኛሽን አስቸገርሽ? ኖኖ ዛሬስ አላስቸገርኩትም። 58 ፐርሰንት ከራሴ 42 ፐርሰንት ከባንክ ተበድሬ ነው።

የአክሲዮን ማህበር፣ ከስልጡን የብልፅግና መንገዶች መካከል አንዱ ቢሆንም በርካታ ችግሮችም ይታዩበታል፡፡ ለአርያነት የሚበቁ የአክሲዮን (ኩባንያዎች) የመኖራቸውን ያህል በውዝግብ የታመሱ የአክሲዮን ማህበራት፣ በምስረታ ላይ አመታትን እያስቆጠሩ ባለ አክሲዮኖችን ተስፋ የሚያስቆርጡ ማህበራት፣ ለብክነትና ለስርቆት የተጋለጡ፣ ለትንሽ ጊዜ ግርግር ፈጥረው እልም የሚሉ የአክሲዮን ሽያጮችም አሉ፡፡ አሰራሩ ለአገራችን አዲስ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ፣ ብዙ ሰው በቂ መረጃ የሌለው መሆኑ ለአገራችን አዲስ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ፣ ብዙ ሰው በቂ መረጃ የሌለው መሆኑ ደግሞ ችግሮቹ አወሳስቧቸዋል፡፡

ከሁለት አመት በፊት በወጣው ህግ መሰረት፣ በታቀደለት ጊዜ ገንዘብ አሰባስበው ያላጠናቀቁ የአክሲዮን አደራጆች፣ ለባለ አክሲዮን ወለድ ለመክፈል እንደሚገደዱ ያውቃሉ? የአክሲዮን ማህበራት ህግ በጣም ጥብቅ ከመሆኑ የተነሳ፣ የአክሲዮን አደራጆች ተጠያቂ በሚሆኑበት ጊዜ የማስታወቂያ ድርጅቶችም ተጠያቂ እንደሚሆኑ ያውቃሉ? በእነዚህና በተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ከንግድ ሚኒስቴር የንግድ ምዝገባና ፈቃድ ጊዜያዊ ዳይሬክተር ከአቶ ኑረዲን መሀመድ ጋር ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ያካሄደችውን ቃለ ምልልስ አቅርበናል፡፡ አክሲዮን ማህበር ላይ ብዙ መሟላት ያለባቸው የህግ ግዴታዎች እንዴት ይነገራል? እነዚህን ነጥቦች ቢጠቃቅሱልን፡፡

አክሲዮን ማህበር ከሌሎች ማህበራት የሚለየው፤ ተስማምተው ከፈረሙት አባላት ውስጥ፤ የተከፈለው ካፒታል 1/4ኛ ሲደርስ አክሲዮን ማህበሩ ሕጋዊ ሠውነት ያገኛል፡፡ ይሄ አንደኛው ነው፡፡ ሌላው የአክሲዮን ማህበር አደራጆች መስራቾች አክሲዮኑ በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ተሸጦ ማለቁንና ገንዘቡ ተሰብስቦ መግባቱን ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ፡፡ አክሲዮን ማህበሮች በንግድ ህጉ ላይ ከ317 እስከ 322 የተጠቀሱ የህጉ አንቀፆችን ማሟላት አለባቸው፡፡ ዝቅተኛው የአባላት ቁጥር አምስት ነው፡፡ ዝቅተኛው የካፒታል መጠን ደግሞ 50ሺህ ብር፡፡ አክሲዮን ማህበር እንደ ማንኛውም የንግድ ማህበር መመስረቻና መተዳደሪያ ደንብ ማዘጋጀት አለበት፡፡ በአባላት መፈረም አለበት፡፡ በተጨማሪ ሌሎች ነገሮችንም ማሟላት አለበት፡፡

ለምሣሌ የግብር ከፋይ መለያ ቁጥር ማግኘት ይኖርባቸዋል፡፡ የንግድ አድራሻቸው በትክክል መታወቅና መለየት አለበት፣ የተከፈለው ወይም የተሰበሰበው የገንዘብ መጠንም ከተስማሙበት እቅድ ከአንድ አራተኛ መብለጥ አለበት ይላል ህጉ፡፡ በሀገራችን የአክሲዮን ምስረታና ሽያጭ መቼ ተጀመረ አሁን የሚስተዋሉ ችግሮችስ ከምን የመነጩ ናቸው? እርግጥ በሀይለ ስላሴ ዘመን የተጀመረ ነው፡፡ የንጉሱ ቤተሠቦች ከሌሎች ሠዎች ጋር ገንዘብ አሠባስበው አክሲዮኖችን መስርተው ነበር፡፡ ለምሣሌ ኢትዮ-መተሀራ አክሲዮን ማህበር ተመስርቶ ነበር፡፡ የኢንሹራንስና የባንክ አክሲዮን ማህበሮችም ነበሩ፡፡

የደርግ ሥርዓት መጥቶ አጠፋቸውና ሁሉም ነገር በመንግስት ቁጥጥር ስር ሆነ፡፡ አክሲዮን ማህበር እንደ አዲስ መፍላት የጀመረው ከ1984 ዓ.ም ወዲህ ነው፡፡ የመንግስት የልማት ድርጅቶችን ወደ አክሲዮን ማህበራት በመቀየር ባለሃብቶች እንዲሳተፉ ተደረገ፡፡ የተወሰነ ብር ያላቸው ሠዎች አቅማቸውን እያሰባሰቡ በባንክና በኢንሹራንስ ዘርፎች የአክሲዮን ማህበር በማቋቋም አሁን እያደጉ የምናያቸውን የፋይናንስ ተቋማት እውን አድርገዋል፡፡ ከፋይናንስ ሴክተሩ ውጤታማነት ጋር የአክሲዮን ማህበራት በሌሎች ዘርፎችም መግባት ጀምረዋል - በቢራ፣ በሲሚንቶ፣ በጅምላ ንግድ፣ በአግሮ ኢንዱስትሪ ፕሮሠሲንግ ዘርፍ፣ በኢንተግሬትድ አግሮ ኢንዱስትሪ ፕሮሠሲንግ ዘርፍ ወዘተ፡፡ የአክሲዮን ማህበር፣ ሰዎች አቅማቸውን አሰባስበው በጋራ እንዲሰሩ የሚያደርግ በመሆኑ ሊደገፍ ይገባዋል፡፡ በሌላ በኩልም የባለ አክሲዮኖችን ገንዘብ ለአደጋ የሚያጋልጡ ቀዳዳዎች እንዳይፈጠሩ መጠንቀቅ ስለሚያስፈልግ በ2002 ዓ.ም የህግ ማሻሻያ ተደርጓል በአዋጅ ቁጥር 686/2002፡፡

እስኪ ስለ አዋጁ ትንሽ ያብራሩልኝ… አዋጁ፣ በአክሲዮን ማህበር አደራጆች ላይ ተጠያቂነትን የሚፈጥር፣ ለአክሲዮን ባለድርሻዎች ደግሞ ከለላ የሚሰጥ ነው፡፡ የአክሲዮን ማህበር ከመቋቋሙ በፊት የፅሁፍ ድጋፍ ከመንግስት ማግኘት አለበት፡፡ ለዚህም መሟላት ያለባቸው ጉዳዮች አሉ፡፡ ህዝቡ አክሲዮን ሲገዛ፣ ገንዘቡ እንዳይባክን በዝግ አካውንት መግባቱን ማረጋገጥ፣ የአክሲዮን ማህበሩ አደራጆች እነማን እንደሆኑ ማወቅ፣ በተሠጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ስለተጠራቀመው ገንዘብና ስለ አጠቃላይ እንቅስቃሴው ሪፖርት እንዲያደርጉ ማድረግ … ለአብነስ መጥቀስ ይቻላል፡፡ በአዋጁ መሰረት መመሪያዎች ከመውጣታቸዉ በፊትም ይህንን ድጋፍ መስጠት ጀምረናል፡፡ መንግስት ጉዳዩን በትኩረት ነው የሚመለከተው፡፡

ለምን ቢባል፣ ጥቂት ገንዘብ ያላቸው ሠዎች በጋራ ትልቅ ሥራ በመስራት ውጤታማ ይሆናሉ ብሎ ያምናልና፡፡ የአክሲዮን ባለ ድርሻ የሆኑ በርካታ ሰዎች የሚያነሱት ቅሬታ አለ፡፡ አንዳንድ አክሲዮን አደራጆች በቃላቸው መሰረት ስራውን አያከናውኑም፡፡ ለምሳሌ በዚህ አመት አስፈላጊውን የአክሲዮን መጠን ሸጠን ወደ ስራ እንገባለን ይላሉ፡፡ ነገር ግን ጊዜ ይፈጅባቸዋል፡፡ የአክሲዮን ማህበሩን ሳይቋቋም ይዳከማል፡፡ የአክሲዮን ማህበራት ያቀዱትን ያህል ገንዘብ ስላልሠበሠቡ አይቋቋሙም የሚል ህግ የለም፤ ይፍረሱ የሚል ህግም የለም፡፡ አባላት ከፈለጉ በሠበሠቡት ብር ተቋቁመው፣ ስራ መጀመርና ጎን ለጎን ተጨማሪ ገንዘብ እየሠበሠቡ መሄድ ይችላሉ፡፡

ካልፈለጉ ግን አለማቋቋም ይችላሉ፡፡ የአክሲዮን ገንዘብ ከሠበሠበ በኋላ በተለያየ ምክንያት ሳይቋቋም ቢቀር፣ በዝግ አካውንት የተቀመጠው ገንዘብ ለባለቤቶች ያለ ብዙ ጣጣ ይመለስላቸዋል? በባለ አክሲዮኖች ላይ የሚደርስ የገንዘብም ሆነ የሞራል ጉዳትስ እንዴት ይካካሳል? ሁለት ነገሮችን ለይተን እናስቀምጥ! አንደኛው ነጥብ፣ አክሲዮን መግዛት በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ስለዚህ ሠዎች አክሲዮን ለመግዛት ሲወስኑ፣ የማመዛዘን ሃላፊነት አለባቸው፡፡ አክሲዮኑ አዋጭ ነው? ህገ-ደንብ አለው? ባይሳካስ ምን መፍትሄ አለው? የሚሉ ጥያቄዎችን ማገናዘብና መወሰን ይጠበቅባቸዋል፡፡ ለምሣሌ ቀደም ሲል የተቋቋሙ የባንክ አክሲዮኖች ወዲያውኑ ውጤታማ ሆነዋል፡፡ አሁን እየተቋቋሙ ያሉ አክሲዮኖች ግን የስራ ዘርፋቸው ከባንክ ይለያል፡፡

ጥረትንና ትጋትን የሚጠይቁ፣ ውጤታማ ለመሆን ረጅም ጊዜ የሚያስፈልጋቸው ናቸው፡፡ ሲሚንቶ የሚያመርት ኩባንያ በአንድ ወር ውስጥ የሚቋቋም አይደለም፡፡ ከሶስት ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ሊያስፈልገው ይችላል፡፡ ገንዘቡን መሰብሰብ ምን ያህል ትጋትና ልፋት እንደሚጠይቅ መገመት የግድ ነው፡፡ የተወሠነውን ገንዘብ ከህዝብ ከሠበሠበ፣ ሌላውን ከልማት ባንክ ብድር፣ ቀሪውን ደግሞ ከውጭ ኩባንያ ጋር በመጣመር አሳካለሁ ብሎ ከተቋቋመ፣ እንደ ስራ ዘርፉ ባህርይ ውጤታማ ለመሆን ረዥም ጊዜ ሊወስድ ይችላል፡፡ ሌላው ቀርቶ፣ ግንባታው ራሱ አምስትና ስድስት አመት ሊፈጅ ይችላል፡፡ አንድ ባለአክሲዮን ከዚህ ዘርፍ በአጭር ጊዜ ውጤት ከጠበቀ ገና ከጅምሩ ተሳስቷል፡፡ ከረዥም ጊዜ በኋላ ከፍተኛ ትርፍ እንደሚያገኝ አረጋግጦ ነው መግባት ያለበት፡፡ ፈጣን የሆነ ትርፍና ውጤት የሚፈልግ ሰው፣ ምናልባት እንደ ባንክ ወደ መሳሰሉ ዘርፎች ማተኮር አለበት፡፡ ስለዚህ አክሲዮን የሚገዙ ሰዎች በመጀመሪያ የስራውን ባህርይ፣ የአጭርና የረዥም ጊዜ አዋጭነትና ትርፍ ማገናዘብ የባለአክሲዮኖች ሃላፊነት ነው፡፡

ሁለተኛው ነጥብ፣ አክሲዮን የሚያደራጁ ሰዎች በንግድ ህጉ ውስጥ በግልፅ የተቀመጠ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ አክሲዮን ማህበሩ ሳይቋቋም ቢቀር፣ አደራጆቹ ለእያንዳንዱ ባለ አክሲዮን ድርሻውን የመመለስ ግዴት አለባቸው፡፡ ገንዘቡ በተሰበሰበ በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ አክሲዮን ማህበሩ ካልተቋቋመ፣ አደራጆች ወለድ የመክፈል ግዴታ አለባቸው፡፡ ነገር ግን ህጉ ከአደራጆቹ ውጭ ለአክሲዮኑ አለመቋቋም ተጠያቂ የሚያደርጋቸው ሌሎች አካላት አሉ … አዎ፤ ለምሳሌ ማስታወቂያ ያወጡ ሚዲያዎች፣ ያሻሻጡ አካላት፣ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ድጋፍ ያደረጉ በሙሉ ተጠያቂ ናቸው፡፡ ህጉ የማስታወቂያ ድርጅቶችን ተጠያቂ ያደርጋል፡፡ ሌላው ቀርቶ ማስታወቂያ ያስተናገዱ ሚዲያዎችም ይጠየቃሉ፡፡ ለምን? ለምሳሌ አክሲዮን የሚያደራጁ ሰዎች መጥተው ማስታወቂያ ስራልኝ ይላሉ፡፡ የማስታወቂያ ድርጅቱ ይሰራላቸዋል፡፡ በቃ ይለያያሉ፡፡

ታዲያ በምን ሂሳብ ነው፣ የማስታወቂያ ድርጅት ተጠያቂ የሚሆነው? በጣም ጥሩ! አንድ አክሲዮን አደራጅ ማስታወቂያ ሊያስነግር ሲመጣ ከንግድ ሚኒስቴር ወይም ከመዝጋቢው አካል የተሰጠውን የፈቃድ ደብዳቤ ማየትና ማረጋገጥ፣ የሚዲያው ወይም የማስታወቂያ ድርጅቱ ድርሻ ነው፡፡ ይህን ሳያደርግ ዝም ብሎ የመጣለትን ሁሉ ተቀብሎ ማስታወቂያ ከሰራና ካሰራጨ ተጠያቂ ይሆናል፡፡ ይሄ ህጉ ነው፡፡ ደብዳቤውን ቢያይም ማስታወቂያው ተአማኒ መሆን አለመሆኑን ማረጋገጥ አለበት፡፡ ያለበለዚያ ማስታወቂያ ድርጅቱ ተጠያቂ ይሆናል፡፡ ህጉ ይህን ያህል በጣም የጠበቀ ነው፡፡ ነገር ግን በአደራጆች ዘንድ ይህንን ህጉን ያለመገንዘብ እጥረት አለ፡፡ ለምሳሌ የአንድ ሺ ብር አክሰዮን ለመግዛት ከ5 እስከ 9% የአገልግሎት ክፍያ ይጠይቃሉ፡፡ ታዲያ ይህ የአገልግሎት ክፍያ በምን ተግባር ላይ እንደዋለ በግልፅ የማስረዳት ሃላፊነት እንዳለባቸው አይገነዘቡትም፡፡ ኦዲት የማድረግ ግዴታዎች አሉ፡፡ በስፋት ከማይታወቁት የህጉ ነጥቦች መካከል አንዳንዶቹን ቢጠቅሱልኝ… ከአክሲዮን ማህበሩ አባላት አስር በመቶ የሚሆኑት ቅሬታ ካላቸው፣ ለመዝጋቢው አካል ቅሬታቸውን ያቀርቡና ንግድ ሚኒስቴር አሊያም ንግድ ቢሮ ኦዲተር ይሠየምላቸዋል፡፡

ከአባላት መካከል ሁለት ሶስተኛው፣ ጠቅላላ ጉባኤ ማስጠራት ይችላሉ፡፡ ነገር ግን በርካታ ባለአክሲዮኖች ህጉን ባለማወቅና የተቀመጡትን የቦርድ ዳይሬክተሮች እንደ ንጉስ በመቁጠር ችግራቸውን በሚዲያ፣ በግልና በሌላ መንገድ ነው ሲናገሩ የሚሠማው፡፡ ምን ያህል የአክሲዮን ማህበራት እንደተቋቋሙ፣ ስንቶቹስ እንደተሳካላቸው ወይም እንደፈረሱ ይታወቃል? በእኛ የመረጃ አውታር ውስጥ ከ762 በላይ አክሲዮን ማህበራት አሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ባንኮችን ጨምሮ ከአራት መቶ በላይ ማህበራት የማቋቋሚያ ፎርም ተሞልተዋል፡፡ የማቋቋሚያ ፎርም ተሞልቷል ሲባል፤ ተቋቁመዋል ማለት ነው? ተቋቁመዋል ማለት አንችልም፡፡ የንግድ ስም አጣርተው በምስረታ ላይ የሚገኙም አሉ፡፡ የተቋቋሙም አሉ፡፡ ተቋቁመው ስራ ጀምረው ዓመታዊ ሪፖርት እያቀረቡ የሚሄዱም አሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ምን ያህሉ ውጤታማ ናቸው የሚለውን ነገር ለማወቅ ገና ሥራው አልተሠራም፡፡

ግን እነዚህን ድርጅቶች ኦዲት እንድናደርግ በህግ ስልጣን ተሠጥቶናል፡፡ እርግጥ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ገና ራሱን እያደራጀ ስለሆነ አክሲዮን ማህበራትን ኦዲት ማድረግ አልጀመረም፡፡ እና ምን የተሰራ ነገር አለ? ችግሮች በተከሰቱባቸው ማህበራት ዙሪያስ መረጃቸው ምን ያህል ነው? ንግድ ሚኒስቴር ራሱን ችሎ ከተቋቋመ ገና ሁለት አመቱ ቢሆንም፤ የተጀመሩ ስራዎችና ጥረቶች የሉም ማለት አይደለም፡፡ የአክሲዮን ጉዳይ ትኩረት የሚሠጠው ጉዳይ መሆኑን እናውቃለን፡፡ ችግር ያጋጠማቸው ማህበራትን በተመለከተ የቀረበው ጥያቄ ላይ … ጉዳዩ ለህግ የተተወ ነው ብዬ በደፈናው አለፍኩት እንጂ ከዚያ ውጭ የሆኑ መረጃዎች ላይ መነጋገር እንችላለን፡፡ ለምሣሌ፤ “ሀገሬ ኮንስትራክሽን” … ለመፍረስ ጉዳዩ በፍርድ ቤት እንዳለ እናውቃለን፡፡ ሙሉ መሶብ ፉድስ አክሲዮን ማህበር … በባለአክሲዮኖቹ መካከል ችግር ተፈጥሮ ነበር፡፡ ነገር ግን እኛ ለማግባባት ጥረን ሥራቸውን እንደቀጠሉ እናምናለን፡፡ ጃካራንዳ የተባለው አክሲዮን ማህበር፣ በባለአክሲዮኖቹ መካከል ትልቅ ረብሻ ቢኖርም ማህበሩ ግን ውጤታማ ነው፡፡

እርግጥ ባለአክሲዮኖች ተጨቃጭቀዋል፣ ፍርድ ቤት ድረስ ሄደዋል፡፡ እኛም የራሣችንን አስተያየት ሠጥተናል - ፍርድ ቤትም የራሱን ውሳኔ ወስኗል፡፡ ይህ ሁሉ ሆኖ ድርጅቱ በሥራው ውጤታማ ነው፡፡ ብዙ የተለያየ ባህሪና ባህል ያላቸው ሠዎች አንድ ላይ በሚሠሩበት ጊዜ ውዝግብ ሊያጋጥም የሚችል ነው እንላለን፡፡ ውጤታማ አልሆንም ብለው በግልፅ የፈረሱ ማህበራት የሉም፤ ሪፖርት የተደረገልንም የለም፡፡ ምክንያቱም መዝጋቢው አካል አውቋቸው የተቋቁሙና የፈረሱ እስካሁን አላጋጠሙም፡፡ አንድ አክሲዮን ማህበር ለመፍረስ ምን ምን ሂደቶችን ማለፍ ይጠበቅበታል? ለዚህም ግልፅ ህግ ተቀምጦለታል፡፡ በመጀመሪያ አባላት ተሠብስበው ቃለ-ጉባኤ ማፅደቅና የሠነዶች ማረጋገጫ ሄደው መፈረም አለባቸው፡፡ ከዚያም ለመፍረስ ስለመወሠናቸው ቢያንስ ሶስት ጊዜ በጋዜጣ ላይ ማስታወቂያ ማውጣት ይኖርባቸዋል፡፡ ይህ የሚሆንበት ምክንያት እንዳይፈርስ ፍላጐት ያለው አካል ካለ አቤቱታ የማቅረብ እድል እንዲያገኝ ነው፡፡ ይህን ህግ ተከትለው በእኛ በኩል ፈርሠዋል የምንላቸው የሉም፡፡

ነገር ግን በህጋዊ መንገድም ባይሆን የፈረሱ ይኖራሉ፡፡ ለምሣሌ ቦርዱ ስራውን የማያከናውን፣ አባላቱ በስብሠባ የማይገናኙና በአክሲዮናቸው ላይ የማይመክሩ እንዲሁም ዓመታዊ ሪፖርት የማያቀርቡም ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ግን አቶ ኑረዲን፣ የበርካታ ማህበራት ምስረታ እየተጀመረ ሳይቋጭ ይቀራል፤ በአንድ ሠሞን ግርግር ተፈጥረው ደብዛቸው የጠፋ በርካቶች ናቸው፡፡ የፈረሠ የለም ካሉኝ ጋር አልጣጣም ስላለኝ ነው … ቅድም እንዳልኩት፣ በራሣቸው መንገድ ችግሮች ተፈጥረው ሥራ ያቆሙ፣ እርስ በእርስ የሚነታረኩ፣ ብር ሠብስበው ወዳልተፈለገ አቅጣጫ በመዞር ባለአክሲዮኖችን የሚያማርሩ የሉም አይደለም፡፡ በህጉ መሠረት ሲፈርሱ ነው ፈረሱ የምንለው፡፡ ባለ አክሲዮኖችም ችግር ሲፈጠር ለመዝጋቢው አካል አሣውቀው ኦዲተር እንዲሰየምላቸው፣ ጠቅላላ ጉባኤ አስጠርተው መቀጠልም መፍረስም ይፈልጉ እንደሆን የመወሠን መብት እንዳላቸው አያውቁም፡፡

ይሄ ህጉን ያለመረዳት ችግር ነው በየቦታው የሚያማርራቸው፡፡ እስካሁን ውጤታማ ሆነዋል የሚሏቸው የአክሲዮን ማህበራት እንደ ምሣሌ የሚያነሷቸው ካሉ … በርካቶች ናቸው፡፡ ለምሣሌ 18 ያህል ውጤታማ ባንኮችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ የአክሲዮን ማህበር ባንኮች ናቸው፡፡ የባንኮቹ እህት ሆነው የሚመሠረቱ ኢንሹራንስ ኩባንያዎችም ውጤታማ ናቸው፡፡ በአግሮ ኢንዱስትሪም ጃካራንዳን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ኢሌምቱን ስንመለከትም በውጤታማ ስራ ምርቶቻቸውን ለገበያ እያቀረቡ ነው፡፡ በመኖሪያ ቤት ግንባታ በርካታ አክሲዮን ማህበራትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ እነዚህን እንደ ምሣሌ ስናስቀምጥ አንዳቸው ከአንዳቸው በልጠው አይደለም፡፡ ሁሉም አክሲዮን ማህበራት ህጉን ጠብቀው እየሄዱ ነው የሚል እምነት ስላለን ነው፡፡

በዱሮ ዘመን፤ ከዕለታት አንድ ቀን፤ በአንድ አካባቢ የሆነው ታሪክ ዛሬ እንደ ተረት ይወጋል፡፡ ወቅቱ ጅብ በጣም የሚፈራበትና ከሰው ጋር እየተጋፋ ገና በደምብ ሳይመሽ የሚመጣበት፣ በረት የሚሰብርበት፣ አጥር የሚጥስበት ነበር ይባላል፡፡ ከዚህም አልፎ ተርፎ ቤት ውስጥ እስከመግባትና ሰው እስከመብላት ደርሶ ነበር አሉ፡፡ በዚያን ዘመን ቀኛዝማች ቢሰውር የሚባል አንድ ክፉ ሹም ነበር ይባላል፡፡ ማዕረጉም የአካባቢው ምክትል ሹም ነው፡፡ ከወንድነት ይልቅ ትዕቢተኛነት? ከአስተዳዳር ችሎታ ይልቅ በጨካኝነት ሰዎችን የመግፋትና የማሰቃየት፣ ከመስጠት ይልቅ የመንጠቅና የመዝረፍ ባህሪ የተጠናወተው የአምባው ምክትል ሹም ነው፡፡ አንድ ማታ ቤቱ አውሬ ገባ፡፡ ቀኛዝማች ቢሰውር ከሚስቱ ጋር እንደተኛ ነው፡፡ ያ ህይወት ያለው የእንስሳ ሸክም እላያቸው ላይ ተከመረ፡፡ የቀኛዝማች ሚስት ነቅታ ብሩክታዊትን ከዘንዶ እንዳዳነ ሁሉ ባሏ ካላዳናት መበላታቸውን ተገንዝባ እንስሳው ሳይሰማ ባሏን ጐሸም ታደርገዋለች፡፡

ባል ሆዬ እንዳልሰማ ጭጭ ይላል፡፡ ደገመችና ጐሸም አደረገችው፡፡ ቀኛዝማች ምኑ ሞኝ ነው እንቅልፍ ድብን አድርጐ እንደወሰደው ሁሉ ፀጥ! ሚስት ፍርሃቱም እያየለ መጣና በጣም ጐነተለችው፡፡ ይሄኔ ባል ልምዝግ አድርጐ ቆነጠጣትና፤ “አርፈሽ ተኚ!” ይላታል፡፡ እንቅልፍ በዐይናቸው ሳይዞር ያንን አውሬ እንደታቦት ተሸከሙት፡፡ ነጋና የጠዋት ብርሃን በበሩ ቀዳዳ ገባ፡፡ እንደምንም ብርድ ልብሱን ገልጠው ሲያዩ ከቤት ለመውጣት በሩን እየገፋ ያለው ለካ አንድ በመንደሩ በአውደልዳይነቱ የሚታወቅ ትልቅ ውሻ ነው! ሚስት ከት ብላ ሳቀች! “አይ ወንድ! አይ ጀግና ባል! አይ ማዕረግ!” እያለች የምፀት ሳቋን ማቆም አቃታት፡፡ “እኔኮ ውሻ መሆኑን በፊትም አውቄዋለሁ!” አለ ባል ቢሰውር - የምንተፍረቱን፡፡ የቢሰውር ሚስት ጠዋት ከአንዲት ውድ ሚስጥረኛ ጓደኛዋ ጋር ደጅ ሲወጡ የሆነውን ሁሉ አጫወተቻት፡፡ ወዲያው መንደሩጋ ወሬው ተዳረሰ፡፡ አገሩ አወቀ፡፡

ቢሰውር የአገር መሳቂያ ሆነ! ወትሮም አገር ይጠላው የነበረው ቀኛዝማች ቢሰውር በየቤተክርስቲያኑ፣ በየገበያው፣ በየእድሩ፣ በየሰንበቴው ሰው ፊት መቆም የሰውን ዐይን ማየት አቃተው፡፡ ተረቡ፣ ሽሙጡ፣ አሽሙሩ፣ ውስጠ-ወይራው መቆሚያ መቀመጫ አሳጣው፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ ሹመቱን የሰጡት ንጉሥ ከሰሙ ሊከተል የሚችለውን በማሰብ ሥጋት ገደለው፡፡ ስለምንም ሲወራ የሱ ታሪክ እየመሰለው መበርገግ ሆነ ሥራው! እረኛ እንዲህ ሲል ዘፈነ፡- አህያ መጣች ተጭና እንሥራ አያ ቢሰውር ውሻ አስፈራራ፡፡ አህያ መጣች ጢሻ ለጢሻ ወንዱ ቢሰውር አዘለ ውሻ!!” ሰውም አውቆ ንጉሥ እንደሰሙ እያረገ በአሽሙር እየነገረ ያስበረግገዋል፡፡ ቀኛዝማች ቢሰውር አንድ ምሽት ከቤቱ በታች ባለ ወርካ ላይ በጠፍር ራሱን ሰቅሎ ተንጠልጥሎ ተገኘ! *** የገዛ ጭካኔያችን ሰለባ ከመሆን ያድነን፡፡

ከሹመት ጀግንነት ይሰውረን! እላያችን ላይ የሚከመር ጅብ መሳይ ውሻን የመሰለ ፈታኝ ወቅት አያምጣብን፡፡ “አረረም መረረም ማበሬን ተወጣሁ!” ከሚል እሳቤ ያውጣን፡፡ ስለስብሰባ ብዙ ተበሏል፡፡ “ስብሰባዎች በአስመስጋኝ ሁኔታ ማጠር አለባቸው፡፡ ለዚህ ዘዴው ተሰብሳቢዎቹ (meetes) ቆመው እንዲሰበሰቡ ማድረግ ነው፡፡ በመጀመሪያ አያምኑም፡፡ ከዚያ በኋላ ትዕግሥታቸው ያልቅና ጥለው ለመሄድ ይቀላቸዋል” ይለናል ሮበርት የተባለ የንግድ መሀንዲስ፡፡ ሩሲያዊው ፀሀፊ ብላዲሚር ቮይኖቪች “ስብሰባ ማለት፤ በርካታ ሰዎች አንድ ላይ ታድመው፤ አንዳንዶች የሚያስቡትን ነገር የማይናገሩበት፤ አንዳንዶች ደግሞ በእርግጥ የሚሠሩትን የማይናገሩበት መድረክ ማመቻቸት ነው” ይለናል፡፡

ከዚህ ያውጣን! የአሜሪካን ኮሜዲያን ደግሞ “ኮሚቴ ማለት በየግላቸው ምንም ለመሥራት የማይችሉ ሰዎች በቡድን ሆነው ምንም ሊሠራ እንደማይቻል ለመወሰን የሚሰበሰቡበት መድረክ ነው” ይለናል፡፡ ከዚህም ይሰውረን፡፡ ሮስፔሮት የተባለ ፖለቲከኛ ደግሞ “እኔ የመጣሁበት አካባቢ እባብ ስታይ ግደለው ነው የሚባለው፡፡ ጄኔራል ሞተርስ ኩባንያ ውስጥ ግን፤ እባብ ስታይ መጀመሪያ ማድረግ ያለብህ ስለ እባብ የሚያማክር ባለሙያ (Consultant) መቅጠር፡፡ ከዚያም ስለ እባብ ዓመት ሙሉ ማውራት ነው!” ይለናል፡፡ ይሄንንማ አይጣልብን፡፡ “ተሰበሰቡ ተሰበሰቡና ያንኑ ነገር ደጋግመው አውርተው፤ ቀና ቀና ያሉት ጐብጠው፤ ጐልማሶቹ አርጅተው ደማቸው ተንዠርግጐ መቋሚያ ይዘው ከጐባኤው አዳራሽ ወጡ” ይለናል የፈረንሣይ ኮሜዲያን፡፡

አንዳንዴ ምነው አለምን የሚመሯት ኮሜዲያን በሆኑ ያሰኛል፡፡ “አሁንስ ህይወት የተራዘመ ስብሰባ መሰለችኝ” ይላል ደራሲ በአሉ ግርማ፤ የዌልሹ ፀሀፊ-ተውኔት ግዋይን ቶማስም “አባዬ ኑሮዬኮ ስብሰባ ነበረ፡፡ አሁንማ የሌለሁበት ኮሜቴ አጀንዳዎች እንደው በመንገድ ሳልፍ እንኳ ይጠቅሱኛል!” ይለናል፡፡ ፍሬያማ ካልሆኑ ስብሰባዎች ያድነን፡፡ ለጉባኤ ስንሰበሰብ ጠቅለል ባለ አገላለፅ ልብ ማለት ያለብን የፖለቲካዊ አሰርቱ - ቃላት ሀሳቦች አሉ፡፡ “አይ መሬት ያለ ሰው! እኔ ዘንድ ሆነህ ባየኸው!” አንዱ ነው፡፡ “የዘመድ ቄስ እየፈታ ያለቅስ!” ሁለተኛው ነው፡፡ “የዘመድ ሞኝ ከልጅህ እኩል አርገኝ አለ” ሦስተኛው ነው፡፡ “እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው!” አራተኛው ነው፡፡ “ዱታ ነኝ ብሎ ለያዥ ለገራዥ ማስቸገር ኋላ ማጣፊያው እንዲያጥር ያደርጋል፡፡

ፉሎው ሲወልቅለት ጊዜ፤ ማን ይቻለው? እንዳይባል እንደፈረስ ሁሉ ልጓም ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ሁሉም በእኩል ዐይን ይገምገም፡፡” ይሄ አመስተኛው ነው፡፡ “ጠላት ናቸው ስንቀርባቸው የእኛው ናቸው” ስድስተኛው ነው፡፡ “ችላ እንዳትባል፣ መቼም ወላድ ናት እንዳይደግፏት፣ የረከሰች ናት ውሻ የት ትግባ፣ ምጥ ሲያጣድፋት?” የሚለውን የኦሮሚኛ አባባል አንርሳ የሚለው፡፡ ሰባተኛው ነው፡፡ እንደ ጥንቱ ምንዝር ለአለቃ፣ የበታች ለበላይ የሚያመጣው፣ የጫንቃ ጠላ የለም፤ ብሎ ከልብ ማመን ስምንተኛው ነው፡፡ “ድንበር ጠብቅልኝ አልኩ እንጂ ሚስቴን ጠብቅ ብዬሃለሁ ያለውን ባላገር ብሶት አለመርሳት ዘጠነኛው ነው፡፡ “ሸክላ ሲሰበር ገል ይሆናል፡፡ ሹሞችም ሲሻሩ ተራ ህዝብ ናቸው” ይሏልና ከሥልጣን መሰናበት ከሀገር መሰናበት አይደለም የሚለው ዘጠነኛው ነው፡፡ ዐሰርቱ ቃላትን በልቦናችን ያሳድርብን!! “የፊተኛውን ባልሺን በምን ቀበርሺው? በሻሽ፡፡ ምነው ቢሉ? የኋለኛው እንዳይሸሽ!” የሚለው ብርቱ ብሂል በፊተኛውም ሆነ በኋለኛው ጉዳያችን ላይ ዐይናችሁን ክፈቱ ይለናልና ሁሉንም ልብ እንበል!!

እስካሁን የተሳካው ምንድነው? ገበሬዎችን በ1ለ5 እየሰበሰቡ “የልማት ሠራዊት” ማደራጀት “የተፈጥሮ ሃብት ልማት” እያሉ ገበሬዎችን በዘመቻ መጥመድ ያልተሳካውስ ምንድነው? “ልማት” የሚባለው አልተሳካም። ትልልቅ ፕሮጀክቶች ተጓተዋል የገበሬዎች የእርሻ ምርት፣ የእቅዱን ግማሽ ያህል እንኳ አልተሳካምእንደኔ እንደኔ፣ የእድገትና የትራንስፎርሜሽ እቅዱ የታሰበውን ያህል እየተሳካ እንዳልሆነና፣ በታለመለት መጠን ሊሳካ እንደማይችል፣ ካሁኑ ቢነገር የሚሻል ይመስለኛል። አሁኑ “እቅጩን” ይነገረን የምለው፤ “እርማችንን እንድናወጣ” በሚል አይደለም። በተጨባጭ መረጃ ላይ በመመስረት እቅዱን መከለስና መስራት ይሻላል ለማለት ፈልጌ ነው። እቅዱ እየተሳካ እንዳልሆነና፣ በታቀደው መጠን ተግባራዊ ሊሆን እንደማይችል ብዙም አከራካሪ አይመስለኝም።

ግዙፎቹን ፕሮጀክቶች ተመልከቱ። ከሁሉም በላይ ትልቅ ትኩረት የተሰጠው የህዳሴ ግድብን መጥቀስ ይቻላል። በአምስት አመት ይጠናቀቃል የተባለው የህዳሴ ግድብ፣ አሁን በሚታየው ሁኔታ ከቀጠለ አስር አመት ሊፈጅ ይችላል። በሁለት አመት ውስጥ የተከናወነው ስራ 18 በመቶ ያህል ነውና። ሌሎቹ ትልልቅ ፕሮጀክቶችም ብንመለከት ከዚህ የተሻለ ውጤት አናገኝም። በአምስት አመቱ እቅድ ተገንብተው ስራ ይጀምራሉ የተባሉት 10 የስኳር ፋብሪካዎች፣ ገና በጣም ገና ናቸው። 10 አዳዲስ ፋብሪካዎችን ገንብቶ ለማጠናቀቅ ይቅርና፤ ከሰባትና ከስምንት አመት በፊት እቅድ ወጥቶላቸው ቢበዛ ቢበዛ በሶስት አመት ይጠናቀቃሉ ተብለው የነበሩት የስኳር ፋብሪካ ግንባታዎችና የማስፋፊያ ፕሮጀክቶችም እስካሁን ስራ አልጀመሩም።

በ1997ቱ የአምስት አመት እቅድ ውስጥ የተጀመረው የተንዳሆ ፕሮጀክት፣ የሸንኮራ ልማቱም ሆነ የስኳር ፋብሪካው ግንባታው ይሄው፣ ለ2002ቱ የአምስት አመት እቅድ ተሸጋግሮ አሁንም አልተጠናቀቀም። የመተሃራና የከሰም ፕሮጀክቶችም እንዲሁ እየተጓተቱና እየተሸጋገሩ የመጡ ነባር ፕሮጀክቶች ናቸው - በመጪው አመትም ስራ ይጀምራሉ ተብሎ አይጠበቅም። ሊጠናቀቅ ተቃርቧል የተባለው ነባሩ የወንጂ ስኳር ፋብሪካ ማስፋፊያ ፕሮጀክት እንኳ፤ በሚቀጥለው ወር፣ በሚቀጥለው የመንፈቅ አመት እየተባለ ስንት አመት አስቆጠረ? ይሄው ዘንድሮም፤ በጥቅምት ወር ስራ ይጀምራል ከተባለ በኋላ፤ ስራው ተጓትቶ ለጥር ይደርሳል ተባለ። ከዚያ ወደ መጋቢት ተሸጋገረ።

አሁን ደግሞ ወደ ሰኔ ወይም ወደ ሃምሌ። መንግስት እነዚህ ነባር ፕሮጀክቶችን ማጠናቀቅ ሳይችል፤ ተጨማሪ 10 አዳዲስ የስኳር ፋብሪካዎችን መገንባት ይችላል ብላችሁ የምታስቡ ከሆነ፤ “ተአምር” የማየት ረሃብ ይዟችኋል ማለት ነው። ሌላኛው ትልቅ ፕሮጀክት የባቡር ሃዲድ ግንባታ ነው። ይሄኛውም ፈቅ አላለም። ከሁሉም በላይ፣ በጣም ተስፋ አስቆራጭ የሆነው ደግሞ የእርሻ ምርት ብዙም ሲያድግ አለመታየቱ ነው። በአማካይ በነፍስ ወከፍ ሲሰላ፣ የእርሻ ምርት በየአመቱ በ6% እንዲያድግ ነበር የታቀደው - በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ። የአምናው እድገት ግን፤ 2.5% ገደማ ብቻ ነው። የእቅዱ ግማሽ ያህል እንኳ አልተሳካም። መንግስትና ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ፣ ይህንን ያውቃሉ። በአምስት አመት ውስጥ ይተገበራል ተብሎ የወጣው “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ”፣ የታሰበውን ያህል እየተሳካ እንዳልሆነ ኢህአደግ በግልፅ ባይናገርም፣ የገበሬዎች ምርት የታሰበውን ያህል እያደገ እንዳልሆነ የሚክደው አይመስለኝም።

እንዲያውም፤ የኢህአዴግ ድርጅቶች ሰሞኑን ባካሄዷቸው ጉባኤዎች ጉዳዩ ተነስቷል። የእርሻ ምርት ላይ የሚታየው እድገት ዝቅተኛ እንደሆነ በኢህአዴግ ጉባኤዎች በየጣልቃው ጠቀስቀስ ተደርጎ ሲታለፍ ታዝባችሁ ይሆናል። ለምሳሌ ብአዴን በባህርዳር ባካሄደው ጉባኤ ላይ፤ “የአምናው የእርሻ ምርት እንደተጠበቀው አይደለም” ተብሏል። በሃዋሳው ጉባኤ ደግሞ፣ “የሰብል ምርት ላይ ድክመት አለ” ተብሏል። አሳሳቢነቱ፣ የአምና ምርት ከጠበቀው በታች መሆኑ ብቻ አይደለም። የዘንድሮው የመኸር ምርትም እንደተጠበቀው እንዳልሆነ የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ጥናት ያረጋግጣል።

እናም፣ በነፍስ ወከፍ ሲሰላ፣ የዘንድሮ የግብርና ምርት እድገትም እንደአምናው 2.5 በመቶ ገደማ ብቻ እንደሚሆን ይገመታል። ምን ለማለት ፈልጌ ነው? እንደሌሎቹ ዋና ዋና የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዶች ሁሉ፣ የእርሻ ምርትም የታቀደለትን ያህል እያደገ እንዳልሆነ ሊካድ አይችልም ለማለት ነው። በእርግጥ፣ ታዲያ በኢህአዴግ ጉባኤዎች ላይ ለምን በጨረፍታ ብቻ ተጠቅሶ ታለፈ? “አልተሳካልኝም” ብሎ መናገር አስጠልቶት ሊሆን ይችላል። በአራቱም ጉባኤዎች ላይ እጅግ ሲበዛ ተደጋግሞ የተነገረውስ ምንድነው? የኢህአዴግ ድርጅቶች በሙሉ በየፊናቸው ባካሄዱት ጉባኤ፤ በገጠርና በገበሬዎች ላይ ስኬታማ ውጤት እንዳስመዘገቡ ደጋግመው ገልፀዋል። የተመዘገበው ውጤት ግን የምርት እድገት አይደለም። እናስ ምንድነው? “በልማት ሠራዊት ግንባታ” እና “በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ” ዙሪያ እጅግ “አስደናቂ ውጤት” መመዝገቡን ነዋ የገለፁት።

አስደናቂውን ውጤት የሚያብራሩ “ድንቅ” መረጃዎችና ሪፖርቶችም ቀርበዋል። በመቶ ሺ እና በሚሊዮን የሚቆጠሩ ገበሬዎችን በ1ለ5 አደራጅተን ሰፊ “የልማት ሠራዊት” ገንብተናል ብለዋል የኢህአዴግ ድርጅቶች። በመቶ ሺ እና በሚሊዮን የሚቆጠሩ ገበሬዎችን ለ”ተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ” በዘመቻ አሰልፈናል ተብሏል። በእርግጥም “የልማት ሠራዊት” ተገንብቶ፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ገበሬዎች “ለተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ” ለበርካታ ቀናት በዘመቻ ሲሰማሩና በየእለቱ እየጨፈሩ ሲመለሱ የሚያሳዩ የኢቲቪ ዘገባዎችን ተመልክተናል። ግን ምን ዋጋ አለው? የ“ልማት” እና የ“ሃብት” ውጤት አልተመዘገበም። የኢህአዴግ ድርጅቶች የሚያቀርቡት፣ ያ ሁሉ አስደናቂ ውጤትና ሪፖርት፤ በገበሬዎች የእርሻ ወይም የሰብል ምርት ላይ ከወትሮው የተለየ ቅንጣት ለውጥ አላመጣም።

ምን አስታወስኩ መሰላችሁ? ከአምስት አመት በፊት ነጋ ጠባ እንሰማው የነበር የ“ውሃ ማቆር” መፈክር። በ“ውሃ ማቆር” ምን ያህል አስደናቂ ውጤት እንደተመዘገ ለማስረዳት ይቀርቡ የነበሩ ድንቅ ሪፖርቶችን አታስታውሱም? በየክልሉ ምን ያህል እልፍ አእላፍ ገበሬዎች፣ ውሃ ማቆሪያ ጉድጓድ እንደቆፈሩ፣ በላስቲክና በሲሚንቶ ጉድጉዱን እያበጃጁ እንደሆነ በዝርዝር የሚተነትኑ እልፍ ዘገባዎችና ሪፖርቶች ቀርበዋል - ያኔ ከአምስት አመት በፊት። ለውሃ ማቆር ዘመቻ ስንትና ስንት ሚሊዮን ብር እንደተመደበ፣ በመቶ ሺ እና በሚሊዮን የሚቆጠሩ ገበሬዎችም በዘመቻው እንደተሳተፉ… የሚያብራሩና የሚዘረዝሩ ሪፖርቶች ትዝ አይሏችሁም? ምን ያደርጋል! አገሪቱ በ’ውሃ ማቆር’ ዘመቻ እንደምትለወጥ የሚያበስሩ ድንቅ ሪፖርቶች ሲቀርቡና ሲደመጡ ከርመው፣ ወራት አልፈው አመታት ተተክተው… መጨረሻ ላይ ሲታይ፤ ምንም ጠብ የሚል ውጤት ጠፋ።

በቃ፤ በገበሬዎች ምርት ላይ ምንም የመጣ ለውጥ የለም ተባለ። የኋላ ኋላ፣ የፌደራል ባለስልጣናትና ከየክልሉ የመጡ ርዕሰ መስተዳድሮችና ከፍተኛ መሪዎች በተሰበሰቡበት ነው ፍርጥርጡ የወጣው። በእርግጥ በስብሰባው ላይ፣ እንደወትሮው ድንቅ የውሃ ማቆር ሪፖርቶችና ማብራሪያዎች ቀርበዋል። በዚህ መሃል ነው፣ አንድ ቀላል ጥያቄ ዱብ ያለው… “ግን በገበሬዎች ምርት ላይ ያመጣው ለውጥ ምንድነው?” የሚል ጥያቄ። ጥያቄውን ለፌደራልና ለክልል ከፍተኛ መሪዎችና ባለስልጣናት በአፅንኦት ያቀረቡት ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ ነበሩ። ከመነሻው “ውሃ ማቆር” የሚለው ሃሳብ የመጣው፤ የገበሬዎችን ምርት የማሳደግ አላማን ለማሳካት ነበር።

አሁን ግን፣ የተነሳንበት አላማ እየተረሳ፣ የውሃ ማቆሪያ ጉድጓዶችን የመቁጠርና የመደመር ነገር… ራሱን የቻለ አላማ እየሆነ መጥቷል ያሉት አቶ መለስ፤ ሥራው የገበሬዎችን ምርት ለማሳደግ በሚጠቅም መንገድ እየተሰራ ነው ወይ? የውሃ ማቆር ዘመቻው ወደ ገበሬው ኪስ ተጨማሪ ገቢ በሚያመጣ መንገድ እየተሰራ ነው ወይ? በማለት አጥብቀው ጠይቀዋል። በእርግጥ፤ የውሃ ማቆር ዘመቻውን በቀዳሚነት ያቀነቀኑት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሊሆኑ እንደሚችሉ የሚገምቱ ሰዎች አሉ። ነገር ግን፤ እዚህ ላይ ዋናው ቁምነገር፣ የሆነ እቅድ የታሰበለትን ውጤት እያስገኘ እንዳልሆነ በተግባር ሲታይ፣ ሳይረፍድበት ቆም ብሎ ማሰብ ማስፈለጉ ነው።

አለበለዚያ፣ ያሸበረቀ ሪፖርት ማዘጋጀትና የተንቆጠቆጠ መግለጫ ማቅረብ፤ በአንዳች ተአምር ወደ ምርት እድገትና ወደ ኢኮኖሚ እድገት እንዲቀየር እየተቁለጨለጩ መጠበቅ ይሆናል። የሆነ ሆኖ፤ “የውሃ ማቆር ዘመቻው ምን አይነት ተጨባጭ ውጤት አስገኘ?” በሚለው ጥያቄ አማካኝነት ነገሩ መቋጫ አገኘ። ከዚያ በኋላማ በየእለቱና በየሰዓቱ በሬድዮና በቲቪ ሲያሰለቸን የነበረው የውሃ ማቆር ነገር ድምፁ ጠፋ። በውሃ ማቆር ፋንታ፤ ባለፉት ሁለት አመታት በመንግስት ሚዲያ የሚቀርብልን የዘወትር ቁርስና እራት፤ “የልማት ሠራዊት ግንባታ” እና “የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ” በሚሉ ሃረጎች የተጥለቀለቁ “ድንቅ ሪፖርቶችና መግለጫዎች” ናቸው - የገበሬዎችን ምርት ለማሳደግ ይጠቅማሉ እየተባለ። ነገር ግን፣ የአምናውና የዘንድሮው ተጨባጭ የምርት መጠን ሲታይ፣ እነዚያ ድንቅ ሪፖርቶች፣ የገበሬዎችን ምርት ለማሳደግ እየጠቀሙ አለመሆናቸውን መገንዘብ ይቻላል።

በ1ለ5 የተደራጀ ገበሬና በየቀበሌው ለስራ ዘመቻ የተጠራ ገበሬ ምን ያህል እንደሆነ እየቆጠሩ “ድንቅ ሪፖርት” ማቅረብ… ራሱን የቻለ ትልቅ አላማ እየሆነ መጥቷል። ይሄ ግን አያዛልቅም። ገበሬዎችን በተፅእኖ አደራጅቶ በዘመቻ እንዲሰሩ ማድረግ፤ ወደ ገበሬዎቹ ኪስ ተጨማሪ ገቢ አያመጣም። እፍኝ የእህል ምርት ለማሳደግም አይጠቅምም፤ ገበሬዎችን ከእውነተኛው የምርት ስራ ከማስተጓጎል ያለፈ ጥቅም አያስገኝም። አሁን ያለው አንዱ አማራጭ፤ “የሠራዊት ግንባታ” እና “የሥራ ዘመቻ” ሪፖርቶችን እያሳመሩ በመጓዝ ያለመፍትሄ ውድቀትን መደገስ ነው። ሌላኛው አማራጭ ደግሞ፤ የአምስት አመቱ እቅድ እየተሳካ እንዳልሆነ በግልፅ ተናግሮ፤ በሌሎች የኢኮኖሚ መስኮች ላይ እንደሚታየው የመንግስት ገናናነት መልካም ውጤት እንደማያስገኝ ተገንዝቦ መፍትሄ መፈለግ ነው። ኢህአዴግ የትኛውን አቅጣጫ እንደሚመርጥ እስካሁን በግልፅ አይታወቅም።

‹‹ለእንዲህ ዐይነት ሰው ለምን ይህ ክብር ይሰጣል በሚል ከጣልያን መንግሥት ጋራ ተነጋግረናል›› - አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ‹‹እስር ቤት የገቡትን ሰዎች ያለአግባብ ያንገላቱትን፣ ቶርች ያደረጉትን በግለሰብ ደረጃ በሕግ እንጠይቃለን›› - አቶ ይልቃል ጌትነት በአበባየሁ ገበያው እና ዓለማየሁ አንበሴ ከመሠረታዊ ዴሞክራሲያዊ መብቶች አንዱ የኾነው ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ መብት ‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ ቅንጦት ነው›› በተባለበት ወቅት ላይ እንገኛለን፡፡ አባባሉ÷ ከተራ ዜጎች ሳይኾን አማራጭ የ[መንግሥታዊ] ሥልጣን/የኀይል ማእከል ከኾኑትና ለዴሞክራሲያዊነትና ሰብአዊ መብቶች መከበር እንቆማለን ከሚሉት የተቃውሞ ፖሊቲካ ፓርቲ አመራሮችና የሲቪክ ማኅበራት ክፍሎች አንደበት ሲደመጥ መስማት÷ የአፈናው የከፋ ገጽታ መልክ አውጥቶ አካል ገዝቶ እንድናየው ያደርጋል፡፡

አመራሮቹ÷ ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ መብት ጨርሶ መከልከሉ ከቶም ጥያቄ ሊኾንብን፣ ሊያነጋግረንና ሊያስገርመን አይገባም ሲሉን ግን የኹኔታውን ተስፋ አስቆራጭነት በጉልሕ ያረጋግጥልናል፡፡ አቶ ዐሥራት ኣብርሃም የአረና ለዴሞክራሲና ሉዓላዊነት ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊና የመድረክ የሥራ አስፈጻሚ አባል ናቸው፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ መብት ስለሚገኝበት ድቅድቅ ጨለማ አስመልክተው ሲናገሩ÷ ‹‹ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ መብት ማንም ሊከለክለው የማይችል ሕገ መንግሥታዊ መብት መኾኑን ጠንቅቀን እናውቃለን፡፡ ከ1997 ዓ.ም. ወዲህ ግን ይህ መብት በተግባር የተከለከለ ኾኖ እናገኘዋለን፡፡

በኛ በኩል ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ይቅርና አባሎቻችን በጽ/ቤት ደረጃ ከሚያካሂዱት ስብሰባ እንኳ ሲወጡ ጠብቀው እያሰሯቸው ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ሰላማዊ ሰልፍ ቅንጦት ነው የሚኾነው፤›› ይላሉ፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ሕገ መግሥታዊ መብት መኾኑን ጠንቅቀው ቢያውቁም ይህን መብት የመጠቀም ዕድል ማግኘት ግን አለመቻላቸውን አቶ ዐሥራት ኣብርሃም ይናገራሉ፡፡ መብቱ በሕግ እንጂ በተግባር የተፈቀደ አለመኾኑን ተገንዝቦ አርፎ ከመቀመጥ ውጭ መብቱን ለማስከበር ገፍተው የሄዱበት አጋጣሚ እንደሌለ የሚናገሩት አቶ ዐሥራት÷ ‹‹ሓላፊነት የሚወስድ ፓርቲና አመራር እስካለ ድረስ ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ መብትን መጠቀም ያስፈልጋል፤›› ይላሉ፡፡ ‹‹ክልክላውን የሚያደርገው አካል ርምጃውን ወደ እስር ከፍ ቢያደርገው ሁሉንም አካል ማሰር ስለማይችል በሂደት ሕግን ወደ ማክበር ሊመጣ ይችል ነበር፤›› የሚሉት አቶ ዐሥራት÷ መብት ለማስከበር የሚደረግ ትግል የምር መኾን እንዳለበት ያምናሉ፡፡

ትግሉ ደግሞ የኢሕአዴግን ባሕርይ ጠንቅቆ ከመረዳት በሚቀየስ ጠንካራና ሰላማዊ የመታገያ ስልት በማስቀመጥ እስከ መጨረሻው መሄድ ነው፡፡ የኢሕአዴግን አረንጓዴ መብራት እየተጠበቁ ብቻ በመንቀሳቀስ በተግባር ክልከላ የተደረገበትን የሰላማዊ ሰልፍ መብት ማስከበር እንደማይቻል የፓርቲው አመራር ያስረዳሉ፡፡ በሚልዮን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንን በግፍ ላስጨፈጨፈው ዓለም አቀፍ ወንጀለኛ ማርሻል ሩዶልፍ ግራዚያኒ መታሰቢያ በስሙ ሐውልትና መናፈሻ መሥራት÷ ‹‹የአባቶቻችንን መሥዋዕትነት የሚያራክስ ነው›› በማለት የተቃውሞ ድምፃቸውን ባሰሙ ዜጎች ላይ የደረሰውን እናውቃለን፡፡ የኢትዮጵያ ተቆርቋሪ የግል ተነሣሽነት ማኅበር፤ ሰማያዊ ፓርቲና ባለራእይ ወጣቶች ማኅበር በጋራ በመኾን በሕጋዊ መንገድ አሳውቀው ለማካሄድ ባቀዱት ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የወጡ ዜጎች ታስረዋል፡፡ ‹‹ይህ የአፈናው ዐይነተኛ ገጽታ ነው፤›› ይላሉ አቶ ዐሥራት፡፡ ‹‹የሰላማዊ ሰልፉ ሐሳብ የአገር ጉዳይ እንጂ የፖሊቲካ አጀንዳ እንደሌለው ግልጽ ነው፡፡ ሕዝብን የጨፈጨፉ ሰዎች ፍርድ ማግኘት ሲገባቸው ይባስ ብሎ መታሰቢያ ሊቆምላቸው አይገባም የሚለው ጉዳይ በሕግም በሞራልም የሚያስጠይቅ በመኾኑ አጀንዳነቱ የመንግሥት መኾን ነበረበት፡፡

አሁን ያለው መንግሥት የኢትዮጵያ መንግሥት ነኝ ብሎ ሃገር እያስተዳደረ ነው፡፡ ኢትዮጵያን የሚመለከት አጀንዳ እንደ አጀንዳ መደገፍ ነበረበት እንጂ በዚህ ጉዳይ ሰልፍ መከልከሉ፣ ከልክሎም የወጡትን ሰዎች ማሰሩ የሚገርም ነገር ነው፡፡›› በአቶ ዐሥራት እምነት÷ ኢሕአዴግ በሰላማዊ መንገድ ለሃገሪቱ ዲሞክራሲያዊነት ይጠቅማል በሚል እሳቤ የሕዝብን ጥያቄ አይቀበልም፡፡ ሰልፍ የሚያስወጡ በርካታ ጉዳዮች ቢኖሩም በተለይ ከ1997 ዓ.ም ወዲህ ሰልፍ ለማድረግ የሚያስችል አበረታች ነገር የለም፡፡ ስለዚህም ፖሊቲካዊ በኾኑ ጉዳዮች ላይ ሰልፍ የማድረግ መብትን እስከ መጨረሻው አሟጦ ከመጠቀም አንጻር ፓርቲዎች ብዙ መሥራት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ‹‹መብቱ የሚፈቅድለትን ያህል ለመጠቀም ታግሎ ለመታሰር ዝግጁ የኾነ የፖለቲካ አመራርና አባል መኖር አለበት፤›› የሚሉት አቶ ዐሥራት÷ ‹‹ማንም የራሱን መብት ማስከበር ካልቻለ ሌላ አካል መጥቶ መብቴን ያስከብርልኛል ማለት አይችልም፤›› ይላሉ፡፡ አሁን ያለው የዜጎች መብት ፅልመታዊ የኾነው በአደባባይ በሚታየው ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ ችሎታ አንጻር ብቻ ሳይኾን፣ ‹‹ፍርድ ቤት ሄጄ መብቴን አስከብራለኹ ማለትም ተስፋ አስቆራጭ ነው፡፡ ፍርድ ቤት አቤቱታ የማቅረብ መብት አለኝ በሚል ለመከራከር ቢሞከር ማስረጃ የለውም ተብሎ አቤቱታው ውድቅ ይኾናል፤›› ይላሉ አቶ ዐሥራት፡፡

‹‹ፍርድ ቤትን ብቸኛ አማራጭ አድርጐ መጠቀም የሚቻለው ነፃና ገለልተኛ መኾኑ የታመነበት የፍርድ ተቋም ሲኖር ነው፡፡ በኛ አገር እንደዚህ ዐይነቱ የፍርድ ቤት ተቋም እንደሌለ ደግሞ ይታወቃል፡፡›› አቶ ዐሥራት በመደራጀት፣ ሐሳብን በነጻነት መግለጽና ሰላማዊ ሰልፍ በማድረግ መብቶች መረጋገጥ ተስፋ የቆረጡ ይመስላሉ፡፡ መብትን ለማስከበር ጠንካራ ተፎካካሪ ፓርቲና ለመታገል የቆረጠ አመራር፣ አባላትና ሕዝብ ያስፈልጋል ባይ ናቸው፡፡ አለበለዚያ በተቃዋሚው በኩል÷ በየጊዜው መታፈንን ከማስተጋባት የዘለለ ፋይዳ የሌለው መብት የማስከበር ሥራ ሊሠራ እንደማይችል፣ ገዢው ፓርቲም የራሱን መቀመጫ ለማደላደል ሌት ተቀን ከመትጋት ውጪ ለሕዝብ መብት ደንታ ያለው ፓርቲ ሊኾን እንደማይችል የፓርቲው አመራር አረጋግጠው ይናገራሉ፡፡

የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀ መንበር አቶ ይልቃል ጌትነት÷ ‹‹የታላቋን ሃገር ኢትዮጵያ ታሪክ እየዘነጋን፣ በቀድሞ አባቶቻችን ደም ላይ እንደቆምን እየረሳን፣ ብሔራዊ ስሜት ከልጆቻችን ከትውልዶችም እየጠፋ ውሎ አድሮ አንድ ያደረገን ክር ሁሉ እየላላ ገመናችንን ለጠላቶቻችን እያጋለጥን ነው፡፡ አልፎ ተርፎ ደግሞ የእኛ ገዳዮች ብሔራዊ ጀግና ተብለው ሐውልት እየተሠራላቸው እኛ ምን ያህል ቁልቁል እየሄድን መኾኑን የሚያመለክት ነበርና ይህን መቃወም፣ አባቶቻችንን ማሰብ ስለነበረብን ይህን ለማስታወስ በሕገ መንግሥቱ ሰላማዊ ሰልፍ ስለማድረግ የሰፈረውን ተጠቅመን ለሚመለከተው አካል አሳውቀን ነበር ሰልፉን የጠራነው፡፡›› ይላሉ፡፡ ‹‹የ30 ሺሕ ሰዎች ደም ሳይገድበው መብታችንን የሚገፍ አካል ካለ፤ ይግፈፉን፤ ለዚያ ግን እኛ የመጨረሻውን ዋጋ ለመክፈል ዝግጁ ነን፤›› የሚሉት አቶ ይልቃል ቀጣይ አካሄዶቻቸውን ያመለክታሉ÷ ‹‹እስሩም ኾነ የሰላማዊ ሰልፍ ክልከላው በጉልበት የተደረገ ነው፡፡ እኛ ግን እስር ቤት የገቡትን ሰዎች ያለአግባብ ያንገላቱትን. ቶርች ያደረጉትን በግለሰብ ደረጃ በሕግ እንጠይቃለን፡፡

›› ‹‹የግራዚያኒ ሐውልት መቆሙ፣ መናፈሻ መሠየሙ አግባብ አይደለም›› የሚሉት ደግሞ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የውጭ ግንኙነት መምሪያ መምህር ሰሎሞን ቶልቻ ናቸው፡፡ በጉዳዩ ላይ የግል አስተያየታቸውን የሰጡን መምህሩ፤ ‹‹ታሪኩን የሚያውቅና ኢትዮጵያዊነቱ የሚቆረቁረው እያንዳንዱ ዜጋ በዋዛ የሚያየው ጉዳይ አይደለም፡፡ በሃገር ደረጃ የየትኛውም እምነት ተከታይ ይኹን ኢትዮጵያዊ ሁሉ ትላንት አባቶቻችንን፣ በምን ዐይነት ኹኔታ እንደጨረሰ፣ በቁም እንደቀበረ፣ ባካፋ ከርጉዝ ሴት ሆድ ፅንስዋን እያወጣ በአደባባይ የንጹሐንን ደም ያፈሰሰበት ነው፡፡ በሃገር ደረጃ ሁሉም ረጋ ባለ መልክ መክረው አንድ ውሳኔ ማስተላለፍ ይጠበቅባቸዋል፡፡›› ይላሉ፡፡ ‹‹ትላንት ባሳለፍነው የብፁዓን አባቶቻችን÷ አቡነ ጴጥሮስ እና አቡነ ሚካኤል÷ ደምና ሕይወት አንደራደርም፡፡ እንዲህ ዐይነት ሰው ለጣልያን ሕዝብና መንግሥት ሞዴል የሚኾነው ከምን አኳያ ነው፡፡

መልእክቱስ ምንድን ነው? እንደምንስ ዛሬ ሊነሣ ቻለ? መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው ብንልም በልማት፣ በሰላምና በጸጥታ፣ የሰው ልጆች በፍቅር ተከባብረው እንዲኖሩ፣ በመልካም አስተዳደር ዙሪያ ቤተ ክርስቲያናችን ከመንግሥት ጋራ በአጋርነት ትሰራለች፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የአገሪቱን ታሪክ በአደራ ተቀብላ አቆይታለች፡፡ በዩኔስኮ ደረጃ የተመዘገቡ የሦስት ሺሕ ዘመን መንፈሳዊና ቁሳዊ ቅርሶች ባሏት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ነው ያሉት፡፡ ጉዳዩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ብቻ የሚወሰን ሳይኾን መንግሥትንም ይመለከተዋል፡፡ ሲቪክ ማኅበራት፣ አባት አርበኞች፣ ተመራማሪዎችም ይኹኑ የሃገር መልካም ገጽታ ግንባታ የሚቆረቁራቸው ሁሉ አብረው ሊሰለፉበት ይገባል - እንደ መ/ር ሰሎሞን ቶልቻ፡፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ጉዳዩን የሚለከቱት ለየት ባለ መንገድ ነው፡፡ የግራዚያኒን ሐውልት ለመትከል የተንቀሳቀሰው የኅብረተሰብ ክፍል/ግለሰቦች÷ በጣሊያን መንግሥት ደረጃ ሳይኾን ከጣልያን ማእከላዊ መንግሥት ፍላጎትና ዕውቅና ውጭ በጣሊያን አንድ ግዛት ውስጥ የራሱ አስተዳደር ባለው አንድ አካባቢ የሚገኝ ነው፡፡ ይህ እንቅስቃሴ እንደተሰማ ከጣልያን መንግሥት ጋራ በዲፕሎማሲ ቻናል ተነጋግረናል፡፡ የፋሺዝም ታሪክ ያጠላበት የኢትዮ - ጣልያን ግንኙነት ሳንካ ሊገጥመው ይችላል፤ ፋሽዝም ደግሞ የኢትዮጵያም ብቻ ሳይኾን የጣልያን ሕዝብ ጠላት ነው፤ ለእንዲህ ዐይነት ሰው ለምን ይህ ክብር ይሰጣል በሚል ከጣልያን መንግሥት ጋራ ተነጋግረናል፡፡

የጣልያን መንግሥት እንደሚለው÷ ይህን ነገር ለማሠራት የተንቀሳቀሰው የኅብረተሰብ ክፍል በማእከላዊው መንግሥት አይታወቅም፤ እንቅስቃሴው የማእከላዊ መንግሥት አቋም አይደለም የሚል ምላሽ ነው ያገኘነው፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ መንግሥት ጉዳዩን በዝምታ አልተመለከተውም፡፡ በሁለት አገሮች መካከል እንዲህ ዐይነት ነገር ሲፈጠር ‹‹ሌጋሲዎን ዲፕሎማሲ›› የሚባል ነገር አለ፡፡ ዝም ብሎ አይነገርም፡፡ መጀመሪያ ውይይት ይደረጋል፡፡ ንግግርና መግባባት ይደረጋል፤ በሂደት ነው፡፡ ጉዳዩ የኢትጵያን ሕዝብ እንደሚያስቆጣ፣ የሁለትዮሽ ግንኙነቱንም እንደሚጎዳ በእኛ ኤምባሲ በኩል ለጣልያን መንግሥት ተገልጾልታል፡፡

አምባሳደር ዲና በመጨረሻም ‹‹ኅብረተሰቡ እንደ ኅብረተሰብ በተለያዩ መንገዶች የሚያደርጋቸው ሰላማዊ ሰልፎች፣ ፒቲሽኖችና ሌሎች የተቃውሞ ተጽዕኖዎች በመጨረሻ ወደምንፈልገው ውጤት ሊያመሩ ይችላሉ፤›› ካሉ በኋላ እንቅስቃሴውን እስከ መጨረሻው ድረስ ተከታትሎ የማስቆም ጥረቱ÷ የሁለቱን ሃገሮች የቆየ ጤናማ ግንኙነት በማይጎዳና ያለፈውን ጠባሳ በማይቀሰቅስ መልኩ እንደሚቀጥል አመልክተዋል፡፡ ከዲፕሎማሲያዊ ጥረቱ ውጭ በኅብረተሰቡ ደረጃ ተጋግሎ ስለቀጠለው የተቃውሞ እንቅስቃሴ የውጭ ጉዳይ ቃል አቀባዩ እንዲህ ይበሉ እንጂ ሕዝባዊውን ዲፕሎማሲ አስመልክቶ በተጨባጭ የታየው ግን ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ ሕገ መንግሥታዊ መብትን በተግባር የሚከለክል ርምጃ ነው፡፡ ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ የሕግ ባለሞያ እንዳሉት÷ ከምርጫ 97 ወዲህ የአንድ ዴሞክራሲያዊ አገር መለኪያዎች የኾኑት የመደራጀት፣ ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግና ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት መጀመሪያ ተራ በተራ በወጡት ሕጎችና ዐዋጆች ገደብ ተጣለባቸው፡፡

አሁን በመጨረሻ÷ ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ ሕገ መንግሥታዊ መብት ለገዢው ፓርቲ አጀንዳዎች ማስተጋቢያ ብቻ የተሰጠ እስከ መምሰል ደርሷል፡፡ ይህም በተቃውሞው ሰፈር ያሉት አካላት ‹‹የመተንፈስ መብት ተከለከልን›› እስከማለት ደርሰው ሲያሰሙት የነበረው ምሬት የተቀላቀለበት አቤቱታ መደምደሚያ ማረጋገጫ ኾኗል፡፡ የተከለከለው ሕገ መንግሥታዊ መብት - ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ ዴሞክራዊ መብት - ለኢትዮጵያውያን ቅንጦት ነው መባሉ እውነት ሳይኾን አይቀርም፡፡

የኢትዮጵያ ክለቦች በአፍሪካ ደረጃ በሻምፒዮንስ ሊግ እና በኮንፌደሬሽን ካፕ በተሳትፎ እና በውጤታማነት ከፍተኛ ደረጃ ከያዙት የአህጉሪቱ ክለቦች ተርታ ለመግባት ብዙ መስራት እንደሚጠበቅባቸው መረጃዎች አመለከቱ፡፡ ዘንድሮ በሁለቱ አህጉራዊ ውድድሮች ተሳታፊ የሆኑት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ወደ የምድብ ድልድል ለመግባት ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ ይህ ስኬት ለኢትዮጵያ ክለቦች የአፍሪካ ደረጃ መሻሻል አስተዋፅኦ እንደሚኖረው ይጠበቃል፡፡ በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ በመሳተፍ ላይ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ ነገ በአዲስ አበባ ስታድዬም በ2ኛ ዙር ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታውን ከማሊው ክለብ ዲጆሊባ ጋር ያደርጋል፡፡ በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌዴሬሽን ካፕ የሚሳተፈው ደደቢት በበኩሉ በ2ኛ ዙር ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታውን ከሜዳው ውጭ በመጓዝ ከሱዳኑ ክለብ አልሃሊ ሼንዲ ጋር ይጋጠማል፡፡

የኢትዮጵያ ክለቦች በአፍሪካ ትልልቅ የክለብ ውድድሮች በነበራቸው የተሳትፎ ታሪክ ከማጣርያ ምእራፍ አልዘለለም፡፡ የኢትዮጵያ ክለቦች በአፍሪካ ያላቸውን ደረጃ ለማሻሻልና ያለባቸውን የፋይናንስ ችግርን ለመቅረፍ በአህጉራዊ የክለብ ውድድሮች የምድብ ድልድል መግባት ያግዛቸዋል፡፡ ይህ ስኬት ለአምስት አመታት በሚዘልቅ ውጤት ሲያጠናክሩ በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን አሰራር መሰረት ነጥብ ያሰጣል፡፡ በአህጉራዊ ክለብ ውድድሮች በ3 ምእራፎች የሚደረጉ ማጣርያዎችን ለመቀነስም ወሳኝ ነው፡፡ በካፍ የውድድር አካሄድ መሰረት በሻምፒዮንስ ሊግ ሻምፒዮን መሆን አምስት ነጥብ፤ ሁለተኛ ደረጃ ማግኘት አራት ነጥብ፤ ግማሽ ፍፃሜ መግባት 3 ነጥብ፤ በምድብ ድልድል 3ኛ ደረጃ ማግኘት 2 ነጥብ እንዲሁም 4ኛ ሆኖ መጨረስ 1 ነጥብ ያስገኛል፡፡ በኮንፌደሬሽን ካፕ ደግሞ ሻምፒዮን መሆን አራት ነጥብ፤ ሁለተኛ ደረጃ ማግኘት ሶስት ነጥብ፤ ግማሽ ፍፃሜ መግባት 2 ነጥብ፤እንዲሁም በምድብ ድልድል 3ኛ እና 4ኛ ሆኖ መጨረስ 1 ነጥብ ያሰጣል፡፡ በሁለቱ ውድድሮች በአምስት የውድድር ዘመናት በሚገኝ ውጤት የሚገኘው ድምር ነጥብ በአፍሪካ እስከ 12ኛ ደረጃ ካስያዘ በየውድድሮቹ ከአንድ በላይ ክለቦችን ለማሳተፍ ያስችላል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ ከካፍ የሽልማት ገንዘብ ክለቦቹም ሆነ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ድርሻቸውን ያስገኝላቸዋል፡፡ በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ ላይ ለምድብ ድልድል መድረስ ለክለብ ብቻ ሳይሆን ለሚወክለው ፌደሬሽንም የገንዘብ ጥቅም አለው፡፡ አንድ ክለብ በኮንፌደሬሽን ካፕ ሻምፒዮን ለመሆን ሲበቃ 625ሺ ዶላር ሲያገኝ የወከለው ፌደሬሽን 35ሺ ዶላር ይታሰብለታል፡፡ በሁለተኛነት ለክለቡ 432ሺ ዶላር ለፌደሬሽኑ 30ሺ ዶላር፤ በምድብ ሁለተኛ ሆኖ መጨረስ ለክለቡ 239ሺ ዶላር ለፌደሬሽኑ 25ሺ ዶላር፤ በምድብ በ3ኛ ደረጃ መጨረስ ለክለቡ 239ሺ ዶላር ለፌዴሬሽኑ 20ሺ ዶላር እንዲሁም በአራተኛ ደረጃ መጨረስ ለክለቡ 150ሺ ዶላር ለፌደሬሽኑ 15ሺ ዶላር ያስገኛል፡፡ በሌላ በኩል የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ከሽልማት ገንዘብ ለፌደሬሽኖች ድርሻ ባይኖርም ለየአገሩ ክለቦች ደረጃ ማደግና ለተጨዋቾቻቸው የፕሮፌሽናል እድል በመፍጠር ከፍተኛ ሚና አለው፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ ሻምፒዮን በመሆን ዋንጫ የሚያነሳ ክለብ በሽልማት 1.5 ሚሊዮን ዶላር ከማግኘቱም በላይ በዓለም ክለቦች ዋንጫ አፍሪካን ወክሎ መሳተፍ እድል ይችላል፡፡ በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ በሁለተኛነት ደ 1 ሚሊዮን ዶላር፤ ለግማሽ ፍፃሜ በመድረስ 700ሺ ዶላር፤ በምድብ 3ኛ ደረጃን ይዞ መጨረስ 500ሺ ዶላር እንዲሁም በአራተኛ ደረጃ ማጠናቀቅ 400ሺ ዶላር ያስገኛል፡፡

በ2013 የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች ደረጃ ላይ ለፓሪስ ሴንትዠርመን የሚጫወተው ዴቪድ ቤካም በ175 ሚሊዮን ፓውንድ የሃብት መጠን አንደኛ ሆነ፡፡ የባርሴሎናው ሊዮኔል ሜሲ በ115.5 ሚሊዮን ፓውንድ እንዲሁም የሪያል ማድሪዱ ክርስትያኖ ሮናልዶ በ112 ሚሊዮን ፓውንድ ሃብታቸው ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ ብራዚላዊው ካካ በ66 ሚሊዮን ፓውንድ፤ ሮናልዲንሆ በ63 ሚሊዮን ፓውንድ፤ የራሽያው አንዚ ማቻካላ ተጨዋች የሆነው ሳሙኤል ኤቶ በ52 ሚሊዮን ፓውንድ፤የማን ዩናይትዱ ዋይኔ ሩኒ በ50 ሚሊዮን ፓውንድ፤ የፓሪስ ሴንትዠርመኑ ኢብራሞቪች በ47 ሚሊዮን ፓውንድ፤ ሪቫልዶ በ45.5 ሚሊዮን ፓውንድ፤ የማን ዩናይትዱ ሪዮ ፈርዲናንድ በ42 ሚሊዮን ፓውንድ የሃብት መጠናቸው ከአራት እሰከ 10 ያለውን ደረጃ ወስደዋል፡፡ የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች እስከ 50ኛ ያላቸውን ደረጃን በመስራት ከሳምንት በፊት ይፋ ያደረገው ታዋቂው የእግር ኳስ ዘጋቢ ድረገፅ ጎል ነው፡፡

ጎል የዓለም የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች ለመጀመርያ ጊዜ ለማዘጋጀት የቻለው ተጨዋቾች ያላቸውን በይፋ የሚታወቅ ሃብትና ንብረት፤ በተለያዩ ኩባንያዎች በሚያንቀሳቅሱት ገንዘብ፤ በደሞዝ ክፍያችው እና ቦነሳቸው እንዲሁም በማስታወቂያ እና በተለያዩ የንግድ ስራዎች የሚያገኟቸውን ገቢዎችን በማስላት ነው፡፡ በጎል ዶት ኮም የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች ተብለው እስከ 50ኛ ደረጃ የተሰጣቸው በአጠቃላይ የሃብታቸው ድምር 1.7 ቢሊዮን ፓውንድ ነው፡፡ በደረጃው ላይ ከሚገኙ ተጨዋቾች 22 በመቶ ያህሉ የእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ሲሆን የተቀሩት ከ18 የተለያዩ አገራት የተውጣጡ ናቸው፡፡ ስምንት ፈረንሳዊያን፤ 6 ጣሊያናዊያን፤ 5 ስፔናዊያንና 5 ብራዚላውያን ገብተዋል፡፡ በደረጃው ሰንጠረዥ አራት ትውልደ አፍሪካዊ ተጨዋቾች አሉ፡፡

ባላቸው ሃብት እስከ 50ኛ ደረጃ ካገኙት ተጨዋቾች መካከል 37 ያህሉ እድሚያቸው ከ30 አመት በላይ ነው፡፡ ከ50ዎቹ ሃብታም የእግር ኳስ ተጨዋቾች የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ከ25 በላይ ተጨዋቾች አስመዝግቦ 50 በመቶ ድርሻ ይዟል፡፡ የስፔኑ ላሊጋ በ46 በመቶ፤ የጣሊያኑ ሴሪኤ በ42 በመቶ፤ የፈረንሳዩ ሊግ 1 በ24 በመቶ እንዲሁም የጀርመኑ ቦንደስ ሊጋ በ12 በመቶ ድርሻ ተወክለዋል፡፡ በደረጃው የገቡት ተጨዋቾች ከ10 በላይ ትልልቅ ዋንጫዎችን በአገር ውስጥ የሊግ ውድድርና በአህጉር ደረጃ ያገኙ ሲሆን 80 በመቶ ያህሉ በአማካይ እና አጥቂ መስመር የሚሰለፉ ናቸው፡፡ ከ50ዎቹ ሃብታም የእግር ኳስ ተጨዋቺች 26 በመቶው ለሪያል ማድሪድ፤22 በመቶ ለቼልሲ፤ 18 በመቶ ለኤሲ ሚላን፤ 16 በመቶ ለባርሴሎና እና ለማን ዩናይትድ እንዲሁም 14 በመቶ ያህሉ ለጁቬንትስ ክለብ ተጫውተዋል፡፡

58ኛው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ወደ ሩብ ፍፃሜ ምእራፍ ሲሸጋገር የውድድሩ የሃይል ሚዛን እንግሊዝን ሸሽቶ ለስፔንና ጀርመን ክለቦች እያጋደለ መምጣቱ ተረጋገጠ፡፡ ዘንድሮ ለሩብ ፍፃሜ የበቁት ስምንት ክለቦች ከአምስት አገራት የተውጣጡ ሲሆኑ ፤ ሶስቱ የስፔን ክለቦች ሪያል ማድሪድ፣ ባርሴሎና እና ማላጋ፤ ሁለት የጀርመን ክለቦች ባየር ሙኒክና ቦርስያ ዶትመንድ እንዲሁም የጣሊያኑ ጁቬንትስ፤ የቱርኩ ጋላታሰራይ እና የፈረንሳዩ ፓሪስ ሴንትዠርመን ናቸው፡፡

ከ17 አመታት በኋላ የእንግሊዝ ክለቦች ሳይወከሉ ቀርተዋል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ ባለፉት 13 አመታት በነበሩት የውድድር ዘመናት የጣሊያን ክለቦች በ2001፣ በ2002 እና በ2009 እኤአ፤ የጀርመን ክለቦች በ2003፣ በ2004 እና በ2008 እኤአ፤ የስፔን ክለቦች በ2005 እኤአ በሩብ ፍፃሜ ለመግባት አልሆነላቸውም ነበር፡፡ የአርሰናሉ አሰልጣኝ አርሴን ቬንገር የእንግሊዝ ክለቦች የበላይነት በስፔን ላሊጋ እና በጀርመን ቦንደስ ሊጋ ክለቦች እየተሸረሸረ መምጣቱን እንደሚያሳይ ሲናገሩ ፤ የሪያል ማድሪዱ ጆሴ ሞውሪንሆ በበኩላቸው የእንግሊዝ ክለቦች ከአውሮፓ እግር ኳስ ሃያልነት ርቀዋል ለማለት ጊዜው ገና ነው ብለዋል፡፡

ለዋንጫው ድል ሁለቱ የስፔን ክለቦች ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና ከፍተኛ ግምት ሲኖራቸው የጀርመኑ ባየር ሙኒክ ተፎካካሪ ነው፡፡ የቱርኩ ክለብ ጋላተሳራይ በቀድሞ ክለባቸው የሻምፒዮንስ ሊግ ድልን ያጣጣሙትን አንጋፋዎቹን ዲድዬር ድሮግባ እና ዌስሊ ስናይደርን በመያዝ በታሪኩ ለመጀመርያ ጊዜ ለሩብ ፍፃሜ ስለበቃ ስኬታ ተብሏል፡፡ የጀርመኑ ቦርስያ ዶርትመንድ በአስደናቂ የቡድን መንፈሱ፤ የፈረንሳዩ ፓሪስ ሴንትዠርመን በተጠናከረ አቅሙ እንዲሁም የጣሊያኑ ጁቬንትስ በጠንካራው የተከላካይ መስመሩ ለዘንድሮው ሻምፒዮንስ ሊግ ማራኪ ገፅታ እንዳላበሱ ተወስቶላቸዋል፡፡ የጣሊያኑ ጁቬንትስ ከ7 አመታት በኋላ፤የጀርመኑ ቦርስያ ዶርትመንድ ከ15 አመታት በኋላ እንዲሁም የፈረንሳዩ ፓሪስ ሴንትዠርመን ከ18 አመታት በኋላ ለሩብ ፍፃሜ መብቃታቸው ነው፡፡

ባለፉት ሶስት አመታት በሻምፒዮንስ ሊጉ ሲደበዝዝ የቆየው የእንግሊዝ ክለቦች ተፎካካሪነት ዘንድሮ በጥሎ ማለፍ ምእራፍ ማብቃቱ የፕሪሚዬር ሊጉ የበላይነት ሙሉ ለሙሉ ማክተሙን አሳይቷል፡፡ እንግሊዝን በመወከል ተሳታፊ ከነበሩት 4 ክለቦች መካከል ማን ሲቲ እና የአምናው የሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊ ቼልሲ የተሰናበቱት ከምድብ ማጣርያው ነበር፡፡ ማን ዩናይትድና አርሰናል ደግሞ ሩጫቸው በጥሎ ማለፍ ምእራፍ አብቅቷል፡፡ ዘ ጋርዲያን በሰራው አሃዛዊ ስሌት መሰረት በዘንድሮ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የእንግሊዝ ክለቦች አሸናፊነት በአራተኛ ደረጃ የሚመደብ ሆኗል፡፡ በአሸናፊነት ግንባር ቀደም የሆነው የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ54 በመቶ ውጤታማነቱ ነው፡፡ የስፔኑ ላሊጋ በ53 በመቶ ፤የጣሊያን ሴሪኤ በ50 በመቶ ውጤታማነታቸው ተለክቷል፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ውጤታማነት በ39 በመቶ ዝቅተኛው ነው፡፡ የጋርድያን ዘገባ እንዳመለከተው የእንግሊዝ ክለቦች ዘንድሮ ባሳዩት ድክመት በሻምፒዮንስ ሊግ የተሳትፎ ኮታ ላይ ቅናሽ እንዲመጣባቸው ሊያደርግ ይችላል፡፡

የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ለሊጎች በሚሰጥ የተሳትፎ ኮታ ወቅታዊ ደረጃ የስፔኑ ላሊጋ በ85.882 ነጥብ የመጀመርያ ደረጃ ይዟል፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በ79.82 ሁለተኛ፤ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ76.75 ሶስተኛ እንዲሁም የጣሊያን ሴሪኤ በ63.4 ነጥብ አራተኛ ላይ ናቸው፡፡ በውድድር ዘመኑ መጨረሻ በዚሁ የሻምፒዮንስ ሊግ የተሳትፎ ኮታ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ወደ 3ኛ ደረጃ መውረዱ አይቀርም፡፡ ስለሆነም ለእንግሊዝ ክለቦች ለሻምፒዮንስ ሊግ የምድብ ቀጥታ ተሳትፎ የነበረው የአራት ክለቦች ኮታ ወደ ሶስት ይወርዳል ተብሏል፡፡ ዴይሊ ቴሌግራፍ በሰራው ዘገባ ደግሞ የእንግሊዝ ክለቦች ከሻምፒዮንስ ሊጉ ጥሎ ማለፍ በመሰናበታቸው ለሩብ ፍፃሜ ፤ለግማሽ ፍፃሜ እና ለዋንጫ ጨዋታ በመድረስ በነፍስ ወከፍ እስከ 35 ሚሊዮን ፓውንድ የገቢ ድርሻም አጥተዋል፡፡

ከሻምፒዮንስ ሊጉ ጥሎ ማለፍ የተሰናበተው ማን ዩናይትድ በተሳትፎው እስከ 34 ሚሊዮን ፓውንድ ሲያገኝ በተመሳሳይ ምእራፍ የቀረው አርሰናል እስከ 29.7 ሚሊዮን ፓውንድ ይኖረዋል፡፡ በምድብ ማጣርያው የተሰናበቱት የአምናው ሻምፒዮን ቼልሲ እስከ 29.4 ሚሊዮን ፓውንድ እንዲሁም ማን ሲቲ 27.8 ሚሊዮን ፓውንድ ገቢ እንደሚኖራቸውም የዴይሊ ቴሌግራፍ ስሌት አመልክቷል፡፡

በኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ስፖንሰርነት የአውሮፓ 24 ምርጥ ክለቦችን የሚያሳትፍ ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ስለመታቀዱ በለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የቀረበ ልዩ ዘገባ እውነታ አልተረጋገጠም፡፡ ኳታር በ2022 እኤአ ላይ በመካከለኛው ምስራቅ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ እንዲካሄድ የተፈቀደውን 22ኛው የዓለም ዋንጫ የምታዘጋጀው ናት፡፡ በሃሳቡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እንዳይቀየሙ ተሰግቷል፡፡ የለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ትልልቅ የአውሮፓ ክለቦች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› እንዲሳተፉ በማግባባት ላይ መሆናቸውን ሲዘግብ እስከ 175 ሚሊዮን ፓውንድ ለተሳትፏቸው ብቻ ለመክፈል ጥሪ አድርገጎላቸዋል ብሏል፡፡ ድሪም ፉትቦል ሊጉን በኳታር፤ በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ፤ በሳውዲ አረቢያ እና በባህሬን በሚገኙ 6 ከተሞች በማዘዋወር በየሁለት ዓመቱ ለማካሄድ መታቀዱን የገለፀው ታይምስ አራቱ የእንግሊዝ ክለቦች ማን ዩናይትድ፤ ማን ሲቲ፤ አርሰናልና ቼልሲ እንዲሁም የስፔኖቹ ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና በቀጥታ የተሳትፎ ግብዣ እንደቀረበላቸውም አውስቷል፡፡

በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› መጀመር ዙርያ ጥሪ ቀርቦላቸዋል የተባሉት እነዚህ ክለቦች በጉዳዩ ላይ እስካሁን የሰጡት መግለጫ የለም፡፡ የኳታር እግር ኳስ ፌደሬሽን በኦፊሴላዊ ድረገፁ ስለ ድሪም ፉትቦል ሊጉ የሚወራውን ሲያስተባብል ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እስካሁን በጉዳዩ ላይ ይፋ መግለጫ ከማውጣት እንደተቆጠቡ ናቸው፡፡ የኳታር ባለሃብቶች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ከ9 አመታት በኋላ አገሪቱ ለምታዘጋጀው 22ኛው ዓለም ዋንጫ ለማሟሟቅ ብለው ውድድሩን ያዘጋጁታል ያሉ ዘገባዎችም ወጥተዋል፡፡ ሌስ ካህሬስ ዴፉትቦል የተባለ የፈረንሳይ ሚዲያ በበኩሉ የለንደኑ ታይምስ ዘገባውን ከማሰራጨቱ አንድ ቀን ቀደም ብሎ የድሪም ፉትቦል ሊግ ጅማሮን በአዝናኝ ሃሳብነት ማቅረቡን ገልጿል፡፡

የአውሮፓ እግር ኳስ በድሪም ፉትቦል ሊግ መጀመር ዙርያ የወጡ መረጃዎችን ለማጣራት እንደሚፈልግ የገለፁ አንዳንድ ዘገባዎች ከሻምፒዮንስ ሊግ እና በፊፋ ከሚዘጋጀው የዓለም ክለቦች ዋንጫ ጋር የሚመሳሰለው ውድድሩ እንዲካሄድ በምንም አይነት ፈቃድ እንደማይሰጥ አብራርተዋል፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ የገንዘብ ተፅእኖ እየጨመረ መጥቷል፡፡ በ2010 እኤአ ላይ ከኳታር የንጉሳውያን ቤተሰብ አንዱ የስፔኑን ክለብ ማላጋ በባለቤትነት ተያዘ፡፡ በ2011 እኤአ ላይ ሌሎች የንጉሳውያን ቤተሰብ አባላት የፈረንሳዩን ፓሪስ ሴንትዠርመን በባለቤትነት ገዙ፡፡ ኳታር ፋውንዴሽን ደግሞ የታላቁ የስፔን ክለብ ባርሴሎና ማልያ በታሪክ የመጀመርያው ስፖንሰር መሆን እንደቻለ ይታወቃል፡፡