Administrator

Administrator

አንድ ብዙ አማካሪ ያላቸው ንጉሥ፤ ሁሉም ባለሟሎቻቸው በተሰበሰቡበት አንድ ጥያቄ ጠየቁ፡፡ “የመጀመሪያው ጥያቄዬ”፣ አሉ ንጉሡ፡፡ “ከዚህ እስከሰማይ ምን ያህል ርቀት እንዳለው የሚያውቅ ይንገረኝ?” አሉ፡፡ ሁለተኛው ጥያቄዬ፤ “እኔ ብሸጥ ምን ያህል የማወጣ ይመስላችኋል?” “አስበን እንምጣ ንጉሥ ሆይ!” ብለው ባለሟሎቹ ሄዱ፡፡ ከዚያም፤ አንደኛው - ኮከብ ቆጣሪዎችን እንጠይቅ አለ ሁለተኛው - ኮከብ ቆጣሪዎች ዕጣ - ፈንታ እንጂ ኪሎ ሜትር አያውቁም፡፡ ይልቅ ደብተራዎችን እንጥራና የሚደግሙትን ደግመው የሚገለጥላቸውን ይንገሩን፡፡ ሦስተኛው - ደብተራዎችም ቢሆኑ ስለአጋንንት ትብትብ መፍቻ፣ ስለመናፍስት እንቅስቃሴ እንጂ ስለምድር - ሰማይ ርቀት የሚደግሙት የላቸውም፡፡

አራተኛው - እንግዲያው አዋቂ እንጠይቅ አምስተኛው - ጠንቋይ ለራሱ አያውቅም ባካችሁ፤ ይህንን ያንን እያነሱና እየጣሉ ሲከራከሩ፤ ከአቅራቢያቸው የሚገኝ አንድ ደበሎ - ለባሽ ያዳምጣቸው ኖሮ፤ “አባቶቼ፤ ይሄ የምትነጋገሩበት ነገር እንዲህ የሚያሟግትና ሊቅና ደብተራ የሚያፋልግ ጉዳይ አይደለም” አላቸው፡፡ ይሄኔ አንደኛው፤ “ታዲያ ምን እናድርግ ትላለህ በእኛ ዕውቀት ደረጃ የምንፈታው ባይሆንልን እኮ ነው፡፡” የቆሎ ተማሪውም፤ “እኔ መልሱን ልሰጣቸው እችላለሁ፡፡ ንጉሡ ፊት አቅርቡኝ” አላቸው፡፡ አማካሪዎቹ ጥቂት ካቅማሙ በኋላ፤ በቃ እንውሰደውና ይናገር ብለው ተስማሙ፡፡ ንጉሡ ዘንድ ቀርበውም፤ “ንጉሥ ሆይ! ንጉሥ ለጠየቁት መልስ መስጠት እችላለሁ የሚል ሰው ይዘን መጥተናል” ንጉሥ - “ይቅረባ እንየው!” የቆሎ ተማሪው ሲቀርብ ንጉሡ ተገርመው፤ “ይሄ ደበሎ - ለባሽ ነው የረባ መልስ ይሰጣል ብላችሁ ያመናችሁት?” አንደኛው - “አዎ ንጉሥ ሆይ!” ንጉሥ - “ጥያቄዬ፤ ‘ከመሬት እስከ ሰማይ ምን ያህል ይርቃል? እኔ ብሸጥስ ምን ያህል አወጣለሁ?’ የሚል ነው፡፡

“ የቆሎ ተማሪውም፤ “ንጉሥ ሆይ! ከዚህ እስከ ሰማይ 1000 ኪ.ሜ ይሆናል፡፡ አይበለውና እርሶ ቢሸጡ 29 ብር ያወጣሉ፡፡” ንጉሥ - እኮ አስረዳና! ቆሎ ተማሪው - “ከመሬት እስከሰማይ ያለውን ለመለካት ስለማይችሉ ነው 1000 ኪ.ሜ ያልኩት 29 ብር ያልኩዎት ደግሞ እየሱስ የተሸጠው 30 ብር በመሆኑ ነው፡፡ እርሶ ከዚያ ያንሳሉ፡፡ ስለዚህም ቢያወጡ ቢያወጡ በአንድ ያንሳሉ ብዬ ነው፡፡ ንጉሡ በመልሱ ተደስተው፣ አመስግነው ሸለሙት፡፡ * * * ስመ-ጥር አማካሪዎች የማይሰነዝሩዋቸው፣ ተራ የሚመስሉ አስተዋይ ሰዎች ግን ሳይጠራጠሩ የሚሰጡት ፋይዳ ያለው አስተሳሰብ፤ አገር ያድናል፡፡ የበታች ሆነው ታስበው፣ ታላቅ ሃሳብ ሊያቀርቡ የሚችሉ ሰዎችን በፋኖስ መፈለግ ያስፈልጋል፡፡ ለመፈለግ ደግሞ “ከእኔ ውጪም ለአገር አሳቢ ሊኖር ይችላል” ብሎ ማመን ተገቢ ነው፡፡ “ትኬት አልገዛም፤ ዝም ብዬ ባቡሩ ላይ እሳፈራለሁ” በሚል ሚንግዌይ ስለድፍረት ነግሮናል። ወይ የባቡሩ ሸፍተራን ይታለላል፡፡

ወይ አይመጣም፡፡ ወይ እንደራደራለን። አለበለዚያ እወርዳለሁ፤ ብለን የምንጓዘው ጉዞ፤ ለግዴለሽ ዕቅድ - አልባነታችን መገለጫ ይሆነናል፡፡ ያለዕውቀት ባቡሩ ላይ መሳፈር ወይ የብልጠት፣ ወይ አይነቃብኝም ብሎ የማሰብ ወይም ሌላውን የመናቅ አሊያም ተደባልቆ የመጓዝ ሁኔታ፤ እነሆ ዛሬ ከዘመናት በኋላ ፈጣን ነው ባቡሩን እንድንዘፍን ያደርገናል፡፡ ሳርኮክ የተባለው ፈላስፋ፤ በፍልሚያ የሚያምኑ አካላት፤ በጦርነት ሌሎቹን ድል ካደረጉ በኋላ፤ ‘ጠላት ካጣን እርስ በርስ ይዋጣልና’ የሚል ደረጃ ይደርሳሉ” የሚለንን ልብ እንበል፡፡ ሁልጊዜ የአገሬ እድገት፤ በኪራይ ሰብሳቢዎች ላይ ያገኘሁት ድል ነው! ምርጫው ያለሳንካ በመካሄዱ ነው! ፀረ - ህዝብና ፀረ - ህገመንግሥት አመራሮችን በማስወገዳችን ነው! ወዘተ… ከሚለው ባሻገር፣ ከሣጥኑ ወጣ ብለን ለማሰብ እንሞክር፡፡

ችግሮችን ወደህዝብ ማድረስ የሀቀኛ ዜጐች ግዴታ ነው!! ሆኖም ያለንበት ሁኔታ አንድ ክስተትን አጉልቶ እያሳየን ነው፡- የታፈኑ የሚመስሉ ጉዳዮች ነበሩንን? የሚል፡፡ የጤናማ አመለካከት ጥያቄ ነው፡፡ በህዝብና በአገር ላይ ክፉ ድርጊት ሲፈፀም እርምጃ ሳይወስዱ እጁን አጣጥፎ መቀመጥ አደገኛ እንደሆነ ሁሉ፤ እርምጃንም በስሜታዊነት ወይም በመካር አሳሳቾች ግፊት ከመውሰድ መቆጠብ ያባት ነው! ሰሞኑን “መልካም አስተዳደር በዘመቻ የሚፈታ ችግር አይደለም” የተባለው አስገራሚ አረፍተነገርና ዕውነታ፤ “የጠፋው በግ ተገኘ” የሚያሰኝ ነው፡፡ መልካም አስተዳደር፣ በሙያ በበሳል - ጥበብ (wisdom)፣ የህዝብ ጥቅም - ተኮር በሆነ መልክ ይቃኝ፤ ተብሎ አያሌ ጊዜ ተነግሮ ዛሬ ይፋ መሆኑ አስደሳች ነው፡፡

ዘመቻ በየአቅጣጫው ሊፈተሽ ሊመረመር ይገባል - ለሀገርና ለህዝብ ጥቅም ሲባል፡፡ ነኒውሪን ቤቫን የተባለው ፖለቲከኛ ስለቸርችል እንደጻፈው፤ ከዓለም ጋር ያለ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፣ የጐረቤት ሀገሮች ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፣ እርስ በርስ ያለ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፤ ሲላላ፤ በ20ኛው ክ/ዘመን ያለው ዲፕሎማት የ18ኛው ክ/ዘመን ቋንቋ የሚናገር ይሆናል፡፡ አስቸጋሪ ሁኔታ በገጠመው ቁጥር ግን “ተኳሽ - ጀልባ ላኩ” ከማለት አይቆጠብም! ይላል፡፡ ቀልብን ገዝቶ፣ አዕምሮን አትብቶ አገርን ማስተዋል የታላቅ መሪ ጥበብ ነው፡፡ መሪ፤ “ንፁህ ወርቅ እሳት አይፈራም!” የሚለውን አልሰማ ብሎ ከተዘናጋና እሳቱ እየበላው መሳቅ መጫወት ከሆነ ሥራው፤ ስለሀገራችን እርግጠኛ መሆን አንችልም፡፡ “ሸማኔ ውሃ ሲወስደው፣ እስካሁን አንድ እሰድ ነበር፤ አለ” ማለት ይሄው ነው!!

  • 1 የአቶ መለስ ዜናዊ ምትክ መሆናቸውን ለማስመስከር የሞከሩበት ነው ግዙፎቹ እቅዶች (ለምሳሌ የባቡር ፕሮጀክት) መጓተታቸውንና የገንዘብ ችግርን በሚመለከት፣ እንዲሁም በቤኒሻንጉል የተፈናቀሉ ሰዎች ዙሪያ ትችት አዘል ጥያቄ ቀርቦላቸዋል። ጠ/ሚ ኃይለማርያም ለፓርላማው የሰጡት ምላሽ፣ የአቶ መለስን ዘዴ የተከተለ ነው - “መንግስት ላይ በተሰነዘረው ትችት ላይ የባሰ ትችት የመጨመር ዘዴ”
  • 2. የማይሳካ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ አጣብቂኝ ሆኖባቸዋል ግዙፎቹ የግድብ፣ የባቡር፣ የኢንዱስትሪ. የኤክስፖርት እቅዶች፣ እንዲሁም የእህል ምርት ለማሳደግና ስራ አጥነትን ለማቃለል የወጡ እቅዶች የማይሳኩ መሆናቸውን ከምር አምነው ለመቀበል አልደፈሩም። እቅዶቹ “በተያዘላቸው ጊዜ እየተተገበሩ ናቸው” እያሉ በተደጋጋሚ ይናገራሉ። ግን ደግሞ “የመቀነስ አዝማሚያ ታይቷል” ይላሉ።

እውነት ለመናገር ኢህአዴግ በ”ስሜት” ተነሳስቶ በ2002 ዓ.ም መጨረሻ ላይ ያዘጋጀው “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ” አልሳካ ያለው በጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሳለኝ ድክመት አይደለም። እቅዱ እንደማይሳካ በተግባር የታየው በመጀመሪያው አመት በ2003 ዓ.ም ነው። አምና ደግሞ፤ የእቅዱ ውድቀት አፍጥጦ ወጣ። በዚህ በዚህ፣ አቶ ኃይለማርያም ከሌሎች የኢህአዴግ መሪዎች የተለየ ተጠያቂነት ሊጫንባቸው አይገባም። በአብዛኛው የመንግስት ፕሮጀክቶች በማስፋፋት የአገሪቱን ኢኮኖሚ በአምስት አመት ውስጥ በእጥፍ ለማሳደግ ታስቦ እቅድ መውጣቱ ነው ዋነኛው ጥፋት። በመንግስት ፕሮጀክቶችና ኮርፖሬሽኖች አማካኝነት አገር ሊያድግ እንደማይችል በደርግ ዘመን በደንብ ታይቷልኮ።

የኢህአዴግ “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድም” ከውድቀት ሊያመልጥ የማይችለው፤ እንደ ደርግ እቅድ የግል ኢንቨስትመንትንና የግል ጥረትን የሚያጣጥ በመሆኑ ነው - በአጭሩ በአቶ ሃይለማርያም ድክመት አይደለም የኢህአዴግ እቅድ ሳይሳካ የሚቀረው። ይልቅስ፣ ጠ/ሚ ኃይለማርያምን ተጠያቂ የምናደርጋቸው፤ የአምስት አመቱ እቅድ እንደማይሳካ እየታወቀ፤ “እየተሳካ ነው፤ እንደታቀደው እየተሰራ ነው” ብለው ሊያድበሰብሱ ከሞከሩ ነው። በእርግጥ፤ እቅዱ እየተሳካ አለመሆኑን ሙሉ ለሙሉ አልካዱም። የእርሻ ምርት እንደታሰበው አላደገም ብለዋል። ኤክስፖርትም እንዲሁ።

“የጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ምርታማነት”ም የተወራለት ያህል እንዳልሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቅሰዋል። እንዲያም ሆኖ፤ እቅዱን አለመሳካት ሙሉ ለሙሉ ባይክዱም፤ ሙሉ ለሙሉም አምነው አልተቀበሉም። “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱ”፤ ከሞላ ጎደል በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ እየተተገበረ እንደሆነ ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተደጋጋሚ የገለፁት። ለመሆኑ የትኛው እቅድ ነው፤ በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ እየተከናወነ የሚገኘው? ካሁን በፊት እንደጠቀስኩት፣ ትልቅ ትኩረት የተሰጠው የህዳሴ ግድብ ግንባታ እንኳ በእቅዱ መሰረት እየተከናወነ አይደለም። በጣም ተጓቷል። በአምስት አመት ውስጥ ግንባታው ይጠናቀቃል ነበር የተባለው። ግን በሁለት አመት ውስጥ የተከናወነው ስራ፣ 18 በመቶ ብቻ ነው። በዚህ ስሌትም፣ ግንባታው 11 አመት ሊፈጅ ይችላል። “የግልገል ጊቤ 3” ግንባታም እንዲሁ፤ በእቅዱ መሰረት ሊሄድ አልቻለም። በ1998 ዓ.ም የተጀመረው የግልገል ጊቤ 3 ሃይል ማመንጫ፣ የዛሬ ሁለት አመት ግንባታው ተጠናቅቆ ወደ ስራ እንዲገባ ታቅዶ ነበር። አልተሳካም።

እቅዱ ተከልሶ፣ የግንባታ ማጠናቀቂያ ጊዜው ወደ ዘንድሮ ተራዘመ። ግን እንኳን ዘንድሮ በሚቀጥለው አመትም አይጠናቀቅም። ግንባታው ገና 71% ላይ ነው። ቢያንስ ተጨማሪ ሶስት አመት ሳያስፈልገው አይቀርም። እናም በ2002 ዓ.ም ወደ ሁለት ሺ ሜጋ ዋት ገደማ የነበረው የኤሌክትሪክ ሃይል የማመንጨት አቅም፣ በ50 በመቶ እንዲያድግና ዘንድሮ ሶስት ሺ ሜጋ ዋት እንዲደርስ የወጣው እቅድ አልተሳካም። እዚያው ከነበረበት ደረጃ ፈቅ አላለም። ከሁሉም የላቀ ትኩረት የተሰጣቸው ግድቦች፣ በተያዘላቸው እቅድ ሊከናወኑ ካልቻሉ፣ ሌሎቹ እቅዶች ምን ያህል እንደሚጓተቱ አስቡት። በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ላይ የተጠቀሱት ግዙፍ የሳሙናና የወረቀት ፋብሪካዎችም ድምፃቸው የለም። ዋነኛ የእድገት መሰረት ይሆናሉ ተብለው በመንግስት በጀት የተመደበላቸው አነስተኛና ጥቃቅን አምራች ተቋማትስ? ከቁጥር የሚገባ ለውጥ አልተመዘገበም። ፈፅሞ የእድገት ምልክት አልታየባቸውም። እንዲያውም፣ ከሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች ጋር ሲነፃፀሩ፣ አነስተኛና ጥቃቅን አምራች ተቋማት ወደ ኋላ እየቀሩ መሆናቸውን የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። ለነገሩ፣ በኢህአዴግ ጉባኤ ላይም በግልፅ ተጠቅሷል።

የአምናው የእርሻ ምርት እድገትም እንዲሁ የእቅዱን ግማሽ አያክልም። በአማካይ በነፍስ ወከፍ ስሌት፣ የእርሻ ምርት በ6 በመቶ እንዲያድግ ቢታቀድም፣ በተግባር ግን ከ2.5 በመቶ ያለፈ እድገት አልተገኘም። ብዙ የተወራላቸው አዳዲስ 10 የስኳር ፋብሪካዎችም ገና ብቅ አላሉም። ከ8 አመት በፊት የተጀመሩ ነባር የስኳር ፋብሪካ ፕሮጀክቶች እንኳ፣ በወጉ ሊጠናቀቁ አልቻሉም። የስኳር ምርት በሶስት እጥፍ አድጎ ዘንድሮ 10 ሚሊዮን ኩንታል ገደማ ይደርሳል ተብሎ ነበር - በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ። እህስ? የዛሬ አራት አመት ከነበረበት ደረጃ ትንሽ እንኳ ፎቀቅ አላለም። እንዲያውም ወደ ታች ወርዷል፤ ከ3 ሚሊዮን ኩንታል በታች ሆኗል። ከአገር ውስጥ ፍጆታ የሚበልጥ ስኳር ተመርቶ፣ ዘንድሮ በኤክስፖርት ወደ ሁለት ቢሊዮን ብር ገደማ ገቢ ይገኝበታል ተብሎ ነበር። ጠብ ያለ ነገር የለም። እንዲያውም የአገር ውስጥ ፍጆታን ለማሟላት ከውጭ ስኳር ለማስመጣት በቢሊዮን የሚቆጠር ብር ወጪ ተደርጓል። ባቡርስ? የባቡር ነገርማ ከሌሎችም የባሰ ሆኗል። የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ላይ እንደተጠቀሰው ቢሆን ኖሮ፤ አገሪቱ ዘንድሮ 1700 ኪሎሜትር የባቡር ሃዲድና የባቡር ትራንስፖርት ይኖራት ነበር። ቢያንስ ቢያንስ የጂቡቲ መስመር ተሰርቶ አገልግሎት መስጠት ይጀምር ነበር። ግን እንደ እቅዱ አልሆነም። እስካሁን የተሰራው ሃዲድ “የ650 ኪሎሜትር 15%” ነው ተብሏል።

ቢበዛ ከመቶ ኪሎሜትር አይበልጥም ማለት ነው። የጂቡቲ መስመር ሁለተኛው ደግሞ ገና የአፈር ቁፋሮ ላይ ነው። ወደ ሰሜን ወደ ምዕራብ አቅጣጫ የተባሉት የባቡር መስመሮችማ ገና ዲዛይናቸው አላለቀም። የኮንዶሚኒዬም ቤት ግንባታም ተመሳሳይ ነው። ስለ ኮንዶሚኒዬም ብዙ ብዙ እቅዶች ሲዘረዘሩና በሪፖርት ሲቀርቡ አይገርማችሁም? በየአመቱ 50ሺ ኮንዶሚኒዬም ቤቶች ይገነባሉ ሲባል ትዝ ይላችኋል - በ97 ዓም። አንድ ሶስተኛውን እንኳ ማሟላት አልተቻለም። በእድገትና ትራንስፎርሜሽ እቅድ ላይ፣ አመታዊው የግንባታ መጠን ወደ 30ሺ ዝቅ እንዲል ተደረገ - በሶስት አመት 90ሺ መሆኑ ነው። ይሄም አልተቻለም። በሶስት አመት ውስጥ ለነዋሪዎች የደረሱ አዳዲስ የቤት ግንባታዎች ሲቆጠሩ፣ በአመት ከአስር ሺ አይበልጡም - የእቅዱ 30 በመቶ እንደማለት ነው። ጠቅላላ የኢኮኖሚውን አዝማሚያ በግልፅ የሚያሳይ ሌላ መረጃ ከፈለጋችሁ፤ በኤክስፖርት የሚገኘውን ገቢ መመልከት ትችላላችሁ። የእድገትና የትራንፎርሜሽን እቅድ የተዘጋጀው፤ በ2002 ዓ.ም ከሸቀጦች ኤክስፖርት 2 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ከተገኘ በኋላ ነው።

አምስት አመት ውስጥ በአራት እጥፍ አድጎ 8 ቢሊዮን ዶላር እንዲደርስ ታስቦ በወጣው እቅድ መሰረት፣ ዘንድሮ ወደ 5 ቢሊዮን ዶላር ገደማ የኤክስፖርት ገቢ መገኘት ነበረበት። ግን ሊሆን አይችልም። ለዚህም ነው እቅዱ ተከልሶ፣ በዚህ አመት ከኤክስፖርት 3.7 ሚሊዮን ዶላር ለማግኘት የታቀደው። ይሄም አልተሳካም። በስምንት ወራት ውስጥ የተገኘው የኤክስፖርት ገቢ 2 ቢሊዮን ዶላር ብቻ ነው። በአመቱ መጨረሻ ቢበዛ ቢበዛ 3 ቢሊዮን ዶላር ሊደርስ ይችላል። የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱ ፈፅሞ ሊሳካ እንደማይችል ሁነኛ ማረጋገጫ የሚሆንብን፣ ይሄው የኤክስፖርት ገቢ ዝቅተኛነት ነው። ለምን ቢሉ፤ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ አገኛለሁ በሚል ሃሳብ መንግስት ያቀዳቸው በርካታ ፕሮጀክቶች ተግባራዊ ሊሆኑ አይችሉም። በትምህርትና በስልጠና በኩልስ፣ እቅዱ እየተሳካ ነው? ቃላትን ማንበብ የማይችሉ ተማሪዎች ምን ያህል ብዙ እንደሆኑ የተለያዩ ጥናቶችን በማጣቀስ መልስ መስጠት ይቻላል። ግን፣ በኢትዮጵያ ሬድዮ የተሰራጨ አንድ ዜና ብቻ በመስማት የአገሪቱን የትምህርት ሁኔታ አዝማሚያውን መገመት የሚቻል ይመስለኛል።

የቴክኒክ ኮሌጅ ውስጥ ከወዳደቁ እቃዎች መበየጃ ተሰራ የሚል ነው የዜናው ርዕስ። በኢትዮጵያ ሬድዮ የምንሰማቸው ዜናዎች “አስገራሚ” አይደሉ? ረቡዕ ማታ ሁለት ሰዓት ላይ፣ የእለቱ ሁለተኛ ትልቅ ዜና፣ በጅጅጋ የቴክኒክ ኮሌጅ፣ ከወዳደቁ ነገሮች መበየጃ እንደተሰራ ይገልፃል። በየጉራንጉሩ የሚዘጋጀውን መበየጃ፣ ለአንድ የቴክኒክ ኮሌጅ እንደ ትልቅ ስራ መቆጠር የጀመረው ከመቼ ወዲህ ይሆን? ግርድፍ “ትራንስፎርመር” እንደማለትኮ ነው። ከመበየጃ ጋር ሲነፃፀር፣ የሞባይል ቻርጀር እጅግ የተራቀቀ “ትራንስፎርመር” ነው። የኮሌጁ አስተማሪዎችና ተማሪዎች፣ መበየጃ ለመስራት መጣራቸው ስህተት ባይሆንም፣ መበየጃው “ከወዳደቁ ነገሮች” የተሰራው ኮሌጁ ምን አይነት ቢሆን ነው? መበየጃ ለመስራት የሚያስችል ቁሳቁስ ከሌለው፣ እንደ ሞተርና ጄነሬተር የመሳሰሉ ነገሮችን ለማደስማ ጨርሶ አይታሰብም ማለት ነው። የቴክኒክ ኮሌጅ እንዲህ ነው? ካስታወሳችሁ፣ የረቡዕ ማታ የመጀመሪያ ዜና፣ ጠ/ሚ ኃይለማርያም ለፓርላማ ያቀረቡትን ሪፖርት የሚመለከት ነበር። ለኢንዱስትሪ ምርትና ልማት ከፍተኛ ትኩረት እንደተሰጠው የገለፁት ጠ/ሚ ኃይለማርያም፣ ለቴክኒክ ትምህርት ስለሚመደበው በጀትና ስለ ትምህርት ጥራት ልብን የሚያሞቅ ሪፖርት ዘርዝረዋል። ታዲያ ይህንን “የምስራች” የሚያፈርስ “የመበየጃ” ዜና ወዲያውኑ ተከትሎ መቅረቡ አይገርምም?

“ከዳያስፖራ ደጋፊዎች የምናገኘው ምላሽ አበረታች ነው”

በአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የውጭ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢና በመድረክ የብሔራዊ ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ ተመስገን ዘውዴ፤ በሁለቱ ድርጅቶች ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ለመምከርና በዲፕሎማሲና በፋይናንስ ድጋፍ ዙሪያ ከውጭ ደጋፊዎቻቸው ጋር ለመወያየት ትላንትና ወደ አሜሪካ ተጓዙ፡፡ በአንድነት እቅድና ስትራቴጂ መሠረት የውጭ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴው በጊዜው ከኢትዮጵያ ውጭ ያሉ ኢትዮጵያዊያን ደጋፊዎች በዲፕሎማሲ እና በፋይናንስ ፓርቲውን የሚረዱበትን ሁኔታ ማፈላለግና በሀገራቸው ጉዳይ እንዲደራጁ የማድረግ ሃላፊነት እንዳለበት የገለፁት አቶ ተመስገን፤ ጥረቱ በፊት የተጀመረ እንደሆነና ይህንኑ ጥረት አጠናክሮ ለመቀጠል ወደ አሜሪካ መጓዛቸውን ተናግረዋል፡፡

“ከዚህ በፊት እንደተለመደው በሀገሪቱ ወቅታዊ ጉዳይ፣ ስለ አደረጃጀትና የፋይናንስ ድጋፍ ለደጋፊዎች ገለፃ አደርጋለሁ” ያሉት አቶ ተመስገን፤ ጉዟቸው ዋሽንግተን ዲሲ፣ ካናዳና ደቡብ አፍሪካን እንደሚሸፍን ገልፀዋል፡፡ ቀደም ባለው ጊዜ በአሜሪካ 10 ያህል ግዛቶች ተዘዋውረው አባላትን አደራጅተው መመለሳቸውን ገልፀው፤ በአሁኑ ጉዞ በአሜሪካ ውስጥ የሚዘዋወሩባቸው ስቴቶች አሜሪካ በሚገኙ የድርጅት ሃላፊዎች ፕሮግራም እንደሚወሰን ተናግረዋል፡፡ ድጋፍ በማሰባሰብ፣ በአደረጃጀት፣ በዲፕሎማሲና በፋይናንስ ድጋፍ ለሚሠሩት ሥራ አምስት ወራትን በአሜሪካ በካናዳና ደቡብ አፍሪካ እንደሚቆዩና ነሐሴ መጨረሻ አሊያም መስከረም መጀመሪያ ላይ ወደ ሀገራቸው እንደሚመለሱ አቶ ተመስገን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

የአንድነትና የመድረክ ደጋፊዎች በተለይ በዋሽንግተን ዲሲ ሲያትል፣ በካሊፎርኒያ ቦስተን፣ አትላንታ፣ በዴንቨርና በሌሎች በርካታ ግዛቶች እንደሚገኙ ገልፀው የድርጅቱ ሃላፊዎች ባላቸው ፕሮግራም ቢቻል ሁሉንም አዳርሰው፣ አደረጃጀቱንና የፋይናንስ ድጋፉን ለማጠናከር እንደሚጥሩ ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ የተቃውሞ ፖለቲካ በመቀዛቀዙ የዲያስፖራውም ድጋፍ ተቀዛቅዟል በሚባልበት በአሁኑ ወቅት ከውጭው ደጋፊ ምን ይጠብቃሉ ተብለው ለተጠየቁት ሲመልሱ “ኢትዮጵያዊያን ደጋፊዎቻችንና ወገኖቻችን በምንም ሁኔታ ውስጥ ሆነው ስለገራቸው ያላቸው ስሜት ከፍተኛ ነው” ያሉት አቶ ተመስገን፤ አንድነትም ሲያደራጃቸው በህጋዊና በሠላማዊ መንገድ በመሆኑ ህጋዊ የዴሞክራሲ ሽግግር እንዲኖር የሚፈልጉ ኢትዮጵያዊያን በምንም ሁኔታ ከመደራጀትና ከመደገፍ ወደኋላ እንዳላሉ፣ ተቀዛቅዟል የሚባለውም ሀሰት እንደሆነ ተናግረዋል።

“እነዚህ በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ህጋዊ የስልጣንና የዴሞክራሲ ሽግግር እንዲኖር ፍላጐት ያላቸው ስለመሆኑ በደንብ እናውቃለን” ብለዋል። የሀገራቸው የልማትና የደህንነት ጉዳይ፣ የሰብአዊ መብት መከበር፣ የህዝብ የስልጣን ባለቤትነት የሚያገባቸው በመሆኑ የሀገር ውስጥ ሠላማዊ ትግልን ከመደገፍ፣ ከመደራጀትና በሠላማዊ መንገድ ከመታገል ቦዝነው እንደማያውቁ በአጽንኦት የገለፁት ሃላፊው፤ በአንድነትና በመድረክ ደጋፊዎች መካከል አንዳችም መቀዛቀዝ እንዳልታየ ተናግረዋል፡፡

“ይህን ጉዳይ ከዚህ ቀደም ወደ እነርሱ እየሄድን ስናደራጅና ስንቀሰቅስ አይተነዋል” ያሉት አቶ ተመስገን፤ ዛሬም እንደተለመደው ሠላማዊና ህጋዊ ትግሉን አጠናክሮ በመቀጠል የኢትዮጵያ ህዝብ የስልጣን ባለቤት እንዲሆን፣ ሰብአዊ መብቱ እንዲጠበቅ፣ የመድብለ ፓርቲ ስርዓትና ዴሞክራሲ በዚህች አገር እውን እንዲሆን መታገል እንዳለባቸው እንደሚያስረዱ ገልፀዋል፡፡ በዚህም እንደ በፊቱ ሁሉ ስኬታማና የተዋጣለት የማደራጀትና የድጋፍ ማሰባሰብ ስራ ሰርተው እንደሚመለሱ እምነታቸውን ገልፀዋል፡፡ “እንኳን እዚያ ሄደን አገር ውስጥም ሆነን ከዳያስፖራ ደጋፊዎች የምናገኘው ምላሽ አበረታች ነው” ብለዋል - አቶ ተመስገን፡፡

ውስብስብነቱ ለማተሚያ ቤት አስቸጋሪ ሆኗል

ህገወጥ የመቶ ዶላር ኮፒዎችን ለመከላከል፣ በአዲስ ዲዛይን የተሰራ ባለ 100 ዶላር ኖት ከስድስት ወር በኋላ ስራ ላይ እንደሚውል የአሜሪካ ብሄራዊ ባንክ (ፌደራል ሪዘርቭ) ባለፈው ረቡዕ ገለፀ። የተጠማዘዘ ሰማያዊ ጥለትና ሌሎች አስቸጋሪ ገፅታዎች ተጨምረውበት የተሰራው ዶላር፣ ከሁለት አመት በፊት ጥቅም ላይ እንዲውል ታስቦ የነበረ ቢሆንም፣ ህትመት ላይ በተፈጠረ ችግር ሲጓተት ቆይቷል። አስመስሎ መስራትን ለመከላከል ተብለው የተጨመሩ ዲዛይኖች ናቸው ህትመት ላይ የመጨማደድ ብልሽት እየፈጠሩ ያስቸገሩት።

በተለይ በዶላሩ ውስጥ የተጠቀቀለለ የሚመዝል ስስ ሪባን ለህትመት በጣም ፈታኝ በመሆኑ፣ የማተሚያ ማሽኖች ላይ ማስተካከያ ማድረግ አስፈልጓል። ሪባኑ ከጥቃቅን ሌንሶች የተሰራ ሲሆን፣ ዶላሩን ወደቀኝ ገፋ ሲደረግ ሪባኑ ወደ ግራ የሚንሸራተት ሆኖ ይታያል ብለዋል የማተሚያ ቢሮ ቃል አቀባይ ዳውን ሃሌ። ዶላሩን ቀና ደፋ በማድረግ፣ ሪባኑ ላይ የሚታዩት የደወል ምስሎች፣ “100” ወደሚል ፅሁፍ ይቀየራሉ። የቀለም ብልቃጥ ምስል ላይ የተጨመረው የደወል ምስል ደግሞ፣ መልኩ ከብጫ ወደ አረንጓዴ ይለወጣል።

በትልቁ የተጻፈው “100” የሚል ቁጥርም እንዲሁ ቀለሙ ይቀያየራል። ነባሩ ዲዛይን ለተወሰኑ አመታት አገልግሎት ላይ እንደሚቆይ የገለፀው የአሜሪካ ቢሄራዊ ባንክ፣ በዚህ አመት 250 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ባለመቶ ዶላር ኖት በአዲሱ ዲዛይን እንደሚታተም አስታውቋል (2.5 ቢሊዮን ኖቶች መሆኑ ነው)። የማሻሻያ ዲዛይኑ የተጀመረው ከአስር አመት በፊት ሲሆን፣ በመጀመሪያ ባለ 20 ዶላር ላይ የቀለማት ለውጥ ከተደረገለት በኋላ፣ ባለ 50፣ ባለ 10 እና ባለ 5 ዶላር ኖቶችም ተሻሽለው ወጥተዋል። የአንድ ዶላር ኖት፣ ምንም ለውጥ አልተደረገበትም።

Saturday, 27 April 2013 10:21

የቢሊዮነሮች መንደር

ለእረፍት ጊዜና ለመዝናኛ የሚፈለጉ አሸዋማ የባህር ዳርቻዎች በጣም ውድ ናቸው። ካርበን የተሰኘችው የካሊፎርኒያ መንደር ደግሞ የአለማችን እጅግ ውድ የባህር ዳርቻ ነች። በእረፍት ጊዜ ጎራ የሚሉበትን ቤት በመግዛት ወይም በመገንባት፣ በካርበን የባህር ዳርቻ፣ ከጫፍ እስከ ጫፍ የተደረደሩት ቢሊዮነሮችና ሚሊዮነሮች ናቸው - ፎርብስ መፅሄት እንደዘገበው። 1. (ጆል ሲልቨር)፡ “ማትሪክስ” በተሰኙት ፊልሞች ከፍተኛ ገቢ ያገኘው ሲልቨር፣ በአካባቢው ከ80 አመት በላይ ያስቆጠረ የተንጣለለ ቤት በ$14.4 ሚሊዮን ገዝቷል። ሁለት ቢሮ፣ ጂም፣ መዋኛና የቴኒስ መጫወቻ አሉት። 2. (ፖል አለን)፡ ከቢል ጌትስ ጋር ማይክሮሶፍትን በመመስረት ዛሬ የ$15 ቢሊዮን ጌታ የሆነው ፖል አለን፣ አምስት መኝታ ቤት፣ ፊልም መመልከቻ ክፍል እንዲሁም መዋኛ ያካተተውን ዘመናዊ ቤት በ$25 ሚሊዮን ገዝቷል። 3. (ጄሚ ማካርት)፡ ሚሊዮነሯ በዚህ የባህር ዳርቻ ከአንዲት የፊልም ተዋናይት የገዛችው ቤት ከ$27 ሚሊዮን በላይ የሚያወጣ ነው። 4. (አሮን ሚልካን)፡ በፊልም ኩባንያ ሃብት ያፈራው አሮን ሚልካን የ$4.2 ቢሊዮን ጌታ ነው።

ከ15 አመት በፊት የገዛው ቤተመንግስት የመሰለ 6 መኝታ ቤት፣ የተንጣለለ መዋኛና የፊልም ማሳያ ክፍል አሉት። ዋጋው $7.3 ሚሊዮን ነው። 5. (ሄም ሳባን)፡ የቴሌቪዥን ቢዝነስን ጨምሮ በበርካታ ኢንቨስትመንቶች የ$3.1 ቢሊዮን ባለቤት የሆነው ሳባን፣ $8.1 ሚሊዮን የሚያወጣው የእረፍት ጊዜ መኖሪያ ቤቱ፣ 9 መኝታ ቤቶችን ይዟል። 6. (ጀፍሪ ካትዘንበርግ)፡ በፊልም ኩባንያ ድሪምወርክስ ውስጥ ከፍተኛ ድርሻ ያለው ካትዘንበርግ፤ ባለ መዋኛ መኖሪያ ቤቱ $3.3 ሚሊዮን ያወጣል። 7. (ላሪ አሊሰን)፡ የኦራክል ኩባንያ መስራች በአለማችን 5ኛው ሃብታም አሜሪካዊ ነው። ሃብቱ $43 ቢ ይገመታል። አምና 9 መኝታ ቤቶች ያሉት ባለ3 ፎቅ መኖሪያ ቤት የገዛው በ$37 ሚሊዮን ነው። በአካባቢው ከ10 በላይ ቤቶችን ገዝቷል። 8. በሬስቶራንት ስራ ሚሊዮነር የሆነው ፒተር ሞርተን ከ15 አመት በፊት በገዛው መሬት $3.4 ሚሊዮን የሚያወጣ የተንጣለለ ቤት አለው።

9. ከሆሊውድ የመዝናኛ ንግድ ወደ ሬስቶራንት ቢዝነስ የገባው ሜር ቲፐር፣ አምስት መታጠቢያ ገንዳዎችን የያዘ ባለሁለት መኝታ ቤት ንብረቱን የገዛው ከ20 አመት ገደማ በፊት ነው። ዋጋው $2 ሚሊዮን 10. ከቢሊዮነሮች ተርታ የተሰለፈው ካናዳዊ ጀራልድ ሽዋርትዝ፣ ከአምስት አመት በፊት ሶስት ጎረቤታም ግቢዎችን ገዝቶ ያስገነባው ግዙፍ ቤት $19 ሚሊዮን ያወጣል። ጠቅላላ ሃብቱ $1.4 ቢሊዮን ነው። 11. በሙዚቃና በፊልም ቢዝነሶቹ ከአለማችን ሁለት መቶ ሃብታሞች መካከል አንዱ የሆነው ዳቪድ ጋፈን፣ 4 ግቢዎችን ገዝቶ በማዋሃድ ነው መዋኛ ገንዳ ያለው ቤት የገነባው። ዋጋው $6 ሚሊዮን ነው። ጠቅላላ ሃብቱ ደግሞ $6 ቢሊዮን። 12. ኢሊ ብሮድ ከ14 አመት በፊት በገዛቸው ሁለት ግቢዎች ላይ ያሰራው፣ መስተዋት የበዛበት ቤት $5.1 ሚሊዮን ያወጣል። በአሜሪካ ባሉት የተለያዩ ኢንቨስትመንቶች $6.3 ቢሊዮን ባለሃብት ሆኗል።

ከአብርሽ ጋር ሲያዩኝ “ኮንግራ ሙሽራው ተገኘ?” ይሉኛል…

ፈረንሳይ ትንሿ የኢትዮጵያ ሆሊዉድ ትባላለች…

የጠበሰም የተጠበሰም፤ የጠየቀም የተጠየቀም የለም (ስለትዳሯ)

በአዲስ አበባ ውስጥ ፈረንሳይ ለጋሲዮን ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ተወልዳ አድጋለች፡፡ ከልጅነቷ ጀምሮ ማንጐራጐር ይቀናት የነበረችው ትንሿ አበባ፤ እንጉርጉሮዋን በማሣደግ በቀበሌ ክበብ አድርጋ፣ በምሽት ክበብ አቋርጣ እስከ ትልቁ ብሄራዊ ቴአትር ቤት ጉዞዋን ቀጥላለች፡፡ ከድምፃዊነት በተጨማሪ በቴአትር መድረክም ላይ ችሎታዋን ያሣየችበትን “ልደት” ቴአትርና “አንድ ምሽት”ን ሠርታለች፡፡ ወደ ፊልሙም ሠፈር ጐራ ብላ “ሩሀማ” እና “ሠካራሙ ፖስታ” ላይ ተውናለች፡፡ ማስታወቂያውንም ሞክራለች፡፡ “ሙሽራዬ ቀረ” የሚል ተወዳጅ አልበም አውጥታ በጣም ተወዶላት ነበር፡፡ አርቲስቷ አምስት ዓመት ገደማ ድምጿን አጥፍታ ከቆየች በኋላ ሠሞኑን “የለሁበትም” የተሠኘ አዲስ አልበም ለማውጣት ደፋ ቀናውን ተያይዛዋለች፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛዋ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ከአበባ ደሣለኝ ጋር በነበራት ቆይታ በአዲሱ ስራዋ፣ ጠፍታ ስለከረመችበት ጉዳይና ሌሎችንም የሥራና የህይወት ቁምነገሮች አንስታ ተጨዋውተዋል፡፡ እነሆ:-

የት ጠፍተሽ ከረምሽ?

ጠፋ ብያለሁ ግን ሥራ እየሠራሁ ስለነበር ነው፡፡ አሁን በአዲስ ስራ እየመጣሁ ነው፡፡ እስከዛሬ ቅጽል ሥም እንዳለሽ አልነገርሽንም? አንቺ ከየት ሰማሽ? እኔ ሰሞኑን ሰምቻለሁ፡፡ ከራስሽ እንስማው…

ማነው ቅጽል ስምሽ?

የሚገርመው ወደ ኪነ-ጥበብ ገብቼ ከ “እርጂኝ አብሮ አደጌ” እስካሁን ድረስ ብዙ ቃለ - ምልልስ አድርጌያለሁ፡፡ እኔም አልተናገርኩም፡፡ ሰዎችም ቅጽል ስም እንዳለኝ አያውቁም፡፡ ሰምቶም የጠየቀኝ የለም፤ አንቺ የመጀመሪያ ነሽ ስለ ቅጽል ስሜ ስትጠይቂኝ ማለቴ ነው፡፡ ስሜ “ሙናና” ነው የሚባለው፡፡ ይሄንን ስም ቤተሰቤ፣ እህቶቼ፣ የቅርብ ዘመድ እና የሠፈር ሰው ነው የሚያውቀው፡፡ ምን ማለት ነው? ስወለድ በጣም ቀጫጫና ትንሽ ነበርኩኝ አሉ፡፡ ካደግኩም በኋላ መወፈር አልቻልኩም፡፡ እና አሁን ይህቺ ሰው ሆና ታድጋለች… የሆነች ሙንን ያለች ነገር ብላ አያቴ ስትናገር፣ በዛው ሙናና ተባልኩኝ፡፡ አንዳንዶቹ ሙኒኒ ብለው ይጠሩኛል፤ ሰፈር ውስጥ ማለት ነው፡፡

እዚህ ለመድረስ ውጣውረዶችን እንዳሳለፍሽ ይነገራል፡፡ እስኪ አጫውቺኝ?

ከሌሎች ሰዎች በጣም የተለየ ውጣ ውረድ አይደለም ግን እንደማንኛውም ባለሙያ እዚህ ለመድረስ ከፍና ዝቅ ይኖራል፡፡ ምክንያቱም አንድ ነገር ሲጀመር ሁሉም አልጋ በአልጋ አይሆንም፤ በየትኛውም የስራ ዘርፍ ቢሆን ማለት ነው፡፡ ፈተናዎቹ እንግዲህ ከክበብ ጀምሮ እስከ ቴያትር ቤት፣ ከዚያም አልበም እስከማውጣት ደፋ ቀና ማለት ያለ ነው፡፡ ናይት ክለብ ስሰራም እንደዚሁ ሴትነትሽን ተከትለው ከሚመጡት ፈተናዎች ጀምሮ የተለያዩ ነገሮች አሉ፡፡ ዋናው ነገር እነሱን በድል ተወጥቼ እዚህ መድረሴ ነው፡፡ ይህ እንግዲህ እግዚአብሔርም ተጨምሮበት ነው፡፡ ከልጅነትሽ ጀምሮ ታንጐራጉሪ ነበር፡፡ በዛን ጊዜ የእነማንን ዘፈን ትዘፍኚ ነበር፡፡ የሂሩትን ዘፈኖች ለመጫወት የመረጥሽበትስ ምክንያት ምንድን ነው?

በነገርሽ ላይ ልጅ ሆኜ የወንድም የሴትም ዘፈን አይቀረኝም፡፡ ሁሉንም በቃ መዝፈን ነው፡፡ ለምሳሌ ደረጀ ደገፋውና ማርታ ሀይሉ እየተቀባበሉ የሚዘፍኑትን “አንቺ ሆዬ ሆይ” የተሰኘ ዘፈን፣ የሷንም የእሱንም ራሴን በራሴ እየተቀባበልኩ እዘፍን ነበር፡፡ ወንዱንም ሴቷንም እየሆንኩ ማለቴ ነው፡፡ የኬኔዲና የየሺመቤትን ዘፈን አሁንም ወንዱንም ሴቷንም ሆኜ እዘፍን ነበር፡፡ የጋሽ ጥላሁንንም እዘፍናለሁ፡፡ ያው ልጅ ስትሆኚ መምረጥ የለም፡፡ ሁሉንም መነካካት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ መዝፈን ማለት ምን እንደሆነ፣ ሜጀር ማለት ምን ማለት እንደሆነ ሲገባሽ፣ መድረክ አያያዝ፣ ማይክ አጨባበጥ ምን እንደሆነ ስታውቂ፣ የማንን ዘፈን ብዘፍን ለድምፄ ከለር ይስማማል በሚል መምረጥ ትጀምሪያለሽ፡፡ እኔም ይሄ ሲገባኝ የፍቅር አዲስን፣ የብዙነሽ በቀለን፣ የሂሩትን፣ የማርታ ሀይሉን እና የሌሎችንም በመዝፈን ነው ወደራሴ የመጣሁት፡፡ የሂሩትን ዘፈን የዘፈንኩት የተለየ ምክንያት ኖሮኝ ሳይሆን ዘፈኖቹን በጣም ስለምወዳቸው ነው፡፡ ናይት ክለብ (የምሽት ክለብ) ውስጥ ረዘም ላለ ጊዜ እንደመስራትሽ ብዙ ገጠመኞችና ፈተናዎች ይኖሩሻል ብዬ አስባለሁ፡፡

እስኪ ከገጠመኞችሽ ጥቂት አውጊኝ? ናይት ክለብ ስሠራ የተለየ የገጠመኝ ነገር የለም፡፡

ግን አምሽቼ ስወጣ ቤቴ ሩቅ ስለነበር ለመሄድ እቸገር ነበር፡፡ የሚያደርሰኝ ሰርቪስ የለም፡፡ ፈረንሳይ ለጋሲዮን ድረስ መሄድ ለእኔ ትልቅ ፈተና ነበር፡፡ አንዳንዴ ጓደኛዬ ቤት ሳድር ቤተሰቤ ይጨነቃል፡፡ በግድ ነው እንጂ እንድሠራም አይፈቀድልኝም ነበር፡፡ ሌላው በወቅቱ ተማሪ ስለነበርኩኝ ደብተር ይዤ ናይት ክለብ የምሄድበት ጊዜ በርካታ ነበር፡፡ በተለይ ፈተና የደረሰ ሰሞን አንድ እዘፍንና እንደገና ደብተር ይዤ እቀመጣለሁ፡፡ በዚህ መልኩ ነው 12ኛ ክፍልን የጨረስኩት፡፡ ከዛ በተረፈ ናይት ክለብ ስትሠሪ የሚወድሽ ይኖራል ወይም የሚናደድብሽ ይኖራል፡፡ በርቺ አሪፍ ነው የሚልሽ ይኖራል፡፡ የሚያመናጭቅ ይኖራል፤ ይሄን ሁሉ አልፌያለሁ፤ የተለየ ገጠመኝ ግን የለኝም፡፡

ስለ ብሔራዊ ቴአትር ቤት ቆይታሽ እናውራ፡፡

ብሔራዊ ቴአትር ቤት ታሪካዊና ቀዳማዊ እንደመሆኑ እዛ በቋሚነት ለመቀጠር ብዙ እንደሚለፋ ሰምቻለሁ አንቺ እድሉን አግኝተሽ ለስምንት ወይም ለሰባት ዓመት ያህል ሰርተሽ እንደገና በራስሽ ፈቃድ መልቀቅሽን ነው የሰማሁት እንዴት ለቀቅሽ? እውነት ለመናገር ብሔራዊ ቴአትርን በጣም ነው የምወደው፡፡ ስገባም ፀልዬ ፈጣሪዬን ለምኜ እንደውም ተስዬ ብል ነው የሚቀለኝ፤ እንደዛ ነው የገባሁት፡፡ እንዳልሽው ብሔራዊ ቴአትር ቤት ትልቅ ቤት ነው፤ ብዙ ባለሙያዎችን ያፈራ ነው፤ አሁንም ብዙ ሙያተኞች አሉት፡፡ በዛን ሰዓት ከክበብ ተነስሽ በአንዴ ቴአትር ቤት መግባት ትልቅ ነገር ነው፡፡ ይሄ ከዛሬ ዘጠኝና አስር ዓመት በፊት ነው፡፡ እዛ በመስራቴ እና የታሪኬ አንድ አካል በመሆኑ ደስተኛ ነኝ፡፡ በወቅቱ 20 ሰው ተወዳደረ፤ የሚፈለገው ግን አንድ ሰው ነበር፡፡ ምንም እንኳ ማስታወቂያውን አይቼ መጀመሪያ ብመዘገብም የፈተናው ቀን ግን በጣም አረፈድኩኝ፡፡

በምን ምክንያት?

ባስ አጥቼ ሁሉም ሰው ተፈትኖ ካለቀ በኋላ ደረስኩኝ፡፡ ከዚያም ፈታኞቹን እባካችሁ ብዬ ለምኜ፣ እስኪ እንያት ተብሎ እድል ተሰጠኝ፤ ግን ፈጣሪ ተጨምሮበት ፈተናውን አልፌ ተቀጠርኩኝ ማለት ነው፡፡ በወቅቱ ስትቀጠሪ በድምፃዊነት ነበር፡፡ ከዚያ ቴአትርም ሰርተሻል፤ ኧረ ተወዛዋዥም ነበርሽ ነው የሚባለው፡፡ እውነት ነው?

ለመጀመሪያ ጊዜ የተጫወትሽውን ቴአትርም በዚያው ንገሪኝ …?

እርግጥ የተቀጠርኩት በድምፃዊነት ነው፡፡ ቴአትር ስሠራ አይተውኝም አያውቁም፡፡ ነገር ግን የቀበሌ ክበብ ውስጥ ቴአትር እሠራ ነበር፡፡ ሲራክ ታደሰ ያዘጋጀው “ልደት” የተሰኘ ትርጉም ቴአትር ነበር፡፡ በወቅቱ ካስት ሲያደርጉ “ይህቺ ልጅ ያቺን ገፀ ባህሪ ታመጣታለች” ብለው መረጡኝ፤ ስፈተንም አለፍኩኝ፤ እሱን ቴአትር ስጫወት ከእነ አርቲስት ጌታቸው ደባልቄ፣ ተስፋዬ ገ/ሀና፣ ትዕግስት ባዩ፣ ሱራፌል ወንድሙ ጋር ነበር፡፡ እነዚህ ትልልቅ አርቲስቶች ናቸው፡፡ በቴሌቪዥን አይቼ ከማደንቃቸው ጋር በአንዴ ተቀላቀልኩኝ፡፡ ቴአትሩ ለአንድ አመት ታይቷል፡፡ ከዛም በኋላ በደብል ካስት ልምምድ አደርግ ነበር፡፡ “ልደት” ቴአትር ላይ በጣም ተሳክቶልኛል፡፡ እንደነገርኩሽ በክበብ ደረጃ ድምጽም፣ ቴአትርም፣ ውዝዋዜም እሠራ ነበር፡፡ ውዝዋዜውን የተውኩት አጭር ስለሆንኩ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ “አንድ ምሽት” የሚል ቴአትር የጐዳና ሴተኛ አዳሪ ሆኜም ሰርቻለሁ፡፡ ትንሽ ክፍል ብትሆንም ስጫወት ጥሩ ነበርኩኝ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያልኩ ነው የቆየሁት፡፡

ታዲያ እንዴት ቴአትር ቤቱን ለቀቅሽ?

እንደምታውቂው የሰው ልጅ አንድ ቦታ ላይ አይቆምም፡፡ ፍላጐት እየጨመረ ሲሄድ ነገ የተሻለ ነገር ማግኘት ይፈልጋል፡፡ እኔም የማደግ የመለወጥ ተስፋ ነበረኝ፡፡ እዚያው ቴአትር ቤት እያለሁ “እርጂኝ አብሮ አደጌ” የተሰኘው ከትዕግስት ፋንታሁን ጋር የሠራሁት አልበም ወጣ፡፡ ከዚያ በኋላ ለስራ ወደ ውጭ እፈለግ ጀመር፡፡ ፈቃድ ወስጄ ወጣ ብዬ ሠርቼ እመለስ ነበር፡፡ በመሀል ነጠላ ዜማም መስራት ጀመርኩኝ፡፡ በመጨረሻ “ሙሽራዬ ቀረ” አልበሜ ወጣ፡፡ በዚህ ጊዜ ከበፊቱ የበለጠ የውጭ ጥሪዎች መብዛት ጀመሩ፡፡ አንዴ አረብ አገር፣ አንዴ አውሮፓ ማለት ጀመርኩኝ፡፡ በመጨረሻ ግን አሜሪካ የተጠራሁበት ሥራ የስድስት ወር ስለነበር ፈቃድ አልሰጡኝም፡፡ እንደነገርኩሽ መለወጥ ማደግ ስለምፈልግ፣ ለስድስት ወር የምትሄጂ ከሆነ ትለቂያለሽ የሚል ነገር መጣ፤ እሺ ብዬ ሄድኩኝ ማስታወቂያ ተለጠፈብኝ፤ በዚህ ምክንያት ነው ቴአትር ቤቱን የለቀቅኩት፡፡ እንደሰማሁት ሰሞኑን ያንቺን ህይወት የሚዳስስ፣ ግለ ታሪክሽን የሚናገር ዘጋቢ ፊልም (ቪዲዮ) እያሠራሽ ነው፡፡ ስለሱ ጉዳይ ትንሽ ብታብራሪልኝ?

እዚህ አገር የተለመደው አንድ ሰው ሲሞት ታሪኩ ከዚህም ከዚያም ተለቃቅሞ ለአንድ ጊዜ ብቻ እከሌ በዚህ ጊዜ ይህን ሰራች (ሠራ)፣ የህይወት ዘመኑ ይህን ይመስላል ተብሎ በዚያው ይረሳል፡፡ ይሄ ከሚሆን አንድ ሰው በህይወት እያለ ትክክለኛ ግለ ታሪኩ የት ተወልዶ የት አደገ፣ የት ተማረ፣ በህፃንነቱ ምን አይነት ሰው ነበር፣ መልኩስ አስቀያሚ ነበር፣ ባህሪውስ? የሚለውን ኦውቶባዮግራፊ ቢያሰራ ጥሩ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ በአንድ በኩል ደግሞ ፕሮሞሽንም ነው፡፡ ምናልባት አበባን ሰው የሚያውቃት “እርጂኝ አብሮ አደጌ”ን ከሠራች በኋላ ሊሆን ይችላል፤ ከዚያ በፊት የነበራትን ነገር አያውቀውም፤ ምን አይነት ፈተናዎችን አልፋለች፣ አይናፋር ነበረች ወይስ በልጅነቷ ረባሽ ነበረች፣ በትምህርቷስ ውጤቷ ምን ይመስል ነበር፣ የሚሉትንና መሰል ጉዳዮችን ሰው ቢያውቀውና ከአሁኑ ማንነት ጋር ቢያስተያየው ደስ ይላል በሚል ቪዲዮውን እያሰራሁ ነው፡፡ አንቺ አሁን ገና ከወጣትነቱ አልወጣሽም፤ ከአንቺ ብዙ ስራዎች ይጠበቃሉ፤ የግለ ታሪኩ ስራ ትንሽ አልፈጠነም?

እንዳልሽው ብዙ ይጠበቃል፤ ያኔ አሁን በተሰራው ላይ እየተጨመረ ስለሚሄድ አሁንም ቢሠራ ችግር አለው ብዬ አላስብም፡፡ አሁን መሠራቱ እንደውም ወደፊት በእኔ መንገድ መጓዝ ለሚፈልግ ብዙ ትምህርት ይሆነዋል፡፡ በአንድ ነጠላ ዜማ ተነስቶ ታዋቂ መሆን እንደማይቻል፣ ብዙ ውጣ ውረድ እንዳለ፣ እንዴት መታለፍ እንደሚችል ይማሩባታል ብዬ አስባለሁ፡፡ በተረፈ ቅድም እንዳልኩሽ በልጅነቴ ያለው ነገሬ የሚያስቅም ነገር ይኖረዋል እና የሚያዝናና ይሆናል፡፡ ለምሣሌ የዱሮ ፎቶዬን ሲያዩ “እንዴ አባባ እንደዚህ አስቀያሚ ነበረች?” አሊያም “ወይኔ ስታምር” የሚሉ ይኖራሉ እና ሊያዝናና ይችላል ብዬ አስባለሁ፡፡

“እርጂኝ አብሮ አደጌ”ን ከዘመድሽ ከትዕግስት ፋንታሁን ጋር ሠርታችሁ ተወዶላችኋል፤ ከዚያ በኋላ አብራችሁ አላየናችሁም፡፡ ለምን ቆመ?

የሚገርምሽ የቆመ ነገር የለም፡፡ በእኔና በቲጂ መካከል ያለው ግንኙነት የቆመ ይመስላል እንጂ አልቆመም፡፡ እንሠራለን፣ በየቀኑ እንገናኛለን፣ በየጊዜው እንደዋወላለን፡፡ ነገር ግን የህይወት መንገድ አንዳንዴ አስቸጋሪ ነው፡፡ በተለይ ባለ ትዳር ስትሆኚ፣ ልጅ ስትወልጂና የቤተሠብ ሀላፊ ስትሆኚ ቤቴን ቤቴን ይመጣል፣ ወይ እኔ ተነስቼ ለስራ አንዱ አገር እሄዳለሁ፣ ቲጂም ተነስታ ወይ አሜሪካ ትሄዳለች፡፡ አየሽው አሁን የህይወት ጐዳና ወዲያና ወዲህ እንደሆነ፡፡ በዚህ ምክንያት እንደድሮው ተረጋግቶና ተጣምሮ ለመስራት ይከብዳል፡፡ ሩጫው አልገጣጠም ብሎን ነው ያልሠራነው፤ በሌላው ግንኙነታችን አብረን ነን፡፡ አሜሪካም በአንድ ወቅት አብረን ሠርተናል፡፡ ለምሣሌ የዛሬ ሁለት ዓመት አሜሪካ አንድ ቤት ነበርን፤ አብረን ሠርተናል፤ ቱር አብረን ነበር የምንወጣው እና ይሄን ይመስላል፡፡ “ሙሽራዬ ቀረ” የተሠኘውን ዘፈን ስትጫዎቺ ሙሽራዉ የእውነት የቀረ ያህል ስሜትን ጨምድዶ ይይዛል፡፡ ለዘፈን ብለሽ ሳይሆን የደረሠብሽ ነው የሚመስለው፡፡ ሙሽራ የቀረበት ዘመድ ወዳጅ አጋጥሞሻል ወይስ በቅርብ የምታውቂው ጉዳይ አለ?

የህዝቡስ ምላሽ ምን ይመስላል?

የሚገርምሽ ነገር “ሙሽራዬ ቀረ” በጣም ተፅዕኖ የፈጠረ ስራ ነው፡፡ አሁንም ድረስ ወይ ከአብርሽ ጋር (ባለቤቷ ነው) ሲያዩኝ ወይም የጋብቻ ቀለበቴን ሲያዩት “ኮንግራ ሙሽራው ተገኘ?” ይሉኛል፡፡ በእኔ ላይ ደርሶ የዘፈንኩት የሚመስላቸው አሉ፡፡ በአጋጣሚ ሀሣቡ መጣ፣ አብርሽ ፃፈው፤ ሮማን አየለ ዳይሬክት ስታደርገው የባሠ ነፍስ ዘራና እንዲህ አነጋጋሪ ዘፈን ሆነ፡፡ በጣም ተመስጬ የእውነት አስመስዬ የሠራሁት ቁጭ ብዬ ስሜቱን አስበው ስለነበር ነው፡፡ ይሄ ዘፈን በወጣ ሠሞን ብዙ ሙሽሮች ቀርተው፣ ድግስ አበላሽተው በ“ፖሊስና ህብረተሠብ” ፕሮግራም ላይ መመልከት ጀምረን ነበር እኮ፡፡ አጋጥሞሻል?

አጋጥሞኛል፤ አይቻለሁ፡፡ እኛ ባንሠማና ባናይ በየቦታው ይሄ ነገር ይከሠታል፡፡ እስኪ አስቢው የእኛን አገር ባህል? አንድ ሴት ተዘጋጅታ ድግስ ተደግሶ፣ ወዳጅ ዘመድ ተሠብስቦ፣ ሙሽራው ሲቀር ምን ያህል እንደሚያሸማቅቅ፡፡ በዘፈኑ እኔ መንገድ ስከፍት፣ ብዙ ሠው ሙሽራው እንደቀረ በክስ መልክ መናገርና ፖሊስም ለማስተማር በቴሌቪዥን ሲያሣየን ነበር፤ ብቻ ዘፈኑ የማንንም ቤት ሊያንኳኳ የሚችል፣ ያንኳኳባቸውንም ብሶት የቀሠቀሠ ስለሆነ በጣም ተወዶ ተደምጧል፡፡

ከሙዚቃና ቴአትር ባሻገር በ “ሩሃማ” እና “ሠካራሙ ፖስታ” ላይ በፊልም ትወና ብቅ ብለሽ ነበር፤ አሁን እልም ብለሻል፡፡ ማስታወቂያም ላይ ተመልክተንሻል፤ አሁን እሱም የለም፣ እንደገና በበጐ ፈቃድ አገልግሎት እንደምትሳተፊ ሠምቻለሁ? እስቲ በዚህ ዙሪያ አውጊኝ… ከፊልሙ እንነሣ፡፡ “ሩሀማ” ፊልም ላይ ያው ሩሃማን ሆኜ ተጫውቻለሁ፡፡ ፊልሙን አይተሽው ከሆነ ሩሀማ በጣም የምታሣዝን ሴተኛ አዳሪ የነበረች ከዚያ የህይወት ብርሀን ያየችና ያ ብርሀን መልሶ የጠፋባት ሴት ናት፤ ጥሩ ተሳክቶልኝ ሠርቼዋለሁ፡፡ እኔ እንደዚህ አይነት ገፀ-ባህሪ አይከብደኝም፡፡ ለምን ብትይ በተፈጥሮዬ አልቃሻና ሆደ ባሻ ነኝ፡፡ ፊቴም ለዚያ አይነት ባህሪ ምቹ ስለሆነ መሠለኝ እዛ ቦታ ላይ የሚመድቡኝ፡ ፊልሙን ትተሽ “እርጂኝ አብሮ አደጌ”ን አስቢው፤ እዛ ላይ ተጨንቄ ፊቴ እንደሚያሣዝን ነው የሚታየው፡፡ “ሠካራሙ ፖስታ ላይም እንዲሁ አሳዛኝ ሴት ሆኜ ነው የሠራሁት፡፡ ይህቺ ሴት ኤች አይቪ በደምሽ ውስጥ አለ ተብላ፣ ራሷን ከማህበረሠቡ ለማግለል ገዳም የምትገባ ግን ከገዳም የሚመልሣት ሠው ያገኘች ሴት ናት፡፡ ሁሉም ላይ እንዲህ አሣዛኝ ክፍል ላይ ነው የሚመርጡኝ፡፡ ማስታወቂያን በተመለከተ ብዙ ባልገፋም ሞክሬያለሁ፡፡ ሁለት ወይ ሶስት ማስታወቂያ ነው የሠራሁት፡፡ አንዱ በፊት ነው፤ አለሙ ገ/አብ ነፍሱን ይማረውና መርጦኝ፣ ጋሽ ውብሸት ወርቅአለማሁ ጋ ለእንቁጣጣሽ በዓል ከጓደኞቼ ጋር ስንዘፍን፣ እኔ ከጐጆ ቤት ወጥቼ ሠንደል ሳጨስ እታያለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ከሠራዊት ፍቅሬ ጋር አምባሣደር ልብስ ላይ ሠርቻለሁ፡፡ ብቻ ብዙ የሚወራለት አይደለም ማስታወቂያው፡፡ ፊልሙ አሁን ቆሟል፡፡ ብዙ ትኩረቴን ያደረግሁት አልበሙ ላይ ነው፡፡ በመሀልም ያው በስራ ምክንያት አሜሪካ ስድስት ወር እሠራለሁ፣ እመጣለሁ፡፡ እንደዚህ ሆነና ግጥም ዜማ ስሠበስብ በቃ ፊልሙ ተረሣ፤ ነገር ግን የመስራት ፍላጐት አለኝ፡፡ በጐ ፈቃደኝነትን በተመለከተ “እናት ለምን ትሙት” ዘመቻ ላይ “እችላለሁ” የሚል ዘፈን ሠርቻለሁ፡፡ ከሌሎችም አርቲስቶች ጋር የበጐ ፈቃድ ዘፈኖችን ሠርቻለሁ፡፡ ወደፊትም የበጐ ፈቃድ ሥራ የመስራት ፍላጐት አለኝ፡፡ አሁን በአልበሙ ስራ ሩጫ ላይ ስለሆንኩ እንጂ እቀጥላለሁ፡፡ በተለይ በትራፊክ ችግር፣ በእናቶች ሞት፣ በህፃናት መደፈርና በመሠል ማህበራዊ ችግሮች ላይ የመስራት ፍላጐት አለኝ፡፡ ከአልበሙ በኋላ እመለስበታለሁ፡፡ አሁን ወደ አዲሱ ሥራሽ እንምጣ በቅርቡ ከአሜሪካ የመጣሽው አዲስ አልበም ልታወጪ መሆኑን ሰምቻለሁ…

አዎ፡፡ አሜሪካ ስራ ላይ ነበርኩኝ፡፡ ከስራዬ ጐን ለጐን ለአልበሜ ግጥምና ዜማ እዛም ካሉ ባለሙያዎች ስሠበስብ ነበር፡፡ አሁን በጣም ጥሩ የሆነ የተለያየ ስብስብ፣ ባህልም ዘመናዊም፣ ጉራጊኛም ያካተተ ሥራ ሠርቻለሁ፡፡ ሠውም በጉጉት እንደሚጠብቅ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ የአልበምሽ መጠሪያ “የለሁበትም” ይሠኛል፡፡ ከምኑ ነው የሌለሽበት?

የለሁበትም እንግዲህ… አንቺ ከብዙ ነገር የለሁበትም ልትይ ትችያለሽ፤ ነገር ግን ይሄ ዘፈን የፍቅር ዘፈን ነው፡፡ ትክክለኛ ሀሣቡ በትዳር ወይም በጓደኝነት ብቻ በፍቅር ውስጥ ያለች ሴት ናት፡፡ ነገር ግን ባሏ ወይም ፍቅረኛዋ እሷን አይንከባከባትም፤ ጊዜ አይሠጣትም፤ ብቻ እንደ ፍቅረኛ ከጐኗ አይሆንም፡፡ የእሷን ድካም ፍቅር አይረዳም፤ ስለዚህ “እባክህ ከእኔ ጋር ከሆንክ አብረን ፍቅራችንን እናጠንክር፤ እምቢ ብለህ እኔ ሀሣቤን ብቀይር በኋላ የለሁበትም” በሚል ነው የምታስጠነቅቀው፡፡

አልበምሽ በዋናነት በምን ላይ ያተኩራል?

ሁሉንም ያካትታል፡፡ ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ ከከተማ እስከ ገጠር የሚዳስስ ነው፡፡ አሁን ስለ ገጠሩ ህይወት የሚዳስስ “ባጥ አሣቅሉኝ” (ጐጆ አቃልሱኝ) እንደማለት ነው፡፡ አይነት ደስ የሚል ዘፈን ሁሉ አለው፡፡ ይህ ዘፈን የአገሬው ሠው ሆ ብሎ ቤት እንዲያሳራት የምትማጠንበት ነው፡፡ ሁለት የሂሩት ዘፈኖች ተካተውበታል፣ “ተረት ተረት”፣ “ቸር ወሬ” የሚሉና ሌሎችም ምርጥ ምርጥ ዘፈኖች ተካተዋል፡፡ በአጠቃላይ 13 ያህል ዘፈኖች አሉት፡፡ አዲስ ሥራ ሲሠራ እነማን ተሳተፉ የሚል የተለመደ ጥያቄ አለ፡፡ አንባቢም ስለሚጠብቅ በግጥም፣ በዜማ፣ በቅንብር ማን ማን እንደተሳተፈ ንገሪኝ? ጌራወርቅ ነቃጥበብ፣ ተመስገን አፈወርቅ፣ አስቻለው ዲሮ በዜማ ተሣትፈዋል አብርሽም በግጥም ተሣትፏል፤ ሁለት ዜማም አለው፡፡ ሄኖክ ነጋሽ የሁለት ባህላዊ ዘፈኖች ዜማ ሠጥቶኛል፡፡ ደሣለኝ መርሻ የተሳተፈበት ጉራጊኛ አለኝ፡፡ የሂሩትን ሁለቱን ስሠራ አንዱ ላይ አርቲስት ተስፋዬ አበበ (ፋዘር) በግጥም ተሣትፎበታል፤ ሻምበል መኮንንም ተሣትፎ አድርጐበታል፡፡ ሌሎች ባለሙያዎች ተሣትፈዋል፡፡ ሌሎች ባለሙያዎችም ተሣትፈዋል፡፡ ቅንብሩስ…? ካሙዙ ካሣ አራት ዘፈኖችን፣ አስቻለው ዲሮ ሶስት፣ ሄኖክ ነጋሽ አንድ ዘፈን፣ እያሱ እስራኤል አለ፤ ተሾመ ጥላሁን፣ አሸብር ማሞ እና ኢዮብ ፋንታሁን ያቀናበሩት ሲሆን ሚክሲንጉን አስቻለው ዲሮ ሠርቶታል፡፡ በአጠቃላይ ብዙ ደክሜበታለሁ፡፡ ወጪውም ወገቤን የሚያሠኝ ነው፡፡ ከወጪው ባሻገር ከተለያየ ባለሙያ ጋር ሲሠራ ብዙ ስሜቶችን አስተናግዶ፣ ታግሶ ማለፍ አስፈላጊ በመሆኑ ፈታኝ ነበር፡፡ አሜሪካ ሲሄድ ስመጣ ብቻ ወደ ሁለት ዓመት ፈጅቷል፡፡ ገንዘቡ፣ ጉልበት፣ የሠዎች ትብብር ሳይጨመር እንኳን ከባድ ነው፡፡ አሁንም ወጪ ላይ ስለሆንኩ ይሄን ያህል አውጥቼአለሁ ልልሽ ግን አልችልም፡፡ የማሣትመውም ራሴ ነኝ፡፡ ኮከብ ሙዚቃ ቤት ለማከፋፈል ስምምነት አለን፡፡

መቼ እንጠብቅ?

እኛ እግዜር ከፈቀደ ለፋሲካ ብለናል፡፡ በሩጫ ላይ ነን፡፡ እንግዲህ ማስተሪንግ የምናሠራባቸው ህንዶች ሠሞኑን ሲዲ አልቆብናል ብለውናል፤ ግን አሁን እናስመጣለን ብለዋል፡፡ እሱ ካለቀልን ለፋሲካ አሪፍ ስራ እናበረክታለን፡፡ ለአንዳንዶቹም ዘፈኖች ክሊፕ እየሠራሁ ነው፡፡ ከስራሽ ወጣ እንበልና ስለ አንቺና ስለ ባለቤትሽ አብርሀም (አብርሽ ዘጌት) ትንሽ እናውራ ይቻላል፡፡ በፊት ጥሩ ወንድምና እህት ሆናችሁ፤ ረጅም ጊዜ ቆይታችሁ በሠዎች ወሬ ባልና ሚስት ሆናችሁ ይባላል፡፡ እንደውም “ወሬውን ሠምቻለሁ” የተባለው ነጠላ ዜማሽ የተዘፈነው ከዚሁ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ነው ይባላል፡፡ ምን ያህል እውነት ነው? እንዳልሽው እኔ እና አብሪ ግንኙነታችን ክለብ ውስጥ ነው፡፡ እኔም ልዘፍን እሱም ሊዘፍን መጥቶ ማለት ነው፡፡ የሚገርምሽ ግን ሁለታችንም የፈረንሳይ ልጆች ሆነን ግን አንተዋወቅም ነበር፡፡ እሱ የአቦ ሠፈር ልጅ ነው፤ እኔ 07 ቀበሌ ነኝ ግን አንተዋወቅም፡፡ ካዛንቺስ “አልማዝ ላሊበላ” የተባለ ክለብ ነው የተገናኘነው፡፡ ከዚያ ሌሎች ቤቶችም አብረን በመስራት በወንድምነትና እህትነት ረጅም የጓደኝነት ጉዞ አድርገናል፡፡

ግን የሆነ ሠዓት ላይ ዝም ብለን ትዳር አደረግነው እና ህይወት ቀጠለ፡፡ የጠበሠም የተጠበሠም የለም እያልሽኝ ነው? (ሣ…ቅ) አዎ የጠበሰም የተጠበሠም፣ የጠየቀም የተጠየቀም የለም፡፡ እኛ ከፍቅር ግንኙነት ውጭ በጣም ጓደኛሞች ሆነን ስንኖር ሠዎች ዝም ብለው ያወሩ ነበር፡፡ ይሄም አንድ ምክንያት ነበር፡፡ እንዳልሽው “ወሬውን ሠምቻለሁ አሜን ይሁን ብያለሁ” የተሠኘው ነጠላ ዜማም ከዚሁ ጋር ግንኙነት አለው፡፡ ሠርግም ግርግርም የለም፤ ከዚያ ክርስቲያን አብርሀም ተወለደች፤ እሷው አጋባችን፡፡ አሁን አምስት አመት ሞላት፡፡ ለክርስቲያን ወንድምና እህት አልሠጣችኋትም? አዎ ገና አልመጣም፡፡ ምክንያቱም ሩጫው ትኩረት እንድንሠጥ አላደረገንም እና አላሠብንበትም፡፡ ተወልደሽ ያደግሽው እውቁ አትሌት ዋቢ ቢራቱ ሠፈር በመሆኑ ሯጭ ትሆኛለች ተብሎ ሲጠበቅ አንቺ ዘፋኝ ሆነሽ አረፍሽው… በመሠረቱ ከፈረንሳይ ብዙ ጥበበኞች ወጥተዋል፡፡ ሁሌ “ከውሀው ነው መሠለኝ” እንላለን፡፡ ትንሿ የኢትዮጵያ ሆሊውድም ትባላለች፡፡ ከያኒ፣ ጋዜጠኛ፣ ሯጭ ብቻ ጥበበኞች አሏት ፈረንሳይ፡፡ እኔ እንደ ዋሚ ቢራቱ ሯጭ ባልሆንም ዘፋኝ ሆኛለሁ ለማለት ነው፡፡ በመጨረሻ ከ “የለሁበትም” አልበምሽ ምን ትጠብቂያለሽ? እኔ ጥሩ ነገር እጠብቃለሁ፡፡ ሁሉንም ያማከለ ስራ ነውና፡፡ ወጣቱም ጐልማሣውም ሊያዳምጠው የሚችለው ስራ ነው፡፡ ከእኔ ጋር ብዙ የደከሙ ባለሙያዎች፣ ጓደኞች፣ ባለቤቴ አብርሽ በጣም ሊመሠገኑ ይገባል፡፡ ቢጂ አይ ኢትዮጵያንም አመሠግናለሁ፡፡ እና አሪፍ ነገር አለ ብዬ ነው የምጠብቀው፡፡ “አንቺ የለሁበትም” እንዳልሽው፣ አልበምሽን አሪፍ አድርገሽ ባታመጪ “እኛም የለንበትም”… አብረን የምናየው ይሆናል፡፡ በጣም አመሠግናለሁ ሙናና፡፡ እኔም ከልብ አመሠግናለሁ፡፡

Saturday, 20 April 2013 12:44

ቀረች ቢሉኝ

ለካ ከልቤ እወድሽ ነበር
ለካስ ከልቤ አፈቅርሻለሁ
ከእውነት እንደማስብሽ
ከአንጀቴ እንደናፈቅኩሽ
ዛሬን ለኔ አውቄዋለሁ፡፡
ዛሬን ነገን ትመጪ እያልኩ
ቀን ስቆጥር እየኖርኩኝ…
አንቺን ከማሰቤ ጋር
አንቺን ከናፍቆቴ ጋር
እያሰብኩሽ እያለምኩ
መልክሽን ይዤ እየዋልኩ
ሰውነትሽን ይዤ እያቀፍኩ
ሳወራልሽ እያደርኩኝ…
ዛሬ ነገ ላገኝሽ
ቀኔን ስቆጥር እየኖርኩኝ
ቀረች ቢሉኝ
መቼ ደርሰሽ
መች አግኝቼሽ
የልቤን ቃል
ላጫውትሽ፡፡
እስክትመጪ አጠራቅሜ
አስቀምጬ ያቆየሁሽን
የፍቅራችንን ምስጢር
ተቃቅፈን “ምናወራትን
ምንንሾካሾካትን
መቼ ደርሰሽ እያልኩ እኔ
ቀኑ ረዝሞ ሌ ቱ ጨንቆኝ
ላንቺ ብዬ ተካፍዬ
ለሌላ የማልነግረውን
ጭንቀቴን ሃሳቤን ሁሉ
ሳሰላስል የኖርኩትን
ሳላዋይሽ ቀረች ቢሉኝ
ምን ሊውጠኝ?
ታህሳስ 18/1980
(“ሶረኔ” ልዩ ልዩ የበረሃ ግጥሞች
ከሚለው መድበል የተወሰደ)

በር አባ ዳዊት ወርቁ የተፃፈው “The Ethics of Zara Yacob” እንዲሁም በአባ ብሩክ ወልደገብር እና አባ ማርዮ አሌክሲስ ፓርቴላ የተዘጋጀው “Abyssinian Christianity. The First Christian Nation?” መጽሐፍ በመጪው ረቡዕ እንደሚመረቁ የቅዱስ ቶማስ አኩዊናስ የኢትዮጵያ ካቶሊክ ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ፡፡ የሁለቱ መጻሕፍት ማስተዋወቂያ ዝግጅት የሚካሄደው አስኮ በሚገኘው የቅዱስ ፍራንሲስ ካቶሊክ ገዳም ካፑቺን ፍራንሲስ የጥናትና ሥልጠና ማእከል አዳራሽ ነው እንደሚከናወን ታውቋል፡፡

ኢትዮጵያን ለሚጐበኙ የውጭ ሀገር ጐብኚዎች የሚያገለግል የመምሪያ መጽሐፍ አሳትሞ ማሰራጨት መጀመሩን “ኬር ኤዢ ኢትዮጵያ” አስታወቀ፡፡ በእንግሊዝኛ እና በእስፓኒሽ ቋንቋ የታተመው የጐብኚዎች መምሪያ መጽሐፍ ግማሽ ሚሊዬን ብር ወጥቶበታል ያሉት አዘጋጆቹ፤ መጽሐፉ ኢንዱስትሪውን ቢያነቃቃም በውጭ ሀገር ታትሞ ወደሀገር ሲገባ የመንግስት ተቋማት አላበረታቱንም ብለዋል፡፡ አብዛኞቹን ማስታወቂያዎችም በነፃ ያሳተሙ መሆናቸውን ለዝግጅት ክፍላችን ተናግረዋል፡፡

በwww.ker_ezhiethiopia.com የሚገኘው መጽሔት 20ሺህ ቅጂ የታተመ ሲሆን ቅጂው ከራስ ሆቴል እና ሌሎች ትልልቅ ሆቴሎች በነፃ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡