Administrator

Administrator

ይድረስ ለኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር
ሰሞኑን ሥርጭቱን በጀመረው “ቃና ቲቪ” ይዘት እና አሰራር ላይ ለመወያየት በደብዳቤ
ባሳወቅናችሁ መሰረት ተወካያችሁን መላካችሁ ይታወቃል፡፡  የኪነ ጥበብ ሞያ ማኅበር ተወካዮቹ (የእናንተም ባሉበት) በተጠቀሰው ጉዳይ ለሁለት የተለያዩ  ቀናት የጋራ ውይይት አካሂደው የጋራ የአቋም መግለጫ ማውጣታቸው ይታወቃል፡፡ ይህ የጋራ  አቋም በፅሁፍና በንባብ ለሚዲያ ከመቅረቡ በፊት የእናንተ ሁለት ተወካዮችን ጨምሮ የሁሉም   የሞያ ማኅበር ተወካዮች መስመር በመስመር በጥንቃቄ ተመልክተው ማሻሻያና ማረሚያ ካደረጉ  በኋላ በጋራ ጋዜጣዊ መግለጫው የተሰጠ መሆኑ አይዘነጋም፡፡ መግለጫ ከመሰጠቱ አንድ ቀን ቀደም  ብሎ (በ20/07/2008) የደራስያን ማኅበር ልሳን በሆነውና ዘወትር ማክሰኞ ምሽት በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 በሚቀርበው ፕሮግራም ላይ የመግለጫውን ፍሬ ሃሳብ ለህዝብ በመግለፅ ሚዲያዎች እንዲገኙ መረጃ ስታደርሱ እንደነበርም ይታወቃል፡፡ይህ ጥሬ ሀቅ ባለበት ሁኔታ ባለፈው ቅዳሜ ሚያዚያ 1 ቀን 2003 ዓ.ም በወጣው የአዲስ አድማስ  ጋዜጣ ላይ የደራስያን ማኅበር ፕሬዝደንት ዶ/ር ሙሴ ያዕቆብ የሰጡት ከእውነት የራቀና የተዛባ  መግለጫ እጅግ የሚያሳፍርና የሚያሳዝን ሆኖ አግኝተነዋል፡፡ የመላው የደራስያን ማኅበር አመራርና አባላት እምነት እንዳልሆነም እናምናለን፡፡ የእሳቸው ማኅበር ተወካይና ሌሎች የጥበብ ማኅበራት በጋራ ተወያይተው ያወጡትን መግለጫ በምን ምክንያትና መነሳሳት ለመካድ እንዳነሳሳቸው ለጊዜው ያወቅነው ነገር የለም፡፡ በሂደቱ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ሲሳተፍ የነበረውን የማኅበራቸውን ተወካይ፤ “መግለጫውን ለመከታተል የተገኘ ነው” በማለት ከደራሲያን ማኅበር ተወካይነት ወደ ሚዲያ ተወካይነት ለውጠው፣ ለጋዜጣው ለመግለፅ ለምን እንደተገደዱም አልተረዳንም፡፡ ከዚህም በላይ ማህበራቱ የቴሌቪዥን ጣቢያውን በሚመለከት እያቀረቡት ካለው አመክንዮና ለህዝብ ከገለፁት አቋም ፈፅሞ የራቀና የማናውቀውን ጉዳይ በመናገር አንባቢን ግራ ከማጋባታቸውም በላይ የማኅበራቱን ጥያቄ ያልተገባ ለማስመሰል መሞከራቸው ከምን በመነጨ አስተሳሰብና ዓላማ እንደሆነ ለጊዜው አልደረስንበትም፡፡ በእሳቸውና በመላው የጋዜጣዊ መግለጫው ተሳታፊ በነበሩ የሚዲያ አካላት እጅ በሚገኘው ባለ አምስት ገፁ የሞያ ማኅበራቱ የአቋም መግለጫ በየትኛው አንቀፅ ላይ ይሆን የሳንሱር ጉዳይ የተነሳው!? የኢትዮጵያ ደራስያንን እወክላለሁ የሚል
የማኅበር ፕሬዚደንት የተፃፈን ፅሑፍ አንብቦ መረዳት ተሳነው ቢባልስ ማን ያምን ይሆን!? የሆነስ
ሆነና “እነ በዓሉ ግርማን የመሳሰሉ ፀሐፍት በሳንሱር ምክንያት የሕይወት መስዋዕትነት ከፍለዋል”
ማለታቸውስ የደራስያን ጉዳይ ጉዳዬ ነው ብሎ የፕሬዚደንትነት ሥልጣን ከተቆናጠጠ ግለሰብ ይጠበቃል ወይ!? ሌላው ቢቀር የደራስያን ማኅበር የአመራር አባል በነበረው ደራሲ እንዳለጌታ  ከበደ ጥልቅ ጥናትና ምርምር የታተሙትን “ማዕቀብ” እና “የበዓሉ ግርማ ሕይወትና ሥራዎች” የተሰኙ በብዙዎች የተነበቡ መፃሕፍትን ቢያነቡ ኖሮ በዓሉ ግርማን ጨምሮ በኢትዮጵያ ውስጥ በሳንሱር ምክንያት የሕይወት መስዋዕትነት የከፈለ (የተገደለ) አንድም ደራሲ እንደሌለ በተረዱ ነበር፡፡ እንደሚታወቀው የኪነ ጥበብ ሞያ ማኅበራቱ በመግለጫቸው ያሉት ዋና ፍሬ ሀሳብ ዶ/ር ሙሴ በስህተት አልያም በችኮላ ተረድተው እንዳሉት ሳይሆን “ቃና” ቴሌቪዥን ለውጭ ሀገር ፕሮግራሞች የሰጠው (70%) ተገቢ አይደለም የሚል ነው፡፡ ይህ ሀሳብ የሳንሱር ሳይሆን በሀገር ውስጥ፣ በሀገር አቅም በሚሰሩ ፊልሞች ላይ ጫና ፈጥሮ ፍትሀዊ ተወዳዳሪነት እንዳይኖር በማድረግ፣ ዳዴ በማለት ላይ ያለውንና የብዙ ዓይነት ጥበቦችና ባለሙያዎች ውህደት ውጤት የሆነውን የኢትዮጵያ ሲኒማ አቀጭጮ ያጠፋል፣ አዲስ ለሚከፈቱ ጣቢያዎች በቀላሉና በውስን ሰዎች ሳይለፉ ገንዘብ እንደሚሰራ በማሳየት በመስኩ የተሰማሩ የኢትዮጵያ ዜጎች በሀገራቸው ስለ ሀገራቸው ጉዳይ የሚተርክ ፊልም በመስራት እንዳይጠቀሙና ሞያውን እንዳያሳድጉ እንቅፋት ይሆናል፣ ህዝብን የሚያረካ ሥራን የሰሩና ይሁንታን በማግኘት የተደነቁ ባለሙያዎችም ዝናቸውን በመጠቀም የደሀ
ህዝባቸውን ችግር ለመቅረፍ በሚደረጉ የማኅበራዊ አገልግሎቶች ላይ የሚያደርጉትን በጎ እንቅስቃሴና ቅስቀሳ ተፅዕኖ አልባ በማድረግ ያዳፍነዋል የሚል ነው፡፡ በእግረ መንገድም ፊልሞቹ በአብዛኛው ከምዕራባውያን የሚመጡ እንደመሆናቸውና የሚተላለፈው ለቤተሰብ ቅርብ በሆነው የቴሌቪዥን ሚዲያ በኩል ከመሆኑ አንፃር አጉል ባህል በቀላሉ ታዳጊ ህፃናትና ልጆች ላይ እንዳይሰርፅ ሥጋታችንን የገለፅንበት ነው፡፡ የኪነ ጥበብ ሞያ ማኅበራቱ በጋራ ባካሄዱት ውይይት ዶ/ር ሙሴ የእሳቸውን ማኅበር በመወከል በተገኘው ግለሰብ እምነት ከሌላቸው፣ ከቢሮአቸው በአራት እርምጃ ከሚርቀው የጋራ ማኅበራቱ
መሰብሰቢያ ቢሮ በመምጣት ጉዳዩን ማጣራት ይችሉ ነበር፡፡ አልያም በአሁን ሰዓት የደራስያን አመራር አባል የሆኑት የሥራ ባልደረባቸው በዚሁ ጋዜጣ ሚያዝያ 26 ቀን 2008 ዓ.ም የፃፉትን ጥልቅና ለብዙዎች ስለ ጉዳዩ የበለጠ ግንዛቤ ያስጨበጠ ፅሑፍ ቢቻል አንብበው ካልሆነም ካነበበ ሰምተው አስተያየታቸውን ቢሰጡ ኖሮ ትዝብት ላይ የሚጥል ስህተት ባልሰሩ፣ መልካም ሥም የነበረውን ማኅበራቸውንም ባላቀለሉ ነበር እንላለን፡፡
(ተፃፈ፡- ከ “የኢትዮጵያ  የኪነ ጥበብ ማኅበራት
ጊዜያዊ አስተባባሪ”)

• ፓርቲው የውስጥ ችግሩን መፍታት ለምን ተሳነው?
• ለፓርቲው ቀውስ ተጠያቂው ማን ነው?
• የመበታተን አደጋ ያሰጋው ይሆን ?
ሰማያዊ ፓርቲ በተለይ ሊቀመንበሩና ሌሎች አመራሮች መዝብረዋል የተባለውን ገንዘብ መነሻ በማድረግ በአጋጅ ታጋጅ ድራማ ታጅቦ በቀውስ
እየተናጠ ይገኛል፡፡ በፓርቲው ችግሮች፣ በመፍትሄዎቹ፣ በፓርቲው የወደፊት እጣ ፈንታና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ
አለማየሁ አንበሴ ከሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ጋር ጥልቀት ያለው ቃለምልልስ አድርጓል፡፡ እነሆ፡-

     ሰማያዊ ፓርቲን ----- ከምርጫ 2007 ዓ.ም በፊትና በኋላ እንዴት ይገልጹታል?
አሁን ባለው ሁኔታ ሰማያዊ ፓርቲ ስራ እየሰራ ነው ማለት አይቻልም፡፡ በብዙ ውጣ ውረዶች ውስጥ ነው ያለው፡፡ የተፈጠሩ ችግሮች ከእለት እለት ፓርቲውን እንደሚጎዳ ሁሉ፣ የህዝቡንም የደጋፊውንም ስነ ልቦና እየጎዳ ነው፡፡ በተለይ ዲሲፒሊንና ኦዲትና ኢንስፔክሽን የሚባሉት በመካሰስና በፍረጃ የተሞላ ስራ እየሰሩ በመሆኑ፣ በአሁን ሰአት አባላት በንቃት እየተሳተፉ አይደለም። በጣም አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ነው ያለነው፡፡
ፓርቲው አሁን ከገባበት ችግር አንፃር እየተዳከመ ነው የሚሉ ወገኖች አሉ…
ፓርቲው ተዳክሟል ማለት አልችልም፡፡ ሊቀመንበሩ እኔ ነኝ፤ አሁን ያሉት ስራ አስፈጻሚዎች በትምህርት ደረጃቸውም የተሻሉ ናቸው፡፡ ነገር ግን አሁን ሰማያዊ ውስጥ ስራ የሚያሰራ ሁኔታ የለም። ወደ ስራ እንዳንገባ ልዩ ተልዕኮና ድብቅ አጀንዳ ያላቸው ሰዎች፣ እለት በእለት ትጉህ አባላትን በመክሰስ፣ በመደብደብ፣ የማይሆን ስም እየሰጡ በመፈረጅ ተጠምደዋል፡፡ በነዚህ ምክንያቶች ከመስከረም ጀምሮ ስራ መስራት አልተቻለም፡፡ በእስር ቤት ያሉ የፓርቲው አባላትን ጭምር አባረናል የሚል ውሳኔ ሁሉ ተወስኗል፡፡ ቀደም ሲል አራት አባላት ተባረዋል ተባለ፡፡ ከዚያ አይባረሩም ተባለ፡፡ ከሰሞኑ ደግሞ አባረናል የሚል ውሳኔ እየሰማን ነው። ከዚያም አልፎ እኔንም አባረንሃል እየተባለ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ እንዴት ነው ስራ መስራት የሚቻለው?
የዲሲፕሊን ኮሚቴው በፓርቲው ውስጥ ያለው ስልጣን ምን ድረስ ነው?
እኔም ግራ የገባኝ ይሄው ነገር ነው፡፡ ብዙዎቹ በኮሚቴው ውስጥ ያሉት የአቅም ችግር አለባቸው። የህግ ትምህርት ያለው አንድ ሰው ብቻ ነው፡፡ እሱም በብዙዎች ውሳኔ የሚዋጥ ነው፡፡ መስራት አልቻለም፡፡ ሌሎቹ ግን የትምህርት ደረጃቸውም ሆነ እውቀታቸው የሚያወላዳ አይደለም፡፡ ከዚያም ባለፈ ሆን ብሎ አባላትን ለመጉዳት የመንቀሳቀስ ነገር አለ፡፡ ለምሳሌ የኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ “የለሁበትም፤ውሳኔ አልሰጠሁም” እያለ ሰዎች በሌሉበት ነው ወሰንን የሚሉት፤ ህገ ወጥ ውሳኔዎች ናቸው የሚደረጉት፡፡ እነዚህ ውሳኔዎች የአባላትና የደጋፊዎቻችንን ስነ ልቦና እየጎዱ ነው፡፡
የኮሚቴው ስልጣን ምን ድረስ ነው?
እኔ በጠቅላላ ጉባኤ ነው የተመረጥኩት፡፡ ውሳኔያቸው ላይ ካየኸው “ተባሯል ግን ለጠቅላላ ጉባኤ ውሳኔ ይቀርባል” ነው የሚለው፡፡ ሊቀ መንበር ከሆንኩ ይሄ ነገር ለምን አስፈለገ፡፡ ተባሯል የሚለውን ማለቴ ነው፡፡ ይሄ ሆን ተብሎ የእኔን ሰብዕና ለማጉደፍ የሚደረግ ነው፡፡ ሆን ብለው የህዝቡን ልብ ለመስበር የሚደረግ ጥረት ነው እንጂ ይሄን ያህል የተሰጠው ስልጣን የለም፡፡ እኔን የመረጠኝ ጠቅላላ ጉባኤው ነው፡፡
የሁሉም መነሻ እርስዎን ጨምሮ ለምርጫ የተመደበን ገንዘብ መዝብራችኋል የሚል ክስ ነው … በእርግጥ የተባለው ድርጊት ተፈፅሟል ?
አንድ በግልፅ የምነግርህ ጉዳይ ይሄ ነገር ሆነ የተባለው በ2005 ዓ.ም ነው፡፡ አሁን 2008 ላይ ነው ያለነው፡፡ በ2007 ጠቅላላ ጉባኤ አድርገን የኦዲት ሪፖርት ቀርቦ ውይይት ተደርጎበት ገቢና ወጪ ላይ የጠፋ ገንዘብ እንደሌለ ተማምነን፣ ያ ሰነድ ፀድቆ ለምርጫ ቦርድ ገብቷል፡፡ አሁን ታዲያ የ2005 ክስ ለምን መጣ? ሲባል ምክንያቱ ግራ ያጋባል፡፡ አጠፋን የተባለው የገንዘብ ልክ እንኳ አልተጠቀሰም፡፡ እነዚህ ሰዎች ያለ ማስረጃ በሃሜት ነው የሚንቀሳቀሱት፡፡ እኛ በፍ/ቤት ልንከሳቸው እንችላለን፡፡ መጨረሻ ላይ መረጃ ሲያጡ፣ ባልታወቀ የገንዘብ መጠን ምዝበራ ተባራችኋል ነው ያሉት፡፡
165 ሺህ ብር ተብሎ የተጠቀሰውስ ?
ኧረ ምንም ነገር የለም፡፡ የቅጣት ውሳኔያቸው ላይ “ገና በኦዲት ሪፖርት ሲደረግ የሚወሰንባችሁን በሁለት ወር ውስጥ ትከፍላላችሁ” ነው የሚለው፡፡
እርስዎ ያጠፋሁት ምንም ገንዘብ የለም እያሉ ነው?
አዎ እኔ ምንም ያጠፋሁት ገንዘብ የለም፤ክስም አልቀረበብኝም፡፡ ከሳሽ ነው የተባለው አቶ ይድነቃቸው ከሰሞኑ በፌስቡክ ገፁ ላይ “እኔ አልከሰስኩም፤ ክሱንም አልተከታተልኩም” ብሏል። ታዲያ ክስ ሳይኖር ፍርድ አለ? ምስክር ከየት መጣ? ዳኛውም ከሳሹም የዲሲፒሊን ኮሚቴው ነው ማለት ነው? ከሳሽ የተባለው ሰው አልከሰስኩም እያለ ክሱ ከየት መጣ? እንደውም “ይሄን ነውረኛ ተግባር ሊቀመንበራችን መናገር ያለበት አሁን ነው” ብሎ ነው የጻፈው፡፡ ታዲያ ከሳሽ ሳይኖር ፍርድ አለ?
የዲሲፒሊን ኮሚቴው ይሄን ሁሉ ግድፈት ሰርቶ ፓርቲውን ለማፍረስ እየተንቀሳቀሰ ነው የሚል እምነት ካላችሁ፣ የፓርቲው ማዕከላዊ ም/ቤት ለምን ዝምታን መረጠ?
እንግዲህ የዲሲፕሊን ኮሚቴው የሚባለውን እኔ አላቋቋምኩም፡፡ ኦዲትና ኢንስፔክሽን የሚባለው ነው ያቋቋመው፡፡ እኛ አናውቀውም፡፡ ይሄን ሁሉ ስህተት ሲሰሩ ዝም ያላቸው እሱ ነው፡፡ መቆጣጠርና መከታተል ያለበት እሱ ነው፡፡ ትልቁ ስህተት የኦዲትና ኢንስፔክሽኑ ነው፡፡  የሚመለከተው እሱን ነው፡፡
ሌላው ሊቀመንበሩ በቢሮ ተገኝቶ አያውቅም፣ ስራ አስፈፃሚውንም ስብሰባ ጠርቶ አያውቅም፣ በአጠቃላይ ፓርቲውን ትቶታል የሚል ክስም ይቀርባል?
ይሄ ውሸት ነው፡፡ ስራ አስፈፃሚው በየጊዜው ይሰበሰባል፣ ስራውን ይሰራል፡፡ ነገር ግን ፅ/ቤት ውስጥ አንድ ችግር አለ፡፡ የፅ/ቤት አገልግሎት ኃላፊው ማህተሙን ይዞ አለቅም ብሎ ቁጭ ብሏል። ከጥቅምት መጨረሻ ጀምሮ የፓርቲውን ንብረት አስረክብ ተብሎ አሻፈረኝ ብሏል፡፡ በነገራችን ላይ ይሄ ሰውዬ ደሞዝተኛ ነው፡፡ ለፅ/ቤት ሰራተኞች ደሞዝ ይከፍላል፣ ቼክ ላይ ይፈርማል፣ ከ10 ሺህ ብር በታች የሆኑ ወጪዎችን ያንቀሳቅሳል፣ የስራ አስፈፃሚውን ቃለ ጉባኤ ይይዛል፡፡ ይሄ ነው የሱ ስራ። አሁን እነዚህን ሁሉ ስራዎች እየሰራ አይደለም። ቢሮውንም አለቅም፤ማህተሙንም አልሰጥም ብሎ ቁጭ ብሏል፡፡ ፅ/ቤቱን የምመራው እኔ ነኝ፤ በሌላ አነጋገር ይሄ ሰውዬ ለኔ አይታዘዝም ማለት ነው፡፡ እንደውም አምባጓሮ በመፍጠር ሰዎችን ይዞ እየመጣ ድብድብ መፍጠር ጀመረ፤ ስለዚህ እኔ እንዲህ ያለውን ነገር አልፈልግም፣ቢሮ ባልገባም ባለሁበት ሆኜ የፓርቲዬን ስራ እሰራለሁ፤ ስራ አስፈፃሚውን እሰበስባለሁ፤ ለሚዲያ መግለጫ እሰጣለሁ፤ በአጠቃላይ ፓርቲዬን ወክዬ እየሰራሁ ነው፡፡ ፅ/ቤት ግን መግባት አያስፈልገኝም፡፡
አንድ የፅ/ቤት ሰራተኛ ማህተም አላስረክብም ሲል አመራሩ እንዴት ማስቆም ይከብደዋል?
አመራሩ ምን ያድርግ?!
በህግ ጠይቆ ማህተሙን ማስመለስ አይችልም?
እሱ እንግዲህ ወደ ህግ እንሂድ ቢባል ይቻላል፤ ነገር ግን ወደ እነዚህ ተቋማት ብንሄድ ችግሩን የበለጠ ነው የምናሰፋው፡፡ የህግ አስከባሪ የሚባሉት ተቋማት ደግሞ እንደማይረዱን እናውቃለን፡፡ ከዚህ በፊት በተለያዩ ፓርቲዎች ላይ የተፈጠረውን አይተነዋል፡፡ ይሄ ሰውዬ ይሄን ያደረገበት የራሱ ምክንያትና አላማ ይኖረዋል፡፡
ለምንድነው ከኃላፊነት እንዲነሳ የተወሰነው?
በጠቅላላ ጉባኤ ወቅት ተወዳድሮ የፓርቲው የምክር ቤት አባል ሆኗል፤ በደንባችን መሰረት ደግሞ የም/ቤት አባል የሆነ ሰው የፅ/ቤት ኃላፊ ሆኖ መስራት አይችልም፡፡ ስለዚህ ይሄ ሰውዬ በራሱ ጊዜ ነው የፅ/ቤት ኃላፊነቱን የለቀቀው፡፡ እኔ አይደለሁም ልቀቅ ያልኩት፤ የፓርቲው ደንብ ነው እንዲለቅ ያስገደደው፡፡
አሁን ባለው ሁኔታ የፓርቲው ማህተም ህገ ወጥ ስራ ቢሰራበትስ?
እንግዲህ ምን እናድርግ እኛ! ወይ ፍርድ ቤት ወይ ምርጫ ቦርድ መሄድ ነው፡፡ ይሄ ደግሞ የሚሆን አይደለም፡፡ ምርጫ ቦርድ ጣልቃ ገብቶ ፓርቲዎችን ለብዙ  ችግር ሲዳርግ ነው የምናውቀው፡፡ ስለዚህ ያለኝ አማራጭ ------ ድብድብ ከመፍጠር በውጭ እየሰራሁ ፓርቲው ወደነበረበት የሚመለስበትን መንገድ ማፈላለግ ነው፡፡ እኔ ፓርቲው ውስጥ የገባሁት ለግብግብና በጠመንጃ ጉልበት ለመታገል አይደለም፡፡ ለዚህ ነው ነገሩን ለመሸሽ በውጪ የምሰራው፡፡
ችግር ፈጥረውብናል የምትሏቸው ሰዎች አላማቸው ምንድን ነው ትላላችሁ?  
እኔ የደረስኩበት ድምዳሜ፣ የእነዚህ ሰዎች አላማ ፓርቲውን ማዳከም ነው፡፡ ፓርቲው ስራውን እንዳይሰራ በማድረግ፣ የነበረውን ጠንካራ እንቅስቃሴ መግታት ነው፡፡
ፓርቲው ከመዳከሙ የተነሳ ለቢሮ ኪራይ የሚከፍለው በወር 18 ሺህ ብር አጥቷል እየተባለ ነው፡፡ ይሄስ እውነት ነው?
ሰማያዊ በብዛት በውጭ ሀገር በህጋዊነት የተመዘገቡ የድጋፍ ሰጪ ማህበራት አሉት፡፡ እነዚህ በድጋፍ ውስጥ ትልቅ ድርሻ አላቸው፤ነገር ግን በአደባባይ አባላት እየተዘላለፉ፣ ንቁ አባላት እየተባረሩ ----- በዚህ ሁኔታ ውስጥ ለሰማያዊ ገንዘብ ለማሰባሰብና ለመርዳት እንቸገራለን ብለው ያለቻቸውን ገንዘብ ከ3 ወር በፊት ላኩ፡፡ አንድ መቶ ሺህ ብር ነች፡፡ ከዚያ በኋላ አልላኩም፡፡ የማይረዱበትን ምክንያት፣ ፓርቲው እርስ በእርሱ እየተወነጃጀለና ስም እየተጠፋፋ በመሆኑ ነው ብለው በግልፅ ተናግረዋል፡፡ እውነትም ነው! ሰው ገንዘቡን የሚሰጠው ትግሉ እንዲሳካ፣ በአንድ አላማ ተሰልፈን እንድንታገል ነው፡፡ ድብቅ አጀንዳ ያላቸው ሰዎች የሚፈልጉት ደግሞ ይሄ እንዳይሳካ ነው፡፡
ፓርቲው በእንዲህ ያለ ቀውስ ውስጥ መግባቱ አባላቶቻችሁንና ደጋፊዎቻችሁን ተስፋ እያስቆረጠ አይመስልዎትም?
አይ፤ አባላትን በተመለከተ አሁንም ቢሆን ስራ ለመስራትና በንቀት ለመሳተፍ ፍላጎታቸው እንዳለ ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ለቅቄያለሁ የሚል ሰው አላየሁም፡፡ ዮናታንም ቢሆን ከኃላፊነቱ ነው እንጂ የለቀቀው ከፓርቲው አይደለም፡፡ የሚያሳዝነው ግን በእስር ላይ እያለ ከፓርቲው ተባረዋል የተባሉት 4 የፓርቲው አባላት መጀመሪያ የተወሰነው ውሳኔ ችግር አለበት ተብሎ በፓርቲው ይቀጥሉ ተብሎ የነበረ ሲሆን አሁን ደግሞ በድጋሚ አባረናቸዋል ተብሏል፡፡ እንዲህ በሆነበት ሁኔታ ሰው ሞራሉ ቢነካ ምን ይገርማል፡፡ እኔን ጨምሮ ቢሮዬን መጠቀም እስከማልችልበት ደረጃ ደርሻለሁ፡፡ ነገሮችን እስካሁን ይፋ ሳናደርግ የቆየነው ለህዝብ ካለን ክብር የተነሳ ነው፤አባላትና ደጋፊዎቻችን በስነ ልቦና እንዳይጎዱ በማሰብ ነበር፡፡ ይሄ ነገር አሁንም ቢሆን መፍታት ካልተቻለ፣ ፓርቲውም አስፈላጊ የማይሆንበት ደረጃ ይደርሳል ማለት ነው፡፡
ተቃዋሚ ፓርቲዎች በየጊዜው እርስ በርስ እየተጠላለፋችሁ ስትፈርሱ፣ ይደግፈናል የምትሉትን ህዝብ ተስፋ የሚያስቆርጥ አይመስልዎትም?…
በተለይ ደግሞ የሰማያዊ ፓርቲ እንደዚህ መሆን-
አሁን እኮ ችግሩ “የእናንተ እንዲህ መሆን ---” የሚለው ነገር ነው፡፡ እኔና የስራ አስፈፃሚ አባላት በሙሉ ልብና በሙሉ አቅም ነው እየሰራን ያለነው። ችግሩ ያለው ዲሲፒሊን ኮሚቴ የሚባለው ጋ ነው፡፡
የእኔ ጥያቄ የውስጠ ፓርቲ ችግራችሁን እንዴት በተረጋጋ መንገድ መፍታት አትችሉም ነው? የዲሲፒሊን ኮሚቴ ነው ችግር ፈጣሪ ካላችሁ ለምን አታስተካክሉትም?
ዲሲፒሊን ኮሚቴውን እንዲያስተካክል ለፈጠረው ኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን እነዚህ ሁሉ አወዛጋቢ ውሳኔዎች ከመምጣታቸው በፊት ደብዳቤ  ፅፌያለሁ፡፡ እስከዛሬ የነበሩትን ድክመቶች አመላክቼ ጠንካራ ደብዳቤ ፅፌላቸዋለሁ፡፡ እንግዲህ ያንን ተመልክተው የእርምት እርምጃ ይወስዳሉ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
በሰማያዊ ውስጥ የተከሰተውን ቀውስ በማንኛውም ፓርቲ ውስጥ የሚያጋጥም ተራ ግጭት ነው ብሎ ማለፍ ይቻላል?
አይቻልም፤ ምክንያቱም ይሄ ሆን ተብሎ ታስቦና ታቅዶ እየተሰራ ያለ ሴራ ነው፡፡
የቢሮአችሁ ቀጣይ እጣ ፈንታስ ምንድን ነው?
በኔ እምነት ገንዘብ አይጠፋም ብዬ አስባለሁ፤ ፓርቲው ከጠነከረ ብር ያገኛል፡፡ ነገር ግን በዚህ ችግር ከዘለቀ ገንዘብ ማግኘት አይችልም፤ያኔ ቢሮ አልባ ይሆናል ማለት ነው፡፡
ፓርቲው የመፍረስ አደጋ ላይ ነው ማለት ይቻላል?
ህጋዊ ሰውነቱን የሚያጣ አይመስለኝም፡፡ እዚህ ሀገር የማይፈጠር ነገር የለም፡፡ ጉዳዩ ምርጫ ቦርድ ዘንድ ቢሄድ የሚፈጠረውን መገመት ቀላል ነው፡፡ ፓርቲዬን ከመፍረስ ለመታደግ  በምንችለው አቅም ጥንቃቄ እያደረግን ነው፡፡
ላለመበታተን ምን ዋስትና አላችሁ?
ምንም ዋስትና የለንም፡፡ እዚህ ሀገር ህግ ዋስትና አይደለም፤ ኢህአዴግ የፈለገውን ነገር ማድረግ የሚችልበት ሀገር ነው፡፡ እኛ ግን ለህሊናችን ተጠንቅቀን የምንችለውን ሁሉ እንሰራለን፡፡
በቀጣይ እንግዲህ ኦዲትና ምርመራ፣ እጣ ፈንታችሁን ያሳውቃል ተብሎ ይጠበቃል … እንዴት ትቀበሉታላችሁ?
ኦዲት ከዚህ በኋላ በእኛ ላይ መወሰን የሚችለው ነገር የለውም፡፡ ምክንያቱም ከሳሽ የተባለው ግለሰብ አልከሰስኩም ባለበት ሁኔታ ምን ውሳኔ ይመጣል? ክስ በሌለበት የምን ውሳኔ ነው የሚጠበቀው፡፡ ማን ከሶኝ ነው የሚፈረድብኝ? ኦዲት አሁን ላይ ምንም የሚመረምረው ጉዳይም ሆነ የሚያስተላልፈው ውሳኔ የለም፡፡ ከነሱ የሚጠበቅ ምንም ውሳኔ የለም፡፡
ፓርቲያችሁን ከቀውስ ለማዳን የምትወስዱት የመጨረሻ እርምጃ ምንድን ነው?
እንግዲህ የመጨረሻው መፍትሄ ጠቅላላ ጉባኤ ጠርቶ፣ ኦዲትና ምርመራ ኮሚሽኑ እየፈጠረ ያለውን ችግር አስረድቶ ውሳኔ እንዲሰጥበት ማድረግ ነው። ጠቅላላ ጉባኤ ጠርተን ችግሩን የፈጠረው አካል እንዲሻር ማስደረግ ብቻ ነው መፍትሄው፡፡
ጉባኤውን ለመጥራት ታዲያ ለምን ዘገያችሁ?
ጉባኤያችንን ያደረግነው በቅርቡ ነው፡፡ በድጋሚ መጥራት ከአቅም አንፃር አስቸጋሪ ስለሚሆን ነው፡፡ አሁን ግን ችግሮቹ እያፈጠጡ ስለሆነ ጉባኤ መጥራቱ የግድ ይሆናል፡፡
ጉባኤው መቼ ይደረጋል?
ችግሮች በዚህ ሁኔታ የሚቀጥሉ ከሆነ በአጭር ጊዜ ውስጥ ይሆናል፡፡
በዚህ ዓመት ይሆናል?
አዎ የግድ ነው፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ የወደፊት እጣ ፈንታ ምንድነው?
እርግጥ ነው ፓርቲያችን ችግር አጋጥሞታል፤ግን የፓርቲውን መሰረታዊ ነገር የሚጎዳ ነው ብዬ አላምንም፤ሆኖም የፓርቲውን ስራ እንዳንሰራ ተሰነካክለናል፡፡ ፓርቲው ጉባኤ ካደረገ በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ ይጠናከራል የሚል እምነት አለኝ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቅርቡ ከተቃዋሚዎች ጋር በተወያዩበት መድረክ ላይ ያልተገኛችሁት ለምንድን ነው?
አልተጠራንም፡፡ የሚጠሯቸው ከኢህአዴግ ቀለብ የሚቆረጥላቸውን ነው፡፡ በአለም ታሪክ ተቃዋሚ ከገዢ ፓርቲ ቀለብ የሚቆረጥለት በኛ ሀገር ብቻ ነው፡፡


አንድ አርሶ አደር በአጥር ግቢው ውስጥ አንድ የፍሬ ዛፍ ነበረው፡፡ ሆኖም ይሄ ዛፍ ፍሬ አላፈራም፡፡ ስለዚህም አርሶ አደሩ፣
“አንተ ዛፍ፤ስንት ዓመት ሙሉ ደጃፌ ቆመህ አንዲት ፍሬ እንኳን ሰጥተኸኝ አታውቅም፡፡ አሁን መቆረጫህ ሰዓት ደርሷል - ተዘጋጅ!” አለው፡፡
በዛፉ ላይ በየቅርንጫፉ ውስጥ የሚኖሩና በጥላው የሚጠቀሙ ድንቢጥ ወፎችና አንበጣዎች አሉ፡፡ እነሱ ማረፊያቸው ሊፈርስባቸው ስለሆነ፤
“እባክህ ይሄንን ዛፍ አትቁረጥብን፡፡ መጠጊያ ታሳጣናለህ፡፡ ዛፉ የኛ መኖሪያ ከመሆኑም በተጨማሪ ለአካባቢው ጥላ ይሆናል፡፡ ነፋሻ አየርም ያመጣል” እያሉ ለመኑት፡፡
አርሶ አደሩ ግን “ምንም የማያፈራ ዛፍ ተሸክሜ አልኖርም” ብሎ መጥረቢያ ሊፈልግ ሄደ፡፡ ከልቡ ሊቆርጠው ወስኗል፡፡ መጥረቢያውን አግኝቶ መጣ፡፡ አንበጦቹና ድንቢጦቹ ደግመው ለመኑት፤
“እባክህ አያ አርሶ አደር፣ ዛፉን በመቁረጥ ምንም አትጠቀምም፡፡ ይልቁንም አያሌ ነብሳት ማደሪያ ያጣሉ፡፡ በጠዋት የሚዘምሩ ወፎች አትክልትህን ስትኮተኩት እያጀቡ ህይወትህን ያለመልሙልሃል” ሲሉ አወጉት፡፡
አጅሬ አንደኛውን ጨክኗልና ምክራቸውን አልሰማ አለ፡፡ የዛፉን ግንድም በመጥረቢያው ይመታው ጀመር፡፡ ደግሞ፣ ሰልሶ ሃይ - በል ካለው በኋላ፣ የዛፉ ውስጡ ይታይ ጀመር፡፡ በራሱ ባዶ ነው፡፡ ቀፎ ነው፡፡ ሆኖም ውስጡ ግን የንብ መንጋ ይኖር ኖሯል፡፡ በንቦቹ ዙሪያ ከባድ የማር ክምችት አለ፡፡ የዚያ ዛፍ ሆድ ዕቃ ለካ ከባድ የማር መጋዘን ኖሯል፡፡ አርሶ አደሩ በደስታ መጥረቢያውን ጥሎ ማሩን ተመለከተ፡፡ ነገር ግን ወዲያው ሀዘን ገባው፡፡
“ወይኔ! ወይኔ!” አለ፡፡ “ይህን ግንድ በህይወት ማቆየት ነበረብኝ፡፡ ውስጡ ምን እንዳለ ሳላውቅ፣ ለስንት ዘመን ማር የሚያጠራቅምልኝን ዛፍ ቆረጥኩት፡፡ ትልቅ ሀብት አፈረስኩኝ!” አለ፡፡
*        *          *
ታላላቅ ያገር ይዞታዎችን፣ የጥንት ታሪካዊ ቅርሶችን፣ በችኮላ ካፈረስን ለከባድ ፀፀት ሊዳርገን ይችላል፡፡ ውስጡ ያለውን እንመርምር፡፡ ብዙ ቅርሶቻችን የዘመናት ፍሬዎቻችን ናቸው፡፡ አንድ ነባር ዋርካ ሲወድቅ፣ በዙሪያው ያሉ የንፍቀ ክበቡ ነዋሪዎች ጥቅም ጭምር ይወድቃል፡፡ ሳናውቀው የብዙ ማህበረሰብም ኑሮ ሊናጋ ይችላል፡፡ ግንባታን ስናስብ ፍርሳታውን፣ አልፎም ልማታዊ ግቡን አበክረን ካላየን ጉዳቱ ሊበዛ ይችላል፡፡ በጥናት፣ በብልህነትና በጥንቃቄ መሰራት ያለባቸውን ነገሮች አስተውሎ ማየት ዋና ነገር ነው፡፡ ሌላው መሰረታዊ ነገር የቅርሶች አጠባበቅ ነው፡፡ ከዚሁ ጋር አስጊው ነገር ደሞ መዘረፋቸው ነው፡፡ ዘረፋ ደግሞ ባህል ሆኗል፡፡ “የአባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ” የሚለው የድሮ ተረት፣ ዛሬ የዕለት - ሰርክ ጉዳይ ሆኗል፡፡ ጥንቃቄ የሚሻው ይህ ጉዳይ ነው፡፡ ውሻ በቀደደው ጅብ ይገባል! የአየር ጠባይ መለዋወጡን አለመዘንጋት እጅግ ብልህነት ነው፡፡ ትላልቅ እርሻዎቻችንን መጪው የአየር ንብረት ለውጥ ምን አደጋ ላይ እንደሚጥላቸው ከወዲሁ በንሥር - ዐይን ማየት ይጠበቅብናል፡፡ ለሁሉም ነገር በሁሉም አቅጣጫ “መረጃም ማስረጃም ይኑረን” የተባለው እጅግ ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ ሁሉም ፍሬ ነገር በእጃችን ያለ እየመሰለ በአፍታ ከእጃችን ያመልጣል፡፡ ተቋሞቻችን የማይናዱ ግንቦች ይመስሉንና ውስጣቸው እየተሸረሸረ አንድ ቀን ባዶ ሆነው ይገኛሉ፡፡ ዲሞክራሲ ጠንካራ ተቋማት ላይ ካልቆመ አብሮ ፈራሽ ነው፡፡ እንኳን እንደኛ አገር በአዲሱ ወለል ላይ መሰረት የሚቸክል ቀርቶ የበለፀጉትም አገሮች ስንቴ ወድቀው ስንቴ ተነስተው፣ ልብ - አድርስ የሚባል የዲሞክራሲ ዋንጫ አልጨበጡም፡፡ እነሱም ጋ ዛሬም ሙስና አለ፡፡ እነሱም ጋ ዘረኝነት አለ፡፡ እነሱም ጋ የኢኮኖሚ ድቀት (Economic Crisis) አለ፡፡ ይሄ የሚያሳየን የእኛን ዲሞክራሲና ኢኮኖሚ በቀላል ሊወድቅ መቻል ብቻ ሳይሆን፤ የእነሱንም ትኩሱን እፍ - እፍ ሳንል እንዳናጋብስና መሸፈኛውን ገልጠን እንድናይ ነው፡፡
የጥንት ታዋቂ ፖለቲከኞች፤ “ፖለቲካ የኢኮኖሚው ጥርቅም መገለጫ ነው” ይላሉና እያንዳንዷን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ አጥርተን ካላየን፣ በፖለቲካ መልክ ብቅ ስትል ማህበራዊ ቀውስን ጭምር አመላካች ትሆናለች፡፡ ለህዝብ የምንገባውን ቃል ተጠንቅቀን ካልሆነ ያስተዛዝባል፡፡ አገርን በሰላም መምራት “እራሱን ያልገዛ፣ አገር አይገዛ” ከሚለው ብሂል ጋር በእጅጉ የተሳሰረ በመሆኑ የራስን ጥንካሬ በየጊዜው መመርመር የግድ ያስፈልጋል፡፡
“ቃል የእምነት ዕዳ” ነው ይላልና ገጣሚው ቃላችንን እንጠብቅ፡፡ የህግ የበላይነት ካልን ከሱ በላይ ምንም እንደሌለ እናረጋግጥ፡፡ በወገን አንሰራም ካልን ዘር፣ ሃይማኖት፣ አብሮ አደግ አናፈላልግ፡፡ የትግሪኛው ተረትና ምሳሌ ይሄንን በአፅንዖት ይገልፀዋል፡፡ እንዲህ ሲል፡-
“እወድሃለሁ እያለ የሚጠላ፣
እፆማለሁ እያለ የሚበላ፣
እሰጣለሁ እያለ የሚነሳ፣
እነዚህን አምላክ ይጠላ”፡፡
በአደባባይ ቃል መግባት በአደባባይ መጠየቅን ነው የሚያመለክት፡፡ በየሚዲያው ለውዳሴም ሆነ ለቅዳሴ ብለን የምንገባውን ቃልና ኋላም አፈፃፀም በጥንቃቄ እናስተውል፡፡

 - ባለፈው አመት በቻይና ከ1ሺህ በላይ ሰዎች ተገድለዋል
              - የሞት ቅጣት የሚፈጸምባቸው ሰዎች ቁጥር ጨምሯል
     አምነስቲ ኢንተርናሽናል የተባለው የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅት ባለፈው የፈረንጆች አመት 2015፣ ዜጎችን በሞት በመቅጣት ቻይና ከአለማችን አገራት ቀዳሚውን ስፍራ እንደያዘችና አገሪቱ በአመቱ የሞት ቅጣት የተጣለባቸውን ከ1 ሺህ በላይ ሰዎችን መግደሏን ገለጸ፡፡
ባለፈው አመት 2015 የሞት ፍርዶችን በማስተላለፍና ተፈጻሚ በማድረግ ረገድ በአለማቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ጭማሪ ታይቷል ያለው ተቋሙ፣ ቻይናን ሳይጨምር በአመቱ በአለማችን ከ1ሺህ 634 በላይ ሰዎች መገደላቸውንና ካለፈው አመት ጋር ሲነጻጸር ቁጥሩ በግማሽ መጨመሩን መግለጹን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ በአመቱ በኢራን 977 ያህል ሰዎች መገደላቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ አብዛኞቹ ሰዎች የተገደሉትም ከአደንዛዥ ዕጽ ጋር በተያያዘ በተመሰረተባቸው ክስ በተላለፈባቸው የሞት ፍርድ ውሳኔ ነው ብሏል፡፡
በ2015 አመት ብቻ በፓኪስታን 326፣ በሳኡዲ አረቢያ 158፣ በአሜሪካ 28፣ በኢራቅ 26፣ በሶማሊያ 25፣ በግብጽ 22፣ በኢንዶኔዢያ 14 እና በቻድ 10 ሰዎች በተለያዩ የወንጀል ክሶች ሳቢያ በሞት መቀጣታቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

 ከ100 ቢሊዮን ብር በላይ መፍጀቱ ታውቋል
     ታዋቂው የሞባይልና የኮምፒውተር አምራች ኩባንያ አፕል፣ በ5 ቢሊዮን ዶላር ወጪ የዓለማችንን ምርጥ የቢሮ ህንጻ በካሊፎርኒያ እየገነባ መሆኑን ዘ ዴይሊ ሜይል ዘገበ፡፡ ግንባታው በመገባደድ ላይ የሚገኘው የአፕል ዋና መስሪያ ቤት የግንባታ ስምምነት የተፈጸመው ከ6 አመታት በፊት እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ህንጻው በ260 ሺህ ስኩዌር ሜትር ቦታ ላይ ማረፉንና 13 ሺህ ያህል ሰራተኞችን መያዝ እንደሚችል ጠቁሟል፡፡
በክብ ቅርጽ ለተሰራውና የዙሪያ መጠኑ 1.6 ኪሎሜትር እርዝማኔ ላለው ለዚህ ግዙፍ ህንጻ የሚገጠሙት መስኮቶች በአለማችን በግዙፍነታቸው ቀዳሚውን ስፍራ እንደሚይዙ የተነገረ ሲሆን የግንባታው ወጪ 3 ቢሊዮን ዶላር ይሆናል ተብሎ ቢጀመርም ወጪው እየጨመረ መጥቶ 5 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን ዘገባው ገልጧል፡፡
1 ሺህ መኪኖችን የማስተናገድ አቅም ያለው የመኪና ማቆሚያ ስፍራ በሚኖረው በዚህ ህንጻ ግቢ ውስጥ 7 ሺህ ያህል ዛፎች መተከላቸው የተገለጸ ሲሆን፣ ግንባታው በስምንት ወራት ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቅቆ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር ይጠበቃል፡፡

   ቻይና ባለፈው ወር በተመድ ማዕቀብ ከተጣለባት ሰሜን ኮርያ ጋር ስታከናውነው የቆየቺውን የተለያዩ የውድ ማዕድናት ምርቶች ግዢና የነዳጅ ሽያጭ ለማቋረጥ የሚያስችሉ የተለያዩ የንግድ ማዕቀቦችን መጣሏን አስታወቀች፡፡ ሮይተርስ እንደዘገበው፤ሰሜን ኮርያ የውጭ ንግድ ምርቶች ሁለት ሶስተኛውን ያህል በመግዛት የምትታወቀው ቻይና፣ የሰሜን ኮርያ ዋነኛ የወጪ ንግድ ምርቶች የሆኑትን ወርቅና ሌሎች ውድ ማዕድናት ላለመግዛት ወስናለች፡፡ የቻይና መንግስት ከሰሜን ኮርያ የግዢ ማዕቀብ ከጣለባቸው ምርቶች መካከል ብረት፣ ወርቅ ቲታኒየም እንደሚገኙበት የጠቆመው ዘገባው፣ ሰሜን ኮርያ በ2013 ለውጭ ገበያ ካቀረበቺው ምርት 65 በመቶ የሚሆነውን የገዛቺው ቻይና እንደሆነች አስታውሷል፡፡
ቻይና ከዚህ በተጨማሪም ለሰሜን ኮርያ የአውሮፕላን ነዳጅ መሸጥ እንደማይቻል ከሰሞኑ ባወጣቺው ማዕቀብ ወስናለች ያለው ዘገባው፣ ማዕቀቡ በሰሜን ኮርያ የወጪ ንግድ ላይ ከፍተኛ የሆነ አሉታዊ ተጽዕኖ ይፈጥራል መባሉን ገልጧል፡፡
ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማና የቻይናው አቻቸው ዢ ጂፒንግ ባለፈው ሳምንት ዋሽንግተን ውስጥ በተካሄደው አለማቀፉ የኒውክሌር ደህንነት ጉባኤ ላይ ተገናኝተው በሰሜን ኮርያ የኒውክሌር እንቅስቃሴ ላይ ቻና ለመፍጠር መስማማታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ አሜሪካ ቻይና በሰሜን ኮርያ ላይ የጣለቺውን የንግድ ማዕቀብ በደስታ እንደተቀበለቺውም አክሎ ገልጧል፡፡

ባለፈው እሁድ ማለዳ ላይ...
አለማቀፉ የምርመራ ጋዜጠኞች ጥምረትና ሱደች ዜቱንግ የተባለው የጀርመን ጋዜጣ፣ አለምን ያስደነገጠ ቁልፍ አለማቀፍ የቅሌት መረጃ ይፋ አደረጉ፡፡
የፓናማ ሰነዶች የሚል ስያሜ የተሰጠው ይህ ቁልፍ መረጃ፣ ባለፉት አራት አስርት አመታት በድብቅ የተከናወኑ የዓለማችን ገናና ፖለቲከኞች፣ ባለሃብቶችና ታዋቂ ግለሰቦችን የገንዘብ ቅሌት ለአለም ያጋለጠ አነጋጋሪ አጀንዳ ሆኗል፡፡
ያሳለፍነው ሳምንት የዓለማችን ታላላቅ መገናኛ ብዙሃን ቀዳሚ ትኩስ ዜና የፓናማ ሰነዶች ቅሌት ነበር፡፡ ይሄው ቅሌት የዓለማችን ስመ ገናና ፖለቲከኞችና ባለጸጎች በቢሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር ወደ ሌሎች አገራት ማሸሻቸውንና ግብርን ለማምለጥ ሲሉ በውጭ አገራት በድብቅ ባቋቋሟቸው ኩባንያዎችና የንግድ ተቋማት ረብጣ ትርፍ ማጋበሳቸውን ያሳያል፡፡
በአለማችን የመረጃ ማፈትለክ ታሪክ እጅግ ትልቁ ነው የተባለውና ሞዛክ ፎንሴካ ከተባለው የፓናማ የህግ አገልግሎት ተቋም አፈትልኮ የወጣው ይህ ቁልፍ ሚስጥር፣ 11 ሚሊዮን ያህል የቅሌት መረጃዎችን የያዘ ሲሆን፣ በ76 የአለማችን አገራት ከሚገኙ መገናኛ ብዙሃን የተውጣጡ 107 ያህል ጋዜጠኞችም ከአንድ አመት በላይ ለሚሆን ጊዜ በመረጃዎቹ ላይ ጥናት ሲያደርጉ ነበር ተብሏል፡፡  
እስካሁን በተገኘው መረጃ የ12 አገራት የወቅቱና የቀድሞ መሪዎች፣ ከ60 በላይ የአገራት መሪዎች ቤተሰቦችና ተባባሪዎች እንዲሁም ፖለቲከኞች በዚህ ቅሌት ውስጥ እንደተሳተፉ የታወቀ ሲሆን፣ ከቅሌቱ ጋር ንክኪ ያላቸው ኩባንያዎችና ተቋማት ቁጥርም 214 ሺህ ያህል እንደሚደርሱ ታውቋል፡፡ አነጋጋሪው መረጃ እ.ኤ.አ ከ1977 እስካለፈው ታህሳስ ወር የተከናወኑ ታላላቅ ቅሌቶችን የያዘ ሲሆን ጥብቅ ሚስጥሩን ለአመታት በእጁ ይዞ የቆየው የፎንሴካ የህግ ተቋምም መረጃው ከውጭ አካላት በተደረገበት ምንተፋ አምልጦት እንደወጣ በማስታወቅ፣ በቅሌቱ ተባባሪ ነው በሚል የቀረበበትን ውንጀላ አስተባብሏል፡፡
የፓናማ ሰነዶች ቅሌት በመገናኛ ብዙሃን ይፋ መደረጉን ተከትሎ በቅሌቱ ውስጥ ስማቸው ከተጠቀሱት የአገራት መሪዎች መካከል አስደንጋጩን ተቃውሞ ቀድመው ያስተናገዱት የአይስላንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሲግሙንዱር ዴቪድ ጉንላጉሰን ናቸው፡፡ በመሪያቸው ቅሌት ክፉኛ የተቆጡት በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ አይስላንዳውያን አደባባይ ወጥተው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስልጣናቸውን እንዲለቁ የጠየቁ ሲሆን፣ በብሪቲሽ ቨርጂን አይስላንድስ የንግድ ኩባንያ አቋቁመው ረብጣ ዶላር እያፈሱ ነው የተባሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩም በነጋታው ስልጣናቸውን በገዛ ፈቃዳቸው መልቀቃቸውን በቴሌቪዥን ባስተላለፉት መልዕክት ገልጸዋል፡፡
የሩስያው ፕሬዚደንት ብላድሚር ፑቲን በቅሌቱ ስማቸው ከተነሳ የአለማችን መሪዎች አንዱ ቢሆኑም፣ የአገሪቱ መንግስት ግን በመሪዬ ላይ የተሰነዘረ መሰረተ-ቢስ ውንጀላ ነው ሲል አጣጥሎታል፡፡ በመሰል ቅሌት የተጠቀሱት የዩክሬኑ ፔትሮ ፖሮሼንኮም ረቡዕ ዕለት ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ራሳቸውን ከደሙ ንጹህ ለማድረግ ሞክረዋል፡፡ አሜሪካውያን ፖለቲከኞችና ታላላቅ ባለስልጣናት ምንም እንኳን እስካሁን ድረስ በቅሌቱ ስማቸው ባይነሳም፣ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ግን፣ የአገራቸው ታላላቅ ባለጸጎች ከመሰል ቅሌት ነጻ እንዳልሆኑ ረቡዕ ዕለት ተናግረዋል፡፡ በፓናማ ሰነዶች ቅሌት ውስጥ በራሳቸው አልያም በቤተዘመዶቻቸውና የስራ አጋሮቻቸው ተሳትፈዋል ተብለው ከተጠቀሱ አፍሪካውያን መካከል ኮፊ አናን፣ ጃኮብ ዙማ፣ ጆን ኩፎር እና ጆሴፍ ካቢላ ይጠቀሳሉ፡፡
በቅሌቱ ውስጥ አሉበት ከተባሉት ታዋቂ ሰዎች መካከልም፣ አሜሪካዊቷ ድምጻዊት ቲና ተርነር፣ አዲሱ የፊፋ ፕሬዚዳንት ጊያኒ ኢንፋንቲኖ፣ ታዋቂው የቦሊውድ የፊልም ተዋናይ አሚታባህ ባቻን፣ ታዋቂው የሆሊውድ ተዋናይ ጃኪ ቻን እና የአለማችን እግር ኳስ ኮከብ ሊዮኔል ሜሲ ይገኙበታል፡፡

    ኢዮሃ አዲስ ኢንተርቴይንመንትና ኤቨንት፤ በ9.5 ሚሊዮን ብር ጨረታ ያሸነፈው “ኢዮሃ ፋሲካ ኤክስፖ” ትላንት ተከፈተ፡፡ በኤክስፖው ላይ ከ450 በላይ የውጭና የአገር ውስጥ የንግድ ድርጅቶች መሳተፋቸውን የጠቆሙት አዘጋጆቹ፤ከ80 በላይ እውቅ ድምፃዊያንም ጐብኚውን እንደሚያዝናኑ የድርጅቱ ዋና ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ አዩ አለሙ ተናግረዋል፡፡
በኤክስፖው ልጆቻቸውን ይዘው ለመጐብኘት የሚመጡ ወላጆች፣የልጆቻቸው ጉዳይ እንዳያሳስባቸው ሲባል፣ ከ“ፀሐይ መማር ትወዳለች” አዘጋጆቹ ዊዝኪድስ ወርክሾፕ ጋር ኢዮሃ ስምምነት በመፍጠር፣ ወላጅ ልጆቹን አስረክቦ ከገባ በኋላ ሲጨርስ ከዊዝኪድስ ወርክሾፕ መረከብ እንደሚችል ወ/ሮ አዩ ገልፀዋል፡፡
በኤክስፖው 23ቱ ቀናት የተለያዩ ዘመናዊና ባህላዊ የውዝዋዜ እንዲሁም በርካታ የተሰጥኦ ውድድሮች የሚካሄዱ ሲሆን ከዘመናዊ አውቶሞቢል ጀምሮ የተለያዩ ሽልማቶች መዘጋጀታቸውም ታውቋል፡፡ ጎብኚው በመረጃ እጦት እንዳይቸገር፣“ሁሉም ቤት” የተባለ የመረጃ አፕልኬሽን መዘጋጀቱም ታውቋል፡፤
የፋሲካው ኤክስፖ እስከ ሚያዝያ 22 የሚቆይ ሲሆን በመቀጠልም ኢዮሐ በቴክኒካል ፕሮፖዛል ያሸነፈውና የበጎ አድራጎት ስራን ለመስራት እየተዘጋጀበት ያለው የቀይ መስቀል ኤግዚቢሽን ከሚያዚያ 28 እስከ ግንቦት 2 ቀን 2008 ዓ.ም እንደሚያካሂድና ገቢው ሙሉ ለሙሉ በድርቁ ለተጎዱ ወገኖች እንደሚውል ለማወቅ ተችሏል፡፡   

Saturday, 09 April 2016 10:09

የኪነት ጥግ

 (ስለ ቴሌቪዥን)
ሁሉም ቴሌቪዥኖች ትምህርታዊ ናቸው፡፡ ጥያቄው፡- ምንድን ነው የሚያስተምሩት ነው?
ኒኮላስ ጆንሰን
ሰዎች እርስ በእርስ ከመተያየት ይልቅ ሌሎች ማናቸውንም ነገሮች መመልከት እንደሚመርጡ ቴሌቪዥን አረጋግጧል፡፡
አን ላንደርስ
ቴሌቪዥንን በጣም ትምህርታዊ ሆኖ አግኝቼዋለሁ ለማለት እገደዳለሁ፡፡ አንድ ሰው ቴሌቪዥን በከፈተ በደቂቃ ውስጥ  ወደ ቤተ መፃህፍት ሄጄ አንድ ጥሩ መፅሃፍ አነባለሁ፡፡
ግሮቾ ማርክስ
ቲያትር ህይወት ነው፡፡ ሲኒማ ጥበብ ነው፡፡ ቴሌቪዥን የቤት ቁስ ነው፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
ቴሌቪዥን? ከዚህ መሳሪያ ምንም ጥሩ ነገር አይወጣም፡፡ ቃሉ ግማሽ ግሪክና ግማሽ ላቲን ነው፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
ቴሌቪዥን በቤትህ ውስጥ ልታገኛቸው በማትችላቸው ሰዎች እንድትዝናና ይፈቅድልሃል።
ዴቪድ ፍሮስት
ቴሌቪዥን 90 በመቶው እንቶ ፈንቶ ነው ይላሉ፡፡ ነገር ግን የሁሉም ነገር 90 በመቶው እንቶ ፈንቶ ነው፡፡
ጌኒ ሮዴንቤሪ
የቴሌቪዥን አንዱ ትልቁ አስተዋፅኦ ነፍሰ ግድያን ወደ ትክክለኛ ቦታው ወደ ቤት መልሶ ማምጣቱ ነው፡፡
አልፍሬድ ሂችኮክ
ኤሌክትሪክ ባይኖር ኖሮ ሁላችንም ቴሌቪዥንን በሻማ ብርሃን እንመለከት ነበር፡፡
ጆርጅ ጎባል
በቴሌቪዥን የተፈጠረ ሰው በቴሌቪዥን ሊጠፋ ይችላል፡፡
ቴዎዶር ኤች ዋይት
ቴሌቪዥንን ለማዝናናት ብቻ ሳይሆን ሰዎች የተሻለ ህይወት እንዲመሩ ለማገዝ ልጠቀምበት እሻለሁ፡፡
ኦፕራ ዊንፍሬይ
ቴሌቪዥንን እንወደዋለን፤ ምክንያቱም ቴሌቪዥን የሌለበትን ዓለም ያመጣልናል፡፡
ሆዋርድ ዚን

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አይጥና አንድ እንቁራሪት በቀጠሮ ይገናኛሉ፡፡
አይጥ፤
“እመት እንቁራሪት፤ አንዳንዴ ከውሃ ወጥተሽ መሬት ላይ ፀሐይ ስትሞቂ ሳይሽ ‘ምነው ከዚች ጋር ጓደኝነት ብንጀምር?’ እያልኩ ልቤ ስፍስፍ ይላል፡፡”
እንቁራሪትም፤
“ሆድ ለሆድ የመነጋገር ነገር ጠፍቶን ነው እንጂ እኔም እኮ ባየሁሽ ቁጥር ‘ምነው ጓደኛ በሆንን’ እያልኩ አስባለሁ፡፡”
አይጥ መልሳ፤
“አየሽ አንቺ ውሃም ውስጥ፣ መሬትም ላይ፣ ኗሪ ነሽ፡፡ እኔ ግን መሬት ላይ ብቻ ኗሪ ነኝ”
እንቁራሪት፤
“እንደሱ ብለሽ ራስሺን አታሳንሺ፡፡ ይልቁንም፤ ምንጊዜም እንዳንለያይ እንስማማ፡፡ እግራችንን በገመድ እንሠር” አለቻት፡፡
አይጥም፤
“እጅግ የብልህ ዘዴ አመጣሽ፡፡ በቃ ገመድ እኔ ከየትም ከየትም ብዬ አመጣለሁ” አለች፡፡
እንደተባለው እግሮቻቸውን አቆራኝተው በገመድ አስተሳሰሩ፡፡
መሬት ላይ ባሉ ጊዜ ሁሉ ወዳጅነታቸው ግሩም ድንቅ ሆኖ ቆየ፡፡ እንቁራሪት ወደ ውሃ ውስጥ ገብታ ዋና ስትጀምር ግን ጣጣ መጣ፡፡
አይጥ ወዴት እንደምትገባ መላው ጠፋት፡፡ አይጥ ከመስመጥ በቀር ምንም ምርጫ አልነበራትም፡፡ አይጥ ተንደፋድፋ ሰመጠች፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላም ሬሣዋ ውሃው ላይ ሲንሳፈፍ ታየ፡፡
ታሪኩ ግን በዚህ አላበቃም፡፡ አሞራ ከሰማይ የአይጥን ሬሣ ፍለጋ መጣ፡፡ አይጢቱን ላፍ አድርጐ ወደ አየር ሲምዝገዘግ፤ እግሯ አብሯት የታሠረውም እንቁራሪት ተንጠልጥላ ወደ ሰማይ ወጣች፡፡ “ከኑግ የተገኘህ ሰሊጥ አብረህ ተወቀጥ” ሆነ ነገሩ፡፡ ሁለቱም የአሞራ ራት ሆኑ!!
***
ጊዜን፣ ቦታን፣ ማንነትንና ተግባራዊ አንድነትን ያላገናዘበ መቀናጆ፤ መጨረሻው ክፉ ውድቀት ነው፡፡ ተያይዞ መንኮታኮት ነው፡፡ እንደ እንቁራሪት ውሃ ውስጥ፣ እንደ አይጥ መሬት ላይ የሚኖሩ፣ አንድ ዓይነት ነን ብሎ ማሰብ አጉል ህልም ነው፡፡ አስቀድሞ ነገር የወዳጅነቱ (የህብረቱ) ፋይዳ ምንድነው? ግቡስ ምን ነው? ምንስ ለመሥራት ነው? ሀገራዊ አንድነትን ስናስብ ሀገራዊ ፋይዳውን ማጤን፣ ለሁሉም ወገን ያለውን ፍሬ - ነገር ማሰላሰል፣ ተግባራዊ ሂደቱን መመርመርና ልብ ለልብ መነጋገር ቁልፍ ነገር ነው፡፡
የእንቁራሪትን የምድር - የውሃ ኑሮ በወጉ ማጥናት፤ አንዴ አይጥ አንዴ የሌሊት ወፍ ነኝ የምትለውንም አይጥ፤ ውስጧን ማመዛዘን እጅግ ወሳኝ መሆኑን አንዘንጋ፡፡ ከልዩ ልዩ መልካችንና ከልዩ ልዩ ይዞታችን ተነስተን ልንፈጥር የምንችለውን አገራዊ አንድነት ስናሰላው ልባዊ ግንኙነት ካላደረግን፤ ወይ “እባብ ለእባብ ይተያያል ካብ ለካብ”፣ “ወይ እርስ በእርሱ ሥጋን በኩበት ጠበሱ”፣ አሊያም “ድንጋይ በድንጋይ ላይ ቆሟል”፤ የከፋ መልክ ከያዘም ከታሪክ እንደምንማረው “ለምሣ ያሰቡንን ለቁርስ አረግናቸው” ዓይነት መበላለት ሊያስከትል የሚችል ሁኔታ ሊመጣ ይችላል፡፡ ከአድሮ ቃሪያ አካሄድ ይሰውረን፡፡
ከታሪካችን ካየናቸው ችግሮች አንዱ የሒስ ባህል አለመኖር ነው፡፡ ማንም ስህተቱን መቀበል ቀርቶ፣ ስህተት ከናካቴው አልታየም በሚባልበት አገር፣ ግትርነት መንሰራፋቱ አይታበሌ ነው፡፡ አማካሪ ምክርን ሂሳዊ ቢያደርግ ብዙ መንገድ መጓዝ ይቻላል፡፡ “ተባባሪ ዋይታ” ችግር አይፈታም፡፡ ይልቁንም እዬዬን ያገር ባህል ያደርጋል!
አልፎ ተርፎም፤ ብሶት እስኪጠራቀም፣ አድሮም እስኪገነፍል፣ ሲሸፋፍኑ መኖር እንደ ፖለቲካ ዘይቤ ይያዛል፡፡ እንዲህ ያለ ዘይቤ ሀገርን ያቆረቁዛል፡፡ ነጋ ጠባ ያንኑ ሐተታ ከማነብነብ አንዳንዴ “እህ?” ብሎ ማዳመጥ፣ ስለ አካሄዴ ምክራችሁን ለግሱኝ፣ ያልተዋጠላችሁን ጠይቁኝ ማለት ያባት ነው፡፡ አሁን ይህ ባህል የተጀመረ ይመስላል፡፡ ዋናው ዘላቂነቱ ነው!
ዛሬ በህይወት የሌሉት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ፤ በ97 ዓ.ም ምርጫ ማግስት በነበሩት ችግሮች ላይ ሒስ ሲያቀርቡ፤
“ዋናውና መሠረታዊ ችግር ንቀት ነው፡፡ ተጠቃዋሚዎች በምርጫው አዲስ አበባን ሲያሸንፉ ገዢውን ፓርቲ ናቁ፡፡ ገዢው ፓርቲ ገና ከመነሻው ተቃዋሚዎች በምንም ረገድ አያሸንፉም የሚል ንቀት አድሮበት ነበር” ብለው ተናግረዋል ይባላል፡፡
በሁለቱም ወገን የታየው ንቀት ከፊውዳላዊ ተዓብዮ የመነጨ ነው፡፡ የመደብ መሠረታችን ይብዛም ይነስ በእያንዳንዱ የህይወት ዱካችን ላይ አሻራውን ማሳረፉ አይቀሬ ነው፡፡ ንቀት ካለን ለትግል ያለን ዝግጁነት ለቋሳ ይሆናል፡፡ ንቀት ካለን ወደ ማንጐላጀት እንጂ ወደ ንቁነት አንራመድም፡፡ ንቀት ካለን ጊዜን በአግባቡ አንጠቀምም፡፡ ንቀት ካለን የአገሩ ቁንጮ እኛ ብቻ ነን የሚል ዕብሪት ይጫነናል፡፡ ምንም አይነት ሒስ አንቀበልም፡፡ የተሠሩትን ስህተቶች ጨርሶ እንዳልነበሩ ስለምንቆጥር፣ ጥፋቶችን ከማየት ይልቅ ሌሎች ላይ ማላከክን ሥራዬ ብለን እንይዘዋለን፡፡
ይህ በፈንታው ሁሉን ኮናኝ፣ ሁሉን ረጋሚ ያደርገናል፡፡ ይሄኔ እንግዲህ ጨዋታው ሁሉ “Do damned don’t damned” የሚሉት ይሆናል ፈረንጆቹ! ሠራህም ትረገማለህ፣ አልሠራህም ትረገማለህ፡፡ ይሄኔ አገር ከሩጫ ወደ መራመድ፣ ከመራመድ ወደ መዳከር፣ ከመዳከር ዝሎ ወደ መቆም ትመጣለች፡፡ ፍትሐችን ልፍስፍስ፣ ዲሞክራሲያችን ወንካራ፣ መልካም አስተዳደሩ “አልሞትኩም ብዬ አልዋሽም” የሚል፣ ልማቱ ህልም እልም፣ ለውጡ አገም - ጠቀም፣ የህዝብ ቁጥር ከአፍ እስከገደፉ፣ የሥራ አጡ መጠን አበስኩ ገበርኩ ወዘተ. ይሆንና ነገን መፍራት ግድ ይሆናል፡፡ ነገን የሚሠራ ሰው ጥርጣሬ ፎቅ ይሠራበታል! ከዚህ ይሰውረን!
ጥርጣሬ የልብ ለልብ መነጋገር ጠር ነው፡፡ የብሔራዊ መግባባት ሃሳብ እስከዛሬ ሲብላላ ኖረ እንጂ ከልብ አልተሞከረም፡፡ የህግ የበላይነትን አምኖ፣ የዲሞክራሲን መላ በአግባቡ ተረድቶ፣ የዜጐች እኩል ተጠቃሚነትን ተማምኖ፣ ባህላዊ የመግባቢያ መንገዶችን ፈትሾ በቁርጠኝነት ከታጓዙ፣ ብሔራዊ መግባባትና ዕርቅ ላይ መድረስ ይቻላል፡፡ እስከዛሬ አልተሞከረም፤ እንሞክረው፡፡ “አባቴ፤ ብዙ መንገድ አለ፡፡ በየቱ እንሂድ? ባልተሄደበት” አሉ የሚባለው ለዚህ ነው፡፡