Administrator

Administrator

"ህልም ነበረኝ፤ ሁለት አልበም በአንድ ቀን ማውጣት"

ሙዚቀኛ ሮፍናን ኑሪ፤ በአንድ ቀን "ሀራንቤ" እና "ኖር" የተሰኙ ሁለት አልበሞችን፣ "ዘጠኝ" በሚል አብይ ርዕስ ውስጥ ለአድማጮች እንደሚያደርስ ተጠቆመ፡፡

"ይህ አልበም ማሳረጊያ ፕሮጀክቴ ነው። በጣም ደክሜበታለሁ። ቴክኒካል ጉዳዮችን ጨምሮ ብዙ የተለፋበት ነው። የኔን እድገት የምታዩበት አልበም  ነው" ብሏል፤ድምጻዊው።

አክሎም ሲናገር፤ "ህልም ነበረኝ፤ ሁለት አልበም በአንድ ቀን ማውጣት" ብሏል፡፡

በ"ዘጠኝ" አብይ ርዕስ ውስጥ ያሉት ሁለቱ አልበሞች፣ በአጠቃላይ ሃያ አንድ ሙዚቃዎችን ይዘዋል ተብሏል።

በአልበሞቹ ላይ ሀይሌ ሩት፣ ሸዊት መዝገቡ፣ የልጅ ተመስገን ልጆችን ጨምሮ የሀገር ውስጥና የውጪ የሙዚቃ ባለሞያዎች ተሳትፈዋል።

"ሀራንቤ" እና "ኖር" አልበሞች ከሦስት ሳምንት በኋላ ለሙዚቃ አድማጮች እንደሚደርሱ ታውቋል፡፡

አልበሞቹ በሮፍናን ዩቲዩብ ቻናልና በሁሉም የሙዚቃ ማሰራጫ መተግበሪያዎች በኩል ይለቀቃሉ።

ከአልበሙ ውስጥ ለሁለቱ Yሙዚቃ ቪዲዮዎች የተሰራ ሲሆን፤ ከአልበሙ የተወሰደ አንድ የሙዚቃ ቪዲዮ ዛሬ ማታ ለአድማጮች ይደርሳል ተብሏል።

Tuesday, 23 January 2024 20:11

ኢህአፓና ስፖርት part 6

https://youtu.be/k-llnz_sfro?si=Sr1-RWyz4-25MfPi

ይህ ሰው ሁሌም በመረጃ አሰባሰብ፣ በዝግጅት አቀራረቡና በሌሎች ነገሮቹ  ድንቅ ከሚሉኝ ሰዎች ውስጥ አንዱ ነው።
 ሁለገቡ ሰው ገነነ መኩሪያ( ሊብሮ)።
 ሊብሮ የምትለውን ስያሜ ያወጣለት በአብዛኛው የእግር ኳስ አፍቃሪ በአዝናኝነቱ፣ በእግር ኳስ ወዳድነቱ የሚታወቀው የኳስ ሜዳው ሰው ሀይሌ ካሴ ነው። በወቅቱ ጊዮርጊስ ከሜታ አቦ በተጫወቱበት ጊዜ አምስት ተጫዋቾችን አልፎ ግብ  ባስቆጠረበት ጊዜ ነበር የተቀፅላው መነሻ።
ሊብሮ የተወለደው ይርጋለም ከተማ ቢሆንም፣ እድገቱ ግን ሻሸመኔ ቀበሌ 09 ነው ።
በልጅነት ወቅትም እግርኳስ ይወድ የነበረው ገነነ፤ በጊዜው በየ15 ቀኑ አዲስ አበባ  የሚመጡት የሆቴላቸው  ሾፌር አብሮቸው ያቀና ነበር፤ በነበራቸው ቆይታም ካምቦሎጆ ገብተው እግር ኳስ ተመልክተው ይመጡ  ነበር፤ በዚያ  በአፍላነት ጊዜው መሆኑ ነው።
ሌላው የሚገርመው ገኔ ሻሸመኔ ውስጥ ላለ ቡድን  ለAም፣ ለBም፣ ለCም ይጫወት ነበር፤ በአንድ ቀን ውስጥ።
የቀበሌ 09 ቡድንም በወቅቱ የአቶ ሙኩሪያ ቀበሌ ቡድን ይባል ነበር። በጊዜው እሱን ጨምሮ ስድስት ወንድሞቹ እዛ ቡድኑ ውስጥ ይጫወቱ  ነበሩ። እንደዚህ እያለ ነው ወደ እግር ኳስ ተጫዋችነት ያመራው።  ወደ ክለብ ደረጃም መጀመሪያ የመጣው በ1975 ዓ.ም አካባቢ፣ የትምህርት ቤት ውደድሮች ላይ በመታየት ከእነ ታሪኩ መንጀታ፣ አስቻለው ጋር በመሆን ነበር፤ ወደ ሜታ ቢራ የተቀላቀለው።
እዚህ ጋ  በወቅቱ በአጨዋወትና በሌሎች ተዛማጅ ነገሮች  ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ከአሰልጣኞች ጋር ሙግት ይገጥም ነበር። በጊዜው ሜታን ያሰለጥን ከነበረው ስዩም ጋር ይጋጩ እንደነበር ይጠቀሳል። በእግር ኳስ ተጫዋችነቱ ወቅት እረፍት ሰአቱን በማንበብ ማሰለፍ ይወድ እንደነበር አብረውት የተጫወቱት ይመሰክራሉ።
የሊብሮ ጋዜጣው መነሻ
ከዛ በፊት በበጎ ፍቃደኝነት በተለያየ የህትመትና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ይሰራ ነበር። ከሰራባቸው የህትመት ሚዲያ ውስጥም መረሀ ስፖርት፣ የኢትዮጵያ ራዲዮና ቴሌቪዥን ውስጥ ይጠቀሳል።
በመቀጠል ከጓደኞቹ ጋር በመሆን ማለትም አበበ ወልደ ፃዲቅ፣ ሁሴን አብድልቀኒ ጋር በመሆን ሻምፕዮን የምትባል የስፖርት ጋዜጣ መስርተው ሰርተዋል።
በማስከተልም የራሱ የሆነችውን ሊብሮ ጋዜጣ አቋቋመ።  የዚህች ጋዜጣ አመሰራረት የሚገርም ነው፤ በተለይ በወቅቱ የነበሩቱ የቦሌ ማተሚያ ስራ አስኪያጂ አሰፋ ከበደ ሊመሰገኑበት የሚገባ ድርጊት ነው። በጊዜው ገነነ የሚያሳትምበት ገንዘብ እጥረት ያጋጥመዋል፤ ሁሉን ነገር ጨርሶ ከሰራ በኋላ ግን እጁን አጣጥፎ ከሰማይ መና አልጠበቀም፤ ወደ ቦሌ ማተሚያ ቤት  ሄዶ ስራ አስኪያጁን ያለበትን ነገር ሁሉ አስረድቶ  በእሳቸው ቀና ትብብር አማካኝነት ጋዜጣዋ ለመጀመሪያ ጊዜ  ለህትመት በቃች። በጊዜውም በጣም ተወዳጅ ጋዜጣ እንደነበረች በጊዜው የነበሩ ሰዎች ያስታውሳሉ፡፡ አብዛኛውን ትኩረት የምታደርገው የሀገር ውስጥ ዜናዎች ላይ ነበር። ለነገሩ አብዛኛዎቹ የዚያን ዘመን ጋዜጦች ትኩረታቸው የሀገር ውስጥ እንደነበር መመልከት ይቻላል።
በህትመት ግን ለ13 አመታት ከብዙ ችግሮች ጋር እየተጋፈጠች ለህዝብ ተደራሽ መሆን ችላ ነበር ። አብዛኛውን ስራ እራሱ  ገነነ ነበር የሚሰራው። የጋዜጣ ስራ ምን ያህል አድካሚ እንደሆነ  የሚያውቀው ያውቀዋል።
ነገር ግን ጋዜጣዋ ከተቋረጠች በኋላ ለአጭር ጊዜ በድረ ገፁ በኩል ጀምሮት ነበር። ቢሆንም ግን  ሊዘልቅ አልቻለም።  ሁሉን ነገር ገታ አድርጎ  በመተው  በመፅሐፍና ሌሎች ተዛማጅ መስኮች ላይ በመስራት በተከታታይ በእግር ኳስ ዙሪያና ፖለቲካ ላይ የሚያጠነጥኑ መፅሀፎችን አበረከተለን፡፡  ለመጥቀስ ያህል፡-
*የአሸናፊ ግርማ የህይወት ታሪክ፤ ከአሸዋ ሜዳ እስከ አርጀንቲና
*የእግር ኳስ ወጎች
*ኢህአፓና ስፖርት 1 እና 2 እዚህ ጋ በቅርብ ለእይታ የቀረበው የነገን አልወልድም የታሪኩ መነሻ ከ ኢህአፓና ስፖርት 1 የተወሰደ ነው)
እና ሌሎች በህትመት ደረጃ ያልወጡ በሙዚቃና በሌሎች ጉዳዮች ያተኮሩ መፅሐፍት ሲያሰናዳ ነበር፡፡
ሌላው በ90ዎቹ አጋማሽ ላይ በስፋት ይወራ ስለነበረው የኢትዮጵያዊ ስልጠና ሀሳብ አመንጪ ሰው ነው፡፡ በተለምዶ  Gk የሚባለውን  የስልጠና ፍልስፍና በኋላ በካሳዬ አራጌ  ዳብሮ ለአጭር ጊዜ የተሞከረው፡፡ በነገራችን ላይ በዚህ ዙሪያ ላይ በ1994 ዓ.ም ኢትዮጵያ ስልጠና መፅሀፍ ማውጣቱ አይዘነጋም። እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ ደብዳቤ ፅፏል በስልጠናው ዙሪያ ላይ።
*****
ገነነ መኩሪያ (ሊብሮ ) ባደረበት ህመም ህክምና ሲከታተል ቆይቶ ማረፉ ተሰምቷል፡፡ የአዲስ አድማስ ዝግጅት ክፍል፣ በታላቁ የስፖርት ሰው ገነነ መኩሪያ ህልፈት የተሰማውን ጥልቅ ሃዘን እየገለጸ፤ ለቤተሰቦቹ ወዳጆቹና አድናቂዎቹ መጽናናትን ይመኛል፡፡ ፈጣሪ ነፍሱን በአጸደ ገነት ያኑርለት፡፡

 

 

ጋዜጠኛ ገነነ መኩሪያ (ሊብሮ) ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።

ገነነ መኩሪያ ባደረበት ህመም ምክንያት በሕክምና ሲረዳ ቆይቶ ሕይወቱ ዛሬ ንጋት ላይ ማለፉን ቤተሰቦቹ አስታውቀዋል፡፡

በአዲስ አበባ "ንባብ እና አገር" የተሰኘ የንባብ ፌስቲቫል ሊካሄድ ነው

የአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ "ንባብና አገር" የተሰኘ የንባብ ፌስቲቫል ከጥር 16 እስከ 23ቀን 2016 ዓ.ም ድረስ እንደሚያካሂድ አስታወቀ።
የባህልና ቱሪዝም ምክትል ቢሮ ሃላፊ አቶ አስፋው ኩማ እንዳሉት፤ የንባብ ፌስቲቫሉ ዓላማ የከተማው ማህበረሰብን የንባብ ባህል ለማሻሻልና ግንዛቤ ለመስጠት ነው።
ባለፉት ሶስት ዓመታት የተለያዩ በራሪ ጽሁፎች በማዘጋጀት የስርፀት ሥራ ሲሠራ መቆየቱን የገለፁት ሃላፊው፤ በዚሁ ዝግጅት በህትመት ታሪክ ውስጥ በርካታ አስተዋፅኦ ያደረጉ ድርጅቶችና ደራሲያን ታሪካቸው ይወሳል ብለዋል።
የንባብ ፌስቲቫሉ ለ8ኛ ጊዜ የተዘጋጀ ሲሆን ዝግጅቱ በአዲስ አበባ ሙዚየም ይደረጋል።

የአንጋፋው ጋዜጠኛ አስፋው መሸሻ የቀብር ስነ-ስርዓት ተፈፀመ

ጋዜጠኛ አስፋው መሸሻ ባደረበት ህመም በአሜሪካ ሕክምናውን ሲከታተል ቆይቶ ባለፈው ሳምንት ሕይወቱ ማለፉ ይታወቃል፡፡

በሚሊኒየም አዳራሽም የስንብት መርሐግብር ከተካሄደ በኋላ በመንበረ ጸባኦት ቅ/ሥላሴ ካቴድራል ቤተሰቦቹ፣ የሙያ አድናቂዎቹ፣ የስራ ባልደረቦቹ በተገኙበት የፍትሃት እና የቀብር ስነ ስርዓት ተካሂዷል፡፡

የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል፣ በአንጋፋው የሬዲዮና ቴሌቪዥን ፕሮግራም አዘጋጅና አቅራቢ አስፋው መሸሻ ህልፈት የተሰማውን ጥልቅ ሃዘን እየገለፀ፤ ለቤተሰቦቹ፣ ለስራ ባልደረቦቹና ለወዳጆቹ ሁሉ መጽናናትን ይመኛል። ፈጣሪ ነፍሱን በአፀደ ገነት ያኑርለት።

የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas

“ጎተ የአጭር ልቦለድ ቡፌ ነው ያቀረበልን“


መስዑድ ጀማል እባላለሁ፡፡ በ“ሠላሳዎቹ“ መድበል ውስጥ “ወሎ ሎጂ“ የተሰኘ ሥራዬ ታትሞልኛል፡፡ በሙያዬ በአማራ ሚዲያ ኮሙኒኬሽን (አሚኮ) ጋዜጠኛ ነኝ፡፡
ድርሰትህ በ“ሠላሳዎቹ“ የአጫጭር ልብወለዶች መድበል ውስጥ በመካተቱ ምን ዓይነት ስሜት ፈጠረብህ? ከዚህ በፊት ተመሳሳይ ዕድል ገጥሞህ ያውቃል? የራስህን መጽሃፍስ አሳትመሃል?
ልዩ ደስታ ነው የሚሰማህ። እስከዛሬ ትደሰተው ከነበረው ደስታ ከፍ ያለ።ትንሽ ኩራትም ቀልቀል ያለበት። ቀደም ሲል በመፅሐፍ መልክ የወጣ ሥራ የለኝም። በሌላ የጥበብ ቅርፅ ግን አለ። ከዚህ በፊት ደራሲ ሜሪ ፈለቀ  የአጭር ፊልም ወድድር አወዳድራ ነበር። ‘ሀቅ’ በሚል አጭር ፊልም ተወዳድሬ 1ኛ በመውጣት 50,000 ብር አሸንፌያለሁ። ያው ስለሚያያዝ  ብዬ ነው። በመፅሐፍ ግን ይህ የመጀመሪያዬ ነው።
የአጫጭር ልብወለዶች ስብስቡን   እንዴት አገኘኸው?
 በጎተ ፅሁፌ ከተመረጠ በኋላ መፅሐፉ ከመታተሙ በላይ በጉጉት ስጠብቀው የነበረው መፅሐፉ ወጥቶ 29 ታሪኮችን እስካነብ ነበር። መፅሐፉ ወጥቶ 29ኙን ታሪኮች ካነበብኩ በኋላም መጓጓቴ ልክ እንደነበረ ነው የገባኝ። ጎተ የአጭር ልቦለድ ቡፌ ነው ያቀረበልን። የተለያየ መልክ፣ መዓዛና ጣዕም ያላቸው አጫጭር ልቦለዶችን ነበር ያገኘሁት።  የመጣንበት አካባቢያዊ ዳራ ደግሞ ድርሰቶቹ በመቼት እንዳይገደቡ አድርጓቸዋል። ኢትዮጵያን በሁሉም መአዘን ትቃኛታለህ። ወደ ወሎ፣ ትግራይ፣ አርባምንጭ፣ ጅማ... የማትሄድበት ሀገር፤ሄደህም የምታጣው ነገር የለም። ራሳቸው ወደቆረቆሩት የምናብ ሀገር የሚወስዱህም አሉ። “ሠላሳዎቹ“ መፅሐፍ በህብረ ቀለማት ያጌጠ እንደምንለው፣ “በህብረ ታሪኮች” ያሸበረቀ መፅሐፍ ነው ማለት እንችላለን። በቋንቋ አጠቃቀም፣በአተራረክ፣በጭብጥ፣በገፀ ባህሪ አሳሳል፣በትልም አጎናጎን፣በአተያይ፣በአፃፃፍ ፍልስፍና ሁሉም የራሱን ቦይ እየቀደደ እንድትፈስ ያደርግሀል። ከአንዱ ታሪክ ወደ ሌላው ታሪክ ስትሄድ በጉጉት ነው፤ “ይሄኛው ደሞ ስለምን ይሆን?” እያልክ ነው። በሁሉም ድርሰቶች የምትደመምበት አንዳች ነገር አታጣም።
የወጣት ጸሃፍት ሥራዎች እንዲህ ተሰባስበው በጋራ መታተማቸው ምን ፋይዳ አለው ብለህ ታስባለህ?
አብዛኛው የመፅሐፉ ደራሲ “ማነህ?” በሚል ጥያቄ  በጥበብ ሸንጎ ቆሞ ነፃ ለመውጣት እየተሰቃየ ባለበት ሰዓት ጎተ  ደርሶ “እሱ እከሌ ነው...ደራሲ ነው” ብሎ ምስክር ሆኖ፣ ነፃነትና ማንነት እንደሰጠን አምናለሁ።
ወጣት እንደመሆናችን ብዙ ጥርጣሬዎችና ፍርሀቶች ወስጣችን ይኖራሉ። መመረጣችን፣ ከምናከብራቸው ደራሲዎች ጋር መገናኘታችን ማውራታችንና “ሠላሳዎቹ” መፅሐፍ መታተሙ እነኚህን ፍርሀቶቻችንና ጥርጣሬዎቻችንን እንድንጋፈጥና እንድናሸንፋቸው አድርጎናል። ሌላኛው ጉዳይ ደግሞ በብዙዎች አልቀመስ ያለውን የመፅሐፍ ህትመት ዋጋ መናርን አልፈን እንድንነበብ ሆነናል። ብዙዎች ይህንን ዕድል አላገኙም። ከዚያ ባለፈ ስራዎቻችን በጋራ መታተማቸው “Gothe 2022 winners” የሚል ቤተሰብ እንዲመሰረት እድል ከፍቷል። አዳዲስ ደራሲዎች ከዚህ በፊት የህትመት ብርሀን ካገኙ ደራሲያን ጋር እንድንተዋወቅና እንድንማማር አድርጓል። ፅሁፎችን መላላክና  አስተያየት እንድንለዋወጥ፣ ቀጣይ ሌሎች ስራዎችን  በጋራ ለመስራት እንድናቅድ አድርጓል።
በጀርመን የባህል ማዕከል ድጋፍ ከተሰጣችሁ አጭር ሥልጠና ምን አዲስ ትምህርት ቀሰምክ?
ስልጠናው ጥሩ ነበር...theory አልነበረም፤ በስልጠናው። የራሳችንን ፅሁፍ እየመዘዙ በጠንካራና በደካማ ጎኖቻችን ነበር ስንሰለጥን የነበረው። ከስልጠናው ስለ ፊደላትና ቃላት አጠቃቀም ብዙ የተማርኩት ነገር አለ። በዘመን ሂደት የተቀየሩ ቋንቋዎች አሉ። “አደረግኩ” ብለን እንፅፋለን፤ “አደረግሁ” ማለት ሲገባን።”ፀሀይ” ነው፣ “ጸሀይ” ብለን መፃፍ ያለብን? ብዙዎቻችን በዚህ ክፍተት ነበረብን። ነገር ግን በስልጠናውም ፤በአርታኢያችን ቴዎድሮስ አጥላው እገዛም የለወጥነው ነገር አለ።
ከአገራችን ወይም ከውጭ አገራት  የአጭር ልብወለድ ጸሃፍት ማንን ታደንቃለህ?
ብዙ የማደንቃቸው የአጭር ልቦለድ ደራስያን አሉ፤ሌሊሳ ግርማ፣አሌክስ አብርሀም...እና አዳም ረታን እመርጣለሁ፡፡ የግድ አንድ ከተባለ አዳም ረታ ምርጫዬ ነው፡፡ አንድን የጥበብ ሰው ስመዝን አይምሮ ውስጥ ተሰንቅረው በሚቀሩ፣ ለትውስታ ቅርብ በሆኑ ስራዎቹ የመመዘን አባዜ አለብኝ። የአዳም ረታ የ”ሎሚ ሽታ” አይምሮዬ ውስጥ የቀረ ታሪክ ነው።ከገፀ ባህሪያቱ እስከ አተራረክ ቴክኒኩ አይምሮዬ ውስጥ አለ። ከውጭ ኦ ኸነሪን  እመርጣለሁ። ያው ቅድም እንዳልኩት ነው። “The last leaf” እያደር የሚደንቀኝ ታሪክ ነው።



ባለፈው ሳምንት የ“ሠላሳዎቹ“ የአጫጭር ልብወለዶች መድበል የሃሳብ ጠንሳሽና የፕሮጀክቱ መሪ እንዲሁም በጀርመን ባህል ማዕከል የቤተ መፃህፍትና የመረጃ ሃላፊ የሆነውን ዮናስ ታረቀኝ በመጽሐፉ ዝግጅቱ ዙሪያ ማነጋገራችን ይታወሳል፡፡ ዛሬ ደግሞ በዚሁ ርዕሰ ጉዳይ ዙሪያ ድርሰቶቻቸው በመድበሉ የተካተተላቸው ሦስት ወጣት ጸሃፍትን አነጋግረን፣ ሃሳባቸውን እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡  




”ለአንባቢያን ምርጫን ያሰፋል ብዬ አምናለሁ“

“እድል መሰጠቱ በራሱ በጣም ትልቅ ነገር ነው”



ነዋል አቡበክር እባላለሁ። በሙያዬ የሚዲያ ባለሞያ ነኝ። በ“ሠላሳዎቹ“ የአጫጭር ልብወለዶች መድበል ፅሁፎቻቸው ከታተመላቸው 30 ወጣት ፀሀፍት አንዷ ነኝ። ‘’የክራሩ ክር’ የሚል ድርሰቴ በመድበሉ ውስጥ  ታትሞልኛል፡፡
ድርሰትሽ በ“ሠላሳዎቹ “ የአጫጭር ልብወለዶች መድብል ውስጥ በመካተቱ ምን ዓይነት ስሜት ፈጠረብሽ? ከዚህ በፊት ተመሳሳይ ዕድል ገጥሞሽ ያውቃል? የራስሽን መጽሐፍስ አሳትመሻል?
ለመጀመሪያ ጊዜ ስሜ በመጽሐፍ ላይ ሰፍሮ ሳየው እጅግ ነበር ደስ ያለኝ። ሥነ ፅሁፍን ለሚወድና ፅሁፍ ለሚሞክር ሰው ለመጀመሪያ ጊዜ ‘የሱ’ የሚባል ፅሁፍ ኖሮት ለመነበብ ሲበቃ ያለው ስሜት ይሄ ነው የሚባል አይደለም። የፃፍከውን ነገር የምታከብራቸው ባለሞያዎች አንብበውት፣ አምነውበትና ወደውት ወደ ህትመት መላኩን ስታውቅ፣ የሚያስፈራና በራስ መተማመን የሚጨምር ስሜት ነው የሚሰማህ፡፡ መፅሐፉ ከተነበበ በኋላም ሰዎች የሚያበረታታ አስተያየት ሲሰጡህ ውስጥህ የሚፈጥረው ትልቅ ተስፋ አለ። ከዚህ በፊት ተመሳሳይ ውድድር ላይ ተሳትፌም ሆነ የራሴን መጽሐፍ አሳትሜ አላውቅም።
. የአጫጭር ልብወለዶች ስብስቡን እንዴት አገኘሽው ?
የ“ሰላሳዎቹ“ አጫጭር ልብወለዶች ስብስብ’፣ ድንቅ ወጣት ፀሀፊያንን ለማንበብ እድል ያገኘሁበት፣ ብዙ አይነት ቀለም የተመለከትኩበት፣ ታሪክ በመንገር አቅማቸው በአተራረካቸውና በሀሳባቸው የተገረምኩባቸውን ፅሁፎች ያገኘሁበት መጽሐፍ ነው።
የወጣት ጸሃፍት ሥራዎች እንዲህ ተሰባስበው በጋራ መታተማቸው ምን ፋይዳ አለው ብለሽ ታስቢያለሽ?
በጣም ትልቁ ነገር እድል መስጠቱ ነው ብዬ አስባለሁ። ወጣቶች በራሳቸው አምነው የሚሉት ነገር ኖሯቸው ለመፃፍ እንዲነሱ የሚያደርግ እድል መሰጠቱ በራሱ በጣም ትልቅ ነገር ነው።  ከዚያ በተጨማሪ እንደ አንባቢ ይሄ መጽሐፍ የዘመናችንን መልክ የምናይበት አንዱ መንገድ ነው። በተቀራራቢ እድሜ የሚገኙ ነገር ግን የተለያየ ህይወትና አመለካከት ያላቸው ፀሀፍት ሃሳብና ስሜት፣ ህመምና ተስፋ ወዘተ-- በአንድ መጽሐፍ ተሰድረው ማንበብ ችለናል። እንደ ጀማሪ ፀሀፊ፣ ፅሁፍን የማሳተምና የመነበብ እድል ማግኘት የሚሰጠው ሞራልና ተስፋ በምንም የሚሰፈር አይደለም።
 ወጣት ጸሀፍት ከሥነ ፅሁፍ ጋር ስለሚኖረን ግንኙነት ለመወሰን እራስን መመልከቻ ነውም ብዬ አስባለሁ።
ከራስም  ከታላላቆቻችንም  ለመማር እድል ይሰጣል።
ከዚህም ባለፈ በጣም ያስደነቁንና የት ነበሩ ያስባሉንን አዲስ ፀሀፍትም  አፍርቷል፤ አበርክቷል ብዬ አስባለሁ።
 በጀርመን የባህል ማዕከል ድጋፍ ከተሰጣችሁ አጭር ሥልጠና ምን አዲስ ትምህርት ቀሰምሽ?
በርግጥ በስራ አጋጣሚ ከተማ ውስጥ ስላልነበርኩ በሥልጠናውን መሳተፍ አልቻልኩም ነበር። ነገር ግን ፅሁፉን ለመፃፍ ከማሰብ ጀምሮ እስከ መጨረሻው የአርትኦት ስራ ድረስ በጣም ብዙ እውቀትን አግኝቻለሁ። እኔ በአፃፃፍ ብዙ የምሳብበትን የአፃፃፍ አይነት ከማወቅና ከመረዳት ጀምሮ ስለ አማርኛ ሰዋሰው ፤ ቃላት መረጣ ፤ ሀሳብ አሰፋፈር ብዙ ነገር አስተምሮኛል።
ብዙ ጊዜ  ጀማሪ ፀሀፊ ስትሆን ልትፅፍ የፈለከውና አእምሮህ የሰጠህን ሀሳብና ቃል ነው ወረቀት ላይ የምታሰፍረው። በዚህ በኩል መንገድ የሚያሳይህ፣ ስህተትህን የሚያርምህና እራስህ እንድታስተካክል እድል የሚሰጥህ ስታገኝ ብዙ ታተርፋለህ፡፡ ለዚህ ደግሞ የጀርመን የባህል ማዕከልን ፣ አርታኢዎቻችንን፣ አስልጣኞቻችንንና አዘጋጆቹን ከልብ እናመሰግናለን።
 ከአገራችን ወይም ከውጭ አገራት የአጭር ልብወለድ ጸሐፍት ማንን ታደንቂያለሽ ?
ከሀገር ውስጥ ተመስገን ገብሬ፣ ከውጭ የፍራንዝ ካፍካ ፅሁፍ ይስበኛል።

ሊድያ ተስፋዬ እባላለሁ። ትውልድና እድገቴ አዲስ አበባ ነው። ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በመጀመሪያ በኢኮኖሚክስ ቀጥሎም በእንግሊዝኛ ሥነ ጽሑፍ ተመርቄአለሁ። በሕትመት ሚድያው ላይ ከጀማሪ ዘጋቢነት ጀምሮ በተለያዩ ድርሻዎች ሠርቻለሁ፣ አሁንም እየሠራሁ ነው። ድርሰቴ በመጽሐፍ ላይ ሲታተም የአሁኑ የመጀመሪያዬ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በመደበኛነት እሠራ በነበረበት “አዲስ ዘመን“ ጋዜጣ እንዲሁም በኋላ ላይ “አዲስ ማለዳ“ ጋዜጣ ላይ የተለያዩ ጽሑፎችን ለአንባቢያን የማድረስ እድልን አግኝቻለሁ። “ሠላሳዎቹ“ በተሰኘው መድበል ውስጥ ‘’ስለምን ታለቅሺያለሽ?’’ የሚለው ድርሰቴ ተካትቶልኛል፡፡
ድርሰትሽ በ“ሠላሳዎቹ“ የአጫጭር ልብወለዶች መድብል ውስጥ በመካተቱ ምን ዓይነት ስሜት ፈጠረብሽ? ከዚህ በፊት ተመሳሳይ ዕድል ገጥሞሽ ያውቃል? የራስሽን መጽሐፍስ አሳትመሻል?
በቅድሚያ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ይህን እድል ስለሰጠን በጣም አመሰግናለሁ። ከዚህ ቀደም የራሴን መጽሐፍ አላሳተምኩም። በተለያዩ ደራሲዎች በኀብረት ተዘጋጅተው የታተሙ የአጫጭር ልብወለድ እንዲሁም የግጥም ስብስብ ሥራዎች መኖራቸውን አውቃለሁ እንጂ እንዲህ ያለ እድል ገጥሞኝ አያውቅም። ደራሲ የመሆን ምኞት  አለኝ፡፡ ድርሰቴ በዚህ “ሠላሳዎቹ“ የተሰኘ መድበል ውስጥ መግባቱን ሳውቅ በጣም ነበር ደስ ያለኝ። በአንድ በኩል መመረጡ ራሱ ለወደፊት በተስፋ እንድበረታ የሚያግዘኝ ነው። አንድ ብሎ መጀመር ከባድ ነው፣ አንዳንዴ እንዲህ ያለ እድልን ይፈልጋል። በሌላ በኩል፤ ለሕትመት ወጪ እንድንጨነቅ አልተደረግንም። ከዚያም ባልተናነሰ በሥነ ጽሑፉ ዘርፍ  የተመሰገኑ፣ የተደነቁ ሰዎች ናቸው አርትዖቱን የሠሩት። ድርብርብ እድል ማለት ነው። በእነዚህ ሁሉ ምክንያቶች የተነሳ እድሉን ማግኘቴም፣ ቀድሞ ነገር እድሉ ራሱ መፈጠሩ ደስ አሰኝቶኛል። በዚህ አጋጣሚ ለዚህ ምክንያት የሆነውን የጀርመን ባሕል ማዕከል ወይም ጎተ’ን፣ እንዲሁም በዋናነት ሐሳቡን ከመጸነስ ጀምሮ ልብወለዶቹ እንዲህ መጽሐፍ ሆነው እንዲወጡ ለማድረግ፣ ባየነውም ባላየነውም ሂደት ውስጥ ሲደክም የነበረውን ዮናስ ታረቀኝን  በጣም አመሰግናለሁ።
የአጫጭር ልብወለዶች ስብስቡን እንዴት አገኘሽው?
በጣም ወድጄዋለሁ። የተለያዩና ጥልቅ ሐሳቦችን፣ ዕይታዎችን፣ ስሜቶችን የተሸከሙ ሥራዎች ናቸው። በወጣቶች ዐይን ሀገር፣ ዓለም፣ ማኅበረሰብና ራሱ ሕይወት የተሳሉበትን መንገድ አሳይቶኛል። ወደፊት በአዳዲስ ሥራዎች  ላያቸው የምናፍቃቸው ደራሲዎችን አስተዋውቆኛል።  
የወጣት ጸሐፍት ሥራዎች እንዲህ ተሰባስበው በጋራ መታተማቸው ምን ፋይዳ አለው ብለሽ ታስቢያለሽ?
ይህን ከኹለት አንጻር ነው የማየው፣ ከደራሲዎችና ከተደራሲዎች አንጻር። ከደራሲዎች አንጻር መተባበርን፣ አንድነትን፣ መተዋወቅን የሚፈጥርና እንደ ሃምሳው ሎሚ የቤት ሥራን አከፋፍሎ ድካምን የሚቀንስ ነው። ይህን የእኛን ሥራ እንኳ ብንመለከት፣ ሠላሳዎቻችንም በመጽሐፉ ላይ በተካተተ አንድ ሥራችን ብቻ የተነሳ አፋችንን ሞልተን መጽሐፉን ‘የእኔ መጽሐፍ’ እንላለን። ልክ እንደዛ ሁሉ፣ አብሮ መሥራቱ አንድነትን ይፈጥራል፣ ያበረታል፣ ያተጋል። ከተደራሲዎች አንጻር ደግሞ የተለያየ ጣዕምን ይሰጣል። አንባቢዎች የአንድ ደራሲን ወይም የአንዲት ደራሲትን ሥራ አይደለም የሚያነብቡት፣ የተለያዩ ደራሲዎችን ሥራ በአንድ ላይ ነው የሚያገኙት። ማኅበራዊ ሚድያው ተወዳጅ ያደረገው አንድ ጠባዩ ይህ ይመስለኛል፣ የተለያዩ ሰዎች ዕይታዎችና ሐሳቦች በአንድ አውድ የሚቀርብበት መሆኑ። በዚያ ልክ ባይሆንም እንኳ፣ መጽሐፍም በራሱ ሜዳ በተለያዩ ጸሐፍት በጋራ የተዘጋጁ ሥራዎችን ሲይዝ፣ ለአንባቢ ምርጫን ያሰፋል ብዬ አምናለሁ። ከዚያ ባሻገር ለሥነ ጽሑፍ አጥኚዎችም  የጥናት ግብዓትና መነሻ ሊሆን ይችላል።
በጀርመን የባህል ማዕከል ድጋፍ ከተሰጣችሁ አጭር ሥልጠና ምን አዲስ ትምህርት ቀሰምሽ?
ድርሰቶቻችን ከተመረጡ በኋላና ለሕትመት ከመዘጋጀታቸው በፊት የሁለት ቀናት ሥልጠና ወስደን ነበር። በዚህ አጋጣሚ እርስ በእርስ ከመተዋወቃችን ጎን ለጎን፣ ስለሥራዎቻችን ጥንካሬና ደካማ ጎን ተነግሮናል። በበኩሌም አስቀድሞ በአስተውሎት የማላያቸው የነበሩ ጉዳዮችን በትኩረት እንዳይ አንቅቶኛል። በዚያው ሥልጠና መሠረታዊ የሚባሉ ከሥነ ጽሑፍ ጋር የተገናኙ ጉዳዮችንም በተመለከተ ሐሳቦችን አግኝተናል። በሥልጠናው የሰማናቸው ልምዶችም ጽሑፎቻችንን ብቻ ሳይሆን እንደ ጸሐፊ ራሳችንም ላይ እንድንሠራ የሚጋብዝ ሆኖ ነው የተሰማኝ።
ከአገራችን ወይም ከውጭ አገራት የአጭር ልብወለድ ጸሐፍት ማንን ታደንቂያለሽ?
ጥቂት ከሚባሉ ሴት ደራሲያት መካከል ሕይወት እምሻውን ብጠቅስ እወዳለሁ። በብዛት በግጥም፣ በጥቂቱ ደግሞ በረጅም ልብወለድ ሥራዎች የሚጠቀሱ ደራሲያት አሉ። በአጫጭር ልብወለድ ግን ጎልተው የሚጠቀሱ ሴት ደራሲያት መኖራቸውን እርግጠኛ አይደለሁም። ከእኔ የንባብ እጥረት ከሆነ ይቅርታ እጠይቃለሁ። ካሉትና ከማውቃቸው ግን ሕይወት እምሻውን አደንቃለሁ።