
Administrator
ኢቦላ - የዛሬ 38 ዓመት
ቤልጂየማዊው ፒተር ፒዮ የኢቦላ ቫይረስን ለመጀመሪያ ጊዜ ከመረመሩና ለቫይረሱም ስያሜ ከሰጡ ሳይንቲስቶች አንዱ ነው፡፡ በቅርቡ ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ የሰጠውን ቃለመጠይቅ ለጋዜጣው በሚመች መልኩ አቅርበነዋል መልካም ንባብ፡፡
“እሼ እዛው ነዋሪ ገበሬ ነው፡፡ ሞቅ ይለዋል! አንዱ ገንዘብ ሰጥቶ ምግብ በሳህን አርጎ ሂድ ወደሚስትህ ይለዋል፡፡
ይሄዳል፡፡ ግን በጨለማ በቀጭኑ ድንጋያማ የዘሙቴ መንገድ ሲሄድ ገንዘቡ ይጠፋዋል፡፡ ሳህኑን መሬት አስቀምጦ ገንዘብ
ፍለጋ ይመለሳል፡፡ ገንዘቡ የለም፡፡
ያኔ የኢቦላ ቫይረስ እንዴት እንደታወቀ ንገረኝ?
እ.ኤ.አ በ1976 በመስከረም ወር በአንዱ ቀን የሳቤና አየር መንገድ አውሮፕላን አብራሪ የነበረ ሰው በወቅቱ ዛየር በሚባለው በአሁኑ አጠራር ኮንጐ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ከሚገኝ አንድ ሃኪም በጥንቃቄ የተላከ የደም ናሙና ወደ ቤልጂየም ይዞልን መጣ፡፡ የደም ናሙናው በዛየር ያምቡኩ በተባለ ቦታ በበጎ አድራጎት ስራ ላይ ከነበሩ የቤልጂየም መነኮሳት የኣንዷ ነበር፡፡ መነኩሲቷ በማይታወቅ ህመም እየተሰቃየች የነበረ ሲሆን የደም ናሙናው ሲላክልንም ቢጫ ወባ ሊሆን ይችላል በሚል ግምት ነበር፡፡
በአሁኑ ወቅት የኢቦላ ቫይረስ ምርመራ የሚካሄደው እጅግ ጥንቃቄ በተሞላበት መንገድ ነው፡፡ ያኔ እንዴት ነበር?
ቫይረሱ ምን ያህል አደገኛ እንደነበር አናውቅም ነበር፡፡ በከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሰራበት ላቦራቶሪም ቤልጂየም ውስጥ አልነበረም፡፡ የምንሰራው የተለመደውን ነጭ ጋውንና ጓንት አድርገን ነበር፡፡
የመነኩሲቷ የደም ናሙና ከቢጫ ወባ ጋር ግንኙነት ነበረው?
አልነበረውም፡፡ ህመሟ ከቢጫ ወባና ከታይፎይድ ጋር ግንኙነት ከሌለው ምን ሊሆን ይችላል በሚል ጥረታችንን ቀጠልን፡፡ ከተላከው ናሙና ላይ ቫይረሱን ለመለየት አይጦችንና ሌሎች የላብራቶሪ እንስሳቶችን ወጋናቸው፡፡ ለብዙ ቀናት በእንስሳቶቹ ላይ ምንም አይነት ለውጥ ስላላየን ምናልባት ናሙናው ሲመጣ በቅዝቃዜ እጦት ተጎድቶ ሊሆን ይችላል ብለን አስበን ነበር፡፡ በኋላ ግን እንስሳቱ ተራ በተራ መሞት ሲጀምሩ ናሙናው ገዳይ ነገር እንዳለው አረጋገጥን፡፡
ከዚያስ ምን አደረጋችሁ?
በትንሽ ጊዜ ውስጥ ሌላ የመነኩሲቷን ደም የያዘ ናሙና መጥቶልን በኤሌክትሮን ማይክሮስኮፕ ለመመርመር ስንዘጋጅ፣ የአለም የጤና ጥበቃ ድርጅት ናሙናውን ከፍተኛ ጥንቃቄ ወዳለበት እንግሊዝ ወደሚገኝ ላቦራቶሪ እንድንልከው መመሪያ ሰጠን፡፡ ነገር ግን አለቃዬ የፈለገው ነገር ቢሆን ስራችንን ማጠቃለል አለብን ብሎ ስላመነ ናሙናውን አልላክነውም፡፡ በወቅቱ አለቃዬ ናሙናውን ለመመርመር ሲቀበል እጁ በጣም ይንቀጠቀጥ ስለነበር፣ ከናሙናው ወደ መሬትና ወደ አንዱ ባልደረባችን እግር ላይ ፈስሶ ነበር፡፡ ሆኖም ጓደኛችን ጠንካራ ቆዳ ጫማ አድርጎ ስለነበር ምንም አልተፈጠረም፡፡
በመጨረሻ የቫይረሱን ምንነት አወቃችሁ?
አዎ፡፡ ለመመርመር ብዙ ጊዜ የፈጀበን ቫይረስ ትልቅና ረዘም ያለ መስሎን ነበር፡፡ ቫይረሱ ከቢጫ ወባ ጋር ምንም አይነት ግንኙነት የለውም፡፡ ይልቁንም በ1960ዎቹ ጀርመን ማርበርግ ውስጥ ብዙ የላቦራቶሪ ባለሙያዎችን ህይወት ከቀጠፈው ማርበርግ ቫይረስ ጋር የሚመሳሰል ነበር፡፡
ስጋት አልፈጠረባችሁም ነበር?
ስለ ማርበርግ ቫይረስ ምንም አላውቅም ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ተማሪዎቼን ስለዚያ ወቅት ስነግራቸው ስለ ድንጋይ ዘመን የማወራላቸው ይመስላቸዋል፡፡ ላይብረሪ ሄጄ የቫይሮሎጂ አትላስ ላይ ማየት ነበረብኝ፡፡
የእኛ ውጤት በታወቀ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሲዲሲ ባወጣው መረጃ ማርበርግ እንዳልሆነ ነገር ግን ተመሳሳይነት ያለው ቫይረስ እንደሆነ ገለፀ፡፡ በወቅቱ ያምቡኩና በአቅራቢያ ባሉ ቦታዎች ብዙ ሰዎች በቫይረሱ ተጠቅተው ነበር፡፡
ወደ ዛየር ከሄዱት ሳይንቲስቶችም አንዱ ነበርክ አይደል?
አዎ፡፡ የሞተችውን መነኩሲት ጨምሮ ትንሽ ሆስፒታል ከፍተው ይሰሩ የነበሩት ቤልጂየሞች ስለነበሩ የቤልጂየም መንግስት ባለሙያ ለመላክ ሲወስን ወዲያው ፈቃደኝነቴን ገለፅኩ፡፡ ያኔ 27 አመቴ ነው፡፡ የወጣትነት ዘመን ጀብድ በለው፡፡
እንዴት ደፈርክ?
ከዚህ በፊት በአለም ያልታየ ገዳይ በሽታ የምናክም ቢሆንም ቫይረሱ ከሰውነት በሚወጡ ፈሳሾች እንደሚተላለፍ አናውቅም ነበር፡፡ ጋውንና ጓንት እንዲሁም ሞተርሳይክል አሽከርካሪዎች የሚያደርጉትን መነፅር ብቻ ነበር የምንጠቀመው፡፡ ኪንሻሳ የገዛሁትን የጋዝ ማስክ ደግሞ በሙቀቱ ምክንያት ማድረግ አልችልም ነበር፡፡ ያስፈራኝ የነበረው ነገር የደም ናሙና ስወስድ የደም ንክኪ ተፈጥሮ በበሽታው እንዳልያዝ ነበር፡፡
ግን በበሽታው ከመያዝ አመለጥክ?
አዎ፡፡ በእርግጥ በአንድ አጋጣሚ ከፍተኛ ትኩሳት ፣ የራስ ምታትና ተቅማጥ ይዞኝ በቃ ተያዝኩ ብዬ ከክፍሌ ሳልወጣ፣ ለቀናት እንቅልፍ በአይኔ ሳይዞር አሳልፌያለሁ፡፡ በኋላ ግን እየተሻለኝ መጣ፣ የታመምኩት በጨጓራ ኢንፌክሽን ነበር፡፡ በህይወት ከሚያጋጥሙ ፈተናዎች የተሻለው ነው፡፡ ሞት ሲመጣ በአይንህ ታየዋለህ፤ ነገር ግን ለመዳን እድል አለ፡፡
ለቫይረሱ ስያሜ ከሰጡት ተመራማሪዎች አንዱ አንተ ነህ፡፡ ለምን ኢቦላ ተባለ?
ስያሜው በተሰጠበት ምሽት የተመራማሪ ቡድኑ አንድ ላይ እየተወያየ ነበር፡፡ ቫይረሱ በተከሰተበት በያምቡኩ መሰየሙ ቦታውን እስከ ወዲያኛው ያገለዋል ብለን አመንን፡፡ እናም አሜሪካዊው የቡድኑ መሪ በአቅራቢያችን በሚገኘው ወንዝ ይሰየም አለ - ፊትለታችን ከተንጠለጠለው ካርታ ላይ የኢቦላን ወንዝ ተመልክቶ፡፡ ነገር ግን የተሰቀለው ካርታ ትንሽና የተዛቡ ነገሮች ነበሩበት፡፡ ኢቦላም በአቅራቢያ የሚገኝ ወንዝ እንዳልሆነ ብናረጋግጥም ስያሜው ግን ኢቦላ እንደሆነ ቀረ፡፡
ለቫይረሱ መዛመት የቤልጂየም መነኩሲቶች ድርሻ አለበት ይባላል...
በወቅቱ መነኩሲቶቹ በሚሰሩበት ሆስፒታል ለነፍሰጡር ሴቶች የቫይታሚን ክትባት ይሰጡ ነበር፤ ነገር ግን የመርፌው ንፅህና የተጠበቀ አልነበረም፡፡ በዚህም ምክንያት ብዙ ነፍሰጡሮች በቫይረሱ እንዲያዙ አድርገዋል፡፡ በቅርቡ በምእራብ አፍሪካ ለተከሰተው የኢቦላ ወረርሽኝ ሆስፒታሎች የመጀመሪያውን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡
ከያምቡኩ በኋላ ላለፉት ሰላሳ አመታት ኤድስ ላይ አተኩረህ ሰርተሃል፡፡ ኢቦላ አሁን አዲስ ስጋት ሆኗል፡፡ የአሜሪካን ሳይንቲስቶች በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በበሽታው ሊጠቁ እንደሚችሉ ገልፀዋል፡፡ ወረርሽኙ በዚህ ደረጃ ትጠብቀው ነበር?
በፍፁም አልነበረም፡፡ እንዲያውም ተቃራኒ ነበር፡፡
ኢቦላ እንደ ወባና ኤድስ ችግር ፈጣሪ አልነበረም፤ ምክንያቱም ሲከሰት የነበረው በጣም በተወሰኑ ገጠራማ አካባቢዎች ነው፡፡ ባለፈው ሰኔ ወደ ትላልቅ ከተሞች መግባቱን ስሰማ ከወትሮው የተለየ ነገር እንደተፈጠረ ገባኝ፡፡ በተመሳሳይ ወር የድንበር የለሹ የሀኪሞች ቡድን ስጋቱን ከገለፀ በኋላ እጅግ አሳሰበኝ፡፡
የአለም የጤና ድርጅት ምላሹን የሰጠው ዘግይቶ ነው፡፡ ለምንድን ነው?
በአንድ በኩል የድርጅቱ የአፍሪካ ቢሮ ብቃት ባላቸው ሳይሆን በፖለቲካ ሹመኞች የተሞላ ነው፡፡
በሌላ በኩል ጄኔቫ ያለው የድርጅቱ ዋና ቢሮ በበጀት ቅነሳ ምክንያት ችግር ያለበት ሲሆን በተለይ ደግሞ የድንገተኛ ወረርሽኞች ዲፓርትመንቱ በጣም የተዳከመ ነው የተዳከመ ነው የተጎዳ ነው፡፡ ከነሐሴ ወር በኋላ ግን ድርጅቱ የመሪነት ሚናውን መጫወት ጀምሯል፡፡
በዛየር የመጀመሪያው ወረርሽኝ ሲከሰት የሆስፒታሎች የንፅህና መጓደል አስተዋፅኦ አድርጎ ነበር፡፡ አሁንም ተመሳሳይ ነገር ነው ያለው፡፡ ሉዊ ፓስተር “ሁሉም ነገር ያለው ባክቴሪያና ቫይረስ ላይ ነው” ብሎ ነበር፡፡ በዚህ ትስማማለህ?
በጣም እስማማለሁ! ኤችአይቪ አሁንም አለ፡፡ ለንደን ውስጥ ብቻ በቀን አምስት ግብረሰዶማውያን በቫይረሱ ይያዛሉ፡፡ ቁጥራቸው በዛ ያሉ ባክቴሪያዎች መድሀኒት የመቋቋም አቅማቸው እየጨመረ ነው፡፡ በባክቴሪያና በቫይረስ ላይ አሸናፊነትን ለመቀዳጀት ገና ብዙ ይቀረናል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ይህ እውነት ብዙ እንድሰራ ያበረታታኛል፡፡ ለዚህም ነው በአለም ላይ ያሉ ሀያላን ለምእራብ አፍሪካ አገራት በቂ እርዳታ እንዲያደርጉ የተቻለኝን እያደረግሁ ያለሁት፡፡
በኢቦላ ላይ ህዝባዊ ውይይት ሊካሄድ ነው
በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ የዓለም ስጋት በሆነው ኢቦላ ላይ ያተኮረ ህዝባዊ ውይይት የፊታችን ረቡዕ በግዮን ሆቴል ይካሄዳል፡፡
የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚና የኢትዮጵያ ጤና አጠባበቅ ማህበር በጋራ ባዘጋጁት በዚህ ህዝባዊ ወይይት ላይ የኢቦላ ቫይረስ ምንነትና የመተላለፊያ መንገዶቹ እንዲሁም ስርጭቱ፣ ምልክቶቹ፣ የመጋለጫ መንገዶችና የቁጥጥር ዘዴዎቹን አስመልክቶ የጤና ባለሙያዎች ገለፃ እንደሚያደርጉ ታውቋል፡፡
የምዕራብ አፍሪካ አገራትን በተለይ ላይቤሪያና ሴራሊዮንን ክፉኛ ያጠቃው የኢቦላ ቫይረስ ወደ አገራችን እንዳልገባ ያስታወቀው የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፤ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ላይ በሰዓት 1ሺ ሰዎችን መመርመር የሚያስችል ዘመናዊ መሣሪያ እንደተከተለና በድንበሮች አካባቢም ባለሙያዎች መድቦ ቁጥጥር እያደረገ መሆኑን መግለጹ ይታወሳል፡፡
አንጎልን የሚጎዱ አጓጉል ልማዶች ቁርስ አለመመገብ
ቁርስ አለመመገብ
ቁርሳቸውን የማይመገቡ ሰዎች በደማቸው ውስጥ የሚገኘው የስኳር መጠን ዝቅተኛ ይሆናል፡፡ ይህም ለአንጎል መድረስ ያለበትን ንጥረ ነገር በማስቀረት አንጎል በተገቢው ሁኔታ እንዳይሰራ ያደርገዋል፡፡
ከመጠን በላይ መመገብ
ከመጠን በላይ መመገብ የአንጎል የደም መተላለፊያ ቧንቧዎችን ያደድራቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ የአዕምሮን ኃይል ይቀንሳል፡፡
ማጨስ
ሲጋራ ወይንም ሌሎች አደገኛ ዕፆችን ማጨስ በርካታ የአንጐል ችግሮችን ከማስከተሉም ሌላ አልዚመር ለተባለ የአዕምሮ ህመም ሊያጋልጥም ይችላል፡፡
ከፍተኛ የስኳር ፍጆታ
ከፍተኛ የስኳር ፍጆታ፤ አንጎል ፕሮቲኖችንና የተለያዩ ንጥረ ነገሮችን በተገቢው ሁኔታ ጥቅም ላይ እንዳያውል ያሰናክላል፡፡ ይህም አንጎል አስፈላጊ ንጥረነገሮች እንዳያገኝ ያደርጋል፡፡
ጭንቅላትን ተሸፋፍኖ መተኛት
በመኝታ ሰዓት ጭንቅላትን በአንሶላ፣ በፎጣ ወይም በብርድልብስ ተሸፋፍኖ መተኛት የካርቦንዳይኦክሳይድ ክምችትን ይፈጥራል፡፡ ይህም በአንጎላችን ውስጥ ያለውን የኦክስጅን ክምችት ይቀንሳል፡፡ በዚህ ምክንያትም አንጎላችን ለአደጋ ይጋለጣል፡፡
ነፃ ገበያ ይለምልም!
ለምን መሰላችሁ ነፃ ገበያን ያወደስኩት? በእኛ አገር “ጨመረ” እንጂ “ቀነስ” የሚባል ነገር ጠፍቶ፣ “ቀነሰ” የሚለው ቃል ካልጠቀመን ምን ያደርግልናል? ከመዝገበ ቃላት ይፋቅልን! በምንልበት ጊዜ የቀነሰ ነገር በማየቴ ነው፡፡
ባለፈው ሰሞን፣ ዘመድ ሞቶብኝ በተለምዶ ዓለም ባንክ እየተባለ የሚጠራው አካባቢ ነበርኩ፡፡ ከቀብር መልስ ውሃ ጥም ሲያቃጥለኝ፣ አንድ ቢራ ልጠጣ ብዬ ግሮሰሪ ቤት ገባሁ፡፡ የምመርጠውን ቢራ ስጠይቅ “አለ” ተባልኩ፡፡ አካባቢው ሩቅ በመሆኑ ዋጋው ይጨምራል በማለት ሰግቼ “ስንት ነው?” አልኩ፡፡ አስተናጋጁ “12 ብር” አለኝ፡፡ መኻል ከተማ ከ13-16 የሚሸጠው ቢራ፣ እዚያ በ12 ብር መገኘቱ እያስገረመኝ ጠጥቼ ወጣሁ፡፡ በሳልስቱም ወደለመድኩት ቤት አመራሁ፡፡ ሁሉም ሰው ፊቱ ያስቀመጠው አዲሱን ቢራ ነው፡፡ የለመድኩትን ቢራ ጠየቅሁ፡፡ የለም ተባልኩ፡፡ ሌላ ቢራ ምን እንዳለ ስጠይቅ፤ አስተናጋጁ ሰዎች ፊት ያለውን እያሳየኝ “ከዚህ በስተቀር ምንም የለም” አለኝ፡፡ ዋጋውን ጠየቅሁ፡፡ 10 ብር አለኝ፡፡ ሌላ አካባቢ 12 እና 13 ብር የሚሸጡ ስላሉ፣ እየተገረምኩ ጠጥቼ ወጣሁ፡፡
በሌላ ጊዜ ደግሞ የረር-ጎሮ አካባቢ ነበርኩ፡፡ የምወደውን ቢራ ስጠይቅ አስተናጋጁ “እሱ የለም፤ ይኼን ይጠጡ ጥሩ ነው” አለኝ፡፡ ችግሬ ዋጋው ላይ ነውና “ስንት ነው?” አልኩት፡፡ “10 ብር ነው፡፡ ፋብሪካው‘ኮ ከዚህ አስበልጠን እንዳንሸጥ አስጠንቅቆናል” አለኝ፡፡ የቢራውን ዋጋ የቀነሰው - ፋብሪካው መሆኑን ስሰማ፣ አዲሱ ቢራ ገበያ ውስጥ ለመግባት የቀየሰው ዘዴ ነው በማለት ደስ አለኝ፡፡
ሰሞኑን ደግሞ ሌላ አስገራሚ ነገር አየሁ፡፡ ቢጂአይ (ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ) አርማውን በያዘ ወረቀት ላይ የድራፍት ብርጭቆ እያሳየ ማክሰኞ፣ ሐሙስ፣ ቅዳሜ “Happy Hour” በማለት በየመጠጥ ቤቱ ለጥፎ አየሁ፡፡ እኔ ጊዮርጊስ ቢራም ሆነ ድራፍት ባልጠጣም የንግድ ውድድር የፈጠረው ነው በማለት በጣም ደስ አለኝ፡፡ ድራፍቱ፣ ከሆነ ጊዜ በፊት ዋጋ ጨምሮ ጃንቦው 11 ብር እየተሸጠ ነው፡፡ አሁን ማክሰኞ፣ ሐሙስና ቅዳሜ 3ብር ቀንሶ በ8 መሸጥ ጀምሯል፡፡
ጊዮርጊሶች በአንድ ጊዜ 3ብር የቀነሱት፣ ደንበኞቹ በ10 ብር ወዳገኙት አዲስ ቢራ ስላዘነበሉ ጭራሽ እንዳይሸሹት ለማባበል ነው የሚል ግምት አደረብኝ፡፡ ወደፊትም ወደ ገበያው አዳዲስ ቢራ ፋብሪካዎች ሲገቡ የንግድ ውድድሩ ይጦፋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ በዚህ የንግድ ውድድር ማን ተጠቀመ? ሸማቹ ህብረተሰብ፡፡ ለዚህ ነው ነፃ ገበያ ይለምልም ያልኩት፡፡
“…እኔስ ይሉኝታን እንዴት ልገላገለው!”
እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሰውየው ሚስት ፈላጊ ነው፡፡ እናማ…አገባታለሁ ለሚላት ሚስት መስፈርቶች ያወጣል፡፡ ለጓደኛውም … “እኔ የምፈልጋት ሚስት መልካም ባህሪይ ያላት፣ ብልህና ቆንጆ መሆን አለባት…” ይለዋል፡፡
ጓድኝዬው፣ “ታዲያ አስቀድመህ እንደዚህ በግልጽ አትነግረኝም ነበር፣“ ይለዋል፡፡
ሰውየውም፣ “ይኸው ነገርኩህ እኮ…“ ሲል ይመላሳል፡፡
ጓደኝዬው ምን ቢል ጥሩ ነው… “ገና አሁን ነው ግልጽ የሆነልኝ፡፡ አንተ እኮ የምትፈልገው አንድ ብቻ ሳይሆን ሦስት ሚስት ነው፡፡ አንዲት መልካም ባህሪይ ያላት፣ አንዲት ብልህና አንዲት ቆንጆ፡ ሦስቱንም አንድ ላይ የያዘች ሴት ከፈለግህ ልብ ወለድ አንብብ!” አሪፍ አይደል! በቃ… እዚህ ላይ እኮ ይሉኝታ አያስፈልግም፡፡ እሱ ማን የማይሆን ጥያቄ ጠይቅ አለው! ልክ ነዋ… ዘንድሮ እኰ እንትናዬዎቹ በአንዱ ነገር “ክንፍ አላት…” ሲባሉ በሌላው ደግሞ “ከእነጭራዋ ብቅ አለች…” ይባላሉ፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
እናላችሁ…እንዲህ አይነት ያለ ይሉኝታ እቅጯን የሚናገሩ ሰዎች ያስፈልጋሉ፡፡ ነገርዬው “…ሦስቱንም አንድ ላይ የያዘች ሴት ከፈለግህ ልብ ወለድ አንብብ!”
ይቺን ስሙኝማ…ሰውየው…ብዙም ከሰው አይገጥምም አሉ፡፡ እናላችሁ…ሠርግ አይሄድ፣ ሀዘን ላይ አይገኝ፣ አብሮ ‘ብርጭቆ አያጋጭ’…በቃ ምን አለፋችሁ በራሱ ዓለም ውስጥ የሚኖር ነው፡፡ እናላችሁ… አንድ ቀን ምን ይሉታል…
“ያቺ ዱሮ ትወዳት የነበረችው ቆንጆዋ ገርል ፍሬንድህ ባል ሞቷል፡፡ ሁልጊዜ ሀዘን ላይ አትገኝም ስለምትባል ቀብር እንዳትቀር …” ሲሉት ምን ቢል ጥሩ ነው… “እንኳን ሞተ፣ እኔም የምፈልገው እሱን አልነበር…” ይላል፡፡
በሌላ ቀን የሚስቱ ወንድም ይሞታል፡፡ ይህን ጊዜ ቀብር ላይ ተገኝቶ ሳይሰናበት እንኳን በዛው ወደ ቤቱ ይመለሳል፡፡ ሚስቱና ሌሎች ዘመዶች ሠልስት፣ አርባ ምናምን ሲሉ እሱ አይገኝም፡፡ በዚህ የራሱ ዘመዶች ሳይቀሩ ይበሳጩበታል፡፡ “አሁንስ አበዛው! አንድ ነገር ይደረግ…” ይባባሉና ሄደው የሚያናግሩት ሦስት ሽማግሌዎች ይመረጣሉ፡፡
ታዲያላችሁ…አንደኛው ሽማግሌ “ለዚህስ ሌላ ሰው አያስፈልግም፣ እኔ ብቻዬን ሀሳቡን አስለውጬ ወደ ጥሩ ኢትዮዽያዊነት እመልሰዋለሁ…” ይላሉ፡፡
ከዛ ይሄዱና እንዲህ ይሉታል…
“አንተ ችግርህ ምንድነው? እኛስ ምን አድርገንሀል! ማንም ሰው ሀዘን ላይ አትገኝም፡፡ አሁንም የሚስትህ ወንድም ሞቶ ቀብር ላይ ብቅ ብለህ በዛው ጠፋህ፡፡ ይሄ ነገር ይብቃ፡ ሰው ቀብር ላይ መገኘት ልመድ...” ይሉታል፡፡
እሱዬው ምን ይላቸዋል… “እኔ ትልቁን በሽታ ገድዬ ቀብሬዋለሁ…” ይላቸዋል፡፡
የተላኩት ሰው ግራ ይገባቸውና… “ምን የሚሉት በሽታ?” ሲሉ ይጠይቁታል፡፡
እሱም… “ይሉኝታ የሚባል በሽታ…” ይላቸዋል፡፡
ሽማግሌ ሆነው የሄዱትም ሰው ትንሽ አሰብ አድርገው ምን ቢሉ ጥሩ ነው… “አንተስ ተገላገልከው፣ እኔስ ይሉኝታን እንዴት ልገላገለው!” ብለው ቁጭ፡፡
እሳቸውም ነገሮችን የሚያደርጉት በይሉኝታ ነዋ!
እኔ የምለው… እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… እዚህ አገር ተጋፍቶ ይቅርታ መጠየቅ ከሲኒማ አድዋ ጋር አብሮ ፈርሷል እንዴ! እኛ ‘ደቃቆቹ’ ግራ ገባና! (በነገራችን ላይ…በአካልም የደቀቅን፣ በፈራንካውም የደቀቅን፣ በሞራሉም የደቀቅን፣ በተስፋውም የደቀቅን… ሰብሰብ ብለን “አይዞህ ለደግ ነው…” “አይዞሽ ሊነጋ ሲል ይጨልማል…” እያልን የምንጽናናበት ማህበር ቢጤ ብኗቋቋም አሪፍ አይደል!
ደግሞላችሁ…አሁን፣ አሁን ደግሞ ክንድና ደረቱን እየተነቀሰ በ‘ቢጢሌ’ ካናቴራ ከተማዋ ውስጥ የሚንጎማለል በዝቷል፡፡ ታዲያላችሁ… በትከሻው ዘፍ ይልባችሁና…አለ አይደል… እሱ በተጋፋው እናንተ በተገፋችሁት ገላምጧችሁ ይሄዳል፡፡ (“ጡንቻ የሚያሳብጥ ኪኒን ከዱባይ እንደ ልብ ይገባል…” የሚባለው እውነት ነው እንዴ!
እናላችሁ…ሲመጡብን ‘ጥግ እንዳንይዝ’…አገሩ ሁሉ ተቆፍሮ ‘የምንለጠፍበት ጥግ’ አጣን፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
እናላችሁ…ይሉኝታ የሚመስል ነገር መነሳት ካለበት እዚህ ላይ ነው፡፡ ‘መድቀቃችንን’ አይቶ ገፍትሮን ከመሄድ ይቅርታ ማለት ለመንግሥተ ሰማያት ‘ሲ.ቪ.’ ማጠናከሪያ ይሆናል፡፡ ልክ ነዋ…ዘንድሮ የምንገፈተረው መንገድ ላይ ብቻ ሳይሆን በሁሉም የህይወታችን መስኮች ሆኗላ!
ስሙኝማ…በዛ ሰሞን አንድ ሚኒባስ ውስጥ የሆኑ ሦስት ሰዎች ጓደኛቸው ለልጁ የስም መዋጮ እንዲያደርጉ ጠይቋቸው ግራ ገብቷቸው ሲጨቃጨቁ ነበር፡፡ አስቸጋሪ ነዋ…አሁን፣ አሁን እኮ አይደለም ጓደኛ ምናምን ወላጆችም ራሳቸው ስም በማውጣቱ ግራ የተጋቡ ነው የሚመስለው፡፡
ሀሳብ አለንማ…ወይም ወላጆች “ለልጄ ስም አውጣልኝ…” ምናምን ሲሉ…አለ አይደል…አብረው ‘ቲ.ኦ.አር.’ ምናምን የሚባለውን ነገር ይላኩልን፡፡ ስሙ ዓለም አቀፍ ይዘት ያለውና ልጁ ድንገት የፊልም ተዋናይ ቢሆን ለአፍ የሚጣፍጥ ምናምን ተብሎ እቅጩ ይጻፍልን፡፡
ወይም ደግሞ…“የሚወጣው ስም የአሜሪካን ወቅታዊ ሁኔታ ያገናዘበና ልጁ በኋላ ዲጄ ሊሆን ስለሚችል ለእሱ የሚስማማ መሆን አለበት…” ተብሎ ይለይልንማ!
እኔ የምለው…የስም ነገር ካነሳን አይቀር…ለልጆች የምንሰጣቸው ስሞቻችንና የቡቲኮቻችን ‘የፈረንጅ ስም’ እየተመሳሰሉብን ነው፡፡ አሀ… ምን ይደረግ… ይሄ ኢንተርኔት የሚሉት ነገር ‘ቆርጦ መለጠፍ’ አስለመደንና ስሞች ሁሉ ‘ከት ኤንድ ፔስት’ እየተደረጉ ነው፡፡
ከሀበሻ እናትና አባት እዚህቹ በግርግር ትንፋሸ ያጠራት ከተማችን ውስጥ የተወለደን ‘ፍራንክ’ ብሎ ስም መስጠት ትንሽ አያስቸግርም፡ ወዳጆቼ እንደዛ አይነት ስም መስማታቸውን ነግረውኛል፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል እዚህ አገር… “እሱን እንኳን ተወው፣ እንዲህማ አይደረግም…” ብሎ ነገር እየቀረ ነው፡፡ ሌላ ቦታ ሊደረግ የማይችለው ነገር… ‘አዲስ ነገር መፍጠር’ በማይሰለቻት፣ ‘ከአፍሪካ የመጀመሪያ ከዓለም ሁለተኛ’ ማለት ዓመል የሆነባት አገራችን ውስጥ ሊሆን የማይችል ነገር በጣም ጥቂት ይመስላል፡፡
እኔ የምለው…አንድ ሰሞን ፑሽኪን ‘የእኛ ነው፣ አይደለም’ ምናምን አይነት ሙግት ነበረላችሁ! ‘ቡና አብረን መጠጣት ያቆምናቸው’ ጎረቤቶቻችን በበኩላቸው “ፑሽኪንማ የራሳችን ነው!” እያሉ በላ ልበልሃ ነገሮች ነበሩ፡፡
እኔ የምለው…የፑሽኪን ዝርያዎች ራሳቸው ለመለየት ምስክርነት ቢጠሩ እኮ… “መጀመሪያ ነገር እነኚህ አገሮች የሚገኙት እስያ ነው ደቡብ አሜሪካ?” ብለው ይጠይቁ ነበር፡፡ “አፍሪካ ውስጥ ናቸው ወይ?” ለማለት መጀመሪያ አፍሪካ አገር ሳትሆን አህጉር መሆኗን ማወቅ አለባቸው፡፡ ዓለም ይሄን ያህል ነች፡፡
ልጄ እዛ ይሉኝታ ምናምን ብሎ ነገር የለማ!
ኮሚክ እኮ ነው…በተለይ በአውሮፓ በርከት ባሉ ሀገራት… “መጤዎች ይውጡልን…” “ማንም በራፋችን ዝር እንዳይል…” አይነት ነገር የሚሉ የፖለቲካ ቡድኖች ጉልበታቸው እየጠነከረ ባለበትና ‘ለዓይናቸው እየተጠየፉን’ ባሉበት ዘመን የልጅን ስም አውሮፓዊ እያደረጉ ከመሰረቱ ማንነቱ ላይ ጥቁር ነጥብ የሚያደርጉ ወላጆች ልብ ይግዙማ!
ሀሳብ አለን… ለአውሮፓ ህብረት የአባልነት ጥያቄ ይቅረብልንማ! ልክ ነዋ! ምድረ የአውሮፓ ከተማ ሁሉ የካፌና የሬስቱራንት መጠሪያ ሆኖ የለም እንዴ! ይህ ‘ወንድማማችነትን ለማጠናከር’ ያለንን ፍላጎት (ቂ…ቂ…ቂ…) ፍላጎታችንን የሚያሳይ አይደለም እንዴ! ቢያንስ ቢያንስ የታዛቢነት ወንበርማ ይገባናል፡፡
ለምሳሌ ‘ጆኒ’ ምናምን ድሮ ማቆላመጫ ነበር፡፡ አሁን ግን መደበኛ ስም ሆኖ ይወጣል አሉ፡፡
በ‘አብዮቱ’ ሁለት ልጆቻቸውን ‘ሆቺ ሚን’ እና ‘ቼ ጉቬራ’ ብለው የሰየሙ ሰዎች ነበሩ፡፡ እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ዘንድሮ የ‘ቦተሊካ ነፋስ’ የነካቸው ስሞች አሉ!
ስሙኝማ… ብሰማው ደስ የሚለኝ አንድ ስም ምን መሰላችሁ… ‘ያለው ሁኔታ ነው ያለው’ የሚል ስም፡፡ ልክ ነዋ…‘ፖፑላር’ ስም ይሆናላ! ደግሞላችሁ… በየስብሰባውና በየቃለ መጠይቁ ሲደጋገም ዘመድ ወዳጅ ሁሉ… “እንዴት ቢወዱት ነው ስሙን እንዲህ የሚደጋግሙት…” ማለታቸው አይቀርማ!
እናላችሁ…ከፍ ብለን የጠቀስነው የይሉኝታ ነገር አስቸጋሪ ሆኗል፡፡ በአንድ በኩል በይሉኝታ ማድረግ የማንፈልጋቸውን ነገሮች እናደርጋለን፣ መቀላቀል የማንፈልጋቸውን ስብስቦች እንቀላቀላለን፣ መሄድ የማንፈልጋቸው ቦታዎች እንሄዳለን፣ በማያስቀው እንንከተከታለን…ብቻ ምን አለፋችሁ… ይሉኝታ ነገራችንን ሁሉ አርቲፊሻል ያደርገዋል፡፡እናማ… ለማግባባት የተላኩት ሰውዬ… “አንተስ ተገላገልከው፣ እኔስ ይሉኝታን እንዴት ልገላገለው!” እንዳሉት ከልማቱ ጥፋቱ ከሚብስ ይሉኝታ የምንገላገልበትን ዘመን አንድዬ ያፋጥልንማ! ደህና ሰንብቱልኝማ!
ከመሸ አትሩጥ ከነጋ አትተኛ
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሽማግሌ አባት የመሞቻው ጊዜ ደርሶ ኖሮ ልጁን ወደ አልጋው እንዲመጣ ይጠራዋል፡፡ ልጁም ይጠጋውና፤
“አባቴ ሆይ ምን ላድርግልህ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
አባትየውም፤
“ልጄ ሆይ! እንግዲህ የመሞቻዬ ጊዜ ደርሷል፡፡ ነገር ግን አንተን ምድር ላይ ጥዬህ ስሄድ ምንም ያጠራቀምኩልህ ጥሪት ስለሌለ ትቸገራለህ ብዬ ተጨንቄያለሁ፡፡ ሆኖም አንድ አውራ ዶሮ አለኝ፡፡ የዚህን አውራ ዶሮ አጠቃቀም ካወቅህበት ብዙ ሀብት ታፈራበታለህ” ይለዋል፡፡
ልጁም፤ “እንዴት አድርጌ?” አለው፡፡
አባቱም፤ “አውራ ዶሮ ወደማይታወቅበት አገር ሂድ፡፡ የአውራ ዶሮን ጥቅም ንገራቸው” ብሎ ሃሳቡን አስፋፍቶ ተናግሮ ሳይጨርስ ትንፋሹ ቆመ፡፡
ልጅየው አባቱን ከቀበረ በኋላ አውራ ዶሮ የማይታወቅበት አገር ለመፈለግ ከቤቱ ወጣ፡፡ ብዙ አገር ዞረ፡፡ ነገር ግን ሁሉም ቦታ መአት አውራ ዶሮ ስላለ ጥቅሙን ያውቁታል፡፡ በመጨረሻ ወደ አንድ ደሴት ሲገባ አንድም ዶሮ የላቸውም፡፡ ቀን መምሸት መንጋቱን እንጂ ምንም ሰዓት አይለዩም፡፡ ስለዚህ እንዲህ አላቸው፡-
“ይሄ አውራ ዶሮ ይባላል፡፡ እዩ አናቱ ላይ ቀይ ዘውድ አለው፡፡ እንደ ጀግና ጦረኛም እግሩ ላይ ሹል ጫማ አለው፡፡ ሌሊት ሌሊት ሶስት ጊዜ ይጮሃል፡፡ ይህንንም የሚያደርገው ለእናንተው ጥቅም ነው፡፡ በየአንዳንዱ ጩኸቱ መካከል ያለው የጊዜ ርዝመት እኩል ነው፡፡ በመጨረሻ ሲጮህ ልክ ሊነጋ ሲል ነው ማለት ነው፡፡ ቀን ከጮኸ ደግሞ አየሩ ሊለወጥ መሆኑን መናገሩ ነው ማለት ነውና መዘጋጀት ይኖርባችኋል” አላቸው፡፡
ነዋሪዎቹ ሁሉ ተገረሙ፡፡ የዚያን እለት ሌሊት ማንም የተኛ ሰው የለም፡፡ አውራ ዶሮው በውብ ድምፁ አንድ ጊዜ ከሌሊቱ ስምንት ሰዓት ላይ፤ ጮኸ፡፡ ቀጥሎ አስር ሰዓት ላይ ጮኸ፡፡ በመጨረሻም ከንጋቱ 12 ሰዓት ላይ ጮኸ፡፡ ህዝቡ ጉድ አለ! ስለዚሁ አውራ ዶሮ ሲያወራ ዋለ፡፡ ነገሩ ንጉሡ ጆሮ ደረሰ፡፡ ንጉሡም እንደ ህዝቡ በሚቀጥለው ሌሊት የአውራ ዶሮውን ጩኸት ሲያዳምጡ አደሩ፡፡ በጣም ተደንቀው ልጁን አስጠርተው፤
“ይሄንን አውራ ዶሮ ትሸጥልናለህ ወይ?” አሉት፡፡
ልጁም “አዎን ግን በወርቅ ነው የምትገዙኝ” ሲል መለሰ፡፡
ንጉሡም፤ “በምን ያህል ወርቅ?” አሉት፡፡
ልጁ - “አንድ አህያ ልትሸከም የምትችለውን ያህል” አለ፡፡
ንጉሡ አንድ አህያ የምትሸከመውን ኪሎ አስጭነው ሰጡትና ወደቤቱ የአባቱን ውለታ እያሰበ ሄደ፡፡ ንጉሡም አውራ ዶሮአቸውን ወሰዱ፡፡ ከዚያን እለት ጀምሮ የዚያ ደሴት ህዝብ ጊዜና ሰዓት ለየ፡፡
***
አውራ ዶሮ የሚሸጥልን አንጣ፡፡ ሰዓትና ጊዜን መለየት ለማንኛችንም ትልቅ ፀጋ ነው፡፡ “የቸኮለች አፍሳ ለቀመችን”ና “የቆየ ከሚስቱ ይወልዳል”ን ዛሬም ባንረሳ መልካም ነው፡፡ ብልህ አባት ለልጁ የዘለአለም ሀብት ማውረሱን ካስተዋልን ዘላቂ ልማት፣ ዘላቂ አገር ይኖረናል፡፡ ቤትና ቀን የለየ፣ ጊዜና ሰዓት ያወቀ ወደፊት መሄድም፣ ባለበት መቆምም፤ ማፈግፈግም የሚያውቅ የነቃ የበቃ ወራሽ ካለን የነገን ጥርጊያ መንገድ አበጀን ማለት ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ቀለበት መንገድ መስራት ብቻ ሳይሆን ከቀለበት መውጪያውንም እንድንሰራ ፈር ይቀድልናል፡፡ ከተማረ የተመራመረ የሚለው ትርጉም የሚኖረው እዚህ ላይ ነው፡፡
“ጊዜ የሥልጣን እጅ ነው” ይላል ጸሐፌ ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን፡፡ ጊዜን ያላወቀ እንኳን ሥልጣኑን ራሱን ያጣል፡፡ በማንኛውም ደረጃ ላይ ቢሆን “በትክክል ጊዜን መጠቀም እወቅበት፤ ይላሉ ጠበብት፡፡ አለልክ አትጣደፍ፤ ነገሮች ከቁጥጥርህ ይወጣሉና፡፡ የትክክለኛዋ ቅፅበት ሰላይ ሁን፡፡ የጊዜን መንፈስ አነፍንፈህ አሽትት፡፡ ወደ ስልጣን (ድል) የሚወስዱህን መንገዶች በዚያ ታገኛለህ፡፡ ጊዜው ካልበሰለ ማፈግፈግን እወቅበት፡፡ ሲበስል ደግሞ ፈፅሞ ወደኋላ አትበል!” የሚሉ ፀሐፍት ታላቅ ቁምነገር እየነገሩን ነው፡፡
ጊዜን በትክክል መጠቀም የሚችል ዝግጅትን ዋና ጉልበቱ ያደርጋል፡፡ ድግሱ ከመድረሱ በፊት የምግብ እህሉን፣ የጌሾ ጥንስስ ስንቁን ማደራጀትና በመልክ መልኩ መሸከፍ፣ መጥኖ መደቆስ፣ መብሰያና መፍያ ጊዜውን በቅጡ ለድግሱ ሰዓት ማብቃትን ከሸማች እስከ አብሳዩ ውል ሊያስገቡት ይጠበቃል፡፡
“ካልተሳፈሩበት ቶሎ ተሸቀዳድሞ
ጊዜ ታክሲ አይደለም አይጠብቅም ቆሞ”
የሚለው የደራሲ ከበደ ሚካኤል ግጥም ይሄንኑ ጊዜ እንኳን ከበሰለ በኋላ እንዲሁም መዘናጋት እንደማይገባ ያስገነዘቡት ነው፡፡
ያለመላ ግጭት ጅልነት ነው፡፡ የዝግጅት ጊዜ ወስዶ አስቦ፣ ሁሉን አመቻችቶ ነው ትግል፡፡ አንዴ ከገቡ ደግሞ መስዋዕት መኖሩን ሳይረሱ ምንጊዜም ሳያቋርጡ፣ ሳይማልሉና ሳይታለሉ መቀጠል ግድ ይሆናል፡፡
በሼክስፔር ሐምሌት ቴያትር ውስጥ፤
“ፈጥነህ ጠብ ውስጥ አትስጠም
አንዴ ከገባህበት ግን፣ እጅህ ከባላንጣህ ይቅደም!”
የሚለን የጊዜ ዕቅጩነት (Perfect - imning) ጉዳይ ነው፡፡
“አውራ ዶሮ ጮሆ፣ መንጋቱን ነገረኝ
ዛሬ ሌሊት ላርደው ቀጠሮ ነበረኝ” ያለውን ያገራችንን ወጣት ገጣሚ ረቂቅነትም አለመዘንጋት ነው!!
የሁሉ ነገር መሳሪያ ጊዜ ነው!
ዘመን የጊዜ ጥርቅምና የቅራኔና የሥምረት ውጤት ነው፡፡ ስለዚህም እንደታሪክ ክፉውንም ደጉንም ማጣጣሚያውና ያንን የመመርመር፣ ከስህተት የመማር፣ ነገን የመተለም ጉዳይ ነው ጊዜን ማወቅ ማለት መጪውንም ምርጫ በጊዜ ማስላት ነው የምንለው ለዚህ ነው፡፡ ጊዜን ጨበጥክ ማለት ድልን ጨበጥክ ማለት ነው፤ የሚባለው እንዲያው ለወግ አይደለም! ጊዜን እንደመሳሪያ የምንቆጥረው ከዚህ በመነሳት ነው፡፡ አውራ ዶሯችንን በጊዜ እንግዛዛ - ሌሊትን፣ ተስፋንና ንጋትን - ይንገረን፡፡ ይህ ሚጠቅመን በማታ ሩጫ እንዳንጀምር ከነጋ በኋላም እንዳንዘናጋ ነው! “ከመሸ አትሩጥ፣ ከነጋ አትተኛ” የሚለው የወላይታ ተረት አደራ የሚለን ይሄንኑ ነው!!
ኢቢሲ የአልጀዚራን ፕሮግራሞች ማሰራጨቱ የአገሪቱን ገጽታ ይጐዳል ተባለ
የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽንና የኦሮሚያ ቴሌቪዥን ጣቢያ የአልጀዚራ የስፖርት ቻናሎችን በህገወጥ መንገድ ማሰራጨታቸው የአገሪቱን ገጽታ በእጅጉ እንደሚጐዳ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን ገለፀ፡፡ ባለስልጣኑ ሰሞኑን ለተወካዮች ምክር ቤት ባቀረበው የዕቅድ ሪፖርት ላይ እንደገለፀው፤ ኢቢሲና የኦሮሚያ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች፤ የአልጀዚራ የስፖርት ቻናሎችን በህገወጥ መንገድ ከማሰራጨት እንዲታቀቡ ቁጥጥር ቢደረግም ህገወጥ ስርጭቱ ሊቆም አልቻለም፡፡ በአገሪቱ የውጭ ብሮድካስት ፕሮግራሞችን በክፍያ ለደንበኞች ለማድረስ የአገልግሎት ፍቃድ የወሰደው ድርጅት ከሚያቀርባቸው የዲኤስቲቪ ቻናሎች ውጪ በህገወጥ መንገድ የአልጀዚራ የስፖርት ቻናሎችን የሚቀበሉ ቢኑ ካርዶችና ዲኮደሮች ከውጪ በማስገባት በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በማሰራጨት ላይ የሚገኙ አካላት እንዳሉም ተረጋግጧል ተብሏል፡፡
የውጭ ብሮድካስት ፕሮግራሞችን በክፍያ ለደንበኞች የማድረስ አገልግሎት (subscription) ፈቃድ የተሰጠው መልቲ ቾይስ ኢትዮጵያ ለተባለ ድርጅት ሲሆን ድርጅቱ በአሁኑ ወቅት ለደንበኞቹ የሚያቀርባቸው ቻናሎች ከተሰጠው ፈቃድ ጋር የሚጣጣም መሆኑ፣ የሚተላለፉት ፕሮግራሞች ይዘት የህፃናትን ስነልቦናና የወጣቶችን ደህንነት እንደማይጐዱ እንዲሁም የህብረተሰቡን ባህላዊና ሞራላዊ እሴቶች የሚጠብቁና የሚዲያ ህጉን ያከበሩ ስለመሆናቸው ክትትል አለመደረጉም በሪፖርቱ ላይ ተገልጿል፡፡
ሲፒጄ በኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እየተባባሰ ነው አለ
በወቅታዊ የመብት ጥሰቶች ዙሪያ የሰራውን ጥናት ይፋ አድርጓል
መቀመጫውን በኒውዮርክ ያደረገው አለማቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ሲፒጄ፤ የኢትዮጵያ መንግስት በዜጎች ላይ የሚፈጽማቸው የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ መሄዱን አስታወቀ፡፡ኢትዮጵያ ሽብርተኝነትን ለመዋጋትና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች ቢሆንም የአገሪቱ መንግስት በዜጎች ላይ የሚፈጽማቸው ዘርፈ ብዙ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ግን እየተባባሱ ቀጥለዋል ያለው ሲፒጄ፣ ይፈጸማሉ ባላቸው የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ዙሪያ የሰራውን ጥናት በትላንትናው ዕለት በተዘጋጀ የውይይት መድረክ ላይ ይፋ አድርጓል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ያወጣቸውን ህጎች ከቅርብ አመታት ወዲህ ዜጎችን በሚጨቁን መልኩ ያለአግባብ እየተጠቀመበት ነው ያለው ሲፒጄ፤ መንግሥት በሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖች፣ በፕሬስ ነጻነትና በዜጎች ሰብዓዊ መብቶች ላይ ከፍተኛ ጥሰት እየፈጸመ ነው በሏል፡፡
በጸረ-ሽብርተኝነት ህግ ሽፋን ለእስር የሚዳረጉ ጋዜጠኞችና የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አባላት ቁጥር እያደገ ነው፤ የሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖች የዜጎችን ሰብዓዊ መብቶች ለማስከበር እንዳይችሉ ተደርገዋል ሲል ኮንኗል - ሲፒጄ፡፡
“ቶም ላንቶስ ሂውማን ራይትስ ኮሚሽን” የተባለው የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅት በትናንትናው ዕለት በአሜሪካ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውስጥ በሚገኘው ሬይበርን ሃውስ አዳራሽ ባዘጋጀው የመወያያ መድረክ፣ በአገሪቱ ይፈፀማሉ የተባሉ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰትን የሚዳስስ ጥናት ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል፡፡
በሲፒጄ የአፍሪካ ፕሮግራም አስተባባሪ ሱኢ ቫለንታይን የተሰራው ጥናት፤ በኢትዮጵያ መንግስት ይፈፀማሉ የተባሉ የሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖችን እንቅስቃሴ የመገደብ፣ መገናኛ ብዙሃንን የመጨቆንና በልማት ፕሮጀክቶች ሰበብ የነዋሪዎችን ሰብዓዊ መብት የመጣስ ድርጊቶች ያብራራል ተብሏል፡፡
የአሜሪካ መንግሥት ለኢትዮጵያ በየዓመቱ የ800ሚ. ዶላር ድጋፍ እንደሚሰጥ የጠቆመው ሲፒጂኤ፤ አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን መልካም ግንኙነት በመጠቀም ድጋፉ ለሰብአዊ መብቶች ጥሰት እንዳይውልና መንግሥት ሰብአዊ መብቶችን እንዲያከብር ተፅእኖ ማድረግ በምትችልበት ሁኔታ ላይ ምክክር መደረጉን ገልጿል፡፡
በውይይት መድረኩ የፓርላማ አባላት፣ የተለያዩ አለማቀፍ መገናኛ ብዙሃን ጋዜጠኞች፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት ተወካዮች፣ ተመራማሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንደተሳተፉበት ሲፒጂ ጠቁሟል፡፡
99 ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በኬኒያ ፍርድ ቤት ተቀጡ
አፍሪካን ሰርቪስ ኮሚቴ ለ25 ችግረኛ እናቶች፤ እንጀራ ጋግረው መሸጥ እንዲችሉ ከጤፍ ጀምሮ የሚያስፈልጉትን ጠቅላላ ጥሬ እቃዎች በማሟላት ከትላንት በስቲያ ሾላ አካባቢ በሚገኘው ክሊኒኩ ውስጥ አስረከበ፡፡
ኤችአይቪ ቫይረስ በደማቸው ውስጥ ላለባቸው ለእነዚህ እናቶች ሁለት ኩንታል ጤፍ፣ የኤሌክትሪክ ምጣድ፣ የዱቄት ማስቀመጫ በርሜል፣ የሊጥ ማቡኪያና የውሃ ባልዲ፣ የአብሲት መጣያ ብረት ድስት፣ ጆግና ማስታጠቢያ፣ ማሰሻ ጨርቅ፣ ጎመን ዘር፣ መሶብ፣ እንቅብና የእንጀራ ማውጫ ሰፌድ በነፍስ ወከፍ ተከፋፍሏል፡፡
ተረጂዎቹ በጨረቃ ቤት፣ በዘመድ ቤትና ባስጠጓቸው በጎ ሰዎች ቤት የሚኖሩ በመሆናቸው የመጀመሪያ ወር የኤሌክትሪክ ፍጆታ ክፍያ ለእያንዳንዳቸው 300 ብርና የተረከቡትን እቃ የሚያጓጉዙበት የትራንስፖርት ወጪ ሁለት መቶ ብር ተሰጥቷቸዋል፡፡
አፍሪካዊ ስደተኞችን ለመርዳት ከ30 ዓመታት በፊት ኢትዮጵያዊ ዜግነት ባላቸው አቶ አስፈሃ ሃደራ በተባሉ ግለሰብ አሜሪካ ኒውዮርክ ውስጥ የተቋቋመው “አፍሪካን ሰርቪስ ኮሚቴ” ከ10 ዓመት በፊት ኢትዮጵያ ተከፍቶ ሥራ የጀመረ ሲሆን ክሊኒኩ የምስጢር ኤችአይቪ ምርመራ፣ የፀረኤችአይቪ (ART) ስርጭት፣ የቲቢ እንዲሁም የአባላዘር በሽታ ምርመራና ህክምና በመስጠት በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያንን ሲያገለግል መቆየቱን የድርጅቱ የኢትዮጵያ ተወካይ ወይዘሪት ሃና ወ/ገብርኤል ተናግረዋል፡፡
ድርጅቱ፤ አዲስ አበባን ጨምሮ በአምስት የክልል ከተሞች በአማራ ክልል ኮምቦልቻ፣ በመቀሌ በዝዋይ እንዲሁም በሃሳዋ የጤናና የማህበረሰብ ልማት ማዕከል በማቋቋም፣ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎችን በተለይም እናቶችና ህፃናትን በማገልገል ላይ መሆኑን ወ/ሪት ሃና አብራርተዋል፡፡
ድርጅቱ ኤች አይቪ ቫይረስ በደማቸው ላለባቸው ህፃናት የወተትና የአልሚ ምግብ ድጋፍ የሚያደርግ ሲሆን በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ለሚገኙ ከ18 ዓመት በታች ላሉ ህፃናትና ታዳጊዎች አሜሪካ ከሚገኝ “ቶምስ ሹ” ከተባለ ድርጅት ጋር በመተባበር በዓመት ሁለት ጊዜ የጫማ የትምህርት መሳሪያዎችና ሌሎች ድጋፎች እንደሚያደርግ ታውቋል፡፡
ከትላንት በስቲያ ችግረኛ እናቶች የገቢ ማስገኛ ስራ እንዲሰሩ ለተደረገው የጥሬ እቃና የገንዘብ ድጋፍ አገር በቀልና የውጭ ድርጅቶች ከፍተኛ ድጋፍ ማድረጋቸው የተገለፀ ሲሆን “በፔፕፋር ስሞምል ግራንት ፕሮግራም” በኩል የአሜሪካ ኤምባሲ የ30 ሺህ ዶላር ድጋፍ ማድረጉም ተጠቁሟል፡፡ እስከዛሬ ለድርጅቱ ድጋፍ ሲያደርጉ የነበሩት ቢጂአይ ኢትዮጵያ፣ ዲኬቲ ኢትዮጵያ፣ አይካፕ ኢትዮጵያ፣ ፈረንሳይ ኤምባሲ፣ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፣ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ማህበራት ኤጀንሲ እንዲሁም ድርጅቱ የሚንቀሳቀስባቸው የክልል መንግስታት የወረዳና የዞን ቢሮዎች በእለቱ ተመስግነዋል፡፡ በእለቱ የአንበሳ ማስታወቂያና የህዝብ ግንኙነት ድርጅት ባለቤትና “የትውልዱ አምባሳደር” አቶ ውብሸት ወርቅአለማሁና አርቲስት ዳንኤል ተገኝ በክብር እንግድነት ተገኝተው ስለ ድርጅቱ እንቅስቃሴ የተሰማቸውን ተናግረዋል፡፡
የጥሬ እቃ ድጋፉን የተረከቡት 18 እናቶች ሲሆኑ ቀሪዎቹ ሰባት እናቶች በሌላ ድርጅት መደገፍ አለመደገፋቸው ተጣርቶ እቃቸውን መረከብ እንደሚችሉ ተገልጿል፡፡
አርቲስት ዳንኤል ተገኝና አቶ ውብሸት ወርቅአለማሁ ለገና በዓል ለተረጂዎቹ የተወሰነ ስጦታ ለማበርከት ቃል እንደገቡም ታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካ የአመቱ ምርጥ ተባለ
ሽልማቱን ላለፉት 3 ተከታታይ አመታት ተቀብሏል
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካ በያዝነው ሳምንት በአልጀርስ በተካሄደው የአፍሪካ አየር መንገዶች ማህበር 46ኛ አመታዊ ጉባኤ ላይ፣ የአመቱ የአፍሪካ ምርጥ አየር መንገድ ተብሎ መሸለሙን አስታወቀ፡፡
አየር መንገዱ ለአመቱ የአፍሪካ ምርጥ አየር መንገድ ሽልማት የበቃው በ2013 የበጀት አመት ባስመዘገባቸው ከፍተኛ ውጤቶች፣ ዘላቂነት ባለው ትርፋማነቱ እና ከሌሎች የአፍሪካ አየር መንገዶች ጋር ለመስራት በሚያስችለው አግባብነት ያለው ስትራቴጂው እንደሆነ ገልጾ፣ ይህንን ሽልማት ላለፉት ሶስት አመታት በተከታታይነት እንዳገኘ አስታውቋል፡፡
የአየር መንገዱ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረ ማርያም፣ ሽልማቱን ሲቀበሉ ባደረጉት ንግግር አየር መንገዱ ለዚህ ሽልማት በመብቃቱ ኩራት እንደሚሰማው ገልጸው፣ ለዚህ ስኬት መሰረቱ ከ8ሺህ በላይ የሚሆኑ ጠንካራ ሰራተኞቹ ትጋት መሆኑን ተናግረዋል፡፡