Administrator

Administrator

በኮሜዲ ፊልሞቹ የሚታወቀው ዊል ፋሬል በሰራቸው ፊልሞች አትራፊ ባለመሆን የአንደኝነት ደረጃን እንደያዘ ፎርብስ መፅሄት አስታወቀ፡፡ ኮሜዲያኑ በሚተወንበት አንድ ፊልም ለተከፈለው 1 ዶላር 3 .30 ዶላር ብቻ በማስገባት ዝቅተኛ ትርፍ ያስመዘገበ ተዋናይ ሊሆን በቅቷል፡፡ በብዙ ፊልሞቹ ላይ ‹የትልቅ ህፃን› ገፀባህርይ እየተጫወተ የሚያሳያቸው ትዕይንቶች እና ንግግሮቹ ተደጋጋሚ እየሆኑ መምጣታቸው እና በአጠቃላይ አሰልቺ መሆናቸው ለተዋናዩ ትርፋማነት መቀነስ ምክንያቶች ናቸው፡፡

ፎርብስ አትራፊ ያልሆኑ 7 የሆሊውድ ተዋናዮችን ደረጃ ይፋ ባደረገበት ወቅት፤ ሁሉም ባለሙያዎች በቅርብ ጊዜ ትርፋማ እና ተፈላጊ በመሆን የማገገም ዕድል ላይኖራቸው እንደሚችል አመልክቷል፡፡ በተወኑባቸው ፊልሞች በተከፈላቸው 1 ዶላር ኢዋን ማክሪጎር 3.75፤ ቢሊ ቦብ ቶርቶን 4 ፤ኤዲ መርፊ 4.43፤ አስ ኪውብ 4.77፤ ቶም ክሩዝ 7.20 እንዲሁ ድሪው ባሪሞር 7.4 ዶላር በማስገባት ከዊል ፋሬል ቀጥሎ እስከ 7 ያለውን ትርፋማ ያለመሆን ደረጃ አግኝተዋል፡፡ በሆሊውድ ትርፋማ ከተባሉ ተዋናች አንዱ የሆነው እና በትራንስፎርመር ፊልሞች የሚታወቀው ሻይ ለበፍ በተከፈለው 1 ዶላር 160 ዶላር ያስገባል፡፡ በሙያ ዘመኑ ከ34 በላይ ፊልሞች ላይ የተወነው ዊል ፋሬል፤ በመላው ዓለም ያስገባው 2.034 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን በአንድ ፊልም በአማካይ እስከ 81.62 ሚሊዮን ዶላር በማስገኘት የሚታወቅ ነበር፡፡ ከ100 ሚሊዮን ዶላር በላይ ያስገቡ 7 ፊልሞችን የሰራው ኮሜድያኑ፤ የትወና ብቃቱን በአዲስ መልክ ካልቀየረ ከገበያው መውጣቱ አይቀርም እየተባለ ነው፡፡

በቦሌ አካባቢ ጌቱ ኮሜርሻል ሴንተር ሕንፃ ላይ የተቋቋመው “ሆሊሲቲ ሲኒማ” ነገ ሥራ እንደሚጀምር የሲኒማ ቤቱ ባለቤት አቶ ኃይለማርያም ኪሮስ አስታወቁ፡፡ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት ሥራ አማርኛ ፊልም በማሳየት ሥራ የሚጀምረው ሲኒማ ቤት፣ በሕንፃው ስድስተኛ ፎቅ ላይ የሚገኝ ሲሆን 250 መቀመጫዎች ያሉት አዳራሽና ካፍቴሪያ አሉት፡፡ የሀገር ውስጥ ፊልም ማሳየቱን በመቀጠልም ከሰኞ እስከ አርብ በቀን ሁለት ፊልሞች፣ ቅዳሜና እሁድ ደግሞ በቀን ሦስት ፊልሞች እንደሚያሳይ ከባለቤቱ መግለጫ መረዳት ተችሏል። ሲኒማ ቤቱ በኮምፒዩተር በታገዘ የትኬት ሽያጭ በመጠቀም ወረፋን ያስቀረ ሲሆን የአካል ጉዳተኞችን ምቾት ታሳቢ በማድረግ እንደተሰራም ለማወቅ ተችሏል፡፡

በገጣሚ መቅደስ ጌታቸው የተዘጋጀው “የኔ” የግጥም መድበል ባሳለፍነው ሳምንት ከማተሚያ ቤት ወጥቶ ለንባብ ደረሰ፡፡ በኖርዌይ ቤተክርስትያን እርዳታ ድርጅት የታተመው የግጥም መጽሐፍ በ50 ገፆቹ 50 ግጥሞች አካቷል፡፡ በፋኖስ ጌት አታሚዎች የታተመው መጽሐፍ በ20ብር ይሸጣል፡፡በሌላም በኩል በበየነ ድንቁ የተደረሱ 17 በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሠረቱ አጫጭር ልቦለዶች የተካተቱበት “ላስቴው ፈረንጅ” ልቦለድ መጽሐፍ ለንባብ ደረሰ፡፡ 145 ገፆች ያሉት መጽሐፉ፣ በ30 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

የአፍሪካ ሕብረትን 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ የተመለከተ የአንድ ሳምንት የሥእል አውደርእይ ማዘጋጀቱን ላፍቶ አርት ጋለሪ አስታወቀ፡፡ ከሰላሳ በላይ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ሀገራት ሰዓሊያን የሚሳተፉበት አውደርእይ፣ ከ70 በላይ ስእሎች የሚቀርቡበት ሲሆን እስከ ግንቦት 26 ለሕዝብ ክፍት ሆኖ ይቆያል ተብሏል፡፡

ያልተዘመረላቸው ጃንሆይ እየተዘመረላቸዉ ነው! (ዕድሜ ለአፍሪካ 50ኛ ዓመት!)
የፓርላማ አባላት የመንግስት ባለሥልጣናትን እያፋጠጡልን ነው (እሰይ!)
ወደፊት ለምትመሰረተው “አንድ አፍሪካ” የሂሩት በቀለን ዘፈን መረጥኩላት!

  ሰሞኑን በኢቴቪ እየቀረበ ያለውን የሙስና “ድራማ-መሳይ” ማስታወቂያ አይታችሁልኛል? መቼም ይሄንን የፀረ-ሙስና ዘመቻው አካል ነው ማለት በጣም ያስቸግራል፡፡ (ሙስናን ለማባባስ ያሰበ ወገን አለ እንዴ?) የአንድ መ/ቤት ሃላፊ (ካድሬ ይመስላል) ሠራተኞቹን ሰብስቦ ሙስናን በጋራ መታገል እንደሚገባቸው ሲደሰኩር ነው ሞባይሉ የሚጮኸው፡፡ ይቅርታ ጠይቆ ስብሰባውን አቋርጦ ይወጣና ቢሮው ውስጥ ከባለሃብት ጋር ይወያያል (የሙስና ውይይት እኮ ነው!) በመጨረሻም ከባለሃብቱ በፖስታ የታሸገ መጠኑ የማይታወቅ ገንዘብ (ሙስና) ተቀብሎ ወደ ሙስና ስብሰባው ይመለሳል፡፡ ከዚያም ምንም እንዳልተፈፀመ “ሙስናን በቁርጠኝነት መታገል አለብን” የሚል የካድሬ ሰበካውን ይቀጥላል፡፡ በዚሁ ነው የሙስና ማስታወቂያው የሚቋጨው፡፡

(ሳይጀመር እኮ ነው ያለቀው!) ቆይ ዓላማው ግን ምንድነው? መቼም አስመሳይ ሞሳኞችን ማስተዋወቅ አይመስለኝም (ምን ሊሰራልን?) ወይስ ለማዝናናት ዓላማ የተሰራ ነው? (እንደኔ ግራ ከመጋባት ይሰውራችሁ!) እኔ ከማስታወቂያው የተረዳሁትን ልንገራችሁ? “ሙስናም ሰርቶ በሰላም ስብሰባን መቀጠል ይቻላል!” የሚል ነው፡፡ እውነቴን እኮ ነው---ከሙስና በኋላ ኑሮ ያለችግር ይቀጥላል የሚል መልዕክት ነው ያለው። (ሞሳኝ እንዳይቀጣ የሚደነግግ ህግ ወጣ እንዴ?) አያችሁ … የሙስናን ነገር አላምነውም፡፡ ወረርሽኝ ነገር እኮ ነው! እናም ሞሳኙ ሳይቀጣ የሚጠናቀቅበት የሰሞኑ ማስታወቂያ ሙስናን እንደሚፀየፍ አንድ ዜጋ አልተመቸኝም ለማለት ያህል ነው፡፡

(እንኳንስ ዘንቦብሽ እንዲያውም እንዲያ ነሽ አሉ!) በነገራችሁ ላይ ያንን የኢህአዴግ ካድሬ ወዳጄን ከስንት ጊዜ በኋላ አግኝቼው በሙስና ዙርያ ብዙ አወጋን፡፡ (እሱ እኮ የፖለቲካ ትኩሳት ሲፈጠር ብቻ ነው ብቅ የሚለው!) እናላችሁ ---- የፀረ ሙስና ኮሚሽንን ያልተጠበቀ እርምጃ፣ ያልተገመቱትን ተጠርጣሪ ባለሥልጣናት (በህልሜ ነው በእውኔ አሉ!) እርምጃውን በተመለከተ አስተያየት ስለሰጡት ተቃዋሚዎች፣ በንዴት የታጀበ አስተያየት በኢቴቪ ስለሰነዘሩት ነጋዴዎች ወዘተ--- ብዙ ቁም ነገሮችን፣ ወሬዎችን፣ ሃሜቶችን -- እንደ ጉድ አልነው - በጃምቦ ድራፍታችን እያወራረድን፡፡ ደህና ቆይተን ቆይተን ችግር የተፈጠረው መቼ መሰላችሁ? ካድሬው ወዳጄ አራተኛ ጃምቦውን ሲያገባድድ ነው፡፡ ድንገት ተነሳና “ሙስና ለምን እንደበዛ ታውቃለህ?” ሲል ጠየቀኝ፡፡

አላውቅም አልኩት (አንተ ንገረኝ በሚል ስሜት!) ምን ገዶት እሱን! እንዲህ አለኝ፤ “ሙስናውን ያመጣው እኮ የኢኮኖሚ ዕድገቱ ነው!” ቃል ሳልተነፍስ ከአጠገቡ ተነስቼ ወጣሁ - የስምንት ጃምቦ ዕዳ አሸክሜው፡፡ (እንደ ጥፋቱማ የስምንት በርሜል መክፈል ነበረበት!) አይገርማችሁም … ሙስና የዕድገት ውጤት ሲሆን! “ኑሮ ተወደደ” ሲባል “የኢኮኖሚ ዕድገቱ ያመጣው ነው”፤ “ኔትዎርክ የለም” ስንል “የዕድገት ውጤት ነው” እንዴ --- ዕድገት ይሄ ሁሉ መዘዝ ካለበት ለምን ጦሳችንን ይዞት አይሄድም፡፡ ይሄውላችሁ … የትራፊክ አደጋ በዛ ስንልም እኮ የዕድገት ውጤት ነው ልንባል ነው፡፡ የእናቶች ሞት ጨመረ ስንልም እንዲሁ ማለት ነው፡፡ እኔ የምለው---ሁሉም አገራት ያደጉት በዚህ የመከራ ሂደት ውስጥ አልፈው ነው እንዴ? (ልማታዊ መንገድ እኮ ጉድ አፈላ!) እናንተ … በገዢው ፓርቲ አባላት የተሞላው ፓርላማ ከመቼ ወዲህ ነው እንዲህ ደፋር የሆነው? (ሰርጐ ገብ ቡድን ገባ እንዴ?) የፓርላማ አባላቱ ስንቱን ቱባ ቱባ የመንግስት ባለስልጣን መሰላችሁ ሲያፋጥጡ የሰነበቱት! አንድ የፓርላማ አባል ስለ ፀረ ሙስና ኮሚሽን አስተያየት ሲሰጡ “ኮሚሽኑ ጥርስ እንዳለው አሳይቷል” ብለው ነበር፡፡ እኔ ደግሞ “ፓርላማው ጥርስ እንዳለው አስመስከረ!” ብያለሁ - ለራሴ፡፡ ከምሬ ነው … እንደ ድሮ አጨብጭቦና እጅ አውጥቶ መለያየት ቀረ እኮ! (እንኳን ፈጣሪ ገላገለን!) ባለፈው ጊዜ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂና ኮሙኒኬሽን ሚኒስቴር ሚኒስትሩ አቶ ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል ለፓርላማ ሪፖርታቸዉን ካቀረቡ በኋላ ከግራና ከቀኝ እንዴት በጥያቄ እንዳፋጠጧቸው አልነግራችሁም፡፡ አንዱ አባል፤ በተወከለበት አካባቢ የኔትዎርክ መቆራረጥ መኖሩን ሲገልፅ፤ ሌላኛው እሱ በተወከለበት አካባቢ ግን ከእነአካቴው ሞባይል እንደማይሰራ ተናገረ፡፡

(ምን ያድርግ ሃቅ ነዋ!) ሃላፊው ታዲያ ምናቸው ሞኝ ነው፡፡ ጥያቄው እንኳንስ በእሳቸው የስልጣን ዘመን በተተኪው ትውልድም መልስ የሚያገኝ ስላልመሰላቸው ስለ ቴሌኮም ማውራቱን ትተው ስለ አገሪቱ ዕድገት መስበክ ጀመሩ፡፡ (ክሊሼ እኮ ነው!) “ምስቅልቅሎች ይኖራሉ፤ ግን የዕድገት ምስቅልቅሎች ናቸው!” አሉን ሚኒስትሩ፡፡ (አዲስ ነገር ግን አልነገሩንም!) እኔ ግን አንድ ጥያቄ አለኝ፡፡ ከሁለቱ “ጉልቤ” የመንግስት ድርጅቶች የሚገላግለን እናገኝ ይሆን? እንግዲህ ለኤልፓና ለቴሌኮም ስንል ጫካ አንገባ? እውነቴን ነው … ኤልፓ የዕለት ተዕለት ኑሮአችንን አመሰቃቀለው እኮ! እሱም እንደባልደረባው “ምስቅልቅሉ የዕድገት ምስቅልቅል ነው!” እንዳይለን እሰጋለሁ፡፡ (ተመሳሳይ ላባ ያላቸው ወፎች አብረው ይበራሉ ይባል የለ!) ይታያችሁ … በአንድ ከሰዓት በኋላ ብቻ ሦስቴ መብራት እየጠፋብን ነው፡፡ ቴሌኮምም ቢሆን እኮ ብሶበታል፡፡ ቅዳሜ ማታ እዚሁ አዲስ አበባ ሲኤምሲ አካባቢ ለሚኖር ጓደኛዬ የላክሁት ማሴጅ መቼ ቢደርስ ጥሩ ነው? ማክሰኞ ማታ - በአራተኛው ቀን ማለት ነው፡፡

ለዚህ ለዚህማ እኔው ራሴ እቤቱ ሄጄ መልዕክቱን አደርስለት ነበር (ከመንገድ ትራፊክ የቴሌ ትራፊክ ባሰ እኮ!) የፖለቲካ ወጋችን ችግርና መከራ ብቻ ሆነ አይደለ! ምን ይደረግ? ወደን እኮ አይደለም! እንደውም የችግራችንን ያህል አላመረርንም (ቻይ አድርጐ ፈጥሮናላ!!) በዚህ ሁሉ ምስቅልቅል ግን ፓርላማ ያሳየው ያልተለመደ ድፍረትና ቁርጠኝነት አስደምሞኛል (የምስቅልቅል ዘመን ጀግናችን ብየዋለሁ!) ይሄውላችሁ … የም/ቤት አባላትን ማበረታታት አሁን ነው (የፓርላማው ህዳሴ ሳይጀመር አልቀረም!) እናም ውዳሴ ብቻ ሳይሆን ማበረታቻም ያስፈልጋቸዋል ባይ ነኝ - ኪስ የሚገባ፡፡

ባለ ሁለት ዲጂት የኢኮኖሚ ዕድገቱ ለነሱ ደሞዝ ጭማሪ ካልሆነ ምን ፋይዳ አለው? (ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ እንዲሉ) ግዴለም እነሱ ሚኒስትሮቹን ያፋጡልን እንጂ እኛ በሰላማዊ ሰልፍም ቢሆን ደሞዛቸውን እናስጨምርላቸዋለን። (“እከክልኝ ልከክልህ” ሆነ እንዴ?) በኢህአዴግ ቋንቋ ግን “ሰጥቶ መቀበል” ይባላል፡፡ እናላችሁ ... ፓርላማችን “የዓመቱ ደፋር ተቋም” የሚል ስያሜ እንዲያገኝ ፊርማ ማሰባሰብ ጀምሬአለሁ (ቸኮልኩ እንዴ?) በዚህ ተነሳሽነቴ “ኮምፕሌክስ” ያቃጠላቸው ፀረ ህዝቦች ምን እያሉ እንደሚጠሩኝ ታውቃላችሁ? “ፈጠነች!” (እውነት ፈጥኜ ይሆን እንዴ?) እናንተ በቀደም ጠ/ሚኒስትሩ የኢትዮጵያ ህዝብ ቁጥር 90 ሚሊዮን መሆኑን ሲናገሩ በኢቴቪ ሰምቼ ክው ነው ያልኩት፡፡ እንዴ --- መቼ ተቆጥረን ነው አምስት ሚሊዮን የጨመርነው? የህዝብ ቁጥር “በአስማት!” ይጨምራል ልበል? ግን እኮ ከባለቤቱ ያወቀ ቡዳ ነው ይባላል (ስለ ህዝቡ ከመሪው በላይ የሚያውቅ አለ እንዴ?) ያ ካድሬ ወዳጄ 90 ሚሊዮን መድረሳችንን ቢሰማ ኖሮ ምን እንደሚል ታውቃላችሁ? “የዕድገታችን ውጤት ነው!” (የዕድገት አባዜ ሳይዘው አይቀርም!) እኔ የምላችሁ … የአፍሪካ ህብረትን 50ኛ ዓመት በዓል እንዴት አያችሁት? ኢቴቪ ሰሞኑን የሚያነጋግራቸውን ሰዎች (ነዋሪዎች) ታዝባችሁልኛል፡፡ አንድ ነዋሪ “ህዝቡ በዓሉ መቼ ነው እያለ ነው” ብለዋል - ጉጉቱን ለመግለፅ፡፡

እኔ ግን ለምን ይዋሻል? ብያለሁ፡፡ ሌላ ነዋሪ ደግሞ “አሁን የአፍሪካ ቀንድ እንደሆንን የዓለምም ቀንድ መሆን አለብን” ሲሉ ተናግረዋል፡፡ አንዲት ወጣት እንዲሁ “ወጣቱ መቼ ነው በዓሉ እያለ ነው!” ስትል ትንሽ ማጋነን የታከለበት በፕሮፖጋንዳ የታሸ አስተያየት ሰጥታለች፡፡ ከሁሉም ምን እንዳስደነቀኝ ታውቃላችሁ? ኢቴቪ ከበዓሉ ጋር በተገናኘ ባዘጋጀው ፕሮግራም፤ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ያከናወኗቸው ድንቅ ድንቅ ሥራዎች ለመጀመሪያ ጊዜ ሲነገርላቸው መስማቴ ነው፡፡ (አምላክ ወረደ ብያለሁ) ቢያንስ ቢያንስ የአፍሪካ አንድነት መስራችነታቸው፣ የአፍሪካ አገራት ከቅኝ አገዛዝ ነፃ እንዲወጡ ቁልፍ ሚና እንደነበራቸው፣ ለአገራቸው ዘመናዊ አስተዳደርን እንዳስተዋወቁ፣ በአገሪቱ የመጀመሪያውን ዩኒቨርስቲ እንደከፈቱ ወዘተ-- ተገልፆላቸዋል (ኧረ ይበቃቸዋል!) እኔማ…እንኳንም የአፍሪካ 50ኛ ዓመት በዓል መጣ ብያለሁ (ያልተዘመረላቸው ንጉስ ተዘመረላቸዋ!) ኢቴቪም ያለፈውን መንግስት ሁሉ ከመጣው ጋር ሆኖ ከማውገዝ አባዜው መላቀቁ ትልቅ ተስፋ ነው፡፡ (የአንድ ሺ ኪ.ሜትር ጉዞ የሚጀመረው በአንድ እርምጃ ነው እንዲሉ!) እኔ የምላችሁ ግን የተባበረች የአፍሪካ መንግስት (The United States of Africa) ይመሰረታል የሚባለው ከምር ነው እንዴ? ነፍሳቸውን ይማረውና አምባገነኑ የሊቢያ መሪ የጋዳፊ ቅዠት መስሎኝ ነበር እኮ! መተባበሩና አንድ አፍሪካ መመስረቱ ባልከፋ ነበር … መጀመሪያ ግን እርስበርስ መግባባት አይቀድምም ትላላችሁ? እንደ አገር ሳንስማማ 53 አገራት ደባልቀን ጉድ እንዳይፈላ! አንዳንድ ህልሞች ከምድጃ ውስጥ ሳይበስሉ ይወጡና “ሊጥ” መብላት ይመጣል፡፡

እናም ለትንሽ ጊዜ እዚያው ኦቭን ውስጥ ቢቆይና ቅንብር እስኪል ቢበስል ይሻላል ባይ ነኝ፡፡ ለምን መሰላችሁ? አፍሪካ እኮ ገና ናት! (እንደሚወራው አይምሰላችሁ!) ፕሮፌሰር ተስፋፅዮን መንግስቱ የተባሉ ምሁር ስለ አፍሪካ ለኢቴቪ በሰጡት አስተያየት ምን አሉ መሰላችሁ? “አፍሪካ ድሃ የሆነችው በአስተዳደር ችግር ነው - በመሪዎቿ!” (የነገሩን ስስ ብልት አግኝተውታል!) ፕሮፌሰሩ ሌላም አንጀት የሚያርስ ነገር ተናግረዋል፡፡ “አፍሪካ ምን ሰርተን እንሙት የሚሉ መሪዎች ያስፈልጓታል” (“ምን በልተን እንሙት” ባዮቹ በዙኣ!) አያችሁ…የአፍሪካ መስራች አባቶች (Founding Fathers) ህልም እውን ከመሆኑ በፊት የመሰረት ሥራው ተጠናክሮ መሰራት አለበት - በጥሩ ግንበኛ፡፡ ያለዚያ ግን “መክሸፍ እንደ አፍሪካ ታሪክ” ልንል ነው፡፡ እኔ የምለው ግን የተባበረችው አፍሪካ የመጀመሪያው ፕሬዚዳንት ማነው የሚሆነው? እርግጠኛ ነኝ ኩዴታ የሚባል ነገር አይኖርም (ማነው ያለው እንዳትሉኝ!) ለማንኛውም ግን Happy Anniversary ብያለሁ - ለአፍሪካ 50ኛ ዓመት!! ወደፊት ትመሰረታለች ለተባለችው The united States of Africa የአንጋፋዋ ድምፃዊት የሂሩት በቀለን ዘፈን መርጬላታለሁ፡፡ (ግጥሙ በእንስት ፆታ ነው የቀረበው - ለአፍሪካ እንዲመች!) “ዝናቡም ዘነበ ደጁም ረጠበ ትመጫለሽ እያልኩ ልቤ እያሰበ እስኪ መጥተሽ ልይሽ እንዳሉሽም ሆነሽ ቆንጆ ነሽ ይላሉ ማን አየሽ ማን አየሽ!!”

በ11ኛው የቡፓ ግሬት ማንችስተር የ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ በ40 ዓመቱ መሳተፉ መቼ ጡረታ ይወጣል የሚለውን አነጋጋሪ አጀንዳ ቀሰቀሰ፡፡ ዘንድሮ በተለይ በእግር ኳስ እነ ፖል ስኮልስ፤ ዴቪድ ቤካም እና ሌሎች ምርጥ እግር ኳስ ተጨዋቾች 40ኛ ዓመታቸውን ሳይደፍኑ ጫማቸውን ሲሰቀሉ ኃይሌ ግን ሩጫን ለማቆም ምንም ሃሳብ እንደሌለው እያረጋገጠ ነው፡፡ ከ2 ወራት በፊት ወደ ማንችስተር ተመልሼ መወዳደር የምችልበትን እድል ላመነታበት አልችልም በማለት በ10ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው ለመሳተፍ የወሰነው ኃይሌ በውድድሩ ለ6ኛ ጊዜ ለማሸነፍ እቅድ እንዳለው በማስታወቁም የውድድሩ አዘጋጆች ተሳትፎውን በጉጉት እንዲጠብቁት አድርጓቸዋል፡፡

የቡፓ ግሬት ማንችስተር የጎዳና ላይ ሩጫ እስከ 40ሺ ተሳታፊዎች እንደሚኖሩት ተጠብቋል፡፡ ኃይሌ 40ኛ ዓመት ልደቱን በማስመልከት መልካም ምኞታቸውን ለገለፁለት ሁሉ ባሰፈረው አጭር የቲውተር መልዕክት‹ ለእኔ የ40 ዓመት ልደቴ ቁጥር ነው። የ20 ዓመት ሰው መሆኔ ነው የሚሰማኝ› ብሎ ነበር፡፡ ሃይሌጋብር በሚል የሚሰራጨው የአትሌቱ የቲውተር ማስታወሻ እስከ 67ሺ ለአድናቂዎች ሲከታተሉት እሱም በዚህ ማህበራዊ ድረገፅ 223 አጫጭር ፅሁፎችን ማስተላለፉን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ኃይሌ ከሩጫ ስፖርት ጡረታ የሚወጣበትን ቀን ይፋ ባያደርግም በርካታ የስፖርቱ ኤክስፕርቶች እና ሙያዊ ትንተናዎች አሁን በደረሰበት እድሜ በማራቶን ለማሸነፍ እንደሚከብደው እየገለፁ ናቸው፡፡ ኃይሌ አምና በቶኪዮ ማራቶን ሲሳተፍ 4ኛ ደረጃ ይዞ የጨረሰው ርቀቱን በ2 ሰዓት ከ8 ደቂቃ ከ17 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በመሸፈን ነበር።

አትሌት ኃይሌ 40 ዓመት ከሆነም በኋላ በማራቶን ውድድሮች ቢሳተፍ ርቀቱን ከ2 ሰዓት 06 ደቂቃ እስከ 2 ሰዓት 08 ደቂቃ የመግባት አቅም እንዳለው የሚመሰክሩ ቢኖሩም ይህን ሰዓት ለማስመዝገብ ወቅታዊ ብቃት እንደሌለው የገለፁም አሉ፡፡ ከ3 ዓመታት በፊት በኒውዮርክ ማራቶን ሲወዳደር በጉልበቱ ላይ ባጋጠመው ጉዳት አቋርጦ ከወጣ በኋላ ሩጫን በቃኝ ብሎ ተሰናብቶ የነበረወ አትሌት ኃይሌ በጥቂት ቀናት ጊዜ ውስጥ ይህን ውሳኔ በመቀየር ወደ ሩጫው እንደተመለሰ ይታወሳል፡፡ ከዚያን ጊዜ ወዲህ በተደጋጋሚ ኃይሌ መቼ ጡረታ ይወጣል የሚለው አጀንዳ ማነጋገሩን ቀጥሏል፡፡ ራኒንግኮምፒውቴተርስ የተባለ ድረገፅ ኃይሌ እድሜው ስንት ነው በሚል ጠያቂ ርእስ በድረገፁ ባሰፈረው ዘገባ ታላቁ ሯጭ ፓስፖርት ላይ ከሰፈረ እድሜው በ5 ዓመት ያረጀ ስፖርተኛ ሳይሆን እንደማይቀር ለመገመት ሞክሮ ነበር፡፡ በ2007 እኤአ ላይ እና በ2008 እኤአ ላይ በበርሊን ማራቶን የዓለም ማራቶን ሪከርድን ለሁለት ጊዜ ሰብሮ ሲያሻሽል ኃይሌ በ34 እና በ35 አመቱ ቢሆንም ትክክለኛው እድሜ 39 እና 40 ሊሆን ይችላል ነው የሚለው የራኒንግ ኮምፒውቴተርስ ሃተታ፡፡

ይህ የእድሜው መጨመር አትሌቱ ምን ያህል ምርጥ ብቃት ያለው እና ማስተር አትሌት የሚያደርገው ነው በማለትም የአድሜው መጭበርበር አትሌቱን ከማድነቅ በስተቀር አሉታዊ ተፅእኖ እነደሌለው ገለፃም አድርጓል፡፡ ኃይሌ ጡረታውን በመቀልበስ ወደ ውድድር ከተመለሰ በኋላ በማራቶን ውድድሮች ባይሳካለትም በግማሽ ማራቶንና በጎዳና ላይ ሩጫ ውድድሮች በመሳተፍ አስደናቂ ውጤት በማስመዝገብ የስፖርቱን ዓለም በጉልምስና እድሜውም ማስደነቁን ቀጥሏል፡፡ ዛሬ በዓለማችን ብዙ የስፖርት አይነቶች በፕሮፌሽናል ደረጃ በጥሩ ብቃት ለመቆየት የሚቻለው ለ20 አመት ቢሆንም አትሌት ኃይሌ ግን በሩጫ ውድድር መሳተፍ ከጀመረ 22 ዓመታትን በማስቆጠር ለየት ያለ ጥንካሬውን አስመስክሯል፡፡ በአብዛኛዎቹ የስፖርት አይነቶች ምርጥ ስፖርተኞች በውድድር የሚቆዩበት አማካይ የእድሜ ማጣርያ ከ38 እስከ 40 ነበር፡፡ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ግን በ40 ዓመቱ በማንችስተር ግሬት ራን ለመሳተፍ መወሰኑን ካሳወቀ በኋላ ከጋርዲያን ጋር ባደረገው ቃለምልልስ በሩጫ ውድድር እስከ 50 እና 60 ዓመቱ የመሮጥ ፍላጎት እንዳለው ተናግሯል፡፡

በዚሁ ቃለምልልስ መሮጥ እና ምግብ መብላት አንድ ናቸው የሚል ሃሳቡን የገለፀው አትሌቱ እያንዳንዱ ቀን በሙሉ ጉልበት እና ሃይል የማሳልፈው በምግብ ብቻ ሳይሆን ስለምሮጥም ነው ብሏል፡፡ በሩጫ ስፖርት ለረጅም ጊዜ የዘለቀበትን ብቃት በተመለከተ በሰጠው አስተያየት ደግሞ‹ ብዙ ምስጥር የለውም፡፡ ልምምድ የምሰራው በከፍተኛ ትጋት እና ጥንቃቄ ነው፡፡ ሁሉም አትሌቶች ለረጅም ጊዜ ብቃታቸውን ጠብቆ ለመቆየት ሶስት ነገሮች ያስፈልጋቸዋል፡፡ የመጀመርያው ቁርጠኛነት ነው። በመቀጠል ደግሞ የተሟላ ዲስፕሊን ሊኖራቸው ያስፈልጋል፡፡ በሶስተኛ ደረጃ ደግሞ ጠንክሮ በትጋት መስራት አስፈላጊ ነው› በማለት ምክሩን አስተላልፏል፡፡ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ በአትሌቲክስ ስፖርት የምንግዜም ምርጥ አትሌት መሆኑን በርካታ ኤክስፕርቶች እና ባለሙያዎች በተደጋጋሚ ቢገልፁትም፤ እሱ ግን ተምሳሌቴ እና ጀግናዬ የሚለውን አበበ ቢቂላ ለዚሁ ክብር ቀዳሚው ተመራጭ ያደርገዋል፡፡

አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ለ22 አመታት በቆየበት የሩጫ ስፖርት ከመካከለኛ ርቀት 800 ሜትር አንስቶ፤ በረጅም ርቀት የ10ሺ እና 5ሺ ሜትር የትራክ እና የቤት ውስጥ ውድድሮች፤ ከ1 ማይል እስከ 10 ማይል በሚወስዱ ሩጫዎች፡ ከ10 እሰከ 15 ኪሎሜትር በሚለኩ የጎዳና ላይ ሩጫዎች እና በማራቶን እና በግማሽ ማራቶን ውድድሮች በአጠቃላይ እስከ 26 በሚደርሱ የሩጫ ውድድር ዓይነቶች በመወዳደር እና አስደናቂ ውጤት በማግኘት በታሪክ መዝገብ ስሙን ያሰፈረ ነው፡፡ በ22 ዓመታት የሩጫ ዘመኑ ከ27 በላይ ሪከርዶችን ማስመዝገብ የቻለው ኃይሌ በተለያዩ የውድድር አይነቶች ያስመዘገባቸው የሪከርድ ጊዜዎች እና ፈጣን ሰዓቶች በምንጊዜም የውጤት ደረጃዎች ከመጀመርያዎቹ አስር አትሌቶች ተርታ እንዳሰለፉት ናቸው፡፡ በ10ሺ ሜትር የምንገዜም ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ እሰከ 10 ባለው ደረጃ ሶስት ፈጣን ሰዓቶች ያሉት ኃይሌ በዚሁ ደረጃ ላይ በ1998 የ10ሺ ሜትር ርቀትን በ26 ደቂቃ ከ22.75 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ የሸፈነበት ጊዜ በሶስተኛ ደረጃ የተመዘገበ ነው፡፡

በ5ሺ ሜትር ውድድር ደግሞ በምንግዜም ፈጣን ሰዓት እስከ 10 ባለው ደረጃ ሶስት ፈጣን ሰዓቶችን ያስመዘገበው አትሌቱ በ1998 እኤአ ላይ ርቀቱን በ12 ደቂቃ ከ39.36 ሰኮንዶች የጨረሰበት ጊዜው ሁለተኛ ደረጃ የተሰጠው ነው፡፡ በማራቶን የምንግዜም ፈጣን ሰዓት ደረጃ ላይ በ2007 እኤአ ላይ 2 ሰዓት ከ04 ደቂቃ ከ26 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ያስመዘገበው ሰዓት በ9ኛ ደረጃ እንዲሁም በ2008 እኤአ ላይ 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃ ከ59 ሰኮንዶች የሆነው ጊዜ በ5ኛ ደረጃ የተመዘገቡ ናቸው፡፡ በመጨረሻም የኃይሌን የምንግዜም ምርጥ አትሌትነት የሚያሳየው መረጃ በዓለም አቀፉ የጎዳና ላይ ሩጫዎች ስታስቲክስ እና ውጤት በሚከታተለው ተቋም የወጣው የምንግዜም ከፍተኛ የሽልማት ገንዘብ ያገኙ አትሌቶች ደረጃ ይሆናል፡፡ በዚሁ ደረጃ ላይ በሩጫ ዘመኑ ከ50 በላይ ውድድሮች ላይ በሰበሰበው 3 ሚሊዮን 546ሺ 674.80 ዶላር ( በኢትዮጵያ ብር 69 ሚሊዬን 511ሺ አካባቢ ነው) አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ የዓለምን አትሌቶች በአንደኛነት እየመራ መሆኑ ነው፡፡

ባየር ሙኒክ ወይስ ቦርስያ ዶርትመንድ? ለ58ኛዋ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ በሚደረግ የፍፃሜ ጨዋታ ዛሬ ምሽት በእንግሊዙ ዌምብሌይ ስታድዬም በቦንደስ ሊጋ ደርቢ ባየር ሙኒክ ከቦርስያ ዶርትመንድ ይገናኛሉ፡፡ የፍፃሜ ጨዋታው በ100 አገራት በሚኖረው የቴሌቭዥን ቀጥታ ስርጭት እስከ 220 ሚሊዮን ተመልካች ሊያገኝ እንደሚችል ተጠብቋል፡፡ በዛሬው የሻምፒዮንስ ሊግ የፍፃሜ ጨዋታ የጀርመን ክለብ በታሪክ ለሰባተኛ ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒዮናነት ክብሩን እንደሚያነሳ ቢረጋገጥም ሁለቱ የጀርመን ምርጥ ክለቦች የአውሮፓ እግር ኳስ ንጉስ ለመሆን ይጫወታሉ።

በጀርመን ክለቦች መካከል የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የዋንጫ ጨዋታ ሲደረግ በታሪክ የመጀመርያው ሲሆን ሁኔታው በዓለም አቀፍ ደረጃ ትኩረት ተነፍጎት የነበረውን የቦንደስ ሊጋ እግር ኳስ ተወዳጅነት በመጨመር አስተዋፅኦ ይኖረዋል፡፡ ዌምብሌይ የሻምፒዮንስ ሊግ የዋንጫ ጨዋታን ሲያስተናግድ የዛሬው ለ7ኛ ጊዜ ሲሆን በስታድዬሙ በ1962 ኤሲ ሚላን፤ በ1968 ማንችስተር ዩናይትድ፤ በ1971 አያክስ፤ በ1978 ሊቨርፑል እነዲሁም በ1992 እና በ2011 እኤአ ላይ ባርሴሎና የአውሮፓ ሻምፒዮን ሆነውበታል። የዋንጫ ጨዋታውን በቅርበት ለመከታተልና ከተቻለም ስታድዬም በመግባት ለመመልከት የሚፈልጉ ከ150ሺ በላይ የሁለቱ ክለቦች ደጋፊዎች ለንደን ከተማን ከሰሞኑ አጥለቅልቀዋታል፡፡

እነዚህ ደጋፊዎች በዌምብሌይ የዋንጫ ጨዋታውን ለመታደም በጥቁር ገበያ እስከ 14ሺ ፓውንድ የትኬት ዋጋ ለመክፈል ተገድደዋል፡፡ በኢንተርኔት ለዛሬው ጨዋታ ቀርቦ የነበረው የ60 ፓውንድ ርካሽ የትኬት ዋጋ በጥቁር ገበያው እስከ 4150 ፓውንድ መቸብቸቡን ለማወቅ ተችሏል፡፡ 86ሺ ተመልካች በሚያስተናግደው ዌምብሌይ ስታድዬም ለሁለቱ ክለብ ደጋፊዎች በአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር የተመደበው የትኬት ብዛት 50ሺ ነው፡፡ በቦንደስ ሊጋው በሜዳው በሚያደርገው ጨዋታ እስከ 80ሺ ስፖርት አፍቃሪ የሚታደመው ቦርስያ ዶርትመንድ 500ሺ ደጋፊዎቹ ትኬት ለመግዛት አመልክተው ለ25ሺው እድሉን የፈጠረው እጣ በማውጣት ነበር፡፡ ባየር ሙኒክ እና ዶርትመንድ ባለፉት አራት የውድድር ዘመናት የጀርመን ቦንደስ ሊጋን በበላይነት ተቆጣጥረውት ቆይተዋል፡፡

በ2009 እና በ2013 እኤአ ላይ ባየር ሙኒክ እንዲሁም በ2010 እና በ2011 እኤአ ላይ ቦርስያ ዶርትመንድ ቦንደስ ሊጋውን እኩል ሁለት ጊዜ ሻምፒዮን ሆነውበታል። በእነዚህ አራት የውድድር ዘመናት ባየር ሙኒክ ለ3ኛ ጊዜ ለአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የፍፃሜ ጨዋታ መቅረቡ ነው፡፡ ከ3 ዓመታት በፊት ባየር ሙኒክ በሻምፒዮንስ ሊግ የፍፃሜ ጨዋታ ከጆሴ ሞውሪንሆ ኢንተር ሚላን ጋር ተገናኝቶ በፍፁም ብልጫ ተሸንፎ ዋንጫውን ተነጠቀ፡፡ ከዓመት በፊት ደግሞ በሜዳው አሊያንዝ አሬና ስታድዬም ከቼልሲ ጋር ተገናኝቶ በመለያ ምቶች ድሉን በማጣት መራር ሽንፈት ገጥሞታል፡፡ በርካታ የስፖርት ትንተናዎች እና ዘገባዎች ሁለቱ የጀርመን ክለቦች የሚፋለሙበት የፍፃሜ ጨዋታ በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በአቻ ውጤት እንደሚጠናቀቅ እየገመቱ ሲሆን ባየር ሙኒክ ሻምፒዮን ሊሆን እንደሚችል የተነበዩም ያመዝናሉ፡፡

በክዋክብት ስብስብ በመጠናከር የሚሻለው ባየር ሙኒክ ሲሆን በቡድን ወጣትነት ደግሞ ዶርትመንድ ጥንካሬ አለው፡፡ በዘንድሮው ሻምፒዮንስ ሊግ ኮከብ ግብ አግቢነት ደረጃን በ12 ጎሎች እየመራ የሚገኘውን የሪያል ማድሪዱ ክርስትያኖ ሮናልዶ በ10 ጎሎች የሚከተለውን ሮበርት ሌዋንዶውስኪ ብቃት ዶርትመንድ ሲመካበት ፤በባየር ሙኒክ በኩል ፍራንክ ሪበሪ እና አርያን ሮበን ከፍተኛ ሚና ሊኖራቸው ይችላል፡፡ ሁለቱ ቡድኖች ለመጨረሻ ጊዜ በቦንደስ ሊጋ ሲገናኙ 1ለ1 ተለያይተው ነበር፡፡ በአጠቃላይ በ4 ጨዋታዎች ዘንድሮ ተገናኝተው ባየር ሙኒክ ሁለቱን ሲያሸንፍ በሁለት የሊግ ግጥሚያዎች ደግሞ አቻ ተለያይተዋል፡፡ ባየር ሙኒክ ዘንድሮ ቦንደስ ሊጋውን ያሸነፈው በሁለተኛ ደረጃ የጨረሰውን ዶርትመንድ በ25 የነጥብ ልዩነት በልጦ እንደነበርም ይታወሳል፡፡ ባየር ሙኒክ እና ዶርትመንድ በሁሉም ውድድሮች ከዛሬው የሻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ በፊት ለ92 ጊዜያት ተገናኝተዋል፡፡

በእነዚህ ግጥሚያዎች ባየር ሙኒክ 41 ጊዜ ሲያሸንፍ ዶርትመንድ ድል የቀናው 23 ጊዜ ነው፡፡ በ28 ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይተዋል፡፡ የባየር ሙኒክ ክለብ በስብስቡ 27 ተጨዋቾች ሲይዝ 13 ከጀርመን ውጭ የመጡ ፕሮፌሽናሎች ናቸው፡፡ ቦርስያ ዶርትመንድ ክለብ በበኩሉ በስብስቡ 28 ተጨዋቾች ሲይዝ 9 ከጀርመን ውጭ የመጡ ፕሮፌሽናሎች ናቸው፡፡ በትራንስፈርማርከት የዝውውር ገበያ የዋጋ ግምት መሰረት የባየር ሙኒክ ቡድን 380 ሚሊዮን ፓውንድ እንደሚያወጣ ሲተመን የቦርስያ ዶርትመንድ ቡድን የተገመተው 225 ሚሊዮን ፓውንድ ነው፡፡ የዶርትመንድ ስብስብ አማካይ እድሜ 24.7 ዓመት ሲሆን የባየር ሙኒክ ደግሞ 26.2 ዓመት ነው፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ዘንድሮን ጨምሮ ለሚቀጥሉት ሶስት ዓመታት በሻምፒዮንስ ሊግ ለሚሳተፉ ክለቦች በውጤታቸው ልክ በሚሰጥ የገንዘብ ሽልማት እና በቴሌቭዥ መብት፤ በስታድዬም ገቢ እና ከተለያዩ ገቢዎች የሚኖራቸው ድርሻ በ15 በመቶ ጭማሪ ይኖረዋል፡፡ ለዌምብሌይ የሻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ የደረሱት ሁለቱ የጀርመን ክለቦች በነፍስ ወከፍ እስከ 66 ሚሊዮን ዶላር ያገኛሉ ተብሎም ተገምቷል፡፡

ወንዶች ከፍቅረኛቸውና ከትዳራቸው ውጭ እየሄዱ እንዳመጣላቸው ለመተኛት ብዙም ምክንያት አያስፈልጋቸውም ይባላል። ኮስሞፖሊታን ረቡዕ እለት ያሰራጨው ፅሁፍ ግን፣ ከፍቅረኛ ጀርባ ማማተርና ግራ ቀኝ መቀላወጥ፣ በወንዶችም ሆነ በሴቶች ዘንድ እኩል ነው ይላል። ምናልባት በወንዶችና በሴቶች መካከል ልዩነት ካለ፣ የሚቀላውጡበት ምክንያት ላይ ነው። በእርግጥ፣ በመካከላቸው ልብን የሚያጠግብ ፍቅር ሳይኖር “ፍቅረኞች” የሚል ስያሜ ከያዙ፣ በስሜት ውጭ ውጭውን ለመናፈቅ ሌላ ምክንያት አያስፈልጋቸውም - አላፊ አግዳሚውን ለማየት አይናቸው የሚቅበዘበዘው ስለማይዋደዱ ነው። በፍቅር የሚዋደዱ ከሆነስ? ይሄ ነው ጥያቄው። ከፍቅረኛቸው ውጭ ሌላ ወንድ እንዲመኙ የሚገፋፉ

5 ምክንያቶች በሚል ኮስሞፖሊታን ባቀረበው ፅሁፍ መነሻነት ነገሩን ብናስብበት አይከፋም።

1. በኑሮ ሽግግር የሚፈጠር ጭንቀት የኑሮ ሽግግር ማለት፣ ከዩኒቨርስቲ መመረቅ ወይም ቀለበት ማሰር ሊሆን ይችላል። 30ኛ አመት እድሜ ላይ መድረስ፣ አልያም አንዱን ስራ ትቶ ሌላ ለመሞከር መወሰንም እንደ ኑሮ ሽግግር ይቆጠራል። የኑሮ ሽግግር፣ አነሰም በዛ፣ በአእምሮዋ ውስጥ ብዙ ጥያቄዎችን መፍጠሩ አይቀርም። የህይወቴ አቅጣጫ ወዴት ያመራል? ከዚህ በኋላ ምንድነው የማደርገው?... እነዚህንና ሌሎች ጥያቄዎችን እያነሳች ከፍቅረኛዋ ጋር ብትመክር ተገቢ ነው፣ በጣም ከተደጋገመ ግን መሰላቸትን ያስከትላል። ለነገሩማ፣ ለብቻዋ ሆና ነገሩን እያወጣች እያወረደች ማሰብና ማሰላሰል እንዳለባት አያከራክርም። ለጥያቄዎቿና ለሃሳቦቿ፣ መቋጫ እያበጀች ካልሄደችና ያንኑን መልሳ መላልሳ የምታሰላስል ከሆነ ግን፣ አላስፈላጊ ጭንቀት ይፈጥርባታል። በማያቋርጥ የእንጥልጥል ስሜት እየተብሰለሰለች ምቾት ታጣለች። ይሄኔ፣ ከጭንቀት የሚገላግልና ለአፍታም ቢሆን ከአስቀያሚው ስሜት የሚያዘናጋት ሰው ብታገኝ ትመኛለች። ከፍቅረኛዋ ውጭ ሰው ፍለጋ ትማትራለች። (በእርግጥ፣ ሰው ማየት አስጠልቷት የምትተኛ ሴትም አትጠፋም። ወይም ከሴት ጓደኞቿ ጋር ሌላ ሌላ ነገር እያወራች ጭንቀቷን ለመርሳት የምትሞክርም ትኖራለች)። ነገር ግን፣ ከኑሮ ሽግግር ጋር የሚከሰት ጭንቀት፣ ከሌላ ወንድ ጋር እንድትወጣም ሊገፋፋት ይችላል።

2. የጓጓችለትና የኮራችበት ነገር፣ ፍቅረኛዋ ካልተጋራት ሴቶች፣ አድናቆትን መስማት ይፈልጋሉ ይባላል። በአድናቆት ጥምና ረሃብ ነጋ ጠባ ይሰቃያሉ ማለት ግን አይደለም። በጣም የምትወዱትን ነገር ሌሎች ሰዎች ቸል ሲሉት፣ የምትጓጉለትን ነገር ሲዘነጉት፣ የምታከብሩትን ነገር ከምንም ሳይቆጥሩት ሲቀሩ ምን ይሰማችኋል? ይደምቃል፣ ይሟሟቃል ያላችሁትን ነገር፣ ሰዎች ሲያደበዝዙትና ሲያቀዘቅዙት… ንዴት፣ ሃዘን፣ ድብርት ይፈጠር የለ? ቢያንስ ቢያንስ፣ “ኩም አልኩ” የሚባለው አይነት አስቀያሚ ስሜት ይፈጠራል። ሴቶች፣ ከምር ትልቅ ዋጋ የሚሰጡትና የሚኮሩበት ነገር ሲሰሩ፣ ስሜታቸውን ተጋርቶ ነገሩን እንዲያደምቅና እንዲያሟሙቅ የሚጠብቁት ፍቅረኛቸውን ነው። ፍቅረኛዋ፣ ነገሩን በቸልታ ካለፈው፣ “ኩም” ትላለች። ብሩህ አድርጋ የቀረፀችው የህይወት ምስል ይጨልምባታል። እናም የጨለመውን የሚያበራ፣ አልያም በመጠኑ ፈካ የሚያደርግ ሌላ ሰው ለማግኘት ግራ ቀኝ ትቃኛለች። በእርግጥ፣ ድብርትን የሚያባርርና ብሩህ ስሜትን የሚያላብስ ፊልም በማየት ከጭጋጋማው መንፈስ ለመላቀቅ የምትሞክርም ትኖራለች። አልያም ድብረቷ በጭፈራ እንዲወጣላት ከጓደኞቿ ጋር ናይት ክለቦችን ስታዳርስ ብታድር አይገርምም። የደበዘዘውን አለም የሚያበራ የሆነ ወንድ ለማግኘት እንድታስብም ሊያነሳሳት ይችላል።

3. ሊበጠስ የተቃረበ ግንኙነት እየሳሳ ሊበጠስ የደረሰ የፍቅር ግንኙነት፣ ምንም ቢሆን የፍቅረኞቹን ስሜት መረበሹ አይቀርም። በእርግጥ፣ “አንድ ሐሙስ የቀረው የፍቅር ግንኙነት”፣ አንዳንድ ሴቶችን ወደ ፍቅረኛቸው ይበልጥ እንዲጠጉ ሊገፋፋቸው ይችላል። ነገር ግን፣ ከወዲሁ ከፍቅረኛቸው ጀርባ አሻግረው እንዲመለከቱና ወደ ሌላ ወንድ እጃቸውን እንዲዘረጉ ሊያነሳሳቸውም ይችላል። የፍቅር ግንኙነት ከተቋረጠ፣ አንዳች የጉድለትና የክፍተት አስቀያሚ ስሜት ይፈጠራል። በዚህ ስሜት ላለመዘፈቅ ብላ ቅድመ ዝግጅት ታደርጋለች፤ ጉድለትን የሚሞላ ማካካሻና ምትክ ፍለጋ አካባቢዋን ትቃኛለች። ይሆናል የምትለው ወንድ ያየች ሲመስላትም፣ ለመሞከር ትነሳሳለች።

4. ሲጀመር አዝናኝ የነበረው ፍቅር ሲደነዝዝ በፍቅር ሲቀራረቡ፣ የሌት ተቀን ሃሳባቸው ሁሉ ደግ ደጉ ላይ ያተኩራል። አንዱ ከሌላው ለሚያገኘው ደስታ ትልቅ ዋጋ ይሰጣሉ። አንዱ የሌላውን መልካም ነገር ከልብ እያደነቀ ይረካል። ሲተያዩ፣ ሲያወሩ፣ ሲበሉም ሆነ ሲተኙ… ብዙ የሚያስደስቱ ነገሮችን ያገኛሉ። የልባቸውን ያወራሉ፣ ይቀላለዳሉ፣ ይተሳሰባሉ፣ ይከባበራሉ። በጣም ሲቀራረቡ ግን፣ ቀናት ተንከባልለው ወራት ሲያልፉ ግን፣ መከባበር ይቀርና መቆጣጠር በቦታው ይተካል። መቀላለድ ይቀርና መናቆር ይመጣል። የልብ ማውራት ሳይሆን ድብብቆሽና ጥርጣሬ ይበቅላል። ይሄ ሁሉ የሚሆነው፣ የአንዳቸውም ፍቅር ሳይቀንስ ነው። አንዳቸውም ሌላውን አልበደሉ ይሆናል። ግን፣ እርስ በርስ ፍቅራቸውን የሚያጣጥሙበትና የሚገልፁበት ሁኔታ ተለውጧል። ያንን የፍቅር አኗኗር ትተው፣ በሌላ “ልማዳዊ” አኗኗር ቀይረውታል። አንዱ ሌላውን የሚያይበት መነፅር ተለውጧል። ጥሩ ጥሩው ሳይሆን ጉድለት ጉድለቱ ብቻ እንዲታያቸው ማድረግ ጀምረዋል። ይሄኔ፣ የፍቅር ህይወታቸውን መልሰው ለማደስ መፍትሄ ካልፈጠሩ በቀር፣ አልያም የደነዘዘውን ሕይወት እንደእጣ ፈንታ በፀጋ ካልተቀበሉ በቀር፣ ደጅ ደጁን፣ ወጪ ወራጁን መመልከት መጀመራቸው አይቀርም።

5. አዳራቸው እንደ ቀድሞው አጓጊነቱ ሲያቆም ሲጀመር የነበረው ፍቅር ሲደበዝዝ፣ የአልጋ ቆይታቸውም እንደ ድሮው አጓጊነቱ እየቀረ ሲሄድ፣ መፍትሄ ያስፈልገዋል - ፍቅራቸውን ለማንቃትና ለማደስ፣ አልጋቸውን ለማነቃነቅና ለመፈንደቅ። ይሄ ቀላል አይደለም። በፍቅር ወይም በትዳር አንድ አመት ከቆዩ በኋላ፣ ግንኙነታቸው እንደ አጀማመራቸው አጓጊ እንዲሆን ማድረግ እንደሚያስፈልግ ያምኑበታል? ድሮ እሷ እሱን፣ እሱ ደግሞ እሷን ለመማረክ ነበር የሚያስቡትና የሚጥሩት። ከአመት በኋላ ግን ሃሳብና ጥረታቸው፣ አንዱ ሌላውን ለመቆጣጠር ነው - እንከን ፍለጋ። ይህንን ወደ ቀድሞው ትክክለኛ የፍቅር ግንኙነት መመለስ እንዳለባቸው ያምኑበታል? ካላመኑበት፣ የደነዘዘውን ፍቅር ማንቃትና የቀዘቀዘውን መኝታ ቤት ማሞቅ አይችሉም። ይሄኔ፣ ፍንደቃ እየናፈቃቸው ሌላ ወንድ ማሰብ የሚጀምሩና ወዲህ ወዲያ ጎራ የሚሉ ይኖራሉ።

እዚህ ፍትህ ካጣን ወደ ዓለምአቀፉ ፍ/ቤት እንሄዳለን 20ሺ ሰው ሲፈናቀል አላውቅም ማለት ተቀባይነት የለውም በቅርቡ የመላ ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እና ሠማያዊ ፓርቲ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በአማራ ተወላጆች ላይ የደረሠውን መፈናቀል አስመልክቶ ድርጊቱን በፈፀሙት የመንግስት ባለስልጣናት እና ተቋማት ላይ ክስ ለመመስረት መዘጋጀታቸውን ገልፀዋል፡፡ በዋናነት የክሡ መነሻ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ የደረሠው መፈናቀል ይሁን እንጂ ከአመት በፊት በደቡብ ክልል ጉራፈርዳ ወረዳ የደረሠው መፈናቀልና ያስከተለው ጉዳትም በክሡ እንደሚካተት ፓርቲዎቹ ተናግረዋል፡፡

ማስረጃዎችን አሠባስቦ በማቀናጀት ሃገር ውስጥ ለሚገኙ ፍርድ ቤቶች ክስ በመመስረት በኩል ደግሞ የቀድሞው የቅንጅት አመራር አባልና በአሁን ሠአት ከማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት አባልነት ተገልለው በአለማቀፍ የህግ ባለሙያነት በመስራት ላይ የሚገኙት ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማርያም እንደሚሳተፉ ታውቋል፡፡ በክሱ አቀራረብና ባህሪ እንዲሁም ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያምን በቢሮአቸው አነጋግሯቸዋል፡፡ የክሡ ሂደት ምን ላይ ደረሠ? በሠማያዊ ፓርቲና በመኢአድ አነሣሽነት ነው ክሡ ሊመሠረት የታሠበው፡፡ ነገር ግን እስካሁን ክሡ አልተጀመረም፡፡ ማስረጃ ሠብስበን ከተጐዱት ሠዎች የውክልና ስልጣን ወስደን ወደ ስራው እንገባለን፡፡

አሁን ግን ገና ነው፤ የውክልና ስልጣኑም አልተዘጋጀም፡፡ በአካባቢው ያሉ ሠዎችን ማግኘት ያስፈልጋል፡፡ ስራው አሁን በውል ተጀመረ ማለት ባይቻልም በቅርቡ ሠዎች ወደዚያው ሄደው የተጐዱና የተፈናቀሉ ሠዎችን በመጠየቅና የደረሠባቸውን ጉዳት በማየት መረጃ እያሠባሠቡ ነው፡፡ ክሡን የምንመሠርተው ከዚያ በኋላ ይሆናል ማለት ነው፡፡ መጀመሪያ እንደሚታወቀው መረጃውን ማሠባሠብ ያስፈልጋል፡፡ በግልፅ ህግ መጣሡን በደንብ ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ እነዚህ ከተሟሉ በኋላ በቀጥታ ወደ ክሡ እንሄዳለን፡፡ መጀመሪያ የሠዎቹን ውክልና ሣታገኙ እንዴት ለመክሠስ እየተዘጋጃችሁ መሆኑን ገለፃችሁ?

መጀመሪያ ውክልናውን ማግኘታችሁን ማረጋገጥ አልነበረባችሁም? እንግዲህ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት ይዘን የምንቀርበው በሁለት አይነት ነው፡፡ የወንጀልም የፍትሃ ብሄር ጉዳይም አለው፡፡ የወንጀል ጉዳይን በተመለከተ ማንኛውም ሠው እንደተጐጂው ሆኖ ለፍትህ አካል አቤት ብሎ፣ ፖሊሶች ጉዳዩን ከመረመሩና ማስረጃውን ካጠናቀሩ በኋላ ወደ አቃቤ ህግ ይመሩታል፡፡ አቃቤ ህግ ክስ ይመሠርታል ወይንም በቂ ማስረጃ የለኝም፤ ክስ አልመሠርትም ብሎ ሊተወው ይችላል፡፡ በቂ ማስረጃ ካለ ደግሞ ክስ መስርቶ ፍርድ ቤት ይቀርባል፡፡ በሁለተኛ ደረጃ በቀጥታ እኛ የምንሣተፍበት ደግሞ አለ። እነዚህ ሠዎች ከቤታቸው ተፈናቅለዋል፤ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፣ የንብረት መውደም ደርሶባቸዋል፣ ጤናቸው ታውኳል፣ ብዙ አይነት ጉዳት ነው የገጠማቸው፡፡ ያ ሁሉ በገንዘብ ተሠልቶ የሚገባቸውን ካሣ፣ ተጠያቂ የመንግስት አካላት እንዲከፍሉ ነው የሚደረገው፡፡ መኢአድና ሠማያዊ ፓርቲ ከተጐጂዎች መካከል በርካቶቹን ጠይቀው ፈቃደኝነታቸውን አረጋግጠዋል፡፡ የውክልና ስልጣን ከዚያ በኋላ ይመጣል ማለት ነው፡፡

ክሱ በዚህ አገር ያልተለመደ ዓይነት ይሆናል ብለው ነበር፡፡ ሊያብራሩት ይችላሉ? ብዙ ሠው የያዘ ቡድን አንድ አይነት ጉዳት ከደረሠበት አንዱ ብቻ ከሶ ፍርድ ካገኘ ሌሎቹም ክስ ሣይመሠርቱ ከውጤቱ ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ። ይሄ በፈረንጆች “ክላስ አክሽን ሱት” ይባላል። ለምሣሌ የተፈናቀለው የአማራው ህብረተሠብ ተመሣሣይ በደል ነው የደረሠጁ እና ከእነሡ ውስጥ አንድ ሠው ብቻ ከሶ ፍርድ ካገኘ (ከረታ) ሌሎቹ የተጐዱ ሠዎች ክስ ሣይመሠርቱ፣ ለፍርድ ቤቱ ተመሣሣይ በደል እንደደረሠባቸው በማመልከት ብቻ ከፍርዱ እኩል ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ እንግዲህ ይህ በሃገራችን ብዙም አልተለመደም ግን እኛ ይህ አካሄድ በሃገራችን ይሠራል የሚለውን ልንፈትሸው ነው፡፡ ጉዳዩን በምሣሌ ማየት ይቻላል። አንድ መለያ ያለው የጥርስ ሣሙና ከገበያ ገዝተህ ሣሙናው የተመረዘ ቢሆንና ብዙ ሠዎች ተጠቅመውት ከተጐዱና አንድ ሠው ብቻ ክስ አቅርቦ ከኩባንያው ካሣ ካገኘ፣ ያንን የጥርስ ሣሙና ተጠቅመው ተጐጂ የሆኑ ሠዎች ከዚያ ፍርድ ውጤት ተጠቃሚ ይሆናሉ፡፡

እኛም በዚህ መልኩ ነው ክሣችንን የምንመሠርተው፡፡ በእያንዳንዱ ተጐጂ ስም ክስ የማቅረብ ሃሣቡ የለንም፡፡ ውክልናውን ከአንድ ሠው ብቻ ብታገኙም መክሠስ ትችላላችሁ ማለት ነው? አዎ በሚገባ ይቻላል፡፡ ውክልና የሠጠን ሠው ከፍርድ ሂደቱ በሚያገኘው ውጤት ተመሣሣይ ጉዳት ያጋጠማቸው ሁሉ ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ በዚህ መሠረት የአንድ ሠውም ውክልና የመንግስትን ተጠያቂ አካላት ለመክሠስ ያስችለናል፡፡ በአገራችን ይህን ለማድረግ የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ አለ?

በህገ መንግሥቱም አለ፣ በወንጀለኛ መቅጫውም በፍትሃ ብሄር ህጉም አለ፡፡ ለምሣሌ በህገ መንግስቱ ላይ “ክላስ አክሽን ሡት” የሚባለውን በተመለከተ የተጠቀሠ አለ፡፡ በህገ መንግስቱ አንቀፅ 37 ላይ “ማንኛውም ቡድን ወይም ተመሣሣይ ጥቅም ያላቸውን ሠዎች የሚወክል ግለሠብ ወይም የቡድን አባል የመጠየቅና የማግኘት መብት አለው” ይላል፡፡ እንግዲህ ማንኛውም ግለሠብ፣ ተመሣሣይ ጥቅም ያላቸው የቡድን አባላትን ወክሎ የመጠየቅና የማግኘት መብት አለው፡፡ እንግዲህ ያ የሚወክለው ግለሠብ ጠበቃ ሊሆን ይችላል፡፡

የቡድኑ አባል ደግሞ ከተበዳዮች አንዱ ሊሆን ይችላል፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች ከተጐጂዎች ውክልና የሚሠጣችሁ ሠው ብታጡስ…ምን ታደርጋላችሁ? የተሠሩ ወንጀሎችን ከአንዳንድ ሠዎች ጠይቀን፣ ያንን ሪፖርት ለፖሊስ እናቀርባለን። ፖሊሶች ለአቃቤ ህግ ያቀርባሉ፡፡ አቃቤ ህግ መረጃና ማስረጃዎችን መዝኖ ክስ ይመሠርታል፡፡ በፍትሃብሄር ካሣ ለማግኘት ግን እነሡ የውክልና ስልጣን ካልሠጡን አይሆንም፡፡ የወንጀሉ ክስ ግን እነሡ ውክልናውን ቢሠጡም ባይሠጡም ይቻላል፡፡ እኛ ሣንሆን በወንጀሉ አቃቤ ህግ ነው የሚከሠው፡፡ እኛ ግን እስካሁን የተረዳነው፣ ሠዎች የዚህ የፍትሃብሄር ክስን በተመለከተ በመኢአድና በሠማያዊ ፓርቲ አማካኝነት ክሡን ለማቅረብ ፍላጐት እንዳላቸው ነው፡፡ ዋነኛ ማስረጃችሁ ሊሆን የሚችለው ምንድን ነው? ዋነኛ ማስረጃ የሚሆኑት ተጐጂዎቹ ራሣቸው ናቸው፡፡ ለምስክርነት ይቀርባሉ፡፡ የመንግስት ባለስልጣናትም ለምስክርነት ይቀርባሉ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሣለኝ ይሄ ነገር ከባድ ወንጀል እንደሆነና መፈፀም እንደሌለበት፤ በአጥፊዎች ላይም መንግስት እርምጃ እንደሚወስድ አረጋግጠዋል፡፡ እሣቸውም በአካልም ሆነ ንግግራቸው በቪዲዮ ማስረጃነት ያለ ጥርጥር ይቀርባሉ፡፡ እርግጥ ማስረጃ በተለይ በተጐጂዎች ሲቀርብ የፍርሃቱ ነገር ሊኖር ይችላል፡፡ የክልሎቹ ባለስልጣናትም ሆኑ የፌደራሎቹ ሊያስፈራሯቸው ይችላሉ፡፡ ጥቃት የደረሠበት ሠው ደግሞ ይፈራል። አሁንም ጥቃት ውስጥ ያሉ ሠዎች ናቸውና ሊፈሩ ይችላሉ፡፡ ግን መኢአድና ሠማያዊ ፓርቲ እንዳረጋገጡልን በዚህ ጉዳይ ላይ ለመግፋት የሚፈልጉ ሠዎች አሉ፡፡ አንዱ የክሱ ጭብጥ “ዘር ማጥፋት” የሚል መሆኑን በሠጣችሁት መግለጫ ላይ ጠቅሳችኋል። ዘር ማጥፋት ሲባል ምንድን ነው? ዘር ማጥፋት በሚለው ክስ ለማቅረብ የሚያስችላችሁ የህግ ማዕቀፍ ይኖራል? ሁለት አይነት ወንጀሎች ናቸው፡፡ የዘር ማጥፋት የሚለው አንዱን ብሄረሠብ ወይም ዘር በከፊልም ሆነ ሙሉ ለሙሉ ለማጥፋት በማቀድ፣ በማሠብ ጥቃት መፈፀም ማለት ነው፡፡ ያን ጥቃት መፈፀም እንግዲህ ዘር ማጥፋት ሊሆን ይችላል። ዘር ማጥፋት (ዲፖርቴሽን) ሊሆን ይችላል፣ ማፈናቀልም ሊሆን ይችላል፣ ልጆች እንዳይወልዱና የዘር መተካካቱ እንዳይቀጥል ማድረግም ሊሆን ይችላል፡፡

ይሄ እንግዲህ በሠው ዘር ላይ የሚሠራ ወንጀል ነው - ጀኖሣይድ ወይም የዘር ማጥፋት ወንጀል ነው። አሁን እኛ እንደምንገምተው አማሮችን ከየክልሉ የማባረሩና የማፈናቀሉ ነገር ቆይቷል፡፡ ከበደኖ ጀምሮ አርባጉጉ፣ ጉራፈርዳ አሁን ደግሞ ቤንሻንጉል… ሌሎችም አሉ፡፡ ይሄ ቢደረግም የአማራን ዘር በከፊልም ሆነ በሙሉ ለማጥፋት ታቅዶ የሚደረግ ነው ወይ ለሚለው ማስረጃ የለንም፡፡ እነዚህ ሠዎች ለመፈናቀላቸው ከቦታ ቦታ መነቀላቸው፣ ንብረታቸውን ማጣታቸው፣ በአካላቸው ላይ ጉዳት መድረሡን እናውቃለን፤ ማስረጃውም አለ። እንግዲህ የዘር ማጥፋት ሣይሆን የዘር ማጥፋት ወንጀል የምንለው ከነበሩበት አካባቢ በዘራቸው ምክንያት ከተፈናቀሉ ነው፡፡ አንድ ሠው በዘሩ፣ በሃይማኖቱ ወይም በሚናገረው ቋንቋ ምክንያት ጉዳት ከደረሠበት በሠው ዘር ላይ የሚሠራ ወንጀል ነው፡፡ አሁን ሠዎች በአማራነታቸው፣ በዘራቸው በተቀነባበረ መልክ ለብዙ ጊዜ የዘር ማጥፋት ወንጀል በዚህ መልኩ ተፈፅሞባቸዋል፡፡

በአካባቢው አንድ ዘር ብቻ እንዲኖር ካለ ፍላጎት፣ እነዚህ ዘሮች (አማሮች)ከሚኖሩበት ተፈናቅለዋል፡፡ እና ይሄ ዘር ማጥፋት ይባላል፡፡ ሁለተኛው የዘር ማጥፋት ወንጀል የሚጀምረው አንድ ሠው በሃይማኖቱ፣ በዘሩ ምክንያት በተቀነባበረ መልኩ በሠፊው ግድያ፣ መፈናቀል፣ የመሣሠሉ ነገሮች ከተፈፀሙበት ነው። ሁለቱም በጣም ከባድ ወንጀሎች ናቸው፡፡ በአለማቀፍ ህግ መሠረትም በተመሣሣይ የወንጀል ፈርጅ ነው የሚቀመጡት፡፡ ተመሣሣይ ቅጣት ያስከትላሉ፡፡ እኛ አሁን በኢትዮጵያ የተፈፀመው ወንጀል የዘር ማጥፋት ነው ብለን ደፍረን ባንወጣም፣ የዘር ማጥፋት ወንጀል ለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ በተለይ በአማራዎች ላይ ያነጣጠረ ነው፡፡ እኔ በአማርኛ ተናጋሪዎች ላይ የሚለውን አልቀበለውም፡፡ ምክንያቱም ሁላችንም አማርኛ ተናጋሪዎች ነን፡፡ በዚህ መሠረት አማራዎች ለረጅም ጊዜያት በተቀነባበረ መልኩ ከተቀመጡበት ሲፈናቀሉ ኖረዋል፡፡ ይህ ደግሞ በአለማቀፍ ህግም በሃገራችን የወንጀለኛ መቅጫ ህግም ወንጀል ነው፡፡

“በዘር ማጥፋት” ወንጀል መክሠስ የሚያስችላችሁ የህግ ማዕቀፎች አሉ? በደንብ አሉ፡፡

አሁን እኔ እንዳጋጣሚ የወንጀለኛ መቅጫ ህጉን አልያዝኩትም እንጂ ይሄን የሚቀጣ አንቀፅ አለ፡፡ እንደውም የደርግ ባለስልጣናት በዘር ማጥፋት ወንጀል ተከሠው ነበር፡፡ በእርግጥ ክሡ ትክክል ነበር ማለት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም ወንጀሉ ያነጣጠረው የፖለቲካ ቡድንን መሠረት አድርጐ ነበር፡፡ የዘር ማጥፋት ወንጀል የምንለው በሃይማኖት፣ በቋንቋ እና በዘር ሲሆን ብቻ ነው፡፡ በፖለቲካ እምነት መሆን የለበትም፡፡ ከዚህ አንፃር በህጋችን የዘር ማጥፋት ምንድን ነው የሚለው በግልፅ ተቀምጧል፡፡ የዘር ማጥፋት ወንጀል ማለት በሠው ዘር ላይ የሚፈፀም ወንጀል ወይም ማፈናቀል መሆኑ በህጋችን በግልፅ ተቀምጧል፡፡ የደርግ ባለስልጣናትም የተከሠሡት አንደኛ በዘር ማጥፋት፣ ሁለተኛ ደግሞ በዘር ማጥራት፣ ሶስተኛ ደግሞ በተራ ግድያ ተጠያቂ ሆነው ነበር፡፡ ጉዳዩ ከመሬት እና ከይዞታ ጋር የተገናኘ እንጂ የዘር ጥላቻ አይደለም የሚሉ አካላት አሉ? የዘር ጥላቻ ሆነም አልሆነም ዋናው ነገር መፈናቀላቸው ነው፡፡

ከቤት ንብረታቸው ብዙ ጊዜ የኖሩበትን ቦታ በግድ ማስለቀቅ ጥላቻ ቢኖረውም ባይኖረውም ወንጀል መሆኑ አይቀርም። በህገ መንግስቱ አንቀፅ 32፣ የመዘዋወር መብትን በተመለከተ “ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በህጋዊ መንገድ በሃገሪቱ ውስጥ የሚገኝ የውጭ ዜጋ በመረጠው የሃገሪቱ አካባቢ የመዘዋወርና የመኖሪያ ቦታ የመመስረት እንዲሁም በፈለገው ጊዜ ከሃገር የመውጣት ነፃነት አለው” ይላል፡፡ ደግሞ ለኢትዮጵያውያን ብቻ አይደለም፤ ለውጭ ዜጐችም ህጋዊ በሆነ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ ከገቡ በፈለጉበት መኖርና ወደፈለጉበት መንቀሣቀስ ይችላሉ፡፡ ለውጭ ሃገር ሠዎች እንኳ መብቱ ተሠጥቷል፡፡ ማንኛውም ዜጋ በየትኛውም የሃገሪቱ ክልል ላይ መኖርና ሠርቶ መለወጥ ይችላል ማለት ነው፡፡ እርግጥ አንዳንድ የተከለሉ አካባቢዎች አሉ፡- እንደጦር ሠፈር፣ ቤተመንግስት፣ የእንስሣት ፓርኮች የመሣሠሉት … እዚያ ልግባ ቢሉም ልኑር ማለት አይቻልም፡፡ በተረፈ ግን ዘሩም ሆነ ቋንቋው ምንም ቢሆን የፈለገበት ቦታ ሄዶ የመኖር መብት እንዳለው ህገ መንግስቱ በግልፅ ይደነግጋል፡፡

አንድ ጊዜ ከጉራፈርዳ ስለተፈናቀሉ ሠዎች ጉዳይ በፓርላማው ጥያቄ ቀርቦ ነበር፡፡ ጠ/ሚ መለስ በወቅቱ እነዚህ ሠዎች ደን ይመነጥሩ ነበር ብለው መልስ ሠጡ፡፡ የዚህ አንደምታው የተወሠደው እርምጃ ትክክል ነው የሚል ነው፡፡ እነዚህ ሠዎች ዛፍ ይቆርጡ እንደሆነ ህግ ካለ በህግ ይጠየቃሉ፤ ጫካ ይመነጥሩ እንደሆነም እንደዚያው፡፡ አሁን አቶ ኃይለ ማርያም የተለየ መልስ ሰጥተዋል፡፡ አቶ መለስ ፍፁም ህጋዊ አድርገው የቆጠሩትን አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ህገወጥ መሆኑንና መደረግ እንደሌለበት፤ መንግስትም እርምጃ እንደሚወስድ ገልፀዋል፡፡ ከአካባቢው አማራዎች ብቻ ሣይሆኑ ኦሮሞዎችም የመፈናቀል እጣ ገጥሟቸዋል ተብሏል።

ይሄንንስ እንዴት ነው የሚያዩት? በእርግጥ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ብለውታል፡፡ ነገር ግን በአማራዎች ላይ እየደረሰ ያለው መጠነ ሰፊ ነው፡፡ የቆየም ነው፡፡ በግብታዊነት ሰዎችን ማፈናቀል በፕላን የተሠራ የቆየ ድርጊት ነው። ሊፈፀም የማይገባው ወንጀል ነው የተፈፀመው፡፡ አሁን ክስ እንመሠርትባቸዋለን ከምትሏቸው ሃላፊዎች መካከል በህዝብ ተመርጠው የምክር ቤት አባላት የሆኑ አሉ፡፡ የእነዚህን ሰዎች ያለመከሰስ መብት ከግምት አስገብታችኋል? እንግዲህ አንድ የህዝብ ተወካይ ሊከሰስ የሚችለው ፓርላማው የዛን ሰው ያለመከሰስ መብት ሲሰርዝ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ምናልባት እንደዚህ አይነት ያለመከሰስ መብት እንዳላቸውና እንደሌላቸው ማጣራት ይኖርብናል፡፡

ካላቸው ፓርላማ ወይም ምክር ቤት በዚህ በዚህ ወንጀል ምክንያት ያለመከሰስ መብታቸውን መሰረዝ አለበት ብለን ማመልከት አለብን፡፡ ያኔ ምክር ቤቱ ፍቃድ ከሰጠና ከሠረዘ ይከሰሳሉ ማለት ነው፡፡ በእርግጥ ይህ ሂደት ካልታለፈ መክሰስ አይቻልም። የትኛውም ፓርላማ እንዲህ አይነት ከባድና ግልጽ ወንጀል በሚፈፀምበት ጊዜ ያንን ያለመከሰስ መብትን ያሠርዛል፡፡ እኛም የትኛው ነው ያለመከሰስ መብት ያለው የሚለውን ካጣራን በኋላ፣ አስቀድመን ለምክር ቤቶቹ አመልክተን መብቱ እንዲሠረዝ እንጠይቃለን፡፡ ክሳችሁ የሚያካትተው በየትኛው ጊዜ እና በየትኛው የሃገሪቱ ክልል የተፈፀሙትን ወንጀሎች ነው? አሁን ለጊዜው ቤንሻንጉል እና ጉራፈርዳ የተከሰተውን ነው ያሰብነው፡፡ ሌላው በቀጠሩን ፓርቲዎች የሚወሰን ነው፡፡ በእርግጥ ድርጊቱ በብዙ ቦታዎች የተፈፀመ ነው፡፡ ግን ክስ የሚመሠረተው አንድም እንዲህ አይነት ድርጊት ለወደፊቱ እንዳይደገም ማስተማሪያ እንዲሆን ነው፡፡

ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲቆም ለማድረግ ነው፡፡ ክስ ብዙ ጊዜ የሚመሠረተው ከክሱ ውጤት ሌላው እንዲማርና ተበዳዩ እንዲካስ ነው፡፡ ክሱ በአገር ውስጥ ፍ/ቤቶች ተቀባይነት ካጣ ወደ አለማቀፍ ፍ/ቤት እንሄዳለን ብላችኋል፡፡ ኢትዮጵያ የአለማቀፍ ፍርድ ቤት አባል ሳትሆን ክስ መመስረት ይቻላል? የክሱ አንዱና ዋናው አላማ ይህ ድርጊት ከእንግዲህ በማንም ኢትዮጵያዊ ላይ እንዳይፈፀም ነው፡፡ ሌላው ደግሞ ይሄ ክስ እዚህ ሊሳካልን ባይችል በአለማቀፍ ፍርድ ቤት ጉዳዩን የሚከታተሉ ኢትዮጵያውያን አሉ፡፡ ለነዚህ ኢትዮጵያውያን የዳበረ ማስረጃ ለመስጠት ነው፡፡ በአለማቀፍ ፍርድ ቤት ክስ ለመመስረት መጀመርያ የአገር ውስጡን ማጣራት አለብን፡፡ በአገር ውስጥ ፍትህ ከተነፈግን ወይንም የአገሩ መንግስት ሊሰማ ካልፈለገ ጉዳዩ ወደ አለማቀፍ ፍርድ ቤት ሊያመራ ይችላል፡፡ በፊት እንደተባለው ኢትዮጵያ የአለማቀፍ ፍርድ ቤት አባል አይደለችም፡፡ ለምን እንዳልሆነች እኔ በእውነት ሊገባኝ አይችልም፡፡ ምክንያቱም ከአፄ ኃይለስላሴ ጀምሮ በደርግም ዘመን ኢትዮጵያ አለማቀፍ ስምምነቶችን በመቀበል ንቁ ተሣትፎ ነበራት፡፡ የተባበሩት መንግስታትን ቻርተር ለመፈረም እኮ የመጀመሪያዎቹ ጥቁር ህዝቦች እኛ ነን፡፡

ኢህአዴግ ለምን ሊቀበለው እንዳልፈለገ አይገባኝም፡፡ ሆኖም ግን አገር ውስጥ ከባድ ወንጀል በሚፈፀምበት ጊዜ አባል አይደለችም፤ ስለዚህ አትከሰስም ተብሎ አይታለፍም፡፡ አባል ከሆነ በቀጥታ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩ እንዲመረመር ያዛል፤ ተመርምሮ ክስ ይቀርብበታል። እንደ ኢትዮጵያ የፍርድ ቤቱ አባል ካልሆነ፣ ጉዳዩ ለተባበሩት መንግስታት የፀጥታ ምክር ቤት ቀርቦ፣ የፀጥታው ምክር ቤት ፍርድ ቤቱ ምርመራ እንዲያደርግና ክስ እንዲመሠርት ሊያደርግ ይችላል፡፡ አሁን ኢትዮጵያኖች የሚንቀሳቀሱበት መንገድ የተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት በጉዳዩ እጁን ያስገባና የአለማቀፍ ፍርድ ቤትን ምርመራ እንዲያደርግ ያዛል (ክስ እንዲመሠረት ሊያዘው አይችልም) ጉዳዩ ወደ ወንጀል ከመራ፣ ክሱ በተጐጂዎች ወይም ወኪሎች ሊቀርብ ይችላል፡፡ ኢትዮጵያ የአለማቀፍ ፍርድ ቤት አባል አለመሆኗ፣ ወንጀል ከተሰራ ከክስ ሊያስመልጣት አይችልም፡፡ እዚህ ፍትህ አለመኖሩ ከተረጋገጠ፣ በዚህ መልኩ ወደ አለማቀፉ ፍርድ ቤት እንሄዳለን፡፡

ክሱን የምትመሠርቱት ግለሰብ ባለስልጣናት ላይ ነው ወይስ ተቋማቱን ነው የምትከሱት?

ለምሣሌ ፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴርን እንደመስሪያ ቤት ነው ወይስ ሚኒስትሩን ነው? እኛ ተቋማቱን ነው የምንከሰው፡፡ እርግጥ ለተቋማቱ ተጠሪዎች አሉ፡፡ ተከሳሾች የሚሆኑት ደግሞ የክልል አስተዳዳሪዎች ብቻ አይደሉም። እንደውም ከፌደራል ጉዳይ መስሪያ ቤት ይጀምራል፡፡ እርግጥ አቶ ኃይለማርያም፤ ይሄ በኪራይ ሰብሳቢዎች፣ በሌቦች የተፈፀመ ነገር ነው፤ መንግስት አያውቀውም ብለው ነው መግለጫ የሰጡት፡፡ ይሄ ተአማኒነትና ተቀባይነት የሌለው ነገር ነው፡፡ ሃያ ሺህ ሰው ሲባረር አላውቅም ማለት የማንን ጐፈሬ ሲያበጥሩ ነበር ያስብላል፡፡ ፌደራል መንግስት ማወቅ ነበረበት፤ ባያውቅም የግዴታ ማወቅ ነበረበት። አላወቅሁም ካለም አለማወቅ ከተጠያቂነት ስለማያድን ማወቅ ይገባው ነበር፡፡ ባያውቅ እንኳ ማወቅ ስለሚገባው በህግ ይጠየቃል። በዚህ መሠረት ክሳችን ከፌደራል መንግስት ይጀምራል፡፡ ወደ ክልል አስተዳደሮች ይሄዳል። ከዚያም ወደ ወረዳ፣ ፌዴራል ፖሊስ እንዲሁም ከጉዳዩ ጋር ወደተነካኩት አካላት ይሄዳል፡፡

እንግዲህ ክሱ እንደገለጽኩት ገና አልተረቀቀም፤ በመነጋገርና መረጃ በማሰባሰብ ላይ ነው ያለነው፡፡ ሀገር ውስጥ ካሉት ፍርድ ቤቶች ምን ውጤት ትጠብቃላችሁ? የመጨረሻ ውጤቱስ ምን ይሆናል ብላችሁ ነው የምታስቡት? እኛ መቸም የምንጠብቀው ህጉ ይተገበራል ብለን ነው፡፡ የወንጀል ህጉም ሆነ ሌሎች ህጐች ይተገበራሉ ብለን ነው የምንጠብቀው፤ ግን የሚሆነው ሌላ ሊሆን ይችላል፡፡ ክሳችንን ውድቅ ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡ ፍርድ ቤቱ ክሱን ተቀብሎ ካሣ የሚያስከፍል ወንጀል አላገኘንም ብሎ ክሱን ሊዘጋው ይችላል፡፡ ሆኖም ግን እኛ አስቀድሜ እንዳልኩት ይሄን ክስ ያነሳነው በአለማቀፍ ችሎት የቀረበ እንደሆነ፣ መጀመሪያ በሃገር ውስጥ ፍትህ ለማግኘት ተሞክሯል ወይ ተብሎ ስለሚጠየቅ ነው።

ፍትህ ለማግኘት ሞክሬ ፍትህ አላገኘሁም ወይም መንግስት ክሱን ለመቀበል ፈቃደኛ አልሆነም ካልክ፣ አለማቀፍ ፍርድ ቤት ጉዳዩን ሊቀበለው ይችላል፡፡ ለዚህ ድጋፍ እንዲሆን ነው ይህን ክስ የምንመሠርተው፡፡ በእውነት ፍትህ በሀገር ውስጥ አግኝተን ለእያንዳንዱ ካሣ ቢከፈል በጣም እገረማለሁ፤ እደነቃለሁ፡፡ ቢሆን ግን እሰየው ነው። ጉዳዩን እንዴት እንደሚያመልጡት አላውቅም፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ራሳቸው በደል ተፈጽሟል፣ ህግ ተጥሷል ካሉ እንዲሁ ዝም ብሎ ተነግሮ የሚታለፍ አይደለም፡፡ በደል ከተፈፀመ የግድ ለተበዳዩ የሚሆን ካሣ ይከተላል፡፡ ይሄ ሊሆን ግድ ነው፡፡ ይህ ባይሆን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ራሳቸው ተጠያቂ ይሆኑበታል፡፡ ወንጀል መሆኑን እያወቁ፣ በደል መፈፀሙን እያመኑ ዝም ብለው ካለፉት፣ ነገ በራሳቸው ቃል ተጠያቂ ይሆኑበታል፡፡

ወንጀልን ለመከላከል በሚታጠቁት መሳሪያ የግድያ ወንጀል የሚፈፅሙ የፖሊስ አባላት በርካታ መሆናቸውንና በአዲስ አበባ ብቻ ባለፉት ሰባት አመታት ከእስር በላይ በፖሊስ አባላት የተፈፀሙ ግድያዎች እንዳሉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ፖሊስ በበኩሉ፣ አብዛኞቹ የፖሊስ አባላት ህግ ለማስከበር፣ ወንጀልን ለመከላከልና ፍትህን ለማስፈፀም ጠንክረው የሚሰሩ መሆናቸውን ገልፆ፣ የፖሊስን አቋም በተቃረነ ወንጀል የሚፈፅሙ አባላትን በአገሪቱ ህግ መሰረት ለፍ/ቤት በማቅረብ ተገቢውን እርምጃ እየወሰደ መቆየቱን ይገልጻል፡፡ የፖሊስ አባላት ፅኑ የፍትህ አቋም እንዲኖራቸው፣ ሥነ ስርዓት አክባሪነታቸዉ እንዲጠናከር፣ እንዲሁም ሥነ ስርዓት የሚጥሱትም ተገቢውን ቅጣት እንዲያገኙ የተለያዩ የመተዳደሪያ ደንቦች ተግባራዊ እየተደረጉ መቆየታቸውን ፖሊስ ይገልፃል፡፡

የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የሥነ ስርዓት ደንቡን ይበልጥ ለማሻሻል የዲሲፕሊን መመሪያና የቅጣት አወሳሰን ሰነድ አዘጋጅቶ እንዳጠናቀቀ ተጠቁሟል፡፡ በባህር ዳር ያጋጠመውን አይነት አሰቃቂና አሳዛኝ ድርጊት ዳግመኛ እንዳይከሰት ለመከላከል፣ በፖሊስ አባላት የሚፈፀሙ የወንጀል ድርጊቶችና የመፍትሄ እርምጃዎች ላይ ውይይት እንዲፈጠር ለማበረታተት በማሰብ ከአዲስ አበባ ዙሪያ ከፖሊስና ከፍ/ቤት ያሰባሰብናቸውን መረጃዎች አቅርበናል፡፡ ከ2 ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ ተፈርዶባቸዋል ባልደረባውን በ18 ጥይት መትቶ የገደለው ፖሊስ ጉዳይ በፍ/ቤት እየታየ ነው የአዲስ አበባ ፖሊስ አባል የሆነው የ20 ዓመቱ ኮሎኔል አወል አብዱልቃድር መስከረም 13 ቀን 1999 ዓ.ም ቦሌ ክ/ከተማ ቀበሌ 15 ክልል አቶ ሚካኤል ተሻለ የተባለ ግለሰብን ከመኪናው ያስወረደው “ትላንት ዘበኛህ የቤት ሠራተኛህን ደብድቦ ከያዝነው በኋላ አምልጦናል፤ እንፈልገዋለን” በማለት ነው፡፡ ከፖሊስ በተገኘ መረጃ መሰረት፤ ከተወሰነ የንግግር ልውውጥ በኋላ ኮሎኔል አወል በታጠቀው ክላሺንኮቭ ጠብመንጃ ግለሰቡን ጭንቅላቱ ላይ በመምታት በመግደሉ በከባድ ሰው የመግደል ወንጀል ተከስሷል፡፡ ጉዳዩን የመረመረው ፍ/ቤትም ግንቦት 7 ቀን 1999 ዓ.ም በዋለው ችሎት በዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት እንዲቀጣ በይኗል፡፡

ኮሎኔል አለሙ አያኖ በጉለሌ ክ/ከተማ፣ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ፊት ለፊት፣ ተስፋዬ ታደለ የተባለ ግለሰብ “ወደ ህግ ቦታ አልሄድም” አለኝ በሚል ምክንያት ለስራ በተሰጠው ክላሽንኮቭ ጀርባው ላይ በመምታት ስለገደለው ተከሶ ፍ/ቤት የቀረበው በጥር 2000 ዓ.ም ነበር፡፡ ሰኔ 18 ቀን 2000 ዓ.ም ፍ/ቤቱ በዋለው ችሎት ተከሳሹ በ10 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣና ለሁለት ዓመት ከህዝባዊ ጥቅማጥቅም እንዲታገድ ወስኗል፡፡ የ23 ዓመቱ ኮንስታብል ሱልጣን ጀማል አሁን የሚገኘው ወህኒ ቤት ነው፡፡ የዛሬ ሰባት ዓመት ከስራ ባልደረባው ኰንስታብል አንሰ ሼህ አብደላ ጋር በተፈጠረ ጊዜያዊ ጠብ ምክንያት ለጥበቃ ሥራ በተሰጠው ክላሽንኮቭ ጠብመንጃ ግለሰቡን ተኩሶ በመግደሉ ፍ/ቤት በ15 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣ ወስኖበታል፡፡ የፌደራል ፖሊስ አባል የሆነው የ34 ዓመቱ ምክትል ሳጅን ደበሽ ታረቀኝም ወህኒ የገባው የስራ ባልደረባውን መግደሉ በፍ/ቤት ተረጋግጦበት ነው፡፡

ግለሰቡ፤ ኮንስታብል መሶር ዊይሰን የተባለውን ባልደረባውን አድርጐት በነበረው የወታደር ከስክስ ጫማ ጭንቅላቱ ላይ በመምታትና በመርገጥ ጉዳት ያደረሰበት መስከረም 17 ቀን 2000 ዓ.ም ሲሆን ለጥቂት ቀናት ህክምና ሲከታተል ቆይቶ ህይወቱ ሊያልፍ ችሏል፡፡ ፍ/ቤቱ የካቲት 13 ቀን 2001 ዓ.ም በዋለው ችሎት ተከሳሹ በ6 ዓመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣ በይኖበታል፡፡ የፌደራል ፖሊስ አባሉ ኮሎኔል ኡፋይሳ ጉንዲስ ሐምሌ 3 ቀን 2004 ዓ.ም እስራኤል ኤምባሲ አካባቢ በጥበቃ ላይ የነበረውን ባልደረባውን በ18 ጥይት መትቶ በመግደል ተጠርጥሮ ክስ የተመሰረተበት ሲሆን ጉዳዩ በፍ/ቤት በመታየት ላይ እንደሚገኝ ከፖሊስ የተገኘ መረጃ ይጠቁማል፡፡ ኮሎኔል ብዟየሁ ግርማም፤ “ሰው በመግደል ወንጀል ተጠርጥሮ ጉዳዩ በፍ/ቤት እየታየ ይገኛል፡፡ ኮሎኔሉ ሌሊት በሥራ ላይ እያለ ከአዲስ አበባ ወደ ድሬዳዋ በመጓዝ ላይ ያለ የነበረ ሚኒባስን እንዲቆም ይጠይቃል፡፡ ሹፌሩ መኪናውን ለማቆም በማቀዝቀዝ ላይ ሳለ ኮሎኔሉ ባልታወቀ ምክንያት ተኩስ በመክፈቱ የሚኒባሱ ሹፌር ህይወት ማለፉን የክስ መዝገቡ ያመለክታል፡፡

ኮሎኔል ብዟየሁ በተጠረጠረበት የሰው መግደል ወንጀል ክስ ተመስርቶበት ጉዳዩ በፍርድ ሂደት ላይ ሲሆን ድርጊቱን መፈፀሙን እንዳመነ የፖሊስ መረጃ ይጠቁማል፡፡ “ድርጊቱን የፈፀምኩት ሰይጣን አሳስቶኝ ነው” ብሏል - ለፍ/ቤት በሰጠው ቃል፡፡ የ22 ዓመቱ ኮሎኔል ሃብታሙ ካሣሁን ጌታሁን፤ እስር ቤት የገባው በግድያ ሳይሆን በዘረፋ ወንጀል ተከሶ ነው፡፡ መስከረም 12 ቀን 2003 ዓ.ም ከቀኑ በ9 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ክ/ከተማ ልዩ ቦታው ዑመር ስመትር ት/ቤት አካባቢ ወ/ት ዘሃራ አብዱራህማንን በያዘው ሽጉጥ ሰደፍ ቀኝ ጉንጯ ላይ በመምታት ከጣላት በኋላ፣ ከቦርሳዋ ውስጥ 1.514566.55 የያዙ የባንክ ቼኮች እንዲሁም 755 ብር የሚያወጡ ልዩ ልዩ እቃዎች ወስዶ ሊያመልጥ ሲል እጅ ከፍንጅ ይያዛል፡፡ በፈፀመው ከባድ የውንብድና ወንጀል የተከሰሰው ግለሰቡ፤ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ ፍ/ቤት በ12 ዓመት ፅኑ እስራትና በ2ሺ ብር እንዲቀጣ ወስኗል፡፡

ኮሎኔል እዮብ ቀልሜሳ የዛሬ አራት ዓመት ሦስት የሥራ ባልደረቦቹ ላይ 18 ጥይቶችን በመተኮስ በፈፀመው የግድያ ሙከራ ተከስሶ ፍ/ቤቱ ጥፋተኝነቱን በማረጋገጡ ነው ወህኒ የወረደው - የ10 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈርዶበት፡፡ በእርግጥ ከዚህ ቀደምም ታስሮ ተፈቷል፡፡ በ1999 ዓ.ም በአደገኛ ቦዘኔነታቸው ከሚታወቁ ሁለት አባሪዎች ጋር ከሌሊቱ 6፡30 ላይ አንድ ግሮሰሪ ገብቶ ከአስተናጋጅ ላይ ገንዘብ በመውሰድና እቃዎችን በመሰባበር ክስ ተመስርቶበት ታስሮ ነበር፡፡ ከተፈታ በኋላ አንድ የስራ ባልደረባው በስብሰባ ላይ “ስራህ በሙሉ ከአንድ ፖሊስ የሚጠበቅ አይደለም፤ ሁልጊዜ እየታሰርክ ትፈታለህ፣ ከወንጀለኛ ጋር ነው የምትውለው” በማለት ከመጥፎ ምግባሩ እንዲመለሰ ይገመግመዋል፡፡ ኮሎኔል እዮብ ግን በስራው ከመፀፀት ይልቅ ቂም ይይዛል፡፡

ስብሰባው ሲጠናቀቅም “ለምሳ ተረኛ የግቢ ጥበቃ ነኝ” በማለት ክላሽንኮቭ ጠብመንጃና 30 ጥይት በመረከብ የገመገመውን ባልደረባውን ጨምሮ ሦስት የስራ ባልደረቦቹ ላይ 18 ጥይቶች በመተኮስ በፈፀመው የግድያ ሙከራ ተከስሶ ጥቅምት 4 ቀን 2001 ዓ.ም በ10 ዓመት ፅኑ እስራት እና በሁለት ዓመት ከህዝባዊ መብት እንዲታገድ ተወስኖበታል፡፡ የ25 ዓመቱ ረዳት ሳጅን አስሬ አየለ ባይዴ፤ ባለፈው ዓመት አንድ ግለሰብ በቁጥጥር ስር ለማዋል ከ20 በላይ የፖሊስ አባላት ጋር በመሆን ወደ መኖርያ ቤቱ ይሄዳል፡፡ ተፈላጊው እጁን ለመስጠት ፈቃደኛ ባለመሆኑ ፖሊሶች አጥር ዘለው ይገባሉ፡፡ ይሄኔ ግለሰቡ የፖሊስ አባላቱ ላይ ድንጋይ፣ ብርጭቆና ስለት መወርወር ይጀምራል፡፡ ረዳት ሳጅን አስሬ የፖሊስ ሙያ የሚጠይቀውን ጥበብ በመጠቀም ተጠርጣሪውን መያዝ ሲገባው በያዘው ክላሽ ጠብመንጃ ግለሰቡ ላይ በመተኮስ አንገቱ ላይ ይመታውና ወዲያው ህይወቱ ያልፋል፡፡

ሳጅን አስሬ አየለ ባይዴ፤ ህጋዊ መከላከልን ከመጠን በማሳለፍ በፈፀመው የግድያ ወንጀል ተከስሶ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ ፍ/ቤት በሁለት ዓመት ቀላል እስራት እንዲቀጣ ወስኗል፡፡ ከፖሊስ የተገኘ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ የፖሊስ አባላት በተለያዩ የግልና ሌሎች ያልታወቁ ችግሮች የተነሳ ራሳቸውን የሚያጠፉበት አጋጣሚዎችም አሉ - ብዙ ነው ባይባልም፡፡ በ1998 ዓ.ም አንድ ኮንስታብል በሚያድርበት ካምፕ ውስጥ በራሱ ክላሽንኮቭ ጠብመንጃ ደረቱ ላይ ሁለት ጊዜ በመተኮስ እራሱን በራሱ ያጠፉ ሲሆን በ2000 ዓ.ም ደግሞ በብሄራዊ ቤተመንግስት በጥበቃ ሥራ ላይ ተመድቦ የነበረ አንድ ምክትል ሥራ ላይ ተመድቦ የነበረ አንድ ምክትል የአስር አለቃ በራሱ መሳሪያ አንገቱ ሥር በመተኮስ ራሱን በራሱ አጥፍቷል-ከፖሊስ በተገኘ መረጃ፡፡