Administrator

Administrator

የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ቢል ክሊንተን ከዋይት ሃውስ ከወጡ ወዲህ ባለፉት 12 አመታት በተለያዩ ቦታዎች ንግግር በማቅረብ ብቻ 106 ሚሊዮን ዶላር ማግኘታቸው ሲኤንኤን ዘገበ፡፡ ቢል ክሊንተን በአንድ መድረክ ንግግር ለማቅረብ በአማካይ 200ሺ ዶላር ይከፈላቸዋል፡፡ የቀድሞው ፕሬዝዳንት በንግግር አዋቂነታቸው በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ተፈላጊ ናቸው፡፡ በናይጄርያ ሌጎስ በአንድ መድረክ የተከፈላቸው 700ሺ ዶላር በተመሳሳይ የስራ ድርሻ የተገኘ ትልቁ ክፍያ እንደሆነ ታውቋል፡፡

ቢል ክሊንተን በንግግር አዋቂነታቸው አምና ከፍተኛ ተፈላጊነት እንደነበራቸው የሚገልፀው ሲኤንኤን በመላው ዓለም በ73 መድረኮች በመስራት 17 ሚሊዮን ዶላር እንደተከፈላቸው ገልጿል። ቢሊ ክሊንተን 42ኛው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት የነበሩ ናቸው፡፡ በበጎ አድራጊነት፤ በንግግር አዋቂነት ፤ በዴሞክራት ፖለቲከኛነት እና በጥብቅና ሙያቸው ከፕሬዝዳንትነት ከወረዱ በኋላ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያላቸው ቢል ክሊንተን 80 ሚሊዮን ዶላር ሃብት እንዳላቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡

ከኤሌክትሮኒክስ ሙዚቃ ዲጄዎች፣ ሆላንዳዊ ዲጄ ቲዬስቶ 75 ሚሊዮን ዶላር መሪነቱን እንደያዘ ሴለብሪቲ ኔትዎርዝ ገለፀ። ለግሉ በገዛው ጄት አውሮፕላን በመላው ዓለም በመዘዋወር የሚሰራው የ44 ዓመቱ ዲጄ ቲዬስቶ፣ በአማካይ ለአንድ ምሽት ስራ እስከ 250ሺ ዶላር እየተከፈለው ባለፈው ዓመት ብቻ ሃያ ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝቷል። ቲዮስቶ፣ በሙዚቃ መሸጫ ሱቅ እየሰራና ፒዛ እየተላላከ ይኖር እንደነበር አስታውሶ፣ ዲጄነትን የጀመረ ጊዜ ባንድ ምሽት ሃምሳ ዶላር ብቻ ይከፈለው እንደነበር ገልጿል።

ከዲጄነት ጎን ለጎን፣ እንደ ሌሎቹ ዲጄዎች በሙዚቃ ፕሮዲውሰርነትና በአቀናባሪነት እየሰራ አምስት ሙሉ አልበሞችን እና ሶስት የሪሚክስ አልበሞችን ለገበያ አብቅቷል፡፡ ባንድ ምሽት በአማካይ ከ100ሺ እስከ 500ሺ ዶላር ከሚከፈላቸው ታዋቂ የኤሌክትሮኒክስ ሙዚቃ ዲጄዎች መካከል አንዳንዶቹ፣ የግል ጄት አውሮፕላንና ውድ ቪላ እየገዙ ለቅንጦት ኑሮ ገንዘባቸውን ሲያፈሱ ይታያሉ። ሴሌብሪቲ ኔትዎርዝ ባወጣው የዲጄዎች ደረጃ፣ ከሁለተኛ እስከ አምስተኛ የወጡት ከሃምሳ እስከ ስድሳ ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ሃብት ያላቸው ዲጄዎች ናቸው።

እናት ህፃን ልጇን አዝላ ከገበያ እየተመለሰች ነው፡፡ በዘንቢሏም እቤት ለሚጠብቋት ልጆቿ የሚሆን ሙዝ፣ ሸንኮራ አገዳና መሰል ቁሶች ይዛለች፡፡ የእናታቸውን ከገበያ መመለስ የተመለከቱ ህፃናት ልጆቿና ውሻቸው እናቲቱን ለመቀበል ወደ እሷ ሲሮጡ የሚያሳየው ሥዕል ዓይንን ጨምድዶ የሚይዝ ቅርፅ ነው፡፡ የግርማችን ፒ ኤል ሲ ሥራ አስኪያጅና የአክሲዮኑ አባል አቶ አንዷለም ግርማ “ከሁሉ በላይ ይኼ ምሥል ልቤን ይገዛዋል፡፡ ይህ ነገር የእኔም፣ የአንቺም የሁሉም ሰው እውነተኛ የህይወት ነፀብራቅ ነው” ይላሉ፡፡ ገበያ ሄዳ ሸንኮራና ሙዝ ለልጇ ይዛ ያልመጣች እናት አለች ብለው እንደማያምኑም አጫውተውኛል፡፡ ሌሎች ሥዕሎችም በብዛት ይታያሉ፡፡ በህንፃው ስር ባለው ሰፊ በር ወደ ውስጥ ሲዘልቁ ነው የቤቱን ተዓምራት መመልከት የሚጀምሩት፡፡ ገና ሲገቡ መሬት ላይ ባለው ሰፊ ባር መሀል ላይ ትልቋና ባለ ግርማ ሞገሷ ንስር፣ ክንፏን ዘርግታ ምንቃሯን ከፈት አድርጋ ይመለከታሉ፡፡

እሱን አይተው ሳይጠግቡ ንስሯ በተቀረፀችበት ፏፏቴ ዙሪያ የተደረደሩት የዝሆን ምስል ያላቸው ወንበሮች እንደገና ያስገርምዎታል፣ እዛው ላይ ቆመው ዞር ዞር እያሉ ግድግዳውን መቃኘት ሲጀምሩ ደግሞ “ለመሆኑ ይኼ ቤት ሆቴል ነው ወይስ ሙዚየም” ብለው እንደሚጠይቁ ጥርጥር የለኝም፡፡ በግድግዳው ላይ ተቀርፀው በልዩ የቀለም ህብር ካማሩ ሥዕሎች ውስጥ ፍቅር፣ ጭፈራ፣ የአባ ገዳ ሥርዓት፣ የእርቅ ሥርዓት፣ የፈረስ ግልቢያ፣ የክሊዮፓትራ ምስል፣ የገጠሩ ሕዝብ አኗናር…በስዕልና በቅርጽ ያልተዳሠሠ ነገር የለም፡፡ ይህን ትንግርት የሚመለከቱት በአዳማ ከተማ መብራት ኃይል ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ቀበሌ 06 ሞቅ ደመቅ ካሉት የምሽት ጭፈራ ቤቶች በአንዱ ነው፡፡ ታዲያ ለሥራም ይሁን ለመዝናናት ወደ ከተማዋ ጐራ ያለ ማንኛውም ሰው፣ አካባቢውን ሳይጐበኝ ይመለሳል ለማለት ይቸግራል፡፡ አንዳንዶች አካባቢውን “የአዳማው ቺቺኒያ” ይሉታል፡፡

በዚሁ አካባቢ ግን አንድ ትልቅ ኤግል ተፈጥሯል፡፡ ኤግሉ ከዚህም በፊት የነበረና ገበያ የነበረው ሆቴል ሲሆን ወደ ትልቅ ኤግልነት ለመቀየር አራት አመት ፈጅቷል፡፡ ተጠናቆ ስራ ከጀመረም ገና ሦስት ወሩ ነው፡፡ የቤተሠቡ ጊዜና ጉልበት ሳይታሠብ 55 ሚሊዮን ብር የጨረሠው አዲሱ ኤግል፣ 40 የመኝታ ክፍሎችን የያዘ ባለ ሰባት ፎቅ ህንፃ ነው፡፡ ኤግል ሆቴል በአምስት ወንድማማቾች፣ በእህትና በእናታቸው በወ/ሮ አበበች ወ/ሥላሴ የተመሠረተ አክሲዮን ነው፡፡ የቤተሰቡ መነሻ አርሲ ውስጥ በአርባ ጉጉ አውራጃ ጮሌ በተባለች መንደር ውስጥ ሲሆን አባታቸው አቶ ግርማ ኃይሉና ባለቤታቸው ወ/ሮ አበበች ወ/ሥላሴ የቢዝነስ መሠረታቸው ሆቴል እንደሆነ የአክሲዮኑ ሥራ አስኪያጅ አቶ አንዷለም ግርማ ይናገራሉ፡፡

ልጆቻቸውን በፍቅርና በስራ ገርተው ያሣደጉ ጠንካራ ወላጆች እንደነበሩ የሚናገሩት አቶ አንዷለም፤ ታላላቆቻቸውም ሆነ ታናናሾቻቸው ከልጅነት ጀምሮ ደረጃ በደረጃ ሥራን ከቤተሠብ ጋር እየለመዱ እየተዋደዱና እየተከባበሩ ማደጋቸውን ይገልፃሉ፡፡ “ለምሣሌ እኔን ብትወስጂ አርሲ በነበረን ሆቴልና ሥጋ ቤት ውስጥ ለሰው ስጋ በማድረስ፣ ከዚያ ለቆራጭ በማቀበል ብሎም ሥጋ ቆራጭ በመሆን ደረጃ በደረጃ ሠርቻለሁ” በማለት የስራ ተሞክሯቸውን አጫውተውኛል፡፡ “የቤተሰቡ ትልቁ የትምህርት ደረጃ 12ኛ ክፍልን ማጠናቀቅ ነው፣ ከዚያ በላይ የተማረ የለም” ያሉት አቶ አንዷለም ፤ ከሰባት ዓመት ዕድሜያቸው ጀምሮ አዳማ ውስጥ እንዳደጉ ይናገራሉ፡፡ ትልቁ ኤግል ከመሠራቱ በፊት ከኪራይ ቤቶች የተከራዩት ትንሽ ሆቴል እንደነበር ገልፀው፤ ትንሹም ሆቴል በጣም ደማቅና የከተማዋን ሁኔታ ያገናዘበ እንደነበር ያብራራሉ፡፡ “ሆቴሏ በጣም ብዙ ገበያና ጥቅም የምታስገኝ ነበረች” የሚሉት የፒኤልሲው ስራ አስኪያጅ፤ በቤተሠቡ ውስጥ ያለው ትልቅ ነገርን መስራት እንደሚቻል የማመን ብቃት አሁን ትልቁን ኤግልና በውስጡ የዓይን ማረፊያ የሆነውን የባህል የፍቅር፣ በአጠቃላይ የጥበብ ሥራ መፍጠሩን ገልፀው፤ ወረቀት ላይ ያሠፈሩት ቅርፅና ሥዕል በቤተሰባችን አዕምሮ ውስጥ ተቀርፆ ያለቀውን ነው” ይላሉ አቶ አንዷለም፡፡

የተዋበ ሆቴል ለመሥራት የነበራቸውን ፍላጎት ሲናገሩ “ሰው በመጠጥና በምግብ ሰውነቱን ከመሙላት ባለፈ አዕምሮውም ምግብና እረፍት እንደሚያስፈልገው በማመን ነው የሠራነው” የሚሉት ሥራ አስኪያጁ፤ ይኼ ሲሠራ ግን ቀጥታ ዒላማው ገንዘብ ያመጣል የሚል ሳይሆን ሰዎች የበለጠ ምቾት እንዲሰማቸው ማድረግ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ወደ ሆቴሉ ቅኝት ስንመለስ ፏፏቴው ሲለቀቅ የተለያዩ ትዕይንቶች ይታያሉ፡፡ ለምሳሌ ኤግሏ የተቀረፀችው ወፎች ውሃ ሲነካቸው ለማራገፍ ክንፋቸውን በሚዘረጉበት ዓይነት ነው፡፡ ከሁሉም ያስገረመኝ ቅርፅ ደግሞ እነሆ፡- አንዲት እንቁራሪትና አንድ ህፃን ፊት ለፊት ተፋጠው ተቀምጠዋል፡፡ ፏፏቴው ሲለቀቅ እንቁራሪቷ ህፃኑ ላይ ትተፋለች፤ ህፃኑ ደንግጦ ሲያያት የሚያሳይ ቅርፅ ነው፡፡ ነገሩ ለህፃናት መዝናኛነት ታስቦ ቢሠራም ትልልቆችንም የሚያፈዝ ነው፡፡ ሁለቱን ፎቅ ወጥተው ቴራሱ ላይ ሲደርሱ እንደ ፔንዱለም ወዲህ ወዲያ የሚወዛወዝ ወንበር ያገኛሉ፡፡ ይህ ወንበር መኻል ላይ ጠረጴዛ ያለውና ፊት ለፊት ለሚቀመጡ ሰዎች በተለይም ህፃናት እየተወዛወዙ እንዲዝናኑ የታሰበ ቢሆንም በወንበሩ እየተወዛወዙ ሲዝናኑ ያየናቸው ግን አዋቂዎች ናቸው፡፡ አጠቃላይ የሆቴሉ አሠራር የአምፊ ቴአትር (ጣሪያ የሌለው) አይነት ነው ፤ለምሣሌ ቴራስ ላይ ቁጭ ብለው አቆልቁለው፣ አሊያም አግድመው በየፎቆቹ ላይ ያሉትን ትዕይንቶች በግልፅ ለመመልከት ምቹ ነው፡፡ በሆቴሉ የተለያዩ ግድግዳዎች ላይ በፈረንሳይኛ፣ በጀርመንኛና በቻይንኛ ቋንቋ ኤግል ሆቴል የሚሉ ፅሁፎች ተፅፈዋል፡፡

አቶ አንዷለም ስለዚሁ ሲያስረዱ፤ ትንሿ ኤግል እያለችም ሆነ አሁን ትልቁም ከተሠራ በኋላ የሦስቱም አገር ዜጐች የሆቴሉ ተጠቃሚዎች በመሆናቸው የእነሱን ቀልብ ለመሳብ የተደረገ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ሆቴሉ የተሠራው የከተማዋን ነዋሪ ከግምት ውስጥ በማስገባት ነው ያሉት አቶ አንዷለም፤ ከከተማው ነዋሪ በተጨማሪ ከሌላ ቦታም የሚመጣ ሰውና የውጭ አገር ቱሪስቶችም የሚስተናገዱበት እንደሆነ ያብራራሉ፡፡ “ቤቱ ደረጃውን የጠበቀ ነው፤ ነገር ግን ቢራ 17 ብር ይሸጣል፣ ድራፍት 13 ብር ነው ይሄ ቫትን ጨምሮ ነው” የሚሉት ስራ አስኪያጁ፤ ምግብም ቢሆን በ40 እና በ50 ብር መካከል መሆኑን ይናገራሉ፡፡ አልጋዎቹ ሶስት ደረጃ ያላቸውና ደረጃቸውን የጠበቁ ሲሆኑ ከ280 ብር እስከ 480 ብር ዋጋ ተተምኖላቸዋል፡፡ ይኼም አቅምን ግምት ውስጥ አስገብቶ የተተመነ እንደሆነ አቶ አንዷለም አጫውተውናል፡፡ ሆቴሉ በአሁኑ ሰዓት ለ235 ቋሚ ሠራተኞች የሥራ ዕድል ፈጥሯል፡፡ በአሁኑ ሰዓት በሆቴሉ የሰው ኃይል አስተዳደር ሆነው በኃላፊነት እየሠሩ የሚገኙት አቶ አቡ፤ የብዙ ሙያ ባለቤት ናቸው፡፡

ከመምህርነት ሙያ ጀምሮ በርካታ ሥራዎችን ሰርተዋል፡፡ በሆቴሉ የቅርፃቅርፆች ሥራ ላይ በስፋት የተሳተፉ ሲሆን በውስጣቸው የነበረውን የአርት ሙያ እዚህ ሆቴል ቅርፃቅርፆች ላይ እውን በማድረጋቸው ደስተኛ ናቸው፡፡ “በኤግል ሆቴል ግንባታ ውስጥ አንድም አርት ያልሆነ ነገር የለም” በማለት አስተያየታቸውን የጀመሩት አቶ አቡ፤ ኤግሏን ለመስራት በተለይ ማንቁርቷ በርካታ ጊዜ ፈርሶ እንደተሠራ ይገልፃሉ። ኤግል በአለም ላይ በርካታ ታሪኮች እንዳሏት የሚናገሩት አቶ አቡ፤ የጥንካሬ፣ የውበት፣ የጠንካራ እይታ እና የመሰል ጥራት መገለጫዎች መሆኗን ጠቁመው በአጠቃላይ ከሆቴሉ እቅድ ጀምሮ በአርቱም ላይ በመሳተፋቸው ጭምር ደስተኛ እንደሆኑም ይናገራሉ፡፡ አርቱ ከግንባታው ጐን ለጐን በተጓዳኝ የተሠራ በመሆኑ ቅርፃቅርፆቹም አራት ዓመት እንደፈጁ ነው የሚናገሩት፡፡ አቶ አቡ መምህር በነበሩበት ጊዜ አርት ስኩል ውስጥ የመማር እድል የገጠማቸው ቢሆንም እንደ አባታቸው ኢንጂነር የመሆን ፍላጐት ስለነበራቸው ትምህርታቸውን ማቋረጣቸውን ገልፀው፤ ሆኖም የአርት ፍቅራቸው እየጠነከረ ሲመጣ ከግርማችን ፒ ኤል ሲ ባለ ድርሻዎች አንዱ ሆነው ህልማቸውን እውን ለማድረግ በመብቃታቸው ደስተኛ ናቸው።

የግርማችን ፒኤልሲ ባለ አክሲዮኖች የቢዝነስ መሠረት ምንም እንኳ ሆቴል ቢሆንም በአሁኑ ሰዓት በትራንስፖርት ዘርፍ፣ በህንፃ መስታወት ገጠማና መሰል ቢዝነሶች መሠማራታቸውን አቶ አንዱአለም ይናገራሉ፡፡ አሁን ኤግል ሆቴል ካለበት ሥፍራ አጠገብ የማስፋፊያ ቦታ እየጠየቁ ነው፡፡ የመሰብሰቢያ አዳራሽ፣ የመዋኛ ሥፍራ፣ የህፃናት መጫወቻና አረጋውያን ለብቻቸው በትንሽ ክፍያ የሚዝናኑበት የራሣቸው የሆነ ደረጃውን የጠበቀ መዝናኛ የማሠራት ሀሣብ እንዳላቸው የግርማችን ፒ ኤል ሲ ባለድርሻዎች ይናገራሉ፡፡ “ስለ አረጋዊያኑ መዝናኛ ማሰባችንን ለእናታችን ስናጫውታት ‘ይህ ትልቁ ሐሣብ ነው’ በማለት ደስታዋን ገልፃልናለች” የሚሉት አቶ አንዷለም ፤ የጊዜ ጉዳይ እንጂ እንደሚሳካ ጥርጥር እንደሌላቸው ይናገራሉ፡፡ በአዳማ ከተማ ትልቅ የእንግዳ ማረፊያ በመገንባትም ላይ ይገኛል፡፡ አቶ አንዷለም እንዳጫወቱን፤ እንግዳ ማረፊያው አስራ ስምንት ክፍሎች የሚኖሩት ሲሆን አንዱ ክፍል መኝታ፣ ሳሎን፣ መታጠቢያና ማብሰያ ክፍሎችን ያጠቃልላል፡፡ እንግዳው የሚፈልገውን ነገር አብስሎ ለመመገብ እንዲችል የታሠበ ሲሆን እቃ ለመግዛት ሩቅ ሄዶ እንዳይቸገር በግቢው ውስጥ ደረጃውን የጠበቀ ሱፐር ማርኬት ይኖረዋል፡፡

የሚያበስልለት የሚፈልግ ከሆነም በገስት ሀውሱ ውስጥ ዝግጁ የሆኑ ሠራተኞች ይኖራሉ ተብሏል፡፡ ኤግል ሆቴል ፊት ለፊት አስፓልቱን ተሻግሮ “ናሽናል” የተሠኘ ታዋቂ ጭፈራ ቤት አለ፡፡ ጭፈራ ቤቱ በግርማችን ፒኤልሲ ባለቤትነት የሚመራ ነው፡፡ ይህ ጭፈራ ቤት ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ሊገነባ ዲዛይኑ አልቆ በጀት እንደተመደበለት የሚናገሩት አቶ አንዷለም፤ እጅግ ዘመናዊና የከተማዋን ደረጃ በጠበቀ መልኩ ሊሠራ ዝግጅቱ ተጠናቋል ብለዋል፡፡ የኤግል መኝታ ክፍሎች ውስጥ በሁለት አቅጣጫ ሲቆሙ ማለትም በምስራቅና በምዕራብ የከተማዋን የተለያዩ ገጽታዎች መቃኘት ይችላሉ። ለምሣሌ የመኝታ ክፍሎቹ ውስጥ ቆመው ወደ ምዕራብ ሲመለከቱ ከሆቴሉ ከምድር ቤቱ ባር ጀምሮ አጠቃላይ የሆቴሉን እንቅስቃሴ መቃኘት ይችላሉ፡፡

አሻግረው ሲመለከቱ ትልቁን ገልማ አባገዳ፣ የንፋስ ኃይል ማመንጫውን ተሽከርካሪና በርካታ የከተማዋን ክፍል ይመለከታሉ፡፡ ይህን ሆቴል በሚያስፋፉበት ጊዜ የገጠማቸው ችግር ምን እንደሆነ ጠይቀናቸው ሲመልሱ “አሁን ደስተኛ ብንሆንም በፊት ግን ፈተና የሆነብን ለማስፋፊያው ሲባል 11 አባወራዎች መነሣት ነበር” ይላሉ አቶ አንዷለም፡፡ ምንም እንኳ ይኖሩበት የነበረው ቤት በጣም ጠባብ ቢሆንም ከለመዱበት ቦታ ማስነሣቱ ፈታኝ እንደነበር አስታውሠው፤ ከከተማው መስተዳድር ጋር በመነጋገር ቦታ ተመርጦ ለእያንዳንዱ አባወራ 80ሺህ ብር በማውጣት አምስት አምስት ክፍል ቤት አሠርተው ማስረከባቸውን ገልፀዋል፡፡

ከብዙ ጊዜ ጀምሮ ስለአንድ በዕብደቱ ስለሚታወቅ የኢራን ሰው የሚተረት አንድ ወግ አለ፡፡ ይህ ዕብድ በዋና ዋና መንገዶች ላይ ባሉ አደባባዮች ዙሪያ ብቻ ነው የሚገኘው፡፡ አንድ አደባባይ አጠገብ መጥቶ ዙሪያውን መዞር ከጀመረ መቆሚያ የለውም፡፡ መሽቶ ጨልሞበት ወደ ማደሪያው እስከሚሄድ ድረስ መዞሩን ይቀጥላል፡፡ “ወዴት ትሄዳለህ?” ይሉታል ሰዎች ጠዋት፡፡ “ወደ አደባባዬ ነዋ!” ይላል፡፡ “አደባባዩን ማን ሰጠህና?” “እኔ የተፈጠርኩት ለአደባባይ መሆኑን አታውቁም? አደባባይስ የተፈጠረው ለእኔ መሆኑን አታውቁም?” እያለ እየዘፈነ ይሄዳል፡፡ ዕብዱ፤ ዋንኛ ጠባዩ ሰው አለመንካቱ ነው፡፡ “ሰውን ትሰድበዋለህ እንጂ አትመታውም” ይላል፡፡

“ለምን?” ይሉታል ሰዎች፤ ሊያጫውቱት፡፡ “የሰው ልጅ ሲደበደብ ይደድባል፡፡ ሲሰደብ ግን ብልጥ ይሆናል” “እንዴት?” “ለመልስ የሚሆን ስድብ ሲያዘጋጅ ማሰብ ይጀምራል፡፡ የስድብ ትምህርት ቤት ስለሌለ፤ ኦርጅናሌው የስድቡ ባለቤት እሱ ይሆናል” ሌላው የዚህ ዕብድ ጠባይ አንድ ጠዋት መናገር የጀመረውን ነገር በጭራሽ አይለውጠውም፡፡

ለምሳሌ አንድ ጠዋት፤ “የማይጮህ ህዝብ ምላሱ መቆረጥ አለበት!” ይላል፤ ካልን ቀኑን ሙሉ፤ “የማይጮህ ህዝብ ምላሱ መቆረጥ አለበት” ሲል ይውላል፡፡ በሚቀጥለው ጠዋት፤ “ሞኝ ያሥራል ብልጥ ይማራል!” ይላል፡፡ “The smarter prisoner yet learns. The fool governer forever imprisons” እንደ ማለት) ቀኑን ሙሉ ይቀጥላል፡፡ ደሞ ሌላ ጠዋት፤ “የሚዘምሩ ወፎች አሉ፡፡ የሚያርፉበት፤ ጐጆ እሚሠሩበት ዛፍ ግን የላቸውም” ይላል፡፡ እንዲህ እንዲህ ሲል ከርሞ አንድ ቀን ጠዋት፤ “ንጉሡ ጭንቅላታቸውን በርዷቸዋል!!” እያለ እየደጋገመ መጮሁን ቀጠለ፡፡ የአገሪቱ ፀጥታ አስከባሪ ኃላፊ፤ “አሁንስ አበዛው!” ብለው አንድ ፖሊስ አስገድዶ እንዲያስረው ላኩበት፡፡ ዕብዱ መሮጥ ጀመረ፡፡ “የዕብድ ጉልበት አያልቅም” ይባላል፡፡ ፖሊሱ ግዴታው ነውና የሚፈፅመው እየሮጠ መከተሉን ቀጠለ፡፡ ዕብዱ ያደባባዩን ዳር ዳር ይዞ ዙሪያውን ነው የሚሮጠው።

እንደወትሮው ከመስመሩ አይወጣም፡፡ ወደአደባባዩ ውስጥም አይገባም፡፡ ፖሊሱ ደከመውና ቆመ፡፡ ይሄኔ ዕብዱ ከት ከት ብሎ ሳቀና፤ “ሞኝ በመሆንህ ነው እንጂ የት እሄድብሃለሁ? ከአደባባይ የበለጠ እሥር ቤት የት አለና ነው? ይልቅ ሰው ከአደባባይ እንዳይጠፋ ማረግ ነው የሚሻለው!” አለ ይባላል፡፡

                                                               * * *

አካባቢያችንን እንፈትሽ፡፡ አደባባዩ ምሽግ ያደረገውንና ዕውነት የሚናገርበትን እንለይ፡፡ አገራችንን እናጥና፡፡ ዙሪያ ገባውን ማትሮ ጣራውንም ግርጌውንም በዐይነ ቁራኛ አይቶ ነው፡፡ የዘንድሮ ጉዞ፡፡ እንኳን የካዝና ግድግዳ የአዕምሮ ሽንቁርም አደገኛ ነው፡፡ “በራቸውን ሳይዘጉ ሌባ ሌባ ይላሉ” አለች አሉ ውሻ፡፡ ሌባው ቢያዝም እንኳ አሁንም በሩ ክፍት ከሆነ ለአዲስ ሌባ ምቹ መሆኑ አይቀርም፡፡ ህጉ ወደ ኋላ አይሰራም፤ ተመስገን ነው፤ በሚል በጊዜ ሰርቄ አምልጫለሁ፤ የሚልንስ እንዴት እንደምናስተናግደው ማጤን አለብን፡፡ ከጥንት ጀምሮ በውል እንደሚታወቀው ለሀገሩ ህልውና፣ ለሉዓላዊነቱ፣ ቀናዒ ህዝብ ነው ያለን። “ያልጠረጠረ ተመነጠረ” የሚለው ወዶ አይደለም፡፡ ተደጋግሞ ለጥቃት አጋልጦት ነው፡፡

አለ ነገር አለ ነገር ቁልቁለቱን ወርደን ወንዙን ስንሻገር”፤ ይላል አርቆ እያሰበ፡፡ ከላይ እስከታች፣ ነገር አለ፣ እያለ እየተጠራጠረ፣ መጓዝን የመረጠ ነው፡፡ መጠራጠርን እንተው ቢባልም እሚጠራጠር ካለ መጠርጠር መጥፎ አደለም፡፡ አንዱ ጓዳ ውስጥ ሲያንጐዳጉድ ሌላው ሳሎን እንደሚወራች አሊያም በተገላቢጦሹ ሊከሰት ይችላል፡፡ የውስጥ ችግሮቻችንን ዐይተው ባላንጦቻችን እንደሚጠራሩ መቼም ቢሆን መዘንጋት አይገባም። “ለነገር ይሁን ለፍቅር” ለዩ፤ ይላሉ አበው፡፡ ስለተጠራሩብን ጆሮአችንን በየአቅጣጫው ማቅናት ይጠበቅብናል፡፡ “እዚያ ማዶ ሆኖ ክፉ ሰው ተጣራ፤ እዚህ ማዶ ሆኖ ክፉ ሰው ወይ አለው፤ ጐበዝ ተጠንቀቁ፣ ይህ ነገር ለኛ ነው!!” ማለትም የአባት ነው፡፡ “ብቻውን የበላ ብቻውን ይሞታልን” አለመርሳትም ብልህነት ነው፡፡ በጥቃቅን መብራት በበራባቸው ነጥብ - ቦታዎች፣ በተመረጡ ወንጀሎች፣ በተመረጡ ሰዎች ላይ ስናተኩር ያልተመረጡትን ማየት ይሳነናል፡፡ ከመካከላቸውም ንፁሃኑን መለየት ይቸግረናል፡፡ ሁለመናችንን እንይ ጐበዝ፡፡ ሁሉም ከተበላሸ ወይም ሁሉም ከተሳሳተ ችግር ነው “በገንፎ የተሠራ ጥርስ፤ አያስቅ፤ አያስፍቅ” ማለት ሥረ - ነገሩ ይሄው ነው፡፡

በወር 140 ሚ. ሞባይል ስልኮች ተሽጠዋል - ግማሾቹ (70 ሚ) እንደ አይፎንና ጋላግክሲ የመሳሰሉ ‘ስማርትፎን’ ናቸው። በስማርትፎን ሽያጭ ዘንድሮ መሪነቱን ከአፕል የተረከበው ሳምሰንግ፣ ከጋላክሲ ሞባይሎች ሽያጭ በየወሩ በአማካይ 8 ቢ. ዶላር ገደማ ገቢ እያገኘ ነው። የአፕልም ገቢ ተቀራራቢ ነው፤ ወደ ስምንት ቢ. ዶላር የሚጠጋ ገቢ ከአይፎን ሞባይሎቹ ሽያጭ በማስገባት በሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የሳምሰንግ ሩጫ የሳምሰንግ ስኬት ይበልጥ እያደገ እንደሚሄድ በእርግጠኛነት የሚገልፁ ዘገባዎች ምክንያታቸውን ሲያስረዱ፣ አዲሱ ‘ጋላግሲ ኤስ4’ ከፍተኛ ተወዳጅነት ማግኘቱን ይጠቅሳሉ። በእርግጥ ነባሩ ጋላግክሲ ኤስ3 ሞባይልም፣ ዋነኛ የአይፎን ተቀናቃኝ ለመሆን በመቻሉ፣ ሳምሰንግ በሞባይል ምርት የመሪነቱን ደረጃ እንዲቆናጠጥ ረድቶታል።

ከወር በፊት ለገበያ የቀረበው ኤስ4 ግን፣ ገና ካሁኑ ሪከርድ ሰብሯል። ኤስ3 ለገበያ የቀረበ ጊዜ፣ አስር ሚሊዮን ሞባይሎችን ለመሸጥ ሁለት ወራት ፈጅቶበት ነበር። ኤስ4 ግን በአንድ ወር ውስጥ ነው አስር ሚሊዮን የተቸበቸበው። በሽያጭ መጠን መሪነቱን መያዝ ግን፣ በአትራፊነትም አንደኛ መሆን ማለት አይደለም። ሳምሰን በየወሩ ከ2 ቢ. ዶላር በላይ ትርፍ እያገኘ እንደሆነ የገለፁ የሰሞኑ ዘገባዎች፣ አፕል በየወሩ የሚያገኘው ትርፍ ከ3 ቢ. ዶላር በላይ እንደሆነ ጠቅሰዋል። የሳምሰንግና የአፕል ኩባንያዎች ስኬት፣ ወደፊትም እያደገ እንደሚሄድ ይጠበቃል - የስማርትፎኖች ገበያ እየተስፋፋ ነውና።

ከመደበኛ ሞባይል ወደ ስማርትፎን ላለፉት አምስት አመታት በአይፎን መሪነት በፍጥነት እያደገ የመጣው የስማርትፎን ገበያ፣ ዘንድሮ ከሌላው መደበኛ ሞባይል ጋር በቁጥር ለመስተካከል እንደበቃ ጋርተር የተሰኘ የጥናት ተቋም ገልጿል። ካለፈው የጥር ወር ወዲህ፣ በመላው አለም በየወሩ 140 ሚ. ገደማ ሞባይሎች ለተጠቃሚ እንደተሸጡ ጋርተር ጠቅሶ፣ ከእነዚህም መካከል ሰባ ሚ. ያህሉ መደበኛ ሞባይሎች ሲሆኑ ሰባ ሚ. ያህሉ ደግሞ ስማርትፎን ናቸው ብሏል። በመደበኛ ሞባይልና በስማርትፎን ገበያ፣ በጥቅሉ ሳምሰንግ በየወሩ 35 ሚ. ገደማ ሞባይሎችን ሲሸጥ፣ ከመሪነት የወረደው ኖኪያ በወር 21 ሚ. ሞባይሎችን ሸጧል። አፕል 13ሚ.፣ ኤልጂ 5ሚ.፣ ከቀድሞ ቦታው አንድ ደረጃ የወረደው ዜድቲኢ ከ4.5 ሚ በላይ፣ ደረጃውን እያሻሻለ የመጣው ሁዋዌ ደግሞ ወደ 4 ሚ. ገደማ ሞባይሎችን ለገበያተኛ አድርሰዋል። የኩባንያዎቹ ስኬታማነት የሚለካው ግን በጥቅል የሞባይል ሽያጭ ሳይሆን በስማርትፎን ሽያጭ ነው - ስማርትፎን ከፍተኛ ገቢ ያስገኛልና። የስማርትፎን ፉክክር በስማትፎን ገበያውን የሚመሩት፣ የጋላክሲ አምራቹ ሳምሰንግ እና የአይፎን አምራቹ አፕል ናቸው። ሳምሰንግ፣ የጋላግሲ ኤስ ሞባይል ምርቱን ባለፈው አመት በሃምሳ በመቶ በማሳደግ፣ አሁን በየወሩ 23 ሚ. ገደማ ሞባይሎችን እየሸጠ መሆኑን ጋርተር ገልጿል።

አፕልም እንዲሁ፣ ምርቱን በማስፋት በየወሩ 13 ሚ. አይፎኖችን ለተጠቃሚዎች ሸጧል። የስማርትፎን ምርታቸውን በእጥፍ ያሳደጉት ኤልጂ እና ሁዋዌ ብርቱ ተፎካካሪ ለመሆን የተዘጋጁ ይመስላሉ። ኤልጂ በወር ከ3 ሚ. በላይ፣ ሁዋዌ ደግሞ ወደ 3 ሚ. የሚጠጉ ሞባይሎችን ገበያ ላይ እያዋሉ ነው። በየእለቱ የሚሰራጩ መረጃዎችና ዘገባዎች ሲታዩ፣ የስማርትፎን ውድድር እየበረታ እንደሚሄድ ያመለክታሉ። የካናዳው ብላክቤሪ እና የታይዋኑ ኤችቲሲ፣ በያዝነው ወር የስማርትፎን ምርቶቻቸውን ለገበያ በማቅረብ የአለምን ትኩረት ስበዋል። ኖኪያና ሶኒም እንዲሁ በአዳዲስ ምርቶች ገበያውን ለመጋራት እየጣሩ ነው። ከዚህም በተጨማሪ፣ በቅናሽ ዋጋ ስማርትፎን የሚያመርቱ ኩባንያዎች ከየአገሩ ወደ ፉክክሩ መግባት ጀምረዋል። ሳምሰንግና አፕል፣ ለዚህ ውድድር ተዘጋጅተዋል። ሳምሰንግ ሰሞኑን ይፋ እንዳደረገው፣ ከጋላክሲ ኤስ4 በዋጋ ግማሽ ያህል የሚቀንስ ሚኒ ኤስ4 ለገበያ አዘጋጅቷል። አፕልም እንዲሁ፣ ሚኒ አይፎን5 ያመርታል ተብሎ ይጠበቃል።

ከህዝብ ቁጥር ጋር የሚስተካከል ሞባይል በመላው አለም በአጠቃላይ ወደ 7 ቢሊዮን የሚጠጉ የሞባይል ስልክ መስመሮች አገልግሎት ላይ ውለዋል። በአፍሪካም 550 ሚ. ያህል ሞባይሎች ለተጠቃሚዎች ደርሰዋል - በአማካይ ለሶስት ሰዎች ሁለት ሞባይል እንደማለት ነው (64%)። የኢትዮጵያ፣ ገና የዚህን ግማሽ ያህል እንኳን አልደረሰም። በየአመቱ 1.7 ቢሊዮን ያህል ሞባይሎች ለገበያ እንደሚቀርቡ የገለፀው ጋርተር፣ የስማርትፎን ድርሻ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየሰፋ ዘንድሮ ከ800ሺ በላይ እንደሚደርስ ጠቁሟል። ግማሽ ሞባይል፣ ግማሽ ላፕቶፕ (ታብሌት) ሳምሰንግ በስማርትፎን ሽያጭ ገበያውን መምራት ቢጀምርም፣ በ‘ታብሌት’ ገበያ ግን የአፕል አይፓድ አልተቻለም። አፕል፤ በወር ውስጥ ወደ ከ6 ሚ. ላይ አይፓዶችን በመሸጥ የአምናውን ሪከርድ ሰብሯል። ሳምሰንግ ወደ 3 ሚ. ገደማ እየሸጠ ይገኛል።

በራፕ የሙዚቃ ስልት የሰው ጆሮ ውስጥ ለመግባት የቻለው ዊል ስሚዝ፤ አሁን በሚታወቅበት የፊልም አለም የሰው አይን ውስጥ የገባው በአጋጣሚ አይደለም። በአገራችን እንደተለመደው፤ “የጥበብ አድባር ጠርታኝ…” ምናምን ብሎ ነገር የለም - በሆሊውድ። ዊል ስሚዝ፣ አይቶና አስቦ፣ አስልቶና ቀምሮ ነው ወደ ሆሊውድ መንደር የዘለቀው። “በተመልካች ብዛትና በትፋማነት፣ በተወዳጅነትና በኦስካር ሽልማት ሪከርድ የሰበሩ ፊልሞች ምን አይነት ናቸው?” የሚል ጥያቄ ነው የዊል ስሚዝ መነሻ። የብዙ አመት መረጃዎች ተሰበሰቡ። ከአንድ እስከ አስር የወጡት ፊልሞች፣ አንድ በአንድ ተመረመሩ። ከአስሩ መካከል ሰባቱ፣ “የሳይንስ ፊክሽን ፊልሞች ናቸው። ከእነዚህም መካከልም በርካታዎቹ ፊልሞች ውስጥ፣ ልዩ ፍጡራን ወይም የሌላ አለም “ሰዎች” ይታያሉ።

በተወዳጅነትና በትርፋማነት ብቻ ሳይሆን፣ ብዙ የኦስካር ሽልማት በማግኘትም፣ የሳይንስ ፊክሽን ፊልሞች ቀዳሚ መሆናቸውን የተመለከተው ዊል ስሚዝ፣ ለኤጀንቱ የሰጠው “መመሪያ” አጭርና ግልፅ ነበር - “የሳይንስ ፊክሽን ፊልም ውስጥ መስራት ይኖርብናል” የሚል። ልክ ያጣ ድፍረት ይመስላል። ምክንያቱም፣ ዊል ስሚዝ በወቅቱ፣ በአንድ የቴሌቪዥን ድራማ ላይ ቢሰራም፣ በሆሊውድ ፊልም ላይ አንድም ጊዜ ሳይሳተፍ ነው፣ ፊልም አማርጦ ለመስራት የፈለገው። ግን እንዳሰበው ተሳካለት። ‘ባድ ቦይስ’ ከተሰኘው አክሽን ፊልም በመቀጠል፣ ዊል ስሚዝ በሰፊው ለመታወቅ የበቃው ‘ኢንዲፐንደንስ ዴይ’ በተሰኘው የሳይንስ ፊክሺን ፊልም ላይ ነው። ከሌላ አለም የመጡ ፍጡራን የሰው ዘርን ለማጥፋትና አለምን ለማውደም ዘመቻ ሲያካሂዱ በሚታዩበት በዚሁ ፊልም አለምን ከጥፋት፣ የሰው ልጅን ከእልቂት የሚታደጋቸው ዊል ስሚዝ ነው። ከዚያም ‘ሜን ኢን ብላክ’ በተሰኙ ሶስት ፊልሞች ላይ፣ ከሌላ አለም የሚመጡ ልዩ ፍጡራንን እየተጋፈጠ ምድርንና የሰው ዘርን ከጥፋት ሲያድን ይታያል።

በዚህም አላበቃም፤ ‘አይ ሮቦት’ ፊልም ላይ እንደገና አለምን ከክፉ ሮቦቶች ያድናታል። ‘አይ አም ሌጀንድ’ በተሰኘው ፊልም፤ የሰው ዘር በክፉ የበሽታ ወረርሽን ጨርሶ እንዳይጠፋ የሚያደርገው ዊል ስሚዝ ነው። ‘ሃንኩክ’ ፊልም ላይም፣ የሰው ልጅን ከጥፋት ይታደጋል። የዊል ስሚዝ ሚስት ጃዳ በበኩሏ፣ በሁለት የ‘ማትሪክስ’ ፊልሞች የድርሻዋን ትወጣለች። የ14 አመቱ ልጃቸው ጃደን ደግሞ፣ በሶስት ፊልሞች የአባትና የእናቱን መንገድ ተከትሎ እየሰራ ነው። ትንሿ ልጃቸው ዊሎው እስካሁን በአንድ ፊልም ላይ ሰርታለች። ለመሆኑ ዊል ስሚዝ እስካሁን በሰራቸው ፊልሞች የስንት ሰው ህይወት አድኗል? ታዋቂው ዋየርድ መጽሔት ሰሞኑን እንደዘገበው ከሆነ፣ ዊል ስሚዝ ከነቤተሰቡ፣ እስካሁን ከ63 ቢሊዮን በላይ ሰዎችን ከእልቂጥ አድኗል ብሏል።

ከአለም የህዝብ ቁጥር በዘጠኝ እጥፍ የሚበልጡ ሰዎች፣ በዊል ስሚዝ ቤተሰቦች ጀግንነት ከእልቂት ተርፈዋል - በፊልም ውስጥ። በእውነተኛው አለም ደግሞ፣ ዊል ስሚዝና ቤተሰቦቹ የተሳተፉባቸው ፊልሞች፣ 6 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ገቢ እንዳስገኙ ዋየርድ ገልጿል። ዊል ስሚዝና የ14 አመት ልጁ ጃደን የሰሩበት አዲሱ “አፍተር ኧርዝ” የተሰኘው ፊልም ላይ ግን፣ አለማችን ኦና ሆናለች። የሰው ዘር የላትም - የሰው ዘርን በሚያጠፉ አውሬዎች ተሞልታለች። ዊል ስሚዝና ጃደን፣ በዚህ ፊልም ሌሎች ሰዎችን ሳይሆን የራሳቸውን ሕይወት ከሞት ለማዳን ይታገላሉ።

የሞባይል አገልግሎት ተጠቃሚዎች በውጪ ሃገር የስልክ ቁጥሮች በሚደወሉ ጥሪዎች እየተጭበረበሩ ናቸው ያለው ኢትዮቴሌኮም፣ ደንበኞቹ ጥሪውን አንስተው እንዳይመልሱ አሳሰበ፡፡ መስሪያ ቤቱ ከደንበኞች የደረሰውን ጥቆማ በማጣራት ለማጭበርበር የሚደውልባቸው የውጪ ሃገር ስልክ ቁጥሮች መሆናቸውን አረጋግጫለሁ ያላቸው የሚከተሉት ናቸው -+35418441045፣ +4238773310፣ +34518441045፣ +4238773952፣ +004238773395፣ 004238773740፣ 004238773050 እንዲሁም 0025270300504፡፡

እነዚህ ቁጥሮች የተደወለለት ደንበኛ ጥሪዎቹን ካነሳና ካነጋገረ የአገልግሎቱ ሂሳብ በእሱ እንደሚታሰብ አረጋግጫለሁ ብሏል ኢትዮ ቴሌኮም፡፡ በተጨማሪም በአጭር የጽሑፍ መልዕክት “እጣ ደርሶዎታል” በማለት ነው በ0037178912368 ቁጥር የሚላክ መልእክት የተጭበረበረና ሃሰተኛ መሆኑን ደንበኞቼ ይወቅልኝ” ብሏል፡፡ ደንበኞች በ0042፣ 0025፣ 0022፣ 0023፣ 0037 እና 0043 በሚጀምሩ የውጪ ሃገር የስልክ ቁጥሮች ለሚደወሉላቸው ጥሪዎች ማንኛውም አይነት ምላሽ እንዳይሰጡ ኢትዮ ቴሌኮም አሳስቧል፡፡

ሠዓሊ ማህሌት እቁባይ ትባላለች፡፡ ኑሮዋ በሀገረ ኖርዌይ ነው፡፡ እዚያ ለሰባት ዓመታት የሥዕል ሙያን አጥንታ በማስትሬት ዲግሪ ተመርቃለች፡፡ ሥዕል ከማስተማር ይልቅ ፋብሪካ ውስጥ የጉልበት ሥራ ስሰራ ነው ለሥዕል የምነሳሳው የምትለው ሰዓሊዋ፤ ባለፈው ቅዳሜ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነ ጥበባት ትምህርት ቤት የተለያዩ የኪነጥበብ ውጤቶች የተካተቱበት በለቅሶ ባህል ላይ የተሰናዳ የኢንስታለሽን ሥራ አቅርባለች፡፡ በዚሁ ወቅት ያገኛት የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ መልካሙ ተክሌ ከሰዓሊዋ ጋር አጭር ቆይታ አድርጓል፡፡

ኖርዌይ ምን እየሰራሽ ነው? ኑሮዬ ኖርዌይ ሀገር ነው፡፡ እዚያ ሰባት ዓመት ሥእል ተምሬአለሁ፡፡ በ1998 ዓ.ም በማስትሬት ዲግሪ በስእል ተመርቄ የተለያዩ ሥራዎች እየሰራሁ ነው፡፡ ከዚያ ሁለት አመት ቀደም ብሎ የሠራሁትን ነው ባለፈው ቅዳሜ ምሽት በአለ የሥነ ጥበብ ትምህርት ቤት ያቀረብኩት፡፡ የድምፅ ጥበብ (Sound art) ነው ለቅሶን አስመልክቶ የሠራሁት፡፡ ለስምንት ዓመት የለፋሽበት ነው ማለት ነው? በአንድ ሰዓት ትዕይንስ ያቀረብሽው? አዎ፡፡ ግን ይህንኑ ዝግጅት ካሁን ቀደም ሁለት ጊዜ አቅርቤዋለሁ፡፡ በኖርዌይና በጎረቤት ሀገር፡፡ መጀመርያ ድምጽ ብቻ ነበር የሰራሁት፡፡ ለለቅሶው የራሴን ድምጽ ነው የቀዳሁት፡፡ ለማስተርስ ዲግሪዬ መመረቂያ ሳቀርበው ተወዳጅነት አገኘና የገንዘብና ቁሳቁስ እገዛ አግኝቼ አዳበርኩት፡፡

ለቅሶ ብቻ ሲሆን ተመልካች አፈንግጦ ነው የሚወጣው፤ ይደነግጣል። ማዳመጥ አይፈለግም፡፡ ተመልካቹን ለመያዝ ለድምፄ ጎጆ ነገር ሠራሁ፡፡ ለሌላው ድምፅ ደግሞ ባለ 5 ሜትር ውሃ የተሞላ እቃ አዘጋጅቼ በጨርቅ የተሰሩ ሕትመቶች አከልኩበት፡፡ ሰው ጨርቁን በውሃ ውስጥ ሲያይ ሳይታወቀው ብዙ ይቆያል፤ ፎቶግራፍ ነው፣ ጨርቅ የማያልቅ ርእሰ ጉዳይ መሆኑን አወቅሁ፡፡ እንዴት ነው ሰዓሊ የሆንሽው? ጣሊያን ትምህርት ቤት ነው የተማርኩት። በስእል፣ በጂኦሜትሪ እና በሂሳብ ጎበዝ ነበርኩ። አስተማሪዬ ለቤተሰብ ስዕል ወይ አርኪቴክቸር ብትማር ብሎ ሃሳብ ሰጠ፡፡ ሁለት መሃንዲስ ወንድሞች ነበሩኝ፡፡ ቤተሰብ አካውንቲንግ አስገባኝ። ትምህርት ቤቱ አካውንቲንግና መሃንዲስ ብቻ ነበር የሚያስተምረው፡፡ አካውንቲንግ መማሩ ግን ፍላጎቴ አልነበረም፡፡ ከዚያ ምግብ ዝግጅት ተማርኩ፡፡ ፍላጎት ስለነበረኝ ግን በትርፍ ሰዓት እዚህ እያለሁ ሰዓሊ አብያለው አሰፋ ውሃ ቀለም ያስተምረኝ ነበር። ኖርዌይ እንደገባሁ አጋጣሚዎች ሲመቻቹልኝ ሥእል ትምህርት ቤት ገባሁ፡፡ ሥዕል ስዬ ዝም ብዬ እወረውረዋለሁ፡፡ ያ ተከማቸ፡፡ ጎረቤቴ የሆነች ፈረንጅ “ለጥበብ ለምን ክብር አትሰጪም” አለችኝና ሰበሰበችው፡፡ ይታይህ የምስለው ለማሳየት ሳይሆን ለስሜቴ ነው፡፡ ታዋቂ ኖርዌያዊ ሠዐሊ ነበር፡፡

እሱ ጋ ወሰደችኝ እዚህ እየመጣሽ ስቱዲዮ ተጠቀሚ አሉኝ - ሠዓሊውና ባለቤቱ፡፡ ሠዓሊ ባለቤቱ ሥራዎችሽን ሰብስቢና አመልክቺ አለችኝ፡፡ ሄጂ በሰባት ወሬ አመለከትኩ፡፡ የሥዕል ትምህርቴን ቀጠልኩ፡፡ በሁለት ዓመት ዲፕሎማ ሁሉን ነገር ተምሬ ወጣሁ፡፡ ቅርፃ ቅርፅ፣ ሥእል፣ ኢንስታሌሽን … ተማርን፡፡ ከዚያ አካዳሚ ተወዳድሬ ገባሁ፡፡ ከ1500 አመልካቾች 15 ብቻ ነው የተቀበሉት፡፡ በሥእል ነው የምትተዳደሪው? አይደለም፡፡ በመጀመርያዎቹ አመታት ሥእል ሰርቼ በመሸጥ እኖር ነበር፡፡ ያንን አልፈለግሁም። የተለያዩ የሥእል ጽንሰ ሀሳቦችን ለማወቅ ጓጓሁ። በተመረቅሁ ጊዜ የሠራኋቸው ሥእሎች በሙሉ ተሸጠዋል፡፡ ግን የበለጠ ማወቅ አለብኝ ብዬ ማስተርስ ቀጠልኩ፡፡ አሁን ግን መሳሉን ትተሽ በተመራማሪነት እየሰራሽ ነው… ኢንስታሌሽን ስትሠራ ለስሜት ነው የምትሠራው፡፡ ገቢ የለውም፡፡ አንድ ሰዓሊ ሥዕል ወይም ቅርፃ ቅርፅ አሊያም ግራፊክስ ሰርቶ ሊሸጥለት ይችላል፡፡ የእኔን የለቅሶ ባህል ላይ የተሠራ ኢንስታሌሽን ግን ማንም አይገዛም፡፡ ከኤግዚቢሽኑ በኋላ ግን ረክቻለሁ፡፡ አንዳንዴ ስፖንሰርም ልታገኝ ትችላለህ፡፡ ከኪስህም አውጥተህ ትሠራለህ ለእርካታ፡፡ ለእርካታ ብቻ እየሰሩ ግን መኖር አይቻልም… ትክክል ነው፡፡ ኖርዌይ አንዳንዴ ፕሮጀክት እሰራለሁ፡፡

አንዳንዴ ደግሞ እንደ አርቲስት ማስተማር ይቻላል፡፡ ኪዩሬተር መሆን ይቻላል። ትክክለኛ የአርት ሥራ ለመሥራት የጉልበት ሥራ ነው የምመርጠው፡፡ የማላስብበትና ብዙ እውቀት የማይጠይቅ ሥራ ላይ ስሆን ጭንቅላቴ ለአርት ይዘጋጃል፡፡ ገንዘብ ሲያስፈልገኝ ፋብሪካ ሄጄ የጉልበት ሥራ እሰራለሁ፡፡ ለምሣሌ አንድ ጊዜ ቺፕስ የሚያመርት ፋብሪካ ውስጥ ሠርቻለሁ፡፡ ብየዳና የመሳሰለውን ነው የምሰራው፡፡ በተደጋጋሚ አንድ ሥራ ሥሠራ ያዝናናኛል፡፡ ሥራውን ስለማመደው ስለ ስዕሌ አስባለሁ፡፡ ሥእል ላስተምር ብል ግን አእምሮዬ ሥራ ስለሚበዛበት ሥእል መሳል አልችልም፡፡ አምኜበት ስለምሰራ በጉልበት ሥራዬ እኮራበታለሁ፡፡ አበሾችም ፈረንጆችም አሉ አብረውኝ የሚሰሩ፡፡ ፈረንጆቹ ከስምንተኛ ክፍል ያላለፉ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ አንዳንዴ ሀበሾቹ ማስተርስ ሆና ከእኛ እኩል ትሠራለች ብለው ይገረማሉ፡፡ በአርቲስትነት ስትሰሪ ትኩረትሽን የሚስቡት ርዕሰ ጉዳዮች ምንድናቸው? በባህል ላይ ያተኮረ ሥራ እሰራለሁ፤ ለምሣሌ የበቀደሙን የለቅሶ ባህል ላይ ያተኮረ የኢንስታሌሽን ሥራ መመልከት ይቻላል፡፡ በእርግጥ ሌሎች አርቲስቶችም በሥራው ተሳትፈዋል። በየቦታው ስሄድ ከቦታው ጋር የተያያዘ ሥራ እሰራለሁ። ሥእል መሳል ከባድ ነው፤ ትልቅ ፈጠራ ይጠይቃል፡፡

አንዳንድ በኮምፒዩተር የታገዘ ስነ ጥበብን የሚቃወሙ ሰዓሊዎች አሉ፡፡ ማህበርም አቋቁመዋል፡፡ እኔ ይኼንን አልደግፍም፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሥራዎቻችን እንዲታወቁ ከፈለግን በኮምፒዩተር መታገዝ አለብን፡፡ ዛሬ እኮ ምዝገባ እንኳን የሚከናወነው በኢሜይል ነው፡፡ ኮምፒዩተር መጠቀም የፈጠራ ችሎታን ያቀጭጫል የሚሉ ሰዓሊዎች እንዳሉ አውቃለሁ? ያንቺ ሃሳብ ምንድነው? ኮምፒዩተር ሥራን በጣም ያግዛል፡፡ የፈጠራ ችሎታን ይቀንሳል ብዬ አላስብም፡፡ ስቱዲዮ ውስጥ ቁጭ ብዬ ብቻ ይህን ዓለም ልከተለው አልችልም፡፡ ከዘመኑ ጋር ካልተራመድክ ተቆራርጠህ ትቀራለህ፡፡ ከኢትዮጵያና ከኖርዌይ ለሰዓሊነት ሙያ የሚመቸው ማነው? በኖርዌይ ስፖንሰርሺፕ በደንብ ታገኛለህ። ኖርዌይ ሆነው ለመሥራት የሚመርጡ ኢትዮጵያውያን ሠዐሊዎች አሉ፡፡ ለኔ ግን ሁኔታዎች ቢሠምሩልኝ ኢትዮጵያ ሆኜ መሣል ነው የምመርጠው፡፡ ኖርዌይ ሀብታሞች ናቸው፡፡ ለአርት ስራ ድጋፍ በመስጠት ያላቸውን አክብሮት ይገልፃሉ፤ ያ ጥሩ ነው፡፡ ጥሩ ፕሮጀክት ካመጣህ ስፖንሰር የማግኘት እድልህ ሰፊ ነው፤ በኖርዌይ። ሀገርህ ሆነህ ስትሥል ግን ዘና ትላለህ፡፡ ጭንቀት የለብህም በጣም ደስ ያለኝ በተለያየ የሥራ አጋጣሚ ከኢትዮጵያ የወጡ አርቲስቶች ኢትዮጵያ ተመልሰው መስራታቸው ነው፡፡

የኖርዌዮች ገብረክርስቶስ ደስታ ወይም አፈወርቅ ተክሌ ማነው? እውቅ ሠዐሊያቸው ጩኸትን አስመልክቶ የሠራው ኤድዋርድ ሞንክ ነው፡፡ አፉን በጣም ከፍቶ ድባቡም ያንን ያጠናከረለት ሥዕል ነው፡፡ ቬጌራን የሚባል ቀራፂም አለ፡፡ በጣም ነው የምወደው፡፡ አንድ ትልቅ ፓርክ ሙሉ ቅርፅ የሳለ ነው፡፡ በጣም አደንቀዋለሁ፡፡ የኖርዌይ የሥእል ታሪክ ግን ከ100 ዓመት የሚበልጥ አይመስለኝም… የሥእል ታሪክ አላቸው፡፡ በዴንማርክና ስዊድን ግዛት ሥር ነበሩ፡፡ ያኔም ግን ሠዐሊዎች ነበሩ፡፡ ልዩነቱ ምንድነው ከዴንማርክና ስዊድን አገዛዝ ነፃ ሲወጡ በራሳቸው ቋንቋ ተጠቅመው ትያትሩንም፣ ሥእሉንም ድርሰቱንም ሌላውንም ማካሄድ መጀመራቸው ነው፡፡ በአገዛዝ ስር የነበሩት አርቲስቶች እኮ እስካሁንም ኖርዌያውያን ናቸው፡፡ ለሕፃናትና ለታዳጊዎች የሚስሉ ሠዐሊዎች ምን ያህል ናቸው? ኢትዮጵያ ውስጥ ምን ያህል ለልጆች የሚስሉ ሠዐሊዎች እንዳሉ አላውቅም፡፡ ግን አሉ፡፡ እንደውም ለሕፃናት መሣል ያዝናናል፡፡ ካርቱን የሚስሉ ጎበዝ ሠዐሊዎች አሉ፡፡ በመፃሕፍት ሥራቸውን ያኖራሉ። ሕፃናት መጻሕፍትንም በሥእል ያሳምራሉ፡፡ ክህሎትና ትዕግስት የሚጠይቀው አኒሜሽንም አለ። አኒሜሽን እና ካርቱን ብዙ ጊዜ ሊፈጅ ይችላል፡፡ ብዙ ገንዘብም ሊያስገኝ ይችላል፡፣

ኖርዌይ ውስጥ የሕይወታት ዘመናቸውን ለሕፃናት የሰጡ ብዙ ሠዓሊያን አሉ፡፡ እስካሁን ከሰራሻቸው የኢንስታሌሽንም ሆነ ሌሎች ሥእሎች ብዙ ገንዘብ አግኝተሽ ታውቂያለሽ? አዎ፡፡ ይህም የሆነው ዲፕሎማዬን ስጨርስ በሠራኋቸው ሥዕሎች ነው፡፡ በአንዴ ነው ስዕሎቹ የተሸዩት፡፡ በኢንስታሌሽንና ሌላ አርት ሥራም ተሳትፌአለሁ፡፡ በተለያዩ ዝግጅቶች ላይ በመስራቴ ትልቅ ሥም ባላቸው ዓለም አቀፍ አውደርእዮች ላይ ተሳትፌአለሁ፡፡ በዚህ ረገድ ሥም አለኝ፤ ምንም ገንዘብ ግን የለኝም፡፡ በሥእል ኤግዚቢሽኑ 34ሺህ የኖርዌይ ኪሮነር አገኘሁ፡፡ እንዲህ ይሸጥልኛል ብዬ ስላላሰብኩ ገንዘቡን በአንዴ ነው ያወደምኩት፡፡ ለቅሶን አስመልክቶ ባለፈው ቅዳሜ በአለ የሥነጥበብ ትምህርት ቤት የኢንስታሌሽንና ሌሎች የኪነጥበባት ስራዎች ተቀላቅለው የቀረቡበት ዝግጅት ከቦታ ጥበት አንፃር ለተመልካች ምቹ አልነበረም … ልክ ነው፡፡ ግን ይኼንኑ ተመልክተን ሥራው ሶስቴ እንዲደገም አድርገናል፡፡ ዝግጅቱ የሥዕል ትምህርት ቤቱና የትያትር ክፍለ ትምህርቶቹ መስተጋብር እንዲኖራቸው ተፈልጎ የተሰራ ነው። ከብሔራዊ ትያትርም ተዋንያን ተሳትፈዋል፡፡ ኬሮግራፈር እና ዳንሰኞችም ነበሩን፡፡ ኤግዚቢሽኑ በጥቅሉ ውጤታማ ሆኗል፡፡

አንድ ወር ተኩል ተዘጋጅታችሁ አንዲት ሰዓት ብቻ ማቅረብ አይደንቅም? እንዴ ከዚያ በላይ ከሆነ እኮ ተመልካቹ ይሰለቻል፡፡ እንዲህ አይነት ሥራ አነስ ብሎ ደረጃውን የጠበቀ ነው መሆን ያለበት፡፡ ቅልብጭ ብሎ ሲቀርብ ተመልካች ካልደገምኩ ይላል፡፡ በዚህ ዝግጅት ሁለቴ ለተመልካች፣ ሦስተኛውን ለተሳታፊዎቹ ፎቶ መነሻ ስንደጋግም ሦስቱንም ጊዜ ያዩ አሉ፡፡ ደጋግሞ ሲያይ ሐሳቡ የበለጠ ግልፅ ይሆንለታል፡፡ በዶክትሬት ዲግሪ ደረጃ ትምህርት ለመቀጠል አስበሻል? አስቤአለሁ፡፡ ለዚሁ የሚያዘጋጁኝን ስድስት መፃሕፍት አምና አንብቤአለሁ፡፡ የኤግዚቢሽን ጥያቄ ሲመጣ አቋረጥኩት፡፡ በአስጎብኚነት ስሰራ ደግሞ ኢትዮጵያን ለማየት ለሚፈልጉ ኖርዌያውያን ለሚጎበኙ ሀገር ጎብኚዎች የጉብኝት ማውጫ በጣሊያንኛና ሌሎች ቋንቋዎች እየሰራሁ አድላለሁ። በዚሁ ጊዜም ሰዎቹን ሊያስለቅሳቸው እንደሚችል እየጠየቅሁ ጥናቴን ቀጥያለሁ፡፡ የቀረ ነገር ካለ? በጣም ብዙ ተዳግሮት አለው ሥራው፡፡ ለሙያው ክብር ኖሯቸው ጊዜአቸውን መስዋእት አድርገው የለቅሶ ሥርአቱን ለማሳየት አብረውኝ የሰሩትን በጣም ማመስገን እፈልጋለሁ፡፡

ከላይ የምትመለከቱት የጡት ስእል የጡትን ተፈጥሮአዊ አቀማመጥ የሚያሳይ ነው፡፡ ስአሉን ለእይታ የጋበዝናችሁ ያለምክንያት አይደለም፡፡ የጡት ካንሰርን መሰረታዊ አመጣጥና ለመከላከልም ምን መደረግ ይገባዋል ከሚል የባለሙያ ትንታኔን ልናስነብባችሁ ነው፡፡ ዶ/ር አበበ ፈለቀ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የቀዶ ሕክምና ባለሙያና አሲስታንት ፕሮፌሰር ለርእሱ ማብራሪያ ሰጥተውናል። ከዚያ በማስቀደም በኢንካርታ ኢንሳይክሎፔድያ ላይ ያገኘነውን መረጃ እነሆ፡፡ “በጥንት ጊዜ በህክምና መታወቅ ወይንም መለየት ከተቻሉት የካንሰር ዓይነቶች ውስጥ አንዱ የጡት ካንሰር ነው፡፡ ይህ መሆን የቻለው ደግሞ የበሽታው ምልክቶች በግልጽ መታየት በመቻላቸው ነው፡፡ ጥንት ከተጻፉ መረጃዎች ውስጥ ከክርስቶስ ልደት በፊት በ1500/ ግብጻውያን የህክምና ባለሙያዎች ፓፒረስ ላይ ያሰፈሩት የኤድዌን ስሚዝ የቀዶ ጥገና መጽሐፍ ላይ ስለጡት ካንሰር ያሰፈሩት መረጃ ያሳያል፡፡

የታሪክ ተመራማሪዎች እንደሚሉት ከሆነ መነሻ የሆነው ለመረጃ የተቀመጡ የስምንት ሰዎች የጡት ካንሰር በሽታ ታሪክ ሲሆን የህሙማኑ የህክምና ምርምር ውጤት ሴቶቹ ጡት ላይ እጢ እንዳለ ያሳይ ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት በሽታው ምን እንደሆነ ቢታወቅም በሽታው ህክምናና መድሀኒት ግን የለውም ተብሎ ተደምድሞ ቆይቶአል፡፡ ለበርካታ ዘመናትም የነበሩ የህክምና ባለሙያዎች ያሰፈሯቸው መረጃዎች እንደሚያስረዱት ከሆነ የጡት ካንሰር ምንም አይነት ህክምና እንደሌለው የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ለበሽታው መከሰት ምክንያት የሚሆኑ ጉዳዮችን እራሱ ጥንት የነበሩት የህክምና ባለሙያዎችና ተመራማሪዎች አያውቋቸውም ነበር፡፡” ከላይ ያስነበብናችሁ ጥናታዊ ስራዎች ለንባብ ከሉዋቸው ውስጥ የመረጥነውን ነው፡፡ ዶ/ር አበበ ፈለቀ እንደሚገልጹት የጡት ካንሰር ማለት ጡት ከተሰራባቸው ክፍሎች የሚነሳ ሕመም ነው፡፡ ካንሰር ማለት ጤነኛ የነበረ የሰው ልጅ ሴል ጤነኛ ወዳልሆነ ሁኔታ ሲለወጥ ማለት ነው፡፡

ይህም ማለት አንድ ሴል ስራውን በትክክል የማይሰራ፣ በትክክል የማያድግ ወደመሆን ሲለወጥ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ጤነኛ የነበረው ሴል የሚኖረው ስራ ሲቋረጥ ወይንም ከቁጥጥር ውጪ ሲራባ አለዚያም ሲያድግ እና ከጎረቤቱ ያለውን ሴል ስራና ጤንነት ሲበጠብጥ የሚፈጠረው በሽታ ነው ካንሰር ማለት፡፡ ካንሰር አንድ ቦታ ሲፈጠር እዛው በነበረበት ቦታ አይቆይም፡፡ ወደ ሳንባ ወደጉበት እና ወደሌሎችም የሰውነት ክፍሎች ይሄዳል፡፡ ወደተለያዩ የሰውነት አካሎች ከሄደ በሁዋላም እድገቱን በመቀጠል የሰውነት ክፍሎችን ይበጠብጣል፡፡ ባጠቃላይም ካንሰር እንደእብድ ሰው የሚቆጠር ሕመም ነው፡፡ አንድ ሰው እብድ ነው ሲባል የተፈጥሮ ሕግ በትክክለኛው መንገድ እንዲመራ ስለማያዙትና ሁሉንም ነገር እንደፈቀደው ከተፈጥሮ ስርአት ውጪ የሚከውን ሲሆን ሴልም ወደ ካንሰርነት ሲለወጥ በዚህ መልክ ሊገለጽ ይችላል፡፡ የካንሰር ሴሎች ቁጥራቸው መጠናቸው በተፈጥሮ ሕግ መሰረት ሳይሆን እንደተመቸው ይጨምራል፡፡ መስራት የሌለባቸውን ስራ ይሰራሉ፡፡

ከራሳቸው አልፈው ከጎረቤት ያለውን ሴል ይበጠብጣሉ። ይህ በእንግሊዝኛው Carcinogenesis በመባል ይታወቃል፡፡ ዶ/ር አበበ እንደገለጹት ከ/100/የጡት ካንሰር ታማሚዎች ውስጥ /90/ያህሉ ሴቶች ሲሆኑ ወንዶች /10/ ብቻ ናቸው፡፡ ስለዚህ የጡት ካንሰር በብዛት የሚታየው ሴቶች ላይ ነው፡፡ የዚህ ምክንያቱም የጡት መጠኑ ሴቶች ላይ ትልቅ ሲሆን የወንዶች ጡት ግን ትንሽ እና በአይን የማይታይና በእጅ የማይዳሰስ በመሆኑ በካንሰር የመያዝ እድሉም ዝቅተኛ ነው፡፡ ይህ ማለት ግን በጥቅሉ ትልቅ ጡት ያላቸው በካንሰር ሲያዙ ትንህ ጡት ያላቸው ግን አይያዙም ለማለት አይደለም፡፡ ሴቶች በተፈጥሮአቸው ጡታቸው ላይ ብዙ ሴሎች የሚገኙ ሲሆን ወንዶች ግን እንደጡታቸው ማነስ ሴሎቹም ትንሽ ናቸው፡፡

ሴሎች ሲፈጠሩ አስቀድሞውኑ ፕሮግራም ያላቸው በመሆናቸው በዚህ ጊዜ ይህን ያህል ማደግ፣ ይህን ያህል ጊዜ መኖር እንዲሁም በዚህ ጊዜ መሞት የሚል የጊዜ ቀመር አላቸው፡፡ ነገር ግን ሴሎቹ በካንሰር ሲያዙ ይህ በተፈጥሮ የተመደበላቸው የአኑዋኑዋር ባህርይ ይለወጥና ከቁጥጥር ውጪ የሆነ ባህርይን ያመጣሉ፡፡ ስለዚህ የጡት ካንሰር ሲጀምር በጡት እና አካባቢው ቀድሞ ያልነበረ እብጠት ይታያል፡፡ እብጠቱም ጊዜ እየጨመረ በሄደ ቁጥር እያደገ በመሄድ ለዳሰሳም አስቸጋሪ ከማይሆንበት በግልጽ ከሚታወቅበት ደረጃ ይደርሳል፡፡ ዶ/ር አበበ አክለውም ሁሉም የጡት ክፍል በካንሰር የመያዝ እድል ቢኖረውም ነገር ግን 60 ኀያህል የጡት ካንሰር የሚያድገው በብብት ስር ነው ብለዋል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ካንሰር ሴሎቹ መሰራጨት ሲጀምሩ ጡቱ ላይ ከሚያብጠው እጢ በተጨማሪ እጅ ስር ያሉት እጢዎች አብረው ማበጥ ይጀምራሉ፡፡ በግዜ ካልተደረሰበትና በጣም ሲያድጉ ወደሌሎች የሰውነት ክፍሎች ይሄዳሉ፡፡ ለምሳሌ ሳንባ ላይ ሲሄድ ሳል ፣ደም የቀላቀለ አክታ ፣የደረት ውጋት ፣አየር ማስወጣትና ማስገባትን መከልከል የመሳሰለውን ጉዳት ያስከትላል፡፡ የካንሰር ሴል ወደ አጥንት ከሄደ በተለይም ጀርባ ላይ ያለው አከርካሪ አጥንት ላይ ከፍተኛ ሕመም ያስከትላል፡፡ ስለዚህ በጡት አካባቢ እብጠት እስኪያድግ መጠበቅ ሳይሆን አስቀድሞውኑ ክትትል በማድረግ እርምጃ መውሰድ ይገባል፡፡ ዋናው የጡት ካንሰር መለያ እብጠት ነው፡፡ ከዚህ ሌላ ምንም አይነት ምልክትም ይሁን ስሜት ስለሌለው አስቀድሞ ማወቅ አስቸጋሪ ነው፡፡ እብጠቱ ገና ከአንድ ሳንቲ ሜትር በታች እያለ በአንዳንድ ምርመራዎች ማወቅ ሲቻል ከአንድ እስከሁለት ሴንቲ ሜትር ሲደርስ ግን በዳሰሳ ማወቅ ይቻላል፡፡

በዚህ ደረጃ ያለ የካንሰር እጢ ገና ያልተሰራጨ እና ማዳን የሚቻል ነው፡፡ ስለዚህም ከእብጠት ውጪ ሌላ ምልክት ስለሌለው ሴቶች እድሜያቸው ከአርባ አመት ከዘለለ እብጠት ቢኖርም ባይኖርም በየአመቱ ምርመራ አድርጎ ሁኔታውን ማወቅ ያስፈልጋል የሚባለው ፡፡ እንደ ዶ/ር አበበ ፈለቀ ማብራሪያ የጡት ካንሰር ደረጃ አለው፡፡ ደረጃውም ከአንድ እስከ አራት ይከፈላል፡፡ 1ኛ ደረጃ የሚባለው የጡት ካንሰር መጠኑ እጅግ ያነሰና በጡት ላይ ብቻ ያበጠ እጢ ነው፡፡ 2ኛ ደረጃ የሚባለው የጡት ካንሰር ጡት ላይ ያለው እጢም አደግ ይላል፡፡ እንደገናም ብብት ስር እብጠቶቹ ሊዳሰሱ ይችላሉ፡፡ 3ኛ ደረጃ የሚባለው የጡት ካንሰር ጡት ላይ ያለው እጢም ትልቅ ሲሆን ብብት ስር እና ዙሪያውን ያሉት እጢዎችም በጣም ጠንንራ እና ያደጉ ሆነው ይዳሰሳሉ፡፡ 4ኛ ደረጃ የሚባለው የጡት ካንሰር ከጡትም ከብብት ስርም አልፎ ወደሌሎች የሰውነት ክፍሎች የተሰራጩ ሲሆን ነው፡፡ ከ1995ዓ/ም እና ከ2000 ዓ/ም በፊት እንደአውሮፓውያኑ የጊዜ አቆጣጠር የጡት ካንሰር አደገኛ ነበር፡፡ በቅርብ ጊዜ ግን በመላው አለም የእኛን አገር ጨምሮ የጡት ካንሰርን ማዳን ተችሎአል፡፡ ስለዚህም ደረጃ አንድ እና ሁለትን ማዳን ወይንም በደንብ መቆጣጠር ከሚቻልበት የህክምና ጥበብ ተደርሶአል፡፡ ደረጃ ሶስትና አራት ትንሽ የሚከብዱ እና ማዳን ባይቻልም እድገታቸውን ግን መግታት ተችሎአል፡፡ በሕክምናው እርዳታም ሕይወትን በደንብ ማራዘም ይቻላል፡፡ የጡት ካንሰር የህመም ስሜት የሚገለጸው ጡት ላይ እብጠት ተገኘ ከሚል በስተቀር ሌላ ምንም ስሜት የለውም፡፡

ነገር ግን አልፎ አልፎ ማለትም ከመቶ አስር ያህል ታማሚዎች ጡት ላይ የህመም ስሜት አለኝ ወይንም ወተት በሚወጣበት ጫፍ ላይ ፈሳሽ ይታየኛል የመሳሰሉትን ስሜቶች ይገለጻሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አንዳንዴ ጡት መጠኑንና ቅርጹን ቀየረ የሚሉ እና ቆዳው ላይ አንደሚፈርጥ ነገር ወይንም ደም መሳይ ነገር አገኘሁበት የሚሉ ምክንያቶችም ለሐኪም ይቀርባሉ፡፡ ይህ ሁሉ ግን በጊዜው ህክምና ከተደረገለት ምንም ችግር የለውም፡፡ ችግር አለው የሚባለው ውስጥ ውስጡን በተለያዩ አካሉች ላይ ሲሰራጭ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜም በጣም ችላ ከተባለ ጡቱ ላይ ያለው እጢ እያደገ ሲመጣ እዛው ጡቱ ላይ ይቆስላል፡፡ ያ ከሆነ ኢንፌክሽን በመፍጠር ሽታ ያለው ፈሳሽ እና ደም ያመጣል፡፡ ለዚህም የሚሰጠው ሕክምና ቀደም ሲል በተቀመጠው ደረጃ መሰረት አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ላይ ከሆነ ኦፕራሲዮን እንዲሁም ኬሞራፒ መስጠት እና እንደአስፈላጊነቱ የጨረር ሕክምና ማድረግ ሲሆን እንደምግብ የሚያገለግሉ ሆርሞኖች በተለይም ኢስትሮጂን የሚባለው ከሰውነት ውስጥ እንዲጠፋ የሚዋጥ መድሀኒት ይሰጣል፡፡

ይሄ ሁሉ የህክምና ዘዴ በአገራችን የሚገኝ ሲሆን ነገር ግን ሕክምናው የሚሰጠው ውስን በሆነ ቦታ ማለትም በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል መሆኑ እንደአንድ ችግር ይጠቀሳል፡፡ ኦፕራሲዮኑ የትኛውም ሆስፒታል ሊሰጥ የሚችል ነው፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ዋናው ችግር ሕክምናው ያለመኖሩ ሳይሆን ህክምናው የሚሰጥባቸው ቦታዎች ያለመስፋፋታቸው ነው ብለዋል ዶ/ር አበበ ፈለቀ /አሲስታንት ፕሮፌሰር/ የቀዶ ሕክምና ባለሙያ ፡፡

በዓመት ከ1500 በላይ ፊልሞች ሰርቶ ለዕይታ በማቅረብ 2 ቢሊዮን ዶላር ገቢ የሚያገኘው የህንዱ የፊልም ማዕከል ቦሊውድ፤ ሰሞኑን 100ኛ ዓመቱን እያከበረ ነው፡፡ የማዕከሉ ፊልሞች ዓለም አቀፍ ገበያ በየዓመቱ 10 በመቶ በማደግ ላይ እንደሚገኝ ያመለከተው “ዘ ታይምስ ኦፍ ኢንድያ” የተባለ ጋዜጣ፤ በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት የፊልሞቹ አመታዊ ገቢ 3.85 ቢሊዮን ዶላር ሊደርስ ይችላል ብሏል፡፡ የቦሊውድ 100ኛ ዓመት በዓልን ምክንያት በማድረግ የወጡ ዘገባዎች እንደሚሉት፤ ፊልሞቹ ገቢያቸው እንዲጨምር የመላውን ዓለም ፍላጎት ባማከለ መልኩ መሰራት ያለባቸው ሲሆን የህንድ መንግስት በአክሽን እና በወሲባዊ ፊልሞች ላይ የሚያደርገውን የበዛ ሴንሰርሺፕ መቀነስ ይኖርበታል፡፡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፤ አብዛኞቹ የቦሊውድ ፊልሞች አማካይ በጀት 1.5 ሚሊዮን ዶላር ሲሆን በከፍተኛ የጥራት ደረጃ ለዓለም አቀፍ ገበያ የሚሰሩት ደግሞ በአማካይ እስከ 20 ሚሊዮን ዶላር በጀት ይመደብላቸዋል፡፡

በህንድ ፊልሞች ላይ የሚሳተፉት ህንዶች ብቻ ሲሆኑ ለወንድ ተዋናዮች ትልቁ ክፍያ በአንድ ፊልም እስከ 16 ሚሊዮን ዶላር ሲሆን ለሴቶች ደግሞ 1.5 ሚሊዮን ዶላር ነው፡፡ ለፊልሞች ስራ የፋይናንስ ድጋፍ በማድረግ ረገድ የህንድ ባንኮች እና የፋይናንስ ተቋማት እንዲሁም በማከፋፈል ስራ ላይ የተሰማሩ የግል ኩባንያዎች ትልቅ ሚና አላቸው፡፡ የመጀመርያው የቦሊውድ ፊልም እ.ኤ.አ በ1913 ዓም ለእይታ የበቃው “ዳዳሼብ ፓላኬ” የተሰኘ ባለጥቁር እና ነጭ ቀለም ድምፅ አልባ ምስል ነው፡፡