
Administrator
የአውሮፓ ህብረት አምባሳደር ዣቪየ ማርሻል አረፉ
የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያ ልኡክ ጽ/ቤት ሃላፊ የነበሩት አምባሳደር ዣቪየ ማርሻል ባደረባቸው የአጭር ጊዜ ህመም ቤልጅየም ብራሰልስ በሚገኘው ቅድስት ኤልሳቤጥ ሆስፒታል በህክምና ሲረዱ ቆይተው፣ ባለፈው ቅዳሜ ግንቦት 17 ቀን 2005 ዓ.ም በተወለዱ በስልሳ አንድ አመታቸው ከዚህ አለም በሞት ተለይተዋል፡፡ አምባሳደር ማርሻል ከተሾሙበት እ.ኤ.አ ከ2010 ዓ.ም ጀምሮ ላለፉት ሶስት አመት ተኩል የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያ ልኡክ ጽ/ቤትን በአምባሳደርነት መርተዋል፡፡ በአምባሳደርነት ባገለገሉበት በዚህ ወቅትም በአውሮፓ ህብረትና በኢትዮጵያ መካከል ያለው ግንኙነትና የልማት ትብብር በከፍተኛ ደረጃ እንዲጠናከር ያላሰለሰ ጥረት አድርገዋል፡፡ አምባሳደሩ በ1988 ዓ.ም የአውሮፓ ኮሚሽንን የተቀላቀሉ ሲሆን በማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ በሞሮኮ እንዲሁም በሶሪያ በሚገኙት የህብረቱ ልኡክ ጽ/ቤቶች በአማካሪነት አገልግለዋል፡፡
ከ1999 እስከ 2010 ዓ.ም ድረስ ደግሞ በሱዳንና በዚምባብዌ የአውሮፓ ህብረት አምባሳደር ነበሩ፡፡ በግብርና ስራ ተሰማርተው ከነበሩ ቤልጅየማዊ ቤተሰቦች በኮንጐ ዲሞክራቲክ ሪፖብሊክ ውስጥ በ1952 ዓ.ም የወለዱትና የግብርና ባለሙያ የሆኑት አምባሳደር ማርሻል፣ ለግብርና ሙያና ለአርሶ አደሮች ልዩና ስስ ልብ ነበራቸው፡፡ የኢትዮጵያን የገጠር አርሶ አደሮች ለመርዳት በሙሉ ሃይላቸውና በከፍተኛ ስሜት ያደረጉት ጥረት የአርሶ አደሮችንና የኢትዮጵያ መንግስትን ድጋፍና ከበሬታ አስገኝቶላቸዋል፡፡
ለኢትዮጵያ ህዝቦች፣ ለዱር እንስሳቶቿና ለተፈጥሮ አካባቢዋ የነበራቸው ፍቅር ወሰን አልነበረውም፡፡ ለዱር እንስሳትና ለአካባቢ ጥበቃ ያደርጉት የነበረው ጥረት፣ የላቀና በምሳሌነት የሚጠቀስ ነበር፡፡ ልማት፣ ሰላምና የአካባቢ ጥበቃ ያላቸውን የእርስ በርስ መስተጋብር እንዲጋሩ የአውሮፓና የሌሎች ሀገራት አምባሳደሮችን በማስተባበር የሰሜን ተራሮችን፣ በምዕራብና ደቡብ ኢትዮጵያ የሚገኙ ደኖችንና የቡና እርሻዎችን እንዲጐበኙ አድርገዋል፡፡ አምባሳደር ማርሻል ምንም እንኳ በቢሮ ውስጥ ከመቀመጥ ይልቅ በባሌ ወይም በሰሜን ተራሮች ላይ ድንኳን ተክለው ቢሰሩ በእጅጉ እንደሚያስደስታቸው የታወቀ ቢሆንም በስራ አመራራቸው፣ የስራ ባልደረቦቻቸውን በማስተባበርና በማነቃቃት ረገድ የባልደረቦቻቸውን አድናቆትና ከበሬታ ያስገኘ ችሎታ ነበራቸው፡፡ አምባሳደር ማርሻል ባለትዳርና የአንድ ወንድና የሁለት ሴቶች ልጆች አባት ነበሩ፡፡
..ሴት መሆንና በእድሜ መግፋት ለጡት ካንሰር.....
ስለተለያዩ በሽታዎች ንቃተህሊና ተፈጥሮ ቅድመ ጥንቃቄ እንዲኖር ወይንም ስለበሽታዎቹ ትኩረት ተሰጥቶ ተገቢው ሕክምና እንዲደረግ ለማሳሰብ የተለያየ ቀለም ያላቸው ሪቫኖች አገልግሎት ላይ ይውላሉ፡ ከእነዚህም ውስጥ አንዱ ፒንክ ሪቫን ነው፡፡ ፒንክ ሪቫን ኣለም አቀፍ እውቅና ያለው በጡት ካንሰር ላይ ንቃተህሊናን እንዲፈጥር ታልሞ የተሰራ ልዩ ምልክት ነው፡፡ ይህ ሪቫን ለእይታ ሲቀርብ ወይንም ስለሪቫኑ ሲነገር በጡት ካንሰር ለተጠቁ ሰዎች የሞራል ድጋፍ ይሆናል ተብሎ ይታመናል፡፡ ፒንክ ሪቫን በስፋት የሚነገርለትና ወደ እይታም ሆነ ወደ ጆሮ በስፋት የሚቀርበውና የሚሰማው የብሔራዊ የጡት ካንሰር ወር በሚከበርበት ወቅት ነው፡፡ ፒንክ ቀለም የተመረጠለት ሪቫን ከጡት ካንሰር ጋር ተቆራኝቶ መልእክት እንዲያስተላልፍ ሲደረግ 22/ ዓመት ሆኖታል፡፡ በዚያን ጊዜ መቀመጫውን በኒውዮርክ ከተማ ያደረገው ሱዛን ጂ ኮሜን komen ፋውንዴሽን እ.አ.አ በ1991/የጡት ካንሰር በሽታን ተቋቁመው ከበሽታው ነፃ መሆን ስለቻሉ ሰዎች የተዘጋጀ ውድድር ላይ ለተሳታፊዎች ሪቫኑ ከተበተነ በ ት ቀን ወዲህ ሪቫኑን መጠቀም ልማድ ሆኖ ቀርቷል፡፡
ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ፒንክ ሪቫን እ.ኤ.አ በ1992 ወይንም ከ21 ዓመታት በፊት ሰፊ እውቅና ተሰጥቶት የብሔራዊ የጡት ካንሰር ንቃተ ህሊና መፍጠሪያ ልዩ መለያ መሆን ችሎአል፡፡ የኤችአይቪ ኤይድስ ምልክት ከሆነው ቀይ ሪቫን ሐሳብ ተወስዶ ለጡት ካንሰር የተሰራው ፒንክ ሪቫን አሌክሳንድራ ፔኒ እና ከጡት ካንሰር በሽታ አገግማ ለመዳን በበቃችው ኤቭለን ላውደር ምክንያት ተፈጥሮ በመላው ኒውዮርክ እንዲሰራጭ ትላልቅ ለሆኑ የኮስሞቲክስ ኩባንያዎች ተሰጥተዋል፡፡ አሌክሳንድራ የሴቶች ጤናን አስመልክቶ በሚዘጋጀው የ..ሰልፍ.. መጽሔት ዋና አዘጋጅ ስትሆን ኤቭለን ደግሞ የ..ኤስ ላውደር.. ኮስሞቲክስ ኩባንያ ምክትል ፕሬዝዳንት ናት፡፡
ፒንክ ሪቫን ከሰማያዊ ሪቫን ጋር አብሮ ሲደረግ አጋጣሚው በጣም ጥቂት ቢሆንም በወንዶች ላይ ስለሚከሰተው የጡት ካንሰር አመላካች ይሆናል፡፡ ከ17/ ዓመታት በፊት የጆን ደብሊው ፋውንዴሽን መስራችና ፕሬዚዳንት የሆኑት ናንሲኒክ ሪቫኑን በሁለት ቀለም አቀናጅተው ሲፈጥሩ ..ወንዶችም የጡት ካንሰር ይይዛቸዋል.. የሚለውን ነጥብ ለማሳሰብና ግንዛቤውንም ለመፍጠር ሲሉ ነው፡፡ የፒንክ ሪቫን ቀለም ፒንክ የሆነበት ምክንያት ምእራባውያን አገሮች በሰነጾታ የሴቶች ተሳትፎን የሚገልጹበት በመሆኑ እና ቀለሙ ሴቶችን ስለመንከባከብ እንዲሁም ቆንጆ መሆንን ስለሚያመላክት ነው ብለው ያምናሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ፒንክ ቀለም ጥሩ መሆንንና ተባባሪ መሆንን ይገልጻል ተብሎም ይታመናል፡፡ ፒንክ ሪቫን ሲወሳ ፡- በጡት ካንሰር ላለመያዝ መጠንቀቅ፣ በበሽታው የተያዙ ለወደፊቱ ተስፋ እንዲያደርጉና የጡት ካንሰር በሽታን ለማጥፋት ንቅናቄ እንዲደረግ ያሳስባል፡፡
በጡት ካንሰር ላይ የሚሰሩ የተለያዩ ተቋማት ስራቸውን ከጡት ካንሰር ጋር ይበልጥ ለማቆራኘት ፒንክ ሪቫንን ይጠቀሙበታል፡፡ ፒንክ ሪቫንን ፡- መግዛት፣ ማድረግ ወይንም ለእይታ ማብቃት ...ሪቫኑን የያዘው ሰው ወይንም ተቋም ስለሴቶች ያላቸወን ጥንቃቄና እንክብካቤ ያሳያል፡፡ በየአመቱ ጥቅምት ወር ላይ በሺዎች ወይንም በመቶዎች የሚቆጠሩ ምርቶች በፒንክ ሪቫን ይወከላሉ ወይንም ደግሞ ፒንክ ቀለም እንዲኖራቸው ይደረጋሉ፡፡ በተጨማሪም ከምርቶቹ ሽያጭ ከሚገኘው ገቢ የተወሰነውን ስለጡት ካንሰር ስለሚደረግ ምርምርና ስለበሽታው ስለሚኖረው የግንዛቤ ማስጨበጫ እንቅስቃሴ እንዲውል ይደረጋል፡፡ የዛሬ ሰባት አመት 15/ሺህ ከብር የተሰሩ ሳንቲሞች ሮያል ካኔዲያን ሚንት የተሰኘው የካናዳ ሳንቲም አምራች ተቋም ሰርቷል፡፡ የሳንቲሞቹ አንደኛው ጎን የንግስት ኤልሳቤጥ ምስል የተቀረጸበት ሲሆን በሌላኛው ጎኑ ደግሞ ሪቫን ተቀርጾበታ፡፡
በዚህ ብቻ ያልተገታው የፒንክ ሪቫን ሳንቲሞች ስሪት የ25/ሳንቲም ዋጋ ያላቸው 30/ሚሊዮን ሳንቲሞች በአንዱ ጎናቸው ፒንክ ሪቫን ተቀርጾባቸው ለተለመደው የግብይት ስርአት እንዲውሉ ተሰራጭተዋል፡፡ በአንድ ጎኑ ቀለም ያለው ሳንቲም ሲቀርብ ፒንክ ሪቫን በታሪክ ሁለተኛው እንደሆነ ይነገራል፡፡ የጡት ካንሰርን በሚመለከት ስላለው አለም አቀፍ እውቅና ይህንን ህል ካልን የጡት ካንሰርን አመጣጥና ሕክምናውን ለአንባቢዎች ባልንበት ባለፈው እትም ዶ/ር አበበ በቀለ እንደገለጹት ሕመሙ በኢትዮጵያ ውስጥ መታከም የሚችል ሲሆን ነገር ግን ሕክምናው ውስን በሆነ ሆስፒታል መሰጠቱ አንዱ ጎጂ ነገር ነው፡፡ የጡት ካንሰር በኢትዮጵያ ውስጥ ምን ያህል ጎጂ ወይንም ገዳይ ነው የሚለውን ለመገመትም አስቸጋሪ የሚሆኑ ነገሮች እንደሚኖሩና ለዚህም እንደማሳያ ተደርጎ የሚወሰደው ብዙ ሰዎች ሕክምናውን በአቅራቢያቸው ስለማያገኙ እና ሕመሙም ወደተቀረው የሰውነት ክፍላቸው ከመሰራጨቱ አስቀድሞ እርምጃ የማይወስዱ ብዙዎች መሆናቸው ነው ብዋል፡፡
ዶ/ር አበበ በቀለ አክለው እንደገለጹትም ጡት ላይ ያበጠ ነገር ሁሉ ካንሰር አለመሆኑን ነው፡፡ ሰዎች በዚህ መደናገጥ አይገባቸውም፡፡ ሆኖም ግን ያበጠ ነገር ባእድ መሆኑን ካለመዘንጋት በፍጥነት ወደሐኪም ዘንድ መቅረብ ይጠቅማል፡፡ ጉዳዩ ከሐኪም ዘንድ ከደረሰ በሁዋላ ካንሰር ነው አይደለም ለማለት በመጠኑ ከእባጩ ሴል ላይ በመርፌ ለምርመራ ይወሰዳል፡፡ ነገር ግን ብዙ ሰዎች ሰውነን መርፌ ከነካው በሽታው ወደሌላ አንሌ ይሰራጨል ከሚል የተሳሳተ ግምት ሕክምናውን እስከነጭርሱም ትተውት ይሄዳሉ፡፡ ይሄ ሙሉ በሙሉ የተሳሳተ ውሳኔ መሆኑን ሁሉም ሊያውቀው ይገባል፡፡ ይህ ምርመራ መደረጉ የግድ መሆኑን እና ሰዎች እንደሚሉት አይነት ጉዳት የማያመጣ መሆኑን ከግምት ውስጥ በማስገባት ህክምናውን በተገቢው ማድረግ ይገባል፡፡ ምርመራውን ለማድረግ የሚፈጀው ጊዜ ከሁለት ደቂቃ ያልበለጠ ሲሆን ምላሹም በ24 ሰአት ውስጥ ይታወቃል፡፡ ስለዚህ ታማሚዎች ሳይረበሹ ምርመራውን ሐኪም በሚያዘው መሰረት ካካሄዱ መዳን ወይንም እድገቱን በመግታት መቆየት ይቻላል፡፡
ጡት ካንሰር ሁሉንም ሴቶች ወይንም ሰው አይይዝም፡፡ ነገር ግን ሁለት መንገዶች አሉት፡፡ 1/እድሜ፡- ማንኛዋም ሴት ከሰላሳ እና ሳላሳ አምስት አመት በፊት ሲሆናት የጡት ካንሰር እንዲያውም አይታይባትም ማለት ይቻላል፡፡ ከሰላሳ አምስት እስከ 50/ አመት አካባቢ ከሰላሳ ወይንም ከሰላሳ አምስት ሴቶች አንዱዋ ላይ ጡት ካንሰር ይታያል፡፡እድሜ ወደ ሰባ ሰማንያ ሲደርስ ከስምንት ሴቶች አንዷ ላይ የጡት ካንሰር ይከሰታል፡፡ ስለዚህ ሴት መሆንና በእድሜ መግፋት ለጡት ካንሰር ሊያጋልጥ ይችላል፡፡ 2/ሆርሞን፡- ሴቶች ላይ ኢስትሮጂንና ፕሮጀስትሮን የተባሉ ሆርሞኖች ይገኛሉ፡፡ የሰውነት ክፍል በብዛት ለኢስትሮጂን እየተጋለጠ ከሄደ ለጡት ካንሰር የመጋለጥ እድሉም የሰፋ ይሆናል፡፡ ኢስትሮጂን በብዛት ያላቸው ሴቶች የወር አበባ ከ13/አመት በፊት የሚያዩ ወይንም የወር አበባቸው ሳይቋረጥ እስከ ሀምሳ እና ሀምሳ አምስት አመት ድረስ የሚቆይባቸው ናቸው፡፡ ልጅ ሳይወልዱ የሚኖሩ ወይንም መጀመሪያ ልጃቸውን ከሰላሳ አመት በሁዋላ የሚወልዱ እንዲሁም ወልደው ጡት ያላጠቡ ሴቶች እና ለተለያየ ምክንያት ኢስተትሮጂንን ለሕክምና ወይንም እንደምግብ የወሰዱ ሴቶች ብዙውን ጊዜ ለጡት ካንሰር ሕመም ይጋለጣሉ ብለዋል ዶ/ር አበበ በቀለ፡፡ ....ባለፈው ሳምንት እትም ዶ/ር አበበ ፈለቀ ተብሎ የተጻፈው ዶ/ር አበበ በቀለ በሚል እርምት እንዲነበብ ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡..
አርቲስት ፈቃዱን በባንኮክ ለማሳከም ርብርቦሹ ቀጥሏል *ለህክምናው 450 ሺ ብር ያስፈልጋል
በነርቭ ሕመም እየተሰቃየ ለሚገኘው አርቲስት ፍቃዱ አያሌው የሕክምና ገንዘብ ለማሰባሰብ ታስቦ ባለፈው ግንቦት 16 የተከፈተው የስዕል አውደርእይ እስከ ፊታችን ረቡዕ እንደሚቀጥል አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ አርቲስቱን በባንኮክ ለማሳከም 450ሺ ብር እንደሚያስፈልግ ታውቋል፡፡ አርባ አርቲስቶች ሥራቸውን በአውደርእዩ አሳይተው ሽያጩን በቀጥታ ለሰዓሊው መታከሚያ ለማዋል አቅደው የነበረ ሲሆን አሁን የአርቲስቶቹ ቁጥር 68 መድረሱን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በአውደርዕዩ ላይ ከሚሳተፉ አንጋፋና ወጣት ሰዓሊያን መካከል ዘርይሁን የትም ጌታ፣ ታደሰ መስፍን፣ መዝገቡ ተሰማ፣ ወርቁ ጐሹ፣ ብርትኳን ደጀኔ፣ ሮቤል ተመስገን፣ ሃይሉ ክፍሌ ይገኙበታል፡፡ በአውደ ርዕዩ ላይ የቀረቡ ስእሎች ከአንድ ሺህ እስከ አስራ አምስት ሺህ ብር በመሸጥ ላይ እንደሆኑ አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአለ ሥነጥበባትና ዲዛይን ትምህርት ቤት የ2001 ዓ.ም የከፍተኛ ማእረግ ተመራቂ የሆነውን አርቲስት ፍቃዱ አያሌውን ባንኮክ፣ ታይላንድ ለማሳከም ከ450ሺህ ብር በላይ የተጠየቀ ሲሆን ይህንኑ ከግምት በማስገባት አውደርእዩ የተዘጋጀበት የአዲስ አበባው ጣይቱ ሆቴል ባለቤቶች በቀን ሁለት ሺህ ብር ይከራይ የነበረውን አዳራሽ ለ12 ቀናት በነፃ ፈቅደዋል፡፡ ከዚህም ሌላ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ እና ከጀርመን የልማት ተቋም (GIZ) ድጋፍ ተጠይቆ ምላሽ እየተጠበቀ ሲሆን ሰዓሊው ከእለት ወደ እለት ህመሙ እየጠናበት እንደሆነም ተገልጿል፡፡ ሠዓሊ ፍቃዱን መርዳት የሚፈልጉ በስልክ ቁጥር +2510919193132 እና +251911635840 ደውለው መርዳት እንደሚችሉ አዘጋጆቹ አስታውቀዋል፡፡
በቢግ ብራዘር አፍሪካ ቤቲ እና ቢምፕ ኢትዮጵያን ይወክላሉ
በ8ኛው የቢግ ብራዘር አፍሪካ ሪያሊቲ ሾው ከሚሳተፉት 28 ተወዳዳሪዎች ሁለት ኢትዮጵያውያን እንደሚገኙበት ታወቀ፡፡ ሁለቱ ኢትዮጵያውያን የ26 ዓመቷ መምህር እና የአዲስ አበባ ነዋሪ የሆነችው ቤቲ እና በደቡብ አፍሪካ ነዋሪና ተማሪ የሆነው የ23 ዓመቱ ቢምፕ ናቸው፡፡ መላው አፍሪካ በቀጥታ ስርጭት በሚያየው ውድድር በመሳተፌ ልዕልት አድርጎኛል ያለችው ቤቲ በውድድሩ ካሸነፈች በሽልማት ገንዘቡ የትራቭል ኤጀንሲ ማቋቋም እፈልጋለሁ ብላለች፡፡ በቢግ ብራዘር አፍሪካ ላይ በመሳተፍ የማገኘው ልምድ አጓጉቶኛል ያለው ቢምፕ በበኩሉ ፤ ውድድሩ ሃገሩን ለማስጠራት የሚችልበት መልካም አጋጣሚ እንደሆነ ገልፆ፤ ማሸነፍ ከቻለ በአዲስ አበባ የመዝናኛ ክለብ የመክፈት ሃሳብ እንዳለው ተናግሯል፡፡ ከመምህርነት ሙያዋ ባሻገር በአስተርጓሚነት የምትሰራው ቤቲ በቢግ ብራዘር አፍሪካ ኢፊሴላዊ ድረገፅ እራሷንነ ስትገልፅ ብልህ፤ በራስ መተማመን ያላት፤ ወሳኝ ሁኔታዎች በቁርጠኝነት የምጋፈጥ ነኝ ብላለች፡፡
ቀጠሮ አክባሪ፤ ምክንያታዊ እና ብዙ የሚያወሩ ሰዎችን እንደምትጠላ የምታሳውቀው ቤቲ መፅሃፍ የማነበብ ዝንባሌ እንዳላት አመልክታ ከሁሉ ማንበብ የምትወደው የግል ማስታወሻዋን እንደሆነ ገልፃለች፡፡ አፍሪካውያን ማንኛውንም ነገር ማሳካት እንደሚችሉ ለዓለም ህዝብ ያሳዩ ህዝቦች ናቸው የምትለው ቤቲ በደብረዝይት ያለው ኩሪፍቱ ሪዞርት ተወዳጅ መዝናኛዋ እንደሆነ ገልፃ የዓለም ሙዚቃ እና ፊልም ወዳጅ በመሆኗ ሆሊውድን ለማየት ሁሌም ያጓጓኛል ብላለች፡፡ ትውልዱ በአዲስ አበባ ቢሆንም አሁን በሚማርበት ደቡብ አፍሪካ የሚኖረው ቢምፕ በበኩሉ ራሱን ታማኝ፤ ግልፅ፤ አስተማማኝ እና ሃላፊነት ተቀባይ አድርጎ ይገልፃል፡፡ አፍሪካውያን ጓደኞች እንግዳ ተቀባዮች እና ብዙ አስደናቂ የባህል መስቦች ያሏቸው ህዝቦች ናቸው የሚለው ቢምፕ በቢግ ብራዘርስ ላይ በመካፈል በቲቪ መታየቱን መላው ቤተሰቡ ስለወደደለት ደስ ብሎኛል ብሏል፡፡
“የመንፈስ ከፍታ” ሰኞ ይመረቃል
በገጣሚና ጋዜጠኛ በረከት በላይነህ የተፃፈው “የመንፈስ ከፍታ” የተሰኘ የግጥም መድበል ሰኞ በ11፡30 በዋቢሸበሌ ሆቴል ይመረቃል፡፡ በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች የተከፋፈለው “የመንፈስ ከፍታ”፡ የገጣሚው 48 ያህል ወጥ ግጥሞችና፣ ጃላላዲን ሩሚን ጨምሮ ሌሎች የታወቁ የፋርስ ገጣሚያን የፃፏቸው 31 ትርጉም ግጥሞች ተካተውበታል፡፡ በምረቃ ስነስርአቱ ላይ ታዋቂ ወጣትና አንጋፋ ገጣሚያን ስራዎቻቸውን ያቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የመጽሐፉ ዋጋ 30 ብር ነው፡፡ ገጣሚው በቅርቡም “ንፋስ አፍቃሪዎች” የተሰኘ የግጥም ሲዲ አሳትሞ ለገበያ ለማቅረብ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡
“የኮሌጅ ቀን ግጥሞች” ነገ ለውይይት ይቀርባል ሚዩዚክ ሜይ ዴይ የውይይት ስፍራ ቀየረ
በየሁለት ሳምንቱ በመፃሕፍት ላይ የንባብ እና የውይይት መድረክ በማድረግ የሚታወቀው ሚዩዚክ ሜይ ዴይ የመወያያ ሥፍራውን ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም ሬዲዮ ፋና አካባቢ ወደሚገኘው ብሔራዊ ቤተመፃሕፍትና ቤተመዛግብት ድርጅት (ወመዘክር) አዛወረ፡፡ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተመፃሕፍትና ቤተመዛግብት አዳራሽ ለውይይት የሚቀርበው መጽሐፍ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ በ1993 ዓ.ም ያሳተመው የኮሌጅ ቀን ግጥሞች” የተሰኘ የግጥም መድበል እንደሆነ ታውቋል፡፡
በመጽሐፉ ከተሰነዱት ግጥሞች መካከል የኃይሉ ገብረዮሐንስ (ገሞራው) “በረከተ መርገም” እና የዮሐንስ አድማሱ “እስቲ ተጠየቁ” ይገኙበታል፡፡ መነሻ ሃሳብ በማቅረብ ለሶስት ሰዓታት የሚዘልቀውን ውይይት የመሻ ሃሳብ በማቅረብ የሚመሩት የሥነጽሑፍ ባለሙያው የዶክትሬት ዲግሪ ተማሪ ገዛኸኝ ፀጋው ናቸው፡፡
ቢል ክሊንተን በንግግር አቅራቢነት 106 ሚ.ዶ አግኝተዋል
የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ቢል ክሊንተን ከዋይት ሃውስ ከወጡ ወዲህ ባለፉት 12 አመታት በተለያዩ ቦታዎች ንግግር በማቅረብ ብቻ 106 ሚሊዮን ዶላር ማግኘታቸው ሲኤንኤን ዘገበ፡፡ ቢል ክሊንተን በአንድ መድረክ ንግግር ለማቅረብ በአማካይ 200ሺ ዶላር ይከፈላቸዋል፡፡ የቀድሞው ፕሬዝዳንት በንግግር አዋቂነታቸው በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ተፈላጊ ናቸው፡፡ በናይጄርያ ሌጎስ በአንድ መድረክ የተከፈላቸው 700ሺ ዶላር በተመሳሳይ የስራ ድርሻ የተገኘ ትልቁ ክፍያ እንደሆነ ታውቋል፡፡
ቢል ክሊንተን በንግግር አዋቂነታቸው አምና ከፍተኛ ተፈላጊነት እንደነበራቸው የሚገልፀው ሲኤንኤን በመላው ዓለም በ73 መድረኮች በመስራት 17 ሚሊዮን ዶላር እንደተከፈላቸው ገልጿል። ቢሊ ክሊንተን 42ኛው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት የነበሩ ናቸው፡፡ በበጎ አድራጊነት፤ በንግግር አዋቂነት ፤ በዴሞክራት ፖለቲከኛነት እና በጥብቅና ሙያቸው ከፕሬዝዳንትነት ከወረዱ በኋላ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያላቸው ቢል ክሊንተን 80 ሚሊዮን ዶላር ሃብት እንዳላቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡
የዓለም ሃብታሙ የኤሌክትሮኒክስ ሙዚቃ ዲጄ ታወቀ
ከኤሌክትሮኒክስ ሙዚቃ ዲጄዎች፣ ሆላንዳዊ ዲጄ ቲዬስቶ 75 ሚሊዮን ዶላር መሪነቱን እንደያዘ ሴለብሪቲ ኔትዎርዝ ገለፀ። ለግሉ በገዛው ጄት አውሮፕላን በመላው ዓለም በመዘዋወር የሚሰራው የ44 ዓመቱ ዲጄ ቲዬስቶ፣ በአማካይ ለአንድ ምሽት ስራ እስከ 250ሺ ዶላር እየተከፈለው ባለፈው ዓመት ብቻ ሃያ ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝቷል። ቲዮስቶ፣ በሙዚቃ መሸጫ ሱቅ እየሰራና ፒዛ እየተላላከ ይኖር እንደነበር አስታውሶ፣ ዲጄነትን የጀመረ ጊዜ ባንድ ምሽት ሃምሳ ዶላር ብቻ ይከፈለው እንደነበር ገልጿል።
ከዲጄነት ጎን ለጎን፣ እንደ ሌሎቹ ዲጄዎች በሙዚቃ ፕሮዲውሰርነትና በአቀናባሪነት እየሰራ አምስት ሙሉ አልበሞችን እና ሶስት የሪሚክስ አልበሞችን ለገበያ አብቅቷል፡፡ ባንድ ምሽት በአማካይ ከ100ሺ እስከ 500ሺ ዶላር ከሚከፈላቸው ታዋቂ የኤሌክትሮኒክስ ሙዚቃ ዲጄዎች መካከል አንዳንዶቹ፣ የግል ጄት አውሮፕላንና ውድ ቪላ እየገዙ ለቅንጦት ኑሮ ገንዘባቸውን ሲያፈሱ ይታያሉ። ሴሌብሪቲ ኔትዎርዝ ባወጣው የዲጄዎች ደረጃ፣ ከሁለተኛ እስከ አምስተኛ የወጡት ከሃምሳ እስከ ስድሳ ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ሃብት ያላቸው ዲጄዎች ናቸው።
በቅርፃ ቅርጽ የተዋበው የአዳማው ኤግል ሆቴል
እናት ህፃን ልጇን አዝላ ከገበያ እየተመለሰች ነው፡፡ በዘንቢሏም እቤት ለሚጠብቋት ልጆቿ የሚሆን ሙዝ፣ ሸንኮራ አገዳና መሰል ቁሶች ይዛለች፡፡ የእናታቸውን ከገበያ መመለስ የተመለከቱ ህፃናት ልጆቿና ውሻቸው እናቲቱን ለመቀበል ወደ እሷ ሲሮጡ የሚያሳየው ሥዕል ዓይንን ጨምድዶ የሚይዝ ቅርፅ ነው፡፡ የግርማችን ፒ ኤል ሲ ሥራ አስኪያጅና የአክሲዮኑ አባል አቶ አንዷለም ግርማ “ከሁሉ በላይ ይኼ ምሥል ልቤን ይገዛዋል፡፡ ይህ ነገር የእኔም፣ የአንቺም የሁሉም ሰው እውነተኛ የህይወት ነፀብራቅ ነው” ይላሉ፡፡ ገበያ ሄዳ ሸንኮራና ሙዝ ለልጇ ይዛ ያልመጣች እናት አለች ብለው እንደማያምኑም አጫውተውኛል፡፡ ሌሎች ሥዕሎችም በብዛት ይታያሉ፡፡ በህንፃው ስር ባለው ሰፊ በር ወደ ውስጥ ሲዘልቁ ነው የቤቱን ተዓምራት መመልከት የሚጀምሩት፡፡ ገና ሲገቡ መሬት ላይ ባለው ሰፊ ባር መሀል ላይ ትልቋና ባለ ግርማ ሞገሷ ንስር፣ ክንፏን ዘርግታ ምንቃሯን ከፈት አድርጋ ይመለከታሉ፡፡
እሱን አይተው ሳይጠግቡ ንስሯ በተቀረፀችበት ፏፏቴ ዙሪያ የተደረደሩት የዝሆን ምስል ያላቸው ወንበሮች እንደገና ያስገርምዎታል፣ እዛው ላይ ቆመው ዞር ዞር እያሉ ግድግዳውን መቃኘት ሲጀምሩ ደግሞ “ለመሆኑ ይኼ ቤት ሆቴል ነው ወይስ ሙዚየም” ብለው እንደሚጠይቁ ጥርጥር የለኝም፡፡ በግድግዳው ላይ ተቀርፀው በልዩ የቀለም ህብር ካማሩ ሥዕሎች ውስጥ ፍቅር፣ ጭፈራ፣ የአባ ገዳ ሥርዓት፣ የእርቅ ሥርዓት፣ የፈረስ ግልቢያ፣ የክሊዮፓትራ ምስል፣ የገጠሩ ሕዝብ አኗናር…በስዕልና በቅርጽ ያልተዳሠሠ ነገር የለም፡፡ ይህን ትንግርት የሚመለከቱት በአዳማ ከተማ መብራት ኃይል ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ቀበሌ 06 ሞቅ ደመቅ ካሉት የምሽት ጭፈራ ቤቶች በአንዱ ነው፡፡ ታዲያ ለሥራም ይሁን ለመዝናናት ወደ ከተማዋ ጐራ ያለ ማንኛውም ሰው፣ አካባቢውን ሳይጐበኝ ይመለሳል ለማለት ይቸግራል፡፡ አንዳንዶች አካባቢውን “የአዳማው ቺቺኒያ” ይሉታል፡፡
በዚሁ አካባቢ ግን አንድ ትልቅ ኤግል ተፈጥሯል፡፡ ኤግሉ ከዚህም በፊት የነበረና ገበያ የነበረው ሆቴል ሲሆን ወደ ትልቅ ኤግልነት ለመቀየር አራት አመት ፈጅቷል፡፡ ተጠናቆ ስራ ከጀመረም ገና ሦስት ወሩ ነው፡፡ የቤተሠቡ ጊዜና ጉልበት ሳይታሠብ 55 ሚሊዮን ብር የጨረሠው አዲሱ ኤግል፣ 40 የመኝታ ክፍሎችን የያዘ ባለ ሰባት ፎቅ ህንፃ ነው፡፡ ኤግል ሆቴል በአምስት ወንድማማቾች፣ በእህትና በእናታቸው በወ/ሮ አበበች ወ/ሥላሴ የተመሠረተ አክሲዮን ነው፡፡ የቤተሰቡ መነሻ አርሲ ውስጥ በአርባ ጉጉ አውራጃ ጮሌ በተባለች መንደር ውስጥ ሲሆን አባታቸው አቶ ግርማ ኃይሉና ባለቤታቸው ወ/ሮ አበበች ወ/ሥላሴ የቢዝነስ መሠረታቸው ሆቴል እንደሆነ የአክሲዮኑ ሥራ አስኪያጅ አቶ አንዷለም ግርማ ይናገራሉ፡፡
ልጆቻቸውን በፍቅርና በስራ ገርተው ያሣደጉ ጠንካራ ወላጆች እንደነበሩ የሚናገሩት አቶ አንዷለም፤ ታላላቆቻቸውም ሆነ ታናናሾቻቸው ከልጅነት ጀምሮ ደረጃ በደረጃ ሥራን ከቤተሠብ ጋር እየለመዱ እየተዋደዱና እየተከባበሩ ማደጋቸውን ይገልፃሉ፡፡ “ለምሣሌ እኔን ብትወስጂ አርሲ በነበረን ሆቴልና ሥጋ ቤት ውስጥ ለሰው ስጋ በማድረስ፣ ከዚያ ለቆራጭ በማቀበል ብሎም ሥጋ ቆራጭ በመሆን ደረጃ በደረጃ ሠርቻለሁ” በማለት የስራ ተሞክሯቸውን አጫውተውኛል፡፡ “የቤተሰቡ ትልቁ የትምህርት ደረጃ 12ኛ ክፍልን ማጠናቀቅ ነው፣ ከዚያ በላይ የተማረ የለም” ያሉት አቶ አንዷለም ፤ ከሰባት ዓመት ዕድሜያቸው ጀምሮ አዳማ ውስጥ እንዳደጉ ይናገራሉ፡፡ ትልቁ ኤግል ከመሠራቱ በፊት ከኪራይ ቤቶች የተከራዩት ትንሽ ሆቴል እንደነበር ገልፀው፤ ትንሹም ሆቴል በጣም ደማቅና የከተማዋን ሁኔታ ያገናዘበ እንደነበር ያብራራሉ፡፡ “ሆቴሏ በጣም ብዙ ገበያና ጥቅም የምታስገኝ ነበረች” የሚሉት የፒኤልሲው ስራ አስኪያጅ፤ በቤተሠቡ ውስጥ ያለው ትልቅ ነገርን መስራት እንደሚቻል የማመን ብቃት አሁን ትልቁን ኤግልና በውስጡ የዓይን ማረፊያ የሆነውን የባህል የፍቅር፣ በአጠቃላይ የጥበብ ሥራ መፍጠሩን ገልፀው፤ ወረቀት ላይ ያሠፈሩት ቅርፅና ሥዕል በቤተሰባችን አዕምሮ ውስጥ ተቀርፆ ያለቀውን ነው” ይላሉ አቶ አንዷለም፡፡
የተዋበ ሆቴል ለመሥራት የነበራቸውን ፍላጎት ሲናገሩ “ሰው በመጠጥና በምግብ ሰውነቱን ከመሙላት ባለፈ አዕምሮውም ምግብና እረፍት እንደሚያስፈልገው በማመን ነው የሠራነው” የሚሉት ሥራ አስኪያጁ፤ ይኼ ሲሠራ ግን ቀጥታ ዒላማው ገንዘብ ያመጣል የሚል ሳይሆን ሰዎች የበለጠ ምቾት እንዲሰማቸው ማድረግ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ወደ ሆቴሉ ቅኝት ስንመለስ ፏፏቴው ሲለቀቅ የተለያዩ ትዕይንቶች ይታያሉ፡፡ ለምሳሌ ኤግሏ የተቀረፀችው ወፎች ውሃ ሲነካቸው ለማራገፍ ክንፋቸውን በሚዘረጉበት ዓይነት ነው፡፡ ከሁሉም ያስገረመኝ ቅርፅ ደግሞ እነሆ፡- አንዲት እንቁራሪትና አንድ ህፃን ፊት ለፊት ተፋጠው ተቀምጠዋል፡፡ ፏፏቴው ሲለቀቅ እንቁራሪቷ ህፃኑ ላይ ትተፋለች፤ ህፃኑ ደንግጦ ሲያያት የሚያሳይ ቅርፅ ነው፡፡ ነገሩ ለህፃናት መዝናኛነት ታስቦ ቢሠራም ትልልቆችንም የሚያፈዝ ነው፡፡ ሁለቱን ፎቅ ወጥተው ቴራሱ ላይ ሲደርሱ እንደ ፔንዱለም ወዲህ ወዲያ የሚወዛወዝ ወንበር ያገኛሉ፡፡ ይህ ወንበር መኻል ላይ ጠረጴዛ ያለውና ፊት ለፊት ለሚቀመጡ ሰዎች በተለይም ህፃናት እየተወዛወዙ እንዲዝናኑ የታሰበ ቢሆንም በወንበሩ እየተወዛወዙ ሲዝናኑ ያየናቸው ግን አዋቂዎች ናቸው፡፡ አጠቃላይ የሆቴሉ አሠራር የአምፊ ቴአትር (ጣሪያ የሌለው) አይነት ነው ፤ለምሣሌ ቴራስ ላይ ቁጭ ብለው አቆልቁለው፣ አሊያም አግድመው በየፎቆቹ ላይ ያሉትን ትዕይንቶች በግልፅ ለመመልከት ምቹ ነው፡፡ በሆቴሉ የተለያዩ ግድግዳዎች ላይ በፈረንሳይኛ፣ በጀርመንኛና በቻይንኛ ቋንቋ ኤግል ሆቴል የሚሉ ፅሁፎች ተፅፈዋል፡፡
አቶ አንዷለም ስለዚሁ ሲያስረዱ፤ ትንሿ ኤግል እያለችም ሆነ አሁን ትልቁም ከተሠራ በኋላ የሦስቱም አገር ዜጐች የሆቴሉ ተጠቃሚዎች በመሆናቸው የእነሱን ቀልብ ለመሳብ የተደረገ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ሆቴሉ የተሠራው የከተማዋን ነዋሪ ከግምት ውስጥ በማስገባት ነው ያሉት አቶ አንዷለም፤ ከከተማው ነዋሪ በተጨማሪ ከሌላ ቦታም የሚመጣ ሰውና የውጭ አገር ቱሪስቶችም የሚስተናገዱበት እንደሆነ ያብራራሉ፡፡ “ቤቱ ደረጃውን የጠበቀ ነው፤ ነገር ግን ቢራ 17 ብር ይሸጣል፣ ድራፍት 13 ብር ነው ይሄ ቫትን ጨምሮ ነው” የሚሉት ስራ አስኪያጁ፤ ምግብም ቢሆን በ40 እና በ50 ብር መካከል መሆኑን ይናገራሉ፡፡ አልጋዎቹ ሶስት ደረጃ ያላቸውና ደረጃቸውን የጠበቁ ሲሆኑ ከ280 ብር እስከ 480 ብር ዋጋ ተተምኖላቸዋል፡፡ ይኼም አቅምን ግምት ውስጥ አስገብቶ የተተመነ እንደሆነ አቶ አንዷለም አጫውተውናል፡፡ ሆቴሉ በአሁኑ ሰዓት ለ235 ቋሚ ሠራተኞች የሥራ ዕድል ፈጥሯል፡፡ በአሁኑ ሰዓት በሆቴሉ የሰው ኃይል አስተዳደር ሆነው በኃላፊነት እየሠሩ የሚገኙት አቶ አቡ፤ የብዙ ሙያ ባለቤት ናቸው፡፡
ከመምህርነት ሙያ ጀምሮ በርካታ ሥራዎችን ሰርተዋል፡፡ በሆቴሉ የቅርፃቅርፆች ሥራ ላይ በስፋት የተሳተፉ ሲሆን በውስጣቸው የነበረውን የአርት ሙያ እዚህ ሆቴል ቅርፃቅርፆች ላይ እውን በማድረጋቸው ደስተኛ ናቸው፡፡ “በኤግል ሆቴል ግንባታ ውስጥ አንድም አርት ያልሆነ ነገር የለም” በማለት አስተያየታቸውን የጀመሩት አቶ አቡ፤ ኤግሏን ለመስራት በተለይ ማንቁርቷ በርካታ ጊዜ ፈርሶ እንደተሠራ ይገልፃሉ። ኤግል በአለም ላይ በርካታ ታሪኮች እንዳሏት የሚናገሩት አቶ አቡ፤ የጥንካሬ፣ የውበት፣ የጠንካራ እይታ እና የመሰል ጥራት መገለጫዎች መሆኗን ጠቁመው በአጠቃላይ ከሆቴሉ እቅድ ጀምሮ በአርቱም ላይ በመሳተፋቸው ጭምር ደስተኛ እንደሆኑም ይናገራሉ፡፡ አርቱ ከግንባታው ጐን ለጐን በተጓዳኝ የተሠራ በመሆኑ ቅርፃቅርፆቹም አራት ዓመት እንደፈጁ ነው የሚናገሩት፡፡ አቶ አቡ መምህር በነበሩበት ጊዜ አርት ስኩል ውስጥ የመማር እድል የገጠማቸው ቢሆንም እንደ አባታቸው ኢንጂነር የመሆን ፍላጐት ስለነበራቸው ትምህርታቸውን ማቋረጣቸውን ገልፀው፤ ሆኖም የአርት ፍቅራቸው እየጠነከረ ሲመጣ ከግርማችን ፒ ኤል ሲ ባለ ድርሻዎች አንዱ ሆነው ህልማቸውን እውን ለማድረግ በመብቃታቸው ደስተኛ ናቸው።
የግርማችን ፒኤልሲ ባለ አክሲዮኖች የቢዝነስ መሠረት ምንም እንኳ ሆቴል ቢሆንም በአሁኑ ሰዓት በትራንስፖርት ዘርፍ፣ በህንፃ መስታወት ገጠማና መሰል ቢዝነሶች መሠማራታቸውን አቶ አንዱአለም ይናገራሉ፡፡ አሁን ኤግል ሆቴል ካለበት ሥፍራ አጠገብ የማስፋፊያ ቦታ እየጠየቁ ነው፡፡ የመሰብሰቢያ አዳራሽ፣ የመዋኛ ሥፍራ፣ የህፃናት መጫወቻና አረጋውያን ለብቻቸው በትንሽ ክፍያ የሚዝናኑበት የራሣቸው የሆነ ደረጃውን የጠበቀ መዝናኛ የማሠራት ሀሣብ እንዳላቸው የግርማችን ፒ ኤል ሲ ባለድርሻዎች ይናገራሉ፡፡ “ስለ አረጋዊያኑ መዝናኛ ማሰባችንን ለእናታችን ስናጫውታት ‘ይህ ትልቁ ሐሣብ ነው’ በማለት ደስታዋን ገልፃልናለች” የሚሉት አቶ አንዷለም ፤ የጊዜ ጉዳይ እንጂ እንደሚሳካ ጥርጥር እንደሌላቸው ይናገራሉ፡፡ በአዳማ ከተማ ትልቅ የእንግዳ ማረፊያ በመገንባትም ላይ ይገኛል፡፡ አቶ አንዷለም እንዳጫወቱን፤ እንግዳ ማረፊያው አስራ ስምንት ክፍሎች የሚኖሩት ሲሆን አንዱ ክፍል መኝታ፣ ሳሎን፣ መታጠቢያና ማብሰያ ክፍሎችን ያጠቃልላል፡፡ እንግዳው የሚፈልገውን ነገር አብስሎ ለመመገብ እንዲችል የታሠበ ሲሆን እቃ ለመግዛት ሩቅ ሄዶ እንዳይቸገር በግቢው ውስጥ ደረጃውን የጠበቀ ሱፐር ማርኬት ይኖረዋል፡፡
የሚያበስልለት የሚፈልግ ከሆነም በገስት ሀውሱ ውስጥ ዝግጁ የሆኑ ሠራተኞች ይኖራሉ ተብሏል፡፡ ኤግል ሆቴል ፊት ለፊት አስፓልቱን ተሻግሮ “ናሽናል” የተሠኘ ታዋቂ ጭፈራ ቤት አለ፡፡ ጭፈራ ቤቱ በግርማችን ፒኤልሲ ባለቤትነት የሚመራ ነው፡፡ ይህ ጭፈራ ቤት ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ሊገነባ ዲዛይኑ አልቆ በጀት እንደተመደበለት የሚናገሩት አቶ አንዷለም፤ እጅግ ዘመናዊና የከተማዋን ደረጃ በጠበቀ መልኩ ሊሠራ ዝግጅቱ ተጠናቋል ብለዋል፡፡ የኤግል መኝታ ክፍሎች ውስጥ በሁለት አቅጣጫ ሲቆሙ ማለትም በምስራቅና በምዕራብ የከተማዋን የተለያዩ ገጽታዎች መቃኘት ይችላሉ። ለምሣሌ የመኝታ ክፍሎቹ ውስጥ ቆመው ወደ ምዕራብ ሲመለከቱ ከሆቴሉ ከምድር ቤቱ ባር ጀምሮ አጠቃላይ የሆቴሉን እንቅስቃሴ መቃኘት ይችላሉ፡፡
አሻግረው ሲመለከቱ ትልቁን ገልማ አባገዳ፣ የንፋስ ኃይል ማመንጫውን ተሽከርካሪና በርካታ የከተማዋን ክፍል ይመለከታሉ፡፡ ይህን ሆቴል በሚያስፋፉበት ጊዜ የገጠማቸው ችግር ምን እንደሆነ ጠይቀናቸው ሲመልሱ “አሁን ደስተኛ ብንሆንም በፊት ግን ፈተና የሆነብን ለማስፋፊያው ሲባል 11 አባወራዎች መነሣት ነበር” ይላሉ አቶ አንዷለም፡፡ ምንም እንኳ ይኖሩበት የነበረው ቤት በጣም ጠባብ ቢሆንም ከለመዱበት ቦታ ማስነሣቱ ፈታኝ እንደነበር አስታውሠው፤ ከከተማው መስተዳድር ጋር በመነጋገር ቦታ ተመርጦ ለእያንዳንዱ አባወራ 80ሺህ ብር በማውጣት አምስት አምስት ክፍል ቤት አሠርተው ማስረከባቸውን ገልፀዋል፡፡
በገንፎ የተሠራ ጥርስ አያስቅ፣ አያስፍቅ!
ከብዙ ጊዜ ጀምሮ ስለአንድ በዕብደቱ ስለሚታወቅ የኢራን ሰው የሚተረት አንድ ወግ አለ፡፡ ይህ ዕብድ በዋና ዋና መንገዶች ላይ ባሉ አደባባዮች ዙሪያ ብቻ ነው የሚገኘው፡፡ አንድ አደባባይ አጠገብ መጥቶ ዙሪያውን መዞር ከጀመረ መቆሚያ የለውም፡፡ መሽቶ ጨልሞበት ወደ ማደሪያው እስከሚሄድ ድረስ መዞሩን ይቀጥላል፡፡ “ወዴት ትሄዳለህ?” ይሉታል ሰዎች ጠዋት፡፡ “ወደ አደባባዬ ነዋ!” ይላል፡፡ “አደባባዩን ማን ሰጠህና?” “እኔ የተፈጠርኩት ለአደባባይ መሆኑን አታውቁም? አደባባይስ የተፈጠረው ለእኔ መሆኑን አታውቁም?” እያለ እየዘፈነ ይሄዳል፡፡ ዕብዱ፤ ዋንኛ ጠባዩ ሰው አለመንካቱ ነው፡፡ “ሰውን ትሰድበዋለህ እንጂ አትመታውም” ይላል፡፡
“ለምን?” ይሉታል ሰዎች፤ ሊያጫውቱት፡፡ “የሰው ልጅ ሲደበደብ ይደድባል፡፡ ሲሰደብ ግን ብልጥ ይሆናል” “እንዴት?” “ለመልስ የሚሆን ስድብ ሲያዘጋጅ ማሰብ ይጀምራል፡፡ የስድብ ትምህርት ቤት ስለሌለ፤ ኦርጅናሌው የስድቡ ባለቤት እሱ ይሆናል” ሌላው የዚህ ዕብድ ጠባይ አንድ ጠዋት መናገር የጀመረውን ነገር በጭራሽ አይለውጠውም፡፡
ለምሳሌ አንድ ጠዋት፤ “የማይጮህ ህዝብ ምላሱ መቆረጥ አለበት!” ይላል፤ ካልን ቀኑን ሙሉ፤ “የማይጮህ ህዝብ ምላሱ መቆረጥ አለበት” ሲል ይውላል፡፡ በሚቀጥለው ጠዋት፤ “ሞኝ ያሥራል ብልጥ ይማራል!” ይላል፡፡ “The smarter prisoner yet learns. The fool governer forever imprisons” እንደ ማለት) ቀኑን ሙሉ ይቀጥላል፡፡ ደሞ ሌላ ጠዋት፤ “የሚዘምሩ ወፎች አሉ፡፡ የሚያርፉበት፤ ጐጆ እሚሠሩበት ዛፍ ግን የላቸውም” ይላል፡፡ እንዲህ እንዲህ ሲል ከርሞ አንድ ቀን ጠዋት፤ “ንጉሡ ጭንቅላታቸውን በርዷቸዋል!!” እያለ እየደጋገመ መጮሁን ቀጠለ፡፡ የአገሪቱ ፀጥታ አስከባሪ ኃላፊ፤ “አሁንስ አበዛው!” ብለው አንድ ፖሊስ አስገድዶ እንዲያስረው ላኩበት፡፡ ዕብዱ መሮጥ ጀመረ፡፡ “የዕብድ ጉልበት አያልቅም” ይባላል፡፡ ፖሊሱ ግዴታው ነውና የሚፈፅመው እየሮጠ መከተሉን ቀጠለ፡፡ ዕብዱ ያደባባዩን ዳር ዳር ይዞ ዙሪያውን ነው የሚሮጠው።
እንደወትሮው ከመስመሩ አይወጣም፡፡ ወደአደባባዩ ውስጥም አይገባም፡፡ ፖሊሱ ደከመውና ቆመ፡፡ ይሄኔ ዕብዱ ከት ከት ብሎ ሳቀና፤ “ሞኝ በመሆንህ ነው እንጂ የት እሄድብሃለሁ? ከአደባባይ የበለጠ እሥር ቤት የት አለና ነው? ይልቅ ሰው ከአደባባይ እንዳይጠፋ ማረግ ነው የሚሻለው!” አለ ይባላል፡፡
* * *
አካባቢያችንን እንፈትሽ፡፡ አደባባዩ ምሽግ ያደረገውንና ዕውነት የሚናገርበትን እንለይ፡፡ አገራችንን እናጥና፡፡ ዙሪያ ገባውን ማትሮ ጣራውንም ግርጌውንም በዐይነ ቁራኛ አይቶ ነው፡፡ የዘንድሮ ጉዞ፡፡ እንኳን የካዝና ግድግዳ የአዕምሮ ሽንቁርም አደገኛ ነው፡፡ “በራቸውን ሳይዘጉ ሌባ ሌባ ይላሉ” አለች አሉ ውሻ፡፡ ሌባው ቢያዝም እንኳ አሁንም በሩ ክፍት ከሆነ ለአዲስ ሌባ ምቹ መሆኑ አይቀርም፡፡ ህጉ ወደ ኋላ አይሰራም፤ ተመስገን ነው፤ በሚል በጊዜ ሰርቄ አምልጫለሁ፤ የሚልንስ እንዴት እንደምናስተናግደው ማጤን አለብን፡፡ ከጥንት ጀምሮ በውል እንደሚታወቀው ለሀገሩ ህልውና፣ ለሉዓላዊነቱ፣ ቀናዒ ህዝብ ነው ያለን። “ያልጠረጠረ ተመነጠረ” የሚለው ወዶ አይደለም፡፡ ተደጋግሞ ለጥቃት አጋልጦት ነው፡፡
አለ ነገር አለ ነገር ቁልቁለቱን ወርደን ወንዙን ስንሻገር”፤ ይላል አርቆ እያሰበ፡፡ ከላይ እስከታች፣ ነገር አለ፣ እያለ እየተጠራጠረ፣ መጓዝን የመረጠ ነው፡፡ መጠራጠርን እንተው ቢባልም እሚጠራጠር ካለ መጠርጠር መጥፎ አደለም፡፡ አንዱ ጓዳ ውስጥ ሲያንጐዳጉድ ሌላው ሳሎን እንደሚወራች አሊያም በተገላቢጦሹ ሊከሰት ይችላል፡፡ የውስጥ ችግሮቻችንን ዐይተው ባላንጦቻችን እንደሚጠራሩ መቼም ቢሆን መዘንጋት አይገባም። “ለነገር ይሁን ለፍቅር” ለዩ፤ ይላሉ አበው፡፡ ስለተጠራሩብን ጆሮአችንን በየአቅጣጫው ማቅናት ይጠበቅብናል፡፡ “እዚያ ማዶ ሆኖ ክፉ ሰው ተጣራ፤ እዚህ ማዶ ሆኖ ክፉ ሰው ወይ አለው፤ ጐበዝ ተጠንቀቁ፣ ይህ ነገር ለኛ ነው!!” ማለትም የአባት ነው፡፡ “ብቻውን የበላ ብቻውን ይሞታልን” አለመርሳትም ብልህነት ነው፡፡ በጥቃቅን መብራት በበራባቸው ነጥብ - ቦታዎች፣ በተመረጡ ወንጀሎች፣ በተመረጡ ሰዎች ላይ ስናተኩር ያልተመረጡትን ማየት ይሳነናል፡፡ ከመካከላቸውም ንፁሃኑን መለየት ይቸግረናል፡፡ ሁለመናችንን እንይ ጐበዝ፡፡ ሁሉም ከተበላሸ ወይም ሁሉም ከተሳሳተ ችግር ነው “በገንፎ የተሠራ ጥርስ፤ አያስቅ፤ አያስፍቅ” ማለት ሥረ - ነገሩ ይሄው ነው፡፡