Administrator

Administrator

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በአገሪቱ የተለያዩ ከተሞች በሚገኙ አመራሮችና አባላቱ ላይ በገዢው ፓርቲ የድብደባ፣ የእስርና የግል ሚስጥር መበርበርና በተደራጀ ሁኔታ የመዝረፍ ድርጊት እየተፈፀመ መሆኑን ገለፀ፡፡
ፓርቲው “ህጋዊና ሠላማዊ ትግላችን በህገወጥ የአፈና ስልት ሊደናቀፍ አይችልም” በሚል ትናንት ባወጣው መግለጫ ላይ፤ መንግስት አንድነት ፓርቲን በሀሰት ፕሮፖጋንዳ ከማጣጣልና ያለ አግባብ ከአክራሪነት ጋር ለማቆራኘት ከመስራት አልፎ ሠላማዊ ሠልፎችና ህዝባዊ ስብሰባዎቹ እንዲደናቀፉ አፈና እያደረገበት እንደሚገኝ ገልጿል፡፡
በወላይት ሶዶና በመቀሌ የፓርቲው አመራሮችና አባላት ላይ የመደብደብ፣ የማሰር፣ የግል ሚስጥር የመበርበርና በተደራጀ ሁኔታ የመዝረፍ ድርጊት እንደተፈፀመበት ጠቅሶ፣ ፖሊስ ድርጊቱን አይቶ እንዳላየ ማለፉን ገልጿል፡፡
ፓርቲው በነገው እለት በጂንካ፣ በአርባ ምንጭ፣ በመቀሌ፣ በወላይታ፣ በባህርዳርና በአዲስ አበባ የሚያካሂዳቸውን ሠላማዊ ሰልፎችና ህዝባዊ ስብሰባዎችን ለማደናቀፍ በገዢው ፓርቲ አፈናና ወከባ እየተፈፀመበት እንደሚገኝም ጠቁሟል፡፡
አንድነት ህግን መሰረት አድርጐ እየተንቀሳቀሰ በመሆኑ በነገው ዕለት ሊካሄዱ የታሰቡት ሁሉም ሠላማዊ ሰልፎችና ህዝባዊ ስብሰባዎች በተያዘላቸው እቅድ መሰረት እንደሚከናወኑና ህጋዊ እርምጃው በህገወጥ አፈናው ምክንያት እንደማይቀለበስ በመጥቀስ፣ መላው አገሪቱ ህዝብ በነቂስ ወጥቶ የታፈነ ድምፁን እንዲያሰማ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

በህንዳዊው መምህርና ፀሐፊ ሚ/ር ጆሴፍ ፍራንሲስ የተዘጋጀ “የድንቂቱ ኢትዮጵያ ድንቃድንቆች” (“This is Ethiopia – A Book of Fascinating Facts”) የተሰኘ ስለ ኢትዮጵያ የተለያዩ ድንቅ መረጃዎችን ያካተተ አዲስ መፅሐፍ የፊታችን ረቡዕ ከምሽቱ 12 ሰዓት ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉጌታ ሰኢድ ዳምጠው በተገኙበት በካፒታል ሆቴል ይመረቃል፡፡
መፅሐፉ፤ ኢትዮጵያን ልዩ የሚያደርጋትን ከ245 በላይ መረጃዎች ያካተተ ሲሆን የተዘጋጀበትም ዓላማ፤ በተለይ የውጭ አገር አንባቢያንና ዳያስፖራዎች፣ ስለ ኢትዮጵያ መረጃዎችን በቀላሉና በአጭሩ እንዲቀስሙ ለማድረግ ነው ተብሏል፡፡ በመፅሐፉ ጀርባ ላይ አስተያየታቸውን ያሰፈሩት የታሪክ ባለሙያው ፕ/ር ሪቻርድ ፓንክረስት፤ “ስለ ኢትዮጵያ ብዙ የማናውቃቸው አስደናቂ ነገሮች መኖራቸውን… መፅሃፉ እንድንገነዘብ ያደርገናል፡፡ መፅሃፉ ያካተታቸው መረጃዎች ብዙ አንባቢዎችን ሊያስደምሙ የሚችሉ ናቸው” ብለዋል፡፡
መፅሃፉ በእንግሊዝኛና በአማርኛ የተዘጋጀ ሲሆን ትርጉሙን የሰራው ደራሲ አማረ ማሞ ነው፡፡ የውስጥ ገፆቹ ሁሉ ባለቀለም ሆነው የተዘጋጀው “የድንቂቱ ኢትዮጵያ ድንቃድንቆች” መጽሐፍ መረጃዎች በተዋቡ ምስሎች ተደግፈው ቀርበውበታል፡፡ ላለፉት 30 ዓመታት ኢትዮጵያ ውስጥ በመምህርነት ያገለገለው ሚ/ር ጆሴፍ ፍራንሲስ፤ ከዚህ ቀደም “የአድዋ ጦርነት”፣ “ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ” እና “የአፄ ቴዎድሮስ ልጅ፣ ልዑል ዓለማየሁ” የተሰኙ የልጆችና ወጣቶች መፃህፍትን አሳትሟል፡፡

“ቦሌ ፒኮክ ጋ ጠብቂኝ” በተሰኘው የሰለሞን ፍስሀ መጽሐፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተመዛግብት እና ቤተመጻሕፍት አዳራሽ ውይይት እንደሚካሄድ ሚዩዚክ ሜይደይ አስታወቀ፡፡ ውይይቱን የሚመሩት ሃያሲ እና የወግ ጸሐፊ መስፍን ሀብተማርያም እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

የጋዜጠኛና ገጣሚ ተስፋዬ ገብረማርያም “የማይሆን ዓለም” የተሰኘ ግጥሞች፣ አጫጭር ልቦለዶች እና ወግ የተካተቱበት መጽሐፍ ነገ በሐገር ፍቅር ትያትር ቤት ትንሿ አዳራሽ እንደሚመረቅ “ሀሳብ መልቲሚዲያ” አስታወቀ፡፡ በ62 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፣ በ20 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ጋዜጠኛና ገጣሚ ተስፋዬ በ“ኢትዮ ቻናል” ጋዜጣ ማህበራዊ ጉዳዮች አምድ ጸሐፊነቱና በዛሚ 90.7 ኤፍ ኤም ሬዲዮ በሚያቀርበው “ድርሻችን” የተሰኘ በአካል ጉዳተኞች ላይ ያተኮረ ፕሮግራም ይታወቃል፡፡

“ዜማ ቃል” የተሰኘ ወርሃዊ የጥበብ ምሽት ሐሙስ ከቀኑ 10፡30 ጀምሮ  በሐገር ፍቅር ትያትር ቤት ትንሿ አዳራሽ እንደሚቀርብ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ ለአንድ ዓመት በሚዘልቀው ዝግጅት፣ የገጣሚያን፣ ጸሐፍትና ኮሜዲያን  ሥራዎች የሚቀርብበት ሲሆን የመግቢያ ዋጋው በነፍስ ወከፍ 50 ብር እንደሆነ ዝግጅቱን የሚያስተባብረው ፈለቀ ካሳ ጥንድ ፕሮሞሽን  ጠቁሟል፡፡ 

በዶ/ር ሱዛን ጄፈርስ የተፃፈው “Feel the Fear and Do it Anyway” የተሰኘ መፅሃፍ፤“ፍርሃትን ማሸነፍ” በሚል ርእስ በቢኒያም አለማየሁ ተተርጉሞ ለንባብ በቃ፡፡ መጽሐፉ አሉታዊ አመለካከትን ስለማስወገድ፣ ውሳኔዎችን በሥራ ስለ መተግበር፣ ፍርሃትን ስለ ማጥፋት እና ሌሎች ተያያዥ ቁም ነገሮችን የያዘ ነው፡፡ 192 ገፆች ያሉት መፅሃፉ፤ ዋጋው 40.50 ብር ነው፡፡
በሌላም በኩል “በአራጣ የተያዘ ጭን” የተሰኘ የአጫጭር ልቦለዶች መድበል ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ በዮፍታሔ ካሳ የተደረሰው መጽሐፍ፤ በ233 ገፆቹ አስራ ዘጠኝ አጫጭር ልቦለዶች ይዟል፡፡ በኤች ዋይ ኢንተርናሽናል ማተሚያ ቤት የታተመውን መጽሐፍ፤ ሊትማን ጀነራል ትሬዲንግ የሚያከፋፍለው ሲሆን ዋጋውም 46.99 ብር ነው፡፡
በተመሳሳይ “ከመለስ ሞት በስተጀርባ” የተሰኘ መጽሐፍ በዚህ ሳምንት ለንባብ በቃ፡፡ መፅሃፉ በኢትዮጵያ፣ በግብፅ፣ በአባይ ግድብ፣ በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ እና ሌሎች ጉዳዮች ዙርያ ያጠነጥናል፡፡ በ70 ገጾች የተዘጋጀው መጽሐፉ፤ ለገበያ የቀረበው በ32 ብር ነው፡፡ በመፅሃፉ ውስጥ ከተካተቱት ፎቶግራፎች መካከልም በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግስት የሃምሳ ብር ኖት ላይ የወጣው የአባይ ግድብን የሚያሳይ ምስል ይገኝበታል፡፡

ከሁለት ወር በፊት ራሷን ከጡት ካንሰር ለመታደግ ሁለት ጡቶቿን በቀዶ ጥገና ያስወገደችው አንጀሊና ጆሊ፤ለመላው ዓለም ስለ ጡት ካንሰር አስከፊነት ባስጨበጠችው ግንዛቤ ከፍተኛ አድናቆትን እንዳተረፈች ተገለፀ፡፡ ዝነኛዋ የሆሊውድ አርቲስት ህክምናውን ለማግኘት የወሰደችው ፈጣን እርምጃና ለመላው ዓለም ግልፅ መረጃ በማቀበል ባሳየችው ድፍረት የተመላበት ተግባር በህክምና ባለሙያዎች ዘንድ ተወድሶላታል። “ተግባሯ በሙያችን መነቃቃትና ግንዛቤ እንዲፈጠር ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበርክቷል” ብለዋል - ባለሙያዎቹ፡፡ የስድስት ልጆች እናት የሆነችው የ37 ዓመቷ አንጀሊና ጆሊ፤ሁለት ጡቶቿን የሚያስወግድ ቀዶ ህክምና ባታደርግ ኖሮ 87 በመቶ ለጡት ካንሰር፣ 50 በመቶ ለማህፀን ካንሰር ትጋለጥ እንደነበር ታውቋል፡፡ አንጀሊና በኒውዮርክ ታይምስ ላይ ባሰፈረችው ፅሁፍ፤ ህክምናውን ለመውሰድ የወሰደችው እናቷ በ56 ዓመታቸው በተመሳሳይ ችግር ለሞት በመዳረጋቸው እንደሆነ ገልፃለች። በመላው ዓለም በየዓመቱ ከ45ሺ በላይ ሴቶች በጡት ካንሰር እንደሚሞቱ መረጃዎች ያመለክታሉ።

“ኤ ሎንግ ዎክ ቱ ፍሪደም” በተሰኘው የኔልሰን ማንዴላ ግለታሪክ መፅሃፍ ላይ ተመስርቶ የተሰራው አዲስ ፊልም ከወር በኋላ በመላው ዓለም መታየት እንደሚጀምር ተገለፀ፡፡ ፊልሙ የደቡብ አፍሪካውያንን የነፃነት ትግል ለመላው ዓለም ለማስተዋወቅ ታልሞ የተሰራ ነው ተብሏል፡፡
በጉበት ኢንፌክሽን በጠና ታመው በሆስፒታል ህክምና ሲደረግላቸው የቆዩት ኔልሰን ማንዴላ፤ ከሳምንት በፊት 95ኛ ዓመት የልደት በዓላቸው የተከበረላቸው ሲሆን አሁን ከህመማቸው ማገገማቸው ታውቋል፡፡
“ማንዴላ፡ ኤ ሎንግ ዎክ ቱ ፍሪደም” በሚል ርእስ በተሰራው ፊልም ላይ የማንዴላን ገፀባህርይ የሚተውነው እንግሊዛዊው ተዋናይ ኤድሪስ ኤልባ እንደሆነ ታውቋል፡፡ የ40 ዓመቱ ኤዲሪስ ኤልባ በፊልሙ ላይ ልዩ የትወና ብቃት እንደሚያሳይ ከወዲሁ የተነበየው ዘ ጋርድያን፤ ይሄም ለኦስካር ሽልማት ሊያሳጨው እንደሚችል ግምቱን አስፍሯል። “ማንዴላ፡ ኤ ሎንግ ዎክ ቱ ፍሪደም” የተሰኘው ፊልም በነፃነት ታጋዩ የልጅነት፤ የአስተዳደግና የትምህርት ሁኔታ እንዲሁም የ27 ዓመታት የእስር ቆይታ እና ደቡብ አፍሪካን በፕሬዝዳንትነት እስከመሩበት ጊዜ ድረስ ያለውን ሂደት የሚተርክ መሆኑን “ዘ ስዌታን” ጠቁሟል፡፡ እ.ኤ.አ በ1994 ዓ.ም በማንዴላ ተፅፎ ለንባብ የበቃው ግለ ታሪክ መፅሃፍ በመላው ዓለም ከ15 ሚሊዮን በላይ ቅጂዎች እንደተሸጡ ለማወቅ ተችሏል፡፡

አጓጊው ዜና ምንድነው?
ዋርነር ብሮስ የተባለው የፊልም ኩባንያ እና ዲሲ ኮሚክስ እ.ኤ.አ በ2015 ባትማንና ሱፐርማንን በማጣመር ልዩ ፊልም እንሰራለን ማለታቸው ነው፡፡ ፊልሙ በሚቀጥለው ዓመት ቀረፃው የሚጀምር ሲሆን እውቆቹ የ“ሱፐርማን ሪተርንስ” ዳሬክተር ዛክ ስናይደር እና የ“ባትማን” ፊልም አካል የሆነው “ዘ ዳርክ ናይትስ” ዳሬክተር ክሪስቶፈር ኖላን በጥምረት ይሰሩበታል ተብሏል፡፡
ፊልሙን ለመሥራት እንዴት ታሰበ ?
የልዕለ ጀግና ጀብደኛ ገፀባህርያትን በመፅሃፍ እና በፊልም በመስራት ስኬታማ የሆነው ዲሲ ኮሚክስ፤ ባትማንና ሱፐርማንን በአንድነት በማጣመር ለመስራት የወሰነው አምና ማርቭል ኮሚክስ፤ የልዕለ ጀብደኛ ገፀባህርያትን ያሰባሰበውን “ዘ አቬንጀርስ” ለእይታ በማብቃት በመላው ዓለም 1.5 ቢሊዮን ዶላር ገቢ መሰብሰቡን በማየት ነው፡፡
እነማን ይተውኑበታል?
ዘንድሮ ለእይታ በበቃው በ“ሱፐርማን ሪተርንስ” ፊልም ላይ በመስራት ባሳየው ብቃቱ የተደነቀው ሄነሪ ካቪል ሱፐርማንን ሲተውን ፤ ባትማንን ለመተወን ደግሞ በ“ዘ ዳርክ ናይትስ” ላይ የተወነው ክርስቲያን ቤል ታጭቷል - ማረጋገጫ ባይገኝም፡፡


ባትማንና ሱፐርማን በንፅፅር
*በካርቱን መፃህፍት ላይ ተመስርተው በመሰራት ትርፋማ ከሆኑት የሱፐርሂሮ ጀብደኛ ገፀባህርያት ባትማንና ሱፐርማን ግንባር ቀደም ናቸው፡፡
የባትማን ገፀባህርይ በመፅሃፍ፤ በፊልም፤ በዲቪዲ ሽያጭ እና ሌሎች ንግዶች በመላው ዓለም 12 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ሲያስገኝ የሱፐር ማን ገፀባህርይ ደግሞ በተመሳሳይ ዘርፍ 5 ቢሊዮን ዶላር አስገኝቷል፡፡
ዘንድሮ ለእይታ የበቃው እና በዳሬክተር ዛክ ስናይደር የተሰራው “ማን ኦፍ ስቲል ሱፕርማን ሪተርንስ” 700 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ተገኝቶበታል፡፡
ባትማን ሰብዓዊ ፍጡር ያለው ገፀባህርይ ሲሆን ሱፐርማን ግን ከሰብዓዊ ፍጡር የላቀ ተሰጥኦ ያለው ልዩ ፍጥረት ነው፡፡
ባትማን ልዩ ሃይልና ተሰጥኦ ባይኖረውም በሳይንስና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም እና ጠቅላላ እውቀት የተገነባ የላቀ አዕምሮ ያለው ጀብደኛ የልዕለ ጀግና ገፀባህርይ ነው፡፡ ባትማን በምርመራ ችሎታው እና በሃብታምነቱም ይለያል፡፡ ሱፐር ማን ደግሞ መብረር የሚችል፤ከፍተኛ ጥንካሬ ያለውና በላቀ ተሰጥኦው የተለያዩ ጀብዶችን የሚያከናውን እንዲሁም ሰብዓዊ ፍጡር ሊያደርጋቸው የማይችላቸውን ተግባራት በቀላሉ የሚሰራ ገፀባህርይ ነው፡፡

  • ሚሊዮኖች በንፁህ ውሃ እጦት ሳቢያ ለህልፈት ይዳረጋሉ 
  • የተበከለ ውሃ - ለታይፎይድ፣ ኮሌራ፣ የአንጀት ቁስለትና የጉበት ብግነት ያጋልጣል

ሰለሞን ፍቃዱ፤ በተደጋጋሚ እየተመላለሰ የሚያሰቃየው የሆድ ቁርጠት በሽታ፣ ቋሚ መፍትሔ ለማግኘት አለመቻሉ አሳስቦታል፡፡ በሽታው በተነሳበት ቁጥር የሚመላለስባቸው ክሊኒኮች ቁና ሙሉ መድሃኒት እያሸከሙት መመለሱን ለምዶታል፡፡ ታይፎይድ፣ ታይፈስ፣ የአንጀት ቁስለት፣ ጃርዲያና ባክቴሪያ ለበሽታው ከሚሰጡት ስሞች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ የእነዚህ በሽታዎች መነሻ ምክንያቱ ደግሞ ንጽህናው ያልተጠበቀ ውሃና የተበከለ ምግብ እንደሆነ ሐኪሞቹ ደጋግመው ነግረውታል፡፡ በዚህ ምክንያትም በየሆቴሉና በየሬስቶራንቱ መመገቡን እርግፍ አድርጐ ከተወው ሰነባብቷል፡፡
ሆኖም በየጊዜው እያገረሸ አቅል የሚያሳጣው ህመሙ አልተወውም፡፡ ግራ ቢገባው ስለሚጠጣው ውሃ ማሰብ ያዘ፡፡ ከቧንቧ እየቀዳ የሚጠጣው ውሃ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተለየ ጣዕምና ሽታ ማምጣቱን ሲያስታውስ፣ ችግሩ ምናልባትም ከውሃው ሊሆን ይችላል ሲል አሰበ፡፡ ግን ደግሞ በቧንቧ የሚመጣው ውሃ የተጣራና ንጽህናው የተረጋገጠ እንደሆነ ሲነገር በተደጋጋሚ ሰምቷል፡፡ ታዲያ ውሃው እንዴት ሆኖ እሱ ለገጠመው ችግር መነሻ ይሆናል? ማሰብ ጀመረ፡፡ የአራትና የአምስት ዓመት ዕድሜ ያላቸው ልጆቹም የተሟላ ጤና ካጡ ሰነባብተዋል፡፡ የህፃናቱ ችግር ንጽህናውን ያልጠበቀ ምግብና ውሃ ሊሆን እንደሚችል ሃኪማቸው ሲናገር ሰምቷል፡፡ ጥርጣሬው ከፍ ሲል ውሃውን በብርጭቆ እየቀዳ ማስተዋል ጀመረ፡፡ በብርጭቆ ውስጥ እየዘቀጡ የሚቀሩት ቆሻሻዎች ጥርጣሬውን አባባሱት፡፡ ስለጉዳዩ ለሃኪሙ መንገር እንዳለበት ወሰነና ነገረው፡፡ ሃኪሙም ውሃ በቧንቧ ስለመጣ ብቻ ንፁህ ነው ብሎ መጠቀሙ አደጋ እንዳለውና የቧንቧ ውሃም በተለያዩ ምክንያቶች ሊበከልና ለጤና እጅግ አደገኛ ሊሆን እንደሚችል አስረዳው፡፡
ይህንን ችግር ለማስወገድም የመጠጥ ውሃን በሚገባ አፍልቶና አቀዝቅዞ መጠቀም እንደሚገባ፣ አለበለዚያም በተለያዩ የማከሚያ መድሃኒቶች በማከም መጠቀም ተገቢ እንደሆነ አብራራለት፡፡ በየጊዜው እየተከሰተ ለሚያሰቃየው የጤና ችግር መነሻው፣ የሚጠጣው ውሃ መሆኑን ማወቁ እፎይታ ቢሰጠውም የችግሩ ቋሚ መፍትሔ አለመገኘት አሳስቦታል፡፡ ለማን አቤት ይባላል? በከተማዋ እንዲህ አይነት ችግር ሲከሰት የሚቆጣጠረውና መፍትሔ የሚሰጠው አካል ማነው? ሰለሞን ይጠይቃል፡፡
ችግሩ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለከተማ፣ አለም ባንክ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ነዋሪ የሆነው የሰለሞን ፍቃዱ ችግር ብቻ አይደለም፡፡ በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች ያሉ በርካታ የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ አገልግሎት ደንበኞች የሚያነሱት ችግር ነው፡፡ የከተማዋ ነዋሪዎች በአብዛኛው የሚጠቀሙበትን ውሃ የሚያገኙት ከቧንቧ ነው፡፡ የከተማው ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን 368ሺ ቆጣሪ ያላቸው ደንበኞች ያሉት ሲሆን ከገፈርሳ፣ ለገዳዲና ድሬ ግድቦችና የማጣሪያ ሥፍራዎች እንዲሁም 110 ከሚደርሱ ጉድጓዶች በቀን 374ሺ ሜትር ኪዩብ ውሃ እያመረተ ለነዋሪው እንዲሰራጭ ያደርጋል፡፡ ውሃው ለህብረተሰቡ ከመድረሱ በፊት በተለያዩ ዘመናዊ የውሃ ማጣሪያ መንገዶች ተጣርቶና በአስተማማኝ ሁኔታ ተዘጋጅቶ እንዲሁም በርካታ የማጣራት ሂደቶችን አልፎ እንደሚሰራጭ ቢነገርም አንዳንድ ጊዜ በቧንቧ የሚመጣው ውሃ የደፈረሰና ለጤና አደገኛ የሆነ ውሃ እንደሆነ ይነገራል፡፡ ውሃውን ሳያፈሉ መጠቀም ለበርካታ የጤና ችግሮች እንደዳረጋቸው መሆኑንም የከተማ ነዋሪዎች ይገልፃሉ፡፡ በቧንቧ የሚመጣው ውሃ የተጣራና ለጤና ጎጂ የሆኑ ባክቴሪያዎች እንዳይኖሩበት በቂ ማጣራትና ህክምና እንደሚደረግለት የሚናገሩ የባለስልጣን መ/ቤቱ የሥራ ኃላፊዎች፣ አንዳንድ ጊዜ የውሃ ቧንቧዎች ሲሰበሩና ጉዳት ሲደርስባቸው የቆሸሸና የደፈረሰ ውሃ በቧንቧ ሊመጣ እንደሚችል ይገልፃሉ፡፡
በተለይ አሁን ከመንገድ ሥራ ግንባታው ጋር በተያያዘ በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ የውሃ ቧንቧዎች በመሰበራቸው ምክንያት በውሃው ንጽህና ላይ ችግር እያስከተሉ መምጣታቸውንም እነዚሁ ኃላፊዎች ይጠቁማሉ፡፡ ይህ ችግር በተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን በግልጽ ተነግሮ፣ ሕብረተሰቡ ለመጠጥነት የሚጠቀመውን ውሃ በማፍላትና በማቀዝቀዝ ወይንም በተለያዩ የማከሚያ መድሃኒቶች አክሞ እንዲጠቀም ማድረጉ ተገቢ መሆኑን የጤና ባለሙያዎች ይመክራሉ፡፡ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የውስጥ ደዌ ስፔሻሊስት ዶ/ር ታደሰ ተስፋዓለም ስለዚሁ ጉዳይ ሲናገሩ፣ የተበከለ ውሃ ለታይፎይድ፣ ኮሌራ፣ የአንጀት ቁስለትና የጉበት ብግነት በሽታዎች እንደሚዳርግ ጠቁመው፣ እነዚህ በሽታዎች በቀላሉና በፍጥነት ከአንዱ ሰው ወደ ሌላው ለመተላለፍ የሚችሉ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ በወቅቱ ህክምና ካልተገኘም ታማሚውን ለሞት የሚያበቁ ገዳይ በሽታዎች ናቸው ብለዋል፡፡
ንጽህናው ያልተጠበቀና በሚገባ ተጣርቶ ያልታከመ ውሃን መጠቀም ለትንሹ አንጀታችን መቁሰልና ለተቅማጥ በሽታ እንደሚዳርገን የሚናገሩት የህክምና ባለሙያው፣ በንፁህ የመጠጥ ውሃ እጦት ሳቢያ የሚከሰተው የተቅማጥ በሽታ በህፃናት ላይ ጐልቶ የሚታይ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ የተቅማጥ በሽታ በወቅቱ ህክምና ካላገኘና በተቅማጥ መልክ የሚወጣውን የሰውነታችንን ፈሳሽ ሊተካ የሚችል ንጥረ ነገር ካላገኘ፣ታማሚውን ለህልፈት የሚዳርግ በሽታ መሆኑን የሚናገሩት ዶ/ር ታደሰ፣ እንዲህ እንደአሁኑ የክረምት ወቅት በሚሆንበት ጊዜ ውሃ በተለያየ መንገድ ሊበከል ስለሚችል፣ በተቻለ መጠን በቤት ውስጥ በማጣራት፣ በማፍላትና በማቀዝቀዝ እንዲሁም የውሃ ማከሚያ መድሃኒቶችን በመጨመር መጠቀሙ አማራጭ የሌለው መፍትሔ ነው ሲሉም ያክላሉ፡፡
በክረምት ወራት የሚከሰቱ የጤና ችግሮች በአብዛኛው ከውሃ ጋር ተያይዞ የሚከሰቱ ናቸው ያሉት ዶ/ር ታደሰ፣ በአገራችን በየአመቱ ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ህዝብ በንፁህ መጠጥ ውሃ እጦት ሳቢያ በሚከሰቱ የጤና ችግሮች ለህልፈት እንደሚዳረግም ጠቁመዋል፡፡ ለመጠጥነት የሚውለውን ውሃ በማጣራት፣ በማፍላትና፣ በማከም በዚህ ሳቢያ የሚከሰተውን የጤና ችግርና ሞት ማስቀረት እንደሚቻልም ገልፀዋል፡፡ በቀላሉ ልንከላከለውና ልናስወግደው በምንችለው ችግር ሳቢያ፣ ለህመምና ለሞት ከመዳረግ መጠንቀቁ ከሁላችንም የሚጠበቅ ተግባር ነው ሲሉ የጤና ባለሙያው ያሳስባሉ፡፡