Administrator

Administrator

በኤርትራዊው ሠዓሊ ሰለሞን ኣብርሓ የተዘጋጁ ሥዕሎች የሚቀርቡበት ያልታ የ“ዕይታ” የሥዕል አውደርዕይ ባለፈው ማክሰኞ በጣልያን የባህል ማዕከል የተከፈተ ሲሆን በነገው ዕለት እምደሚዘጋም ታውቋል፡፡ በኤርትራዊው ስደተኛ የተሳሉ በርካታ ሥእሎች የተካተቱበት አውደርዕይ ዓላማ “የኢትዮጵያ እና ኤርትራ ህዝቦችን በማቀራረብ ወደ አንድነት ለማምጣት የበኩሌን አስተዋፅኦ ለማበርከት ነው” ብሏል፤ ሰዓሊው፡፡ሠዓሊው ካሁን ቀደም በኤርትራ የደቀመሃሪ መንደፍራ እና ሳዋ ከተሞች ሽልማት ባስገኙለት የሥዕል ትርኢቶች አውደርዕዮች ለይ መሳተፉን ለማወቅ  ተችሏል፡፡

Monday, 07 April 2014 15:56

ህልመኛው ክንፈኛ

ከትከሻዬ ጫፍ ግራና ቀኝ ካለው፣
ጉቶ የመሳሰለ ብቅ ያለ መሰለኝ፣
ይኸ እንግዳ ነገር እጅጉን ገረመኝ፡፡
የህልም ነገር ሆኖ መች አድሮ መች ውሎ፣
አየሁታ ወዲያው ጉቶው ክንፍ አብቅሎ፡፡
ወደፊት ወድሬ ሁለቱን እጆቼ፣
እግሬን ወደ መሬት ወደታች ዘርግቼ፣
በእነዚህ ረጃጅም ሰፋፊ ክንፎቼ፣
ከፍ ከፍ ወደ ላይ፣
ወዲያ ወደ ሰማይ!
አየሩን ቀዝፌ፣
ሄድሁ ተንሳፍፌ፡፡
ዕድሜዬን በሙሉ መሬት ተጣብቄ፣
አንድ ሜትር እንኳ ከፍ ያላልሁ ርቄ፣
ይኸው አየሩ ላይ ቀጨሁት ዓለምን፣
ያከራርመውና ዕድሜ ይስጥልኝ ህልሜን፡፡
እያደር ግን ኋላ ስካነው መብረሩን፣
ልክ እንደ ጭልፊቷ ሽው እልም ማለቱን፣
ጅው ብዬ ወርጄ ልክ እንደ የሎሱ፣
ወይ እንደ ድራጎን ያየር ላይ ንጉሱ(ሡ)፣
ይመስለኛል ያሰብሁ ልመካ በክንፌ፣
ያሻኝኝ ለመውሰድ ከመሬት ጠልፌ፡፡
አንዳንዱን ክፉ ሰው ላጥ አደርገውና፣
አንጠልጥዬ ወደ ላይ ርቄ እወስደውና፣
እንደ ሥራው መጠን ከድንጋይ ዓለቱ፣
ከጥልቅ ውቅያኖስ አልያም ከጅረቱ፣
ለቅቄ ስተወው ላይመለስ ከቶ፣
እረካለሁ መሰል ሳየው ሲቀር ሞቶ፡፡
ደግሞም ሆዳሙን ሰው ብድግ አደርግና፣
ፊቱን ወደ መሬት ዘቅዝቄ አይና፣
እጥለው መስሎኛል ጭው ካለው መሬት፣
አራዊት አምባ ምድር ሰው ከማይኖርበት፡፡
ይኸ ባለጌውን አለብላቢት ምላስ፣
የባጡን የቆጡን ቀባጥሮ የሚላላስ፣
ሳያስበው ድንገት ሁለት እጁን ይዤ፣
ከሰዎች መካከል ይህን ሰው መዝዤ፣
ወደ ላይ ወስጄው እዚያ ላይ አምጥቄ፣
ያዝ ለቀቅ አድርጌው ነፍሱን አስጨንቄ፣
ለቅቄ ስተወው ከላይ ደመናው ጥግ፣
ወደ ታች ወረደ ሄደ ሲምዘገዘግ፡፡
የሞተ መሰለኝ ምላሱን ጎልጉሎ፣
ብረት ምሰሶ ላይ በልቡ ተተክሎ፡፡
ሃይ የሚል የሌለው ከልካይም ተቆጪ፣
እኔው ራሴ ሆኜ ፈራጅ ዳኛ ቀጪ፣
ክንፎቼ እንዳይረግፉ እየለመንሁ ዕድሜ፣
እየቀጣሁ አለሁ ባለጌውን በህልሜ፡፡
ደግሞስ ማን ደርሶብኝ እንዴት ተነክቼ፣
ሽው ነው ወደ ላይ እብስ በክንፎቼ፡፡
ይህን ህልም እያየሁ ሳልነሳ ካልጋ፣
ሌቱ በረዘመ ጨርሶ ባልነጋ፡፡
ምን እንደ ህልም አለ፣ ከቶ ሌላ የለም፤
ህልመኛው ክንፈኛ አድራጊ ፈጣሪ …
        የሆነበት ዓለም፡፡
ይዘቱም መጠኑም የተስተካከለ፣
እንደዚህ እንደኔው ያለመ ሰው ካለ፣
ወደኔ ብቅ በሉ ሰማችሁኝ ሰዎች?
በጉዳዩ እናውራ የሌት አላሚዎች፡፡
በዝርዝር እንንገር ይህንን ሁኔታ፣
ምስጢሩን ገላልጦ ህልም ለሚፈታ፡፡
    ከአምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
የካቲት 2006 ዓ.ም

Monday, 07 April 2014 15:55

የፍቺ ነገር!

በአሜሪካ
በፍቺ የሚጠናቀቁ ጋብቻዎች የሚቆዩበት አማካይ ጊዜ 8 ዓመት ነው፡፡
ሰዎች ፍቺ ከፈፀሙ በኋላ እንደገና ለማግባት በአማካይ ለሶስት ዓመት ይጠብቃሉ፡፡
ጥንዶች የመጀመሪያ ፍቺያቸውን የሚፈጽሙበት አማካይ ዕድሜ 30 ዓመት ነው፡፡
ወላጆቻችሁ ስኬታማ ትዳር የነበራቸው ከሆነ ለፍቺ የመጋለጥ ዕድላችሁ በ14 በመቶ ይቀንሳል
ከጋብቻ በፊት አብሮ መኖር የፍቺን ዕድል 40 በመቶ ይጨምራል፡፡
ኮሌጅ የተማራችሁ ከሆናችሁ፣ ለፍቺ የመጋለጥ ዕድላችሁ 13 በመቶ ይቀንሳል፡፡
ከአሜሪካ ህፃናት ገሚሱ የወላጆቻቸው ትዳር ሲፈርስ ይመለከታሉ፡፡ ከእነዚሁ ህፃናት ግማሽ ያህሉ የወላጆቻቸው ሁለተኛ ጋብቻ ሲፈርስም ያያሉ፡፡
ኦክላሆማ ከፍተኛ ፍቺ የሚፈፀምባት ግዛት ስትሆን ከግዛቷ ያገቡ አዋቂዎች መካከል 32 በመቶው ፍቺ ፈጽመዋል፡፡
ዛሬ በአሜሪካ ካሉ ህፃናት ውስጥ 43 በመቶው ያለአባት ነው የሚያድጉት፡፡

      የ17 ዓመቱ ፕሮፌሽናል እግር ኳስ ተጨዋች ጌድዮን ዘላለም በብሔራዊ ቡድን ደረጃ ለየትኛው አገር መጫወት እንደሚፈልግ ለመወሰን ቢያንስ እስከ 3 ዓመት ሊዘገይ እንደሚችል ዘገባዎች አመለከቱ፡፡ ጌድዮን ከወር በፊት በታላቁ የእንግሊዝ ክለብ አርሰናል እስከ ከ2017 ለመቆየት የኮንትራት ማራዘሚያ ውል የፈረመ ሲሆን ጀርመን፤ በወላጆቹ ዘር ግንድ ከኢትዮጵያ፤ በተወለደበት አገር ጀርመን እና ለስምንት ዓመታት በኖረበት አሜሪካ  በብሄራዊ ቡድን ደረጃ እንዲጫወት ይፈልጋል፡፡  በብሔራዊ ቡድናቸው እንዲጫወትላቸው በተለይ አሜሪካ እና ጀርመን በየአቅጣጫው ጥረት እያደረጉ መሆናቸውን ያወሱ ዘገባዎች፤ ከ2 ሳምንት በፊት ወጣቱ በጀርመን ሀ- 17 ቡድን እንዲሰለፍ የቀረበለትን ጥሪ ሳይቀበል ከቀረ በኋላ  ጉዳዩ ማነጋገር መጀመሩን ያወሳው የኢኤስፒኤን ነው፡፡ አንዳንድ የጀርመን ሚዲያዎች ጌድዮን በጀርመን ብሄራዊ ቡድን የሚጫወትበትን እድል ማበላሸቱ ለወደፊት የእግር ኳስ ህይወቱ መጥፎ ጠባሳ መሆኑን በማውሳት እንደ ባየር ሙኒክ አይነት ክለቦች ውስጥ ለመጫወት ያለውን ተስፋ እንደሚያደበዝዘው እየገለፁ ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ጌድዮን በጀርመን ሀ -17 ቡድን  እንዲሰለፍ የቀረበለትን ጥሪ ወደ ጐን ገሸሽ ማድረጉን ተከትሎ በርካታ የአሜሪካ ስፖርት ሚዲያዎች እና የብሄራዊ ቡድን ደጋፊዎች አጋጣሚውን ለመጠቀም ተሯሩጠዋል፡፡ እንደ ኢኤስፒኤን  ዘገባ ጌድዮን ዘላለም፤ አሜሪካዊ ዜግነቱን በአፋጣኝ አግኝቶ ከወራት በኋላ ብራዚል በምታስተናግደው 20ኛው ዓለም ዋንጫ  በሚሳተፈው የአሜሪካ ብሔራዊ ቡድን  እንዲካተት ፊርማ በማሰባሰብ  እና ለፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ግልፅ ደብዳቤ በማስገባት  ዘመቻ ማድረግ ቀጥለዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በኢትዮጵያ እግር ኳስ አፍቃሪዎች ከፍተኛ ድጋፍ እና ክትትል ባለው የእንግሊዙ ክለብ አርሰናል የሚጫወተው ጌድዮን ዘላለም ከዋልያዎቹ ጎን እንዲሰለፍ ከወራት በፊት ተፈጥሮ የነበረው ፍላጎት የተቀዛቀዘ መስሏል፡፡
ኢትዮጵያና የትዊተር ምልልሱ
ጌድዮን በአርሰናል ክለብ በታቀፈበት ወቅት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከ31 ዓመታት መራቅ በኋላ ደቡብ አፍሪካ ላይ በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ መሳተፍ ላይ ነበር፡፡ ከዚያም በኋላ ዋልያዎቹ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ የምድብ ማጣርያ ስኬታማ ጉዞ  ነበራቸው፡፡ በዚሁ ጊዜ ጌድዮን ዘላለም ወደ እናት አባቱ አገር ኢትዮጵያ መጥቶ  ለብሄራዊ ቡድን እንዲጫወት  ከስፖርት አፍቃሪው ጋር ፍላጐት ያሳዩ ግለሰቦች ነበሩ፡፡ እነሱም የቀድሞው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ቴዎድሮስ አድሃኖም ነበሩ፡፡
አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ስለወጣቱ የተናገሩት በጋዜጣዊ መግለጫዎች ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በመደገፍ የቅርብ ክትትል የሚያደርጉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ደግሞ የማህበረሰብ ድረገፆችን ተጠቅመዋል፡፡
ከወራት በፊት በዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ የመጀመርያ ጨዋታ ኢትዮጵያ ከናይጄርያ  አዲስ አበባ ላይ ሲጫወቱ  ጌድዮን ዘላለም በትዊተር ድረ-ገጹ ሁለት መልክቶችን በመፃፍ አስነብቦ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በወቅቱ የመጀመርያው ጎል በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ሲመዘገብ ደስታውን ለመግለፅ “ጎልልልልልልልልል......” ብሎ በመፃፍ አስነበበ፤ ጨዋታዉ በናይጄርያ 2ለ1 አሸናፊነት ከተጠናቀቀ በኋላ ደግሞ “ ...አሁንም ኮርቻለሁ ” የሚል አስተያየቱን በማስፈር ለዋልያዎቹ ብቃት አድናቆቱን ሲገልፅ አገሩን በቅርብ ርቀት እንደሚከታተል አረጋግጦ ነበር፡፡
ይህንን ተከትሎም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቴዎድሮስ አድሀኖም ጌድዮን ዘላለም ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እንዲጫወት በትዊተር ድረገፃቸው መልዕክታቸውን በማስፈር ያደረጉት ማግባባት ትኩረት ስቦ ነበር፡፡ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ለጌድዮን ባደረሱት ፈጣን መልዕክት “ ሃይ ጌድዮን…. ያንተን ሃሳብ መስማቱ  ጥሩ ነው፡፡ በቶሎ ለኢትዮጵያ መጫወትህን ተስፋ አድረጋለሁ”  ብለዋል፡፡ ጌድዮን ዘላለም ለዚህ ምላሽ አልሰጠም፤ ከዚያን በኋላ ኢትዮጵያ ተጨዋቹን ወደ ብሄራዊ ቡድን ለመቀላቀል የነበራት ፍላጎት እንደተቀዛቀዘ ቀርቷል፡፡
ምላሽ የተነፈገው የጀርመን ጥሪ
የቀድሞው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ቴዎድሮስ አድሃኖም ለጌድዮን ዘላለም ወደ አገሩ መምጣት የነበራቸው ፍላጐት ለወር ያህል በይፋ ሲያነጋግር ሰንብቶ ለወጣቱ የጀርመን እግር ኳስ ፌደሬሽን ጥሪ ቀረበለት፤ በሀ-17  ቡድን በመካተት ከስፔን ጋር በሚደረገው የወዳጅነት ጨዋታ እንዲሳተፍ ነበር፡፡ በዜግነት ሁኔታው ላይ የሚፈጥረው ችግር ስላልነበር ጌድዮን ጥሪውን በመቀበል ተጫወተ፡፡
ከዚሀ የጨዋታ ልምድ ከ4 ወራት በኋላ ግን ሌላ ጥሪውን የጀርመን እግር ኳስ ፌደሬሽን አቀረበ፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት ማለት ነው፡፡ ጌድዮን ዘላለም በአውሮፓ ደረጃ በሚደረገው የሀ-17 አህጉራዊ የምድብ ማጣሪያ ጨዋታ በሚሳተፈው የጀርመን ሀ-17 ቡድን እንዲቀላቀል የቀረበ ጥያቄ ነበር፡፡ ይህን ጥሪ ግን ጌድዮን ሳይቀበለው ቀረ፡፡ በምን ምክንያት እንደሆነ በይፋ የታወቀ ነገር የለም፡፡ አንዳንድ መረጃዎች እንደገለፁት ግን ጌድዮን ዘላለም ጥሪውን በመቀበል በዚሁ አህጉራዊ ሻምፒዮና ላይ ለጀርመን ሀ-17 ቡድን  ተሰልፎ ቢጫወት ኖሮ በተለይ ለአሜሪካ ብሔራዊ ቡድን ዜግነቱን ቀይሮ በዓለም አቀፍ ውድድሮች መሳተፍ የሚችልበትን ሁኔታ ያበላሽ ነበር ብለዋል፡፡
የአሜሪካውያን የፊርማ ማሰባሰብ ዘመቻ
ጌድዮን ከ2 ሳምንት በፊት በጀርመን ሀ-17 ቡድን  የቀረበለትን ጥሪ ገሸሽ ማድረጉ ግን በአሜሪካ ያለውን ፍላጎት ቆስቁሶታል፡፡ የአሜሪካ ሚዲያዎችና ደጋፊዎች ለጌድዮን በአስቸኳይ ዜግነት ተሰጥቶት ለብሄራዊ ቡድን እንዲጫወት ሰፊ ዘመቻ ጀምረዋል። ጌድዮን ዘላለም ለ8 ዓመታት በአሜሪካ በመኖር በእግር ኳስ ልምምድና ጨዋታ በሶስት አማተር ክለቦች ልምድ ስለነበረው ፍላጎቱ እንዲጠናከር ምክንያት ሆኗል፡፡
ጌድዮን ዘላለም የአሜሪካ ዜግነት፤ የመኖርያ እና የስራ ፈቃዶች የሉትም፡፡ በአሜሪካ እግር ኳስ  ሰፊ ልምድ ነበረው፡፡ ግን መቼም ቢሆን በዚያ አገር ብሔራዊ ቡድን ተሰልፎ ለመጫወት እንደሚፈልግ የሚያመላክት አስተያየት የሰጠበት ሁኔታ አላጋጠመም፡፡  የእሱን ፍላጎት ባይሰሙም የአሜሪካ ሚዲያዎችና የብሄራዊ ቡድን ደጋፊዎች ዘመቻቸውን ፊርማ በማሰባሰብ እና ለፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ይድረስ ብለው የፃፉት ግልፅ ደብዳቤ  እየጣሩ ናቸው፡፡ እነዚህ አካላት ጌድዮን ለአሜሪካ ብሄራዊ ቡድን እንዲሰለፍ ፅፈውታል የተባለው ደብዳቤ  ከዚህ በታች የቀረበው ነው፡፡
“አገራችንን በመምራት ያላችሁን ታላቅ ኃላፊነቱ እናከብራለን፡፡ በትህትና የምንጠይቀው ጌድዮን ዘላለም ለአሜሪካ ብሔራዊ ቡድን እንዲጫወት የሚቻለው ሁሉ እንዲደረግ ነው፡፡ የማይቻል ከሆነ የሌላ አገር ማልያ ይለብሳል - ምናልባትም የኮሚኒስቶችን”
የአሜሪካ  ሚዲያዎችና ብሄራዊ ቡድን ደጋፊዎች በዚህ ዘመቻቸው  ተስፋ የቆረጡ አይመስሉም፡፡ በጥቂት ሳምንታት ውስጥ የጌድዮን ዘላለም ጉዳይ እልባት አግኝቶ ወጣቱ  በብራዚል በሚደረገው 20ኛው ዓለም ዋንጫ ከብሄራዊ ቡድን ጋር እንዲሳተፍ ግፊት ማድረጋቸውን ቀጥለዋል። የወቅቱ የአሜሪካ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ የሆነው ጀርመናዊው የርገን ክሊስማን ይህን ፍላጎት በማጤን በተጨዋቹ ላይ የቅርብ ክትትል ማድረግ መጀመሩን ሰሞኑን የገለፀው ደግሞ የኢኤስፒኤን ዘገባ ነው፡፡
በመጨረሻስ የማንን ማልያ ይለብሳል?
የ17 ዓመቱን ጌድዮን ዘላለምን ወደ ብሄራዊ ቡድናቸው ለመቀላቀል ጀርመንና አሜሪካ ከፍተኛ ፍላጎታቸውን በማሳየት ያለፈውን አንድ አመት በትኩረት ተከታትለውታል፡፡ በኢትዮጵያ በኩል የነበረው ፍላጎት ከአራት ወራት በፊት በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ቴዎድሮስ አድናሆም እና በቀድሞው የዋልያዎቹ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ከተንፀባረቀ ወዲህ ብዙም እንቅስቃሴ  እየተስተዋለ አይደለም። በተለያዩ ድረገፆች ስለ ጌድዮን ዘላለም በቀረቡ መረጃዎች ወጣቱ የኢትዮጵያ እና የጀርመን ዜግነት እንዳለው ይጠቀሳል፡፡ ስለ አሜሪካዊ ዜግነቱ የሚገለፅ መረጃ ግን የለም፡፡ በእርግጥ ጌድዮን የሚፈልግ ከሆነ በጀርመን ፓስፖርቱ ላይ ተጨማሪ የዜግነት እና የስራ ፈቃድ በመያዝ በአሜሪካ ብሄራዊ ቡድን የመጫወት እድል አለው፡፡ በአንፃሩ ግን በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ለመጫወት ሁለት ዜግነት መያዝ አይፈቀድለትም፡፡ በኢትዮጵያ  ህግ መሰረት አንድ ሰው የሁለት አገራት ዜግነት እንዲኖረው አይፈቀድም፡፡
በአርሰናል ክለብ እስከ 2017 እኤአ የኮንትራቱን ማራዘሚያ ውል  ከወር በፊት የፈፀመው ጌድዮን ዘላለም አሁን ትኩረቱ በክለቡ መጫወት ብቻ እንጂ በብሄራዊ ቡድን ደረጃ የየትኛውን አገር ማልያ ለብሶ እንደሚጫወት መግለፅ እንደማይፈልግ ከአርሰናል ክለብ የቅርብ ምንጮች የተገኙ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ጌድዮን ዘላለም ዜግነቱን ሰጥቶ የሚጫወትበትን ብሄራዊ ቡድን ለመወሰን ቢያንስ 3 ቢበዛ 5 ዓመታት ሊዘገይ እንደሚችል ያወሱ መረጃዎች ወቅታዊ ፍላጎቱ በአርሰናል ክለብ ማደግ እና በአውሮፓ እግር ኳስ ከፍተኛ ልምድ ማካበት እንደሆነ ይገልፃሉ፡፡ ተጨዋቹ በብሄራዊ ቡድን ደረጃ ለመጫወት የሚያስብ ከሆነ በ2018 እኤአ ራሽያ ላይ እንዲሁም በ2022 እኤአ በኳታር የሚደረጉትን 21ኛው እና 22ኛው የዓለም ዋንጫዎች መጠበቅ ግድ እንደሚሆንም ያስገነዝባሉ፡፡

  • 100 ሜትር በ56 ሰከንድ በክራንቾቹ ሮጧል፡፡
  • ሪከርዱ ገና በጊነስ መዝገብ እውቅና በማግኘት አልሰፈረም፡፡
  • የዩሲያን ቦልት አድናቂ ነው፡፡ ሊያገኘውም ይፈልጋል፡፡
  • በጀርመን ለመኖር የጥገኝነት ጥያቄ አቅርቧል፡፡
  • ከዓመት በፊት ስለህይወት ውጣውረዱና ሪከርድ ስለማስመዝገብ  አላማው ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረገው ቃለምልልስ ተናግሮ ነበር፡፡

   ከሳምንት በፊት “ፋርዝ” በተባለችና በሰሜን በቫርያ በምትገኝ የጀርመን ከተማ የ32 ዓመቱ ታምሩ ፀጋዬ በክራንቾቹ 100 ሜትርን በ56 ሴኮንዶች  በመሮጥ ባስመዘገበው ልዩ የዓለም ሪከርድ አነጋጋሪ ሆኗል፡፡ ታዋቂው የእንግሊዝ ታብሎይድ ጋዜጣ ዴይልሜል በፃፈው ዘገባ  አካል ጉዳተኛው  ታምሩ ፀጋዬ በክራንቾቹ ተጠቅሞ 100 ሜትሩን በመሮጥ ያሳየው አስደናቂ ስፖርታዊ ብቃት ለመላው የሰው ልጆች ከፍተኛ የሞራል መነቃቃት የሚፈጥር ልዩ ስኬት ነው ብሎ አድንቆታል፡፡
የታምሩ ፀጋዬ  ልዩና አስገራሚ ሪከርድ በጊኒስ የሪከርዶች መዝገብ ገና አለመስፈሩን የዘገበው ጨምሮ የዘገበው ዴይሊ ሜል፤ በአጭር ጊዜ እውቅና ማግኘቱ እንደማይቀር ገልፆ፤ ሪከርዱን ያስመዘገበበት ትእይንት በአገሪቱ ብሄራዊ የቴሌቭዥን ጣቢያ ሽፋን ማግኘቱን አውስቷል፡፡ አካል ጉዳተኛ ሆኖ ለመንቀሳቀስ በሚጠቀምባቸው ክራንቾች አስገራሚና ልዩ ክብረወሰኖችን በማስመዝገብ የተሳካለትን እንግሊዛዊውን  ጆን ሳንድ ፎርድ የጠቀሰው የዴይሊ ሜል ዘገባ ታምሩ ለእነዚህ ክብረወሰኖች ተቀናቃኝ መሆን እንደሚችልም ጠቁሟል፡፡ እንግሊዛዊው አካል ጉዳተኛበክራንቾቹ በመታገዝ ሁለት የዓለም ክብረወሰኖችን በማሳካት በጊነስ የሪኮርዶች መዝገብ ሰፍሯል፡፡  ጆን ሳንድ ፎርድ  በ2009 እ.ኤ.አ ላይ የኪሊማንጀሮ ተራራን በ4 ቀናት ከ20 ሰዓታት እና ከ30 ደቂቃዎች የወጣ ሲሆን፤ በ2011 እ.ኤ.አ ላይ ደግሞ በለንደን ማራቶን በመሳተፍ 42.195 ኪ.ሜ ርቀትን በ6 ሰዓት ከ24 ደቂቃዎች ከ48 ሰኮንዶች ጨርሶ በእነዚህ ሁለት ልዩ ክብረወሰኖች በጊነስ የሪከርዶች መዝገብ ለመስፈር በቅቷል፡፡  ታምሩ ፀጋዬ በጀርመኗ ፋርዝ ከተማ ካስመዘገበው ልዩ የዓለም ሪከርድ በኋላ  “አንድ በአንድ ህልሞቼን እያሳካሁ ነኝ፡፡ በህይወቴ ብዙ ውጣውረዶችን አሳልፌያለሁ፤ አካል ጉዳተኛ ብሆንም ብዙ ነገር ማድረግ እችላለሁ። በስፖርታዊ ብቃቴ እና አስደናቂ ተሰጥኦዎቼ ሌሎችን ሪኮርዶችን በማስመዝገብ መላው ዓለምን ማስደነቅ እፈልጋለሁ” ብሏል፡፡  ለዓለማችን ፈጣን የአጭር ርቀት ሯጭ ዮሴያን ቦልተ ከፍተኛ አድናቆት እንዳለው መናገሩን የጠቀሰው የዴይል ሜል ዘገባ “ዮሲያን ቦልትን እንደተምሳሌት የምመለከተው ጀግና ነው፡፡ እኔም ምርጥ ስፖርተኛ ነኝ፡፡ እሱ በፈጣን እግሮቹ እንደተሳካለት በጠንካራ እጆቼ በክራንቾቼ በመሮጥ ሪከርድ አስመዝግቢያለሁ፡፡ የሰራሁትን ታሪክ ቢያይልኝና ባገኘውገኘውም ደስ ይለኛል” ብሎ መናገሩንም አውስቷል፡፡
በሌላ በኩል ታምሩ ፀጋዬ ባለፉት ጥቂት ወራት በመላው አውሮፓ ከሚታወቀው እና “ሲርኪዊ ዲ ሶሊል” ከተባለ የሰርከስ ቡድን ጋር  እየሰራ እንደሚገኝ ያመለከተው አንድ የጀርመን ሚዲያ፤ በተለያዩ የጀርመን ከተሞች በመዘዋወር ትርኢቶችን ማቅረቡን  እንደሚቀጥል ቢገልፅም ወደ አገሩ ለመመለስ ፍላጐት እንደሌለውና በጀርመን አገር ለመኖር የጥገኝነት ማመልከቻ ማስገባቱን ጎን ለጎን ዘግቧል፡፡
በአዲስ አድማስ ያደረገው ቃለምልልስ
ታምሩ ፀጋዬ ለአስራ አምስት ዓመት እግሮቹ መራመድ ስለማይችሉ እጁን እንደ እግር በመጠቀም እየተሳበ ነበር የሚጓዘው፡፡ እናትና አባቱ አግልለውታል፡፡ ከቤተሰብ፣ ከማህበረሰብና ከጓደኞች ብዙ ተፅዕኖ፣ ብዙ ንቀትና ጥላቻ ደርሶበታል፡፡ ማደርያ አጥቶ ጐዳና አድሯል፤ ሊስትሮነትም ሰርቷል፡፡ ግን ሁሌም ትልቅ ታሪክ የመስራት ሪከርድ የማስመዝገብ ህልም እንደነበረው ከዓመት በፊት የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ከሆነችው አበባየሁ ገበያው ጋር ባደረገው ቃለምምልስ ተናግሮ ነበር፡፡  ታምሩ በክራንች በመታገዝ መንቀሳቀስ የቻለበትን ከፍተኛ የቀዶ ጥገና ህክምና ያገኘው በአጋጣሚ ነው፡፡ “ተዓምር” ከሚመስል ህክምናው በኋላ በእግሩ መሄድ ጀመረና በ16 ዓመቱ አንደኛ ክፍል ገባ፡፡ እስከ ኮሌጅ ዘለቀ፡፡ ከዛም ወደ ስፖርት ገባ፡፡ ሪከርድ ለማስመዝገብ አለመ፡፡ ይህንንም ፊልም የሚመስለው አስገራሚ የህይወት ታሪኩን በወቅቱ ከጋዜጣው ጋር ባደረገው ቃለምልልስ በስፋት ሲያወጋ ሁሉንም የህይወት ተሞክሮውን በማጠቃለል ሲናገር ወደቅሁ፤ ተጋጋጥኩ፤ ግን ተሳካልኝ  ብሎ ነበር፡፡ ታምሩ ፀጋዬ ከሳምንት በፊት ካስመዘገበው ልዩ የዓለም ሪከርድ በኋላ ከዓመት በፊት ከአዲስ አድማስ ጋር ካደረገው ቃለምልልስ አንዳንድ ምላሾቹን ለትውስታ እንዲህ ይቀርባሉ፡፡
‹‹ስወለድ አፈጣጠሬ የሚያስደንቅ ስለነበረ ፈቃዱ ዘገዬ አሉኝ፡፡ “እሱ እንደፈቀደ፣ እንደፈጠረው የሚያደርገውን ያድርገው” ለማለት ይመስለኛል፡፡ ታምሩ የሚለው ግን የቆሎ ት/ቤት እያለሁ የወጣልኝ ስም ነው፡፡ ይሄም ተመሳሳይ ትርጉም አለው፡፡ ሁለቱም እግሮቼ ስወለድ ወደ ኋላ ተቆልምመው ነው የተወለድኩት፡፡ አካል ጉዳተኛ ሆኜ ማለት ነው፤… የተወለድኩት ከላሊበላ 60 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ባለች የገጠር ሰፈር (ምዢ ማርያም በምትባል ቦታ) ነው፡፡ እናቴ፤ አያቴ ቤት  በቤት ሠራተኝነት ታገለግል ነበር፡፡ እኔ የተረገዝኩት አባቴ ከእናቴ ጋር በነበረው የምስጢር ግንኙነት ነው፡፡ አባቴ ሊዳር ሁለት ወር ሲቀረው እኔ ተወለድኩ፡፡›› በማለት ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ የልጅነት ታሪኩን አጫውቷል፡፡
ስትወለድ በቤት ውስጥ የነበረው ስሜት እንዴት ነበር፤ ካደግህ በኋላ ስትሰማ ምን ስሜት ተፈጠረብህ በሚል ጥያቄ ቀርቦለት ነበር፡፡ ታምሩ ፀጋዬ ምላሹን ሲሰጥ‹‹ ለእናቴም ለእኔም መጥፎ እንደነበር ዛሬ ዛሬ እሰማለሁ፡፡ አካል ጉዳተኛ ሆኜ በመወለዴ የአባቴ ቤተሰቦች ‹‹ይሄ ልጅ ከእኛ ዘር አይደለም፤ ዘር አሰዳቢ ነው›› ይሉ ነበር፡፡ እናቴ መረራትና ጥላኝ ጠፋች፡፡  ለ3 ወር ብቻ ጡት አጥብታኝና ከተማ ገባች፡፡ ሴት አያቴ ደረቅ ጡቷን ታጠባኝ ነበር፡፡ እናቴ  ካደግሁ በኋላ አልፎ አልፎ ቤተሰብ ለመጠየቅ ትመጣ ነበር፡፡ እኔን ያሳደገኝ አያቴ ነው፡፡ እስከ አምስት አመቴ ድረስ ከቤት መውጣት አልችልም ነበር፡፡ አፈና ተደርጐብኝ ሳይሆን በቃ መራመድ አልችልም፡፡ እንደ እባብ ነበር የምሳበው፤ በእጄ እየተራመድኩ፣ እጄን እንደ እግር እየተጠቀምኩ ማለት ነው፡፡ ሰው ስለሚያገለኝ ብቻዬን አወራለሁ፤ ብቻዬን እጫወታለሁ፡፡ አያቴ ቄስ ትምህርት ቤት እንድማር ይፈልግ ነበር…ያኔ በየደብሩ ቄስ ትምህርት ቤት አለ፡፡ እኔ ግን ፍላጐቴ ጨዋታ ብቻ ነው፡፡ በእጄ እየተሳብኩ …በሩጫም እንኳን የሚቀድመኝ አልነበረም፡፡ አያቴ የትምህርት ፍላጐት እንደሌለኝ ሲረዳ ከብት ጠባቂ አደረገኝ፡፡›› በማለት ያሳለፈውን የህይወት ውጣውረድ ገልፆታል፡፡
እንዴት የስፖርት እንቅስቃሴዎችን ማድረግ እንደጀመረ ሲናገር ደግሞ ‹‹ብቻዬን፡፡ አንድ ጓደኛዬ ነበር፤ ያየኛል፤ አብሮኝም ይሰራል፡፡ የማልሞክረው ነገር የለም፡፡ ኦፕራሲዮን አድርጌ በክራንች ነበር የምሄደው፡፡ ስለዚህ ለምን ተዘቅዝቄ በክራንች በእጄ አልሄድም ብዬ ተነሳሁ፡፡ በኢንተርኔት ላይ እንደዚህ ዓይነት ሪከርድ ያስመዘገበ የለም፡፡ በዚህ መንገድ ለምን ራሴን አላወጣም ብዬ ጀመርኩ። ወደቅሁ፣ ተነሳሁ፣ ተጋጋጥኩ፡፡ አሁን ከመቶ ሜትር በላይ እሄዳለሁ፡፡ የሚፈለገው በአንድ ደቂቃ ውስጥ ምን ያህል ሜትር ይኬዳል የሚለው ነገር ነው።›› ብሎም ነበር፡፡  በዓለም ላይ እንደዚህ ዓይነት ጅምናስቲክ የሚሰራ እንዳለም ተጠይቆ ነበር፡፡ ‹‹የለም፡፡ ተዘቅዝቆ በክራንች ላይ በእጅ በመሄድ እኔ ብቻ ነኝ፡፡ ቆየሁና ለምን በክራንች ላይ ሆኜ ደረጃ አልወርድም አልኩና ልምምድ ጀመርኩ፡፡ በተደጋጋሚ ወደቅሁ፤ ተጋጋጥኩ ግን አደረግሁት።›› የሚል ምላሽ ሰጥቶ የነበረው ታምሩ ፀጋዬ በዚያው ቃለምልልስ ለማስመዝገብ ስላሰበው ሪኮርዱ ስኬታማነት ማብራርያ እንዲሰጥ ተደርጎም ነበር፡፡ ‹‹በአንድ ደቂቃ ከ76 ሜትር በላይ ተዘቅዝቆ በክራንች ላይ በእጅ በመሄድ ሶስት ድርጅቶች እውቅና ሰጥተውኛል፡፡ “ወርልድ ሪኮርድ አካዳሚ”፣ “ወርልድ ሪኮርድ ሴንተር”፣ እና “ወርልድ ኦቶራይዝ›› ናቸው፡፡ የእነዚህ ሪከርዶች ባለቤት ነኝ፡፡ ሁለቱ ሪከርዶች ያገኘሁት በክራንች በመሄድ ነው፡፡ የራሴን ስም አስጠርቼ አገሬን ማስጠራት ነበር የምፈልገው፡፡ ይሄው ተሳካልኝ፡፡ ጊነስ ወርልድ ሪከርድ በዚህ ወር እውቅና ይሰጠኛል፡፡›› ብሎ ነበር፡፡  

         በአንድ እጇ አሜሪካ ውስጥ በሌላው እጇ አፍሪካ ውስጥ ስኬታማ ሥራ ፈጣሪ የቢዝነስ ባለሙያ የሆነችው ሶፊያ በቀለ እሸቴ፣ ወንዶች በገነኑበት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በኩባንያ አስተዳደር፣ እንዲሁም በስጋት አያያዝና አወጋገድ ዙሪያ አንቱ የተሰኘች ባለሙያ ነች። በመረጃ (በኢንፎርሜሽን) ደህንነት፣ ጥበቃና ምርመራ ዙሪያ በአለማቀፍ የአሜሪካ ኩባንያዎች ውስጥ ለበርካታ አመታት የሰራችው ሶፊያ፤ እጇን ወደ አፍሪካ በመዘርጋት እንደ አገር ግንባታ ሊቆጠሩ የሚችሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን አከናውናለች። ለአፍሪካ ህብረት እና ለኢትዮጵያ ፓርላማ የተቀናጀ የመረጃ አያያዝና አጠቃቀም ስርዓቶችን ዘርግታለች።
ከዚያም የኢንተርኔት ግንኙነትን ከአደጋ ለመጠበቅ በሚያስፈልጉ ጥንቃቄዎችና እርምጃዎች ዙሪያ የኩባንያ አስተዳደርና የስጋት አያያዝ አማካሪ ሆና ሰርታለች። የኩባንያ ግንባታና የኮሙኒኬሽን አማካሪ በመሆን የአሜሪካ ኩባንያዎችን ከማገልገሏ በተጨማሪ፣ በአለማቀፍ ደረጃም የኢንተርኔት ፖሊሲ አማካሪ ሆናለች። በቅርቡ ደግሞ፣ ዶትኮኔክት አፍሪካ ትረስት (ባለአደራ) እንዲሁም ዶትኮኔክትአፍሪካ ረጂስትሪ ሰርቪስስ ሊሚትድ የተሰኙ ተቋማትን መስርታለች። በዚህም በመላው አለም የሚኖሩ አፍሪካዊያንን በመወከል .africa የተሰኘ የኢንተርኔት አድራሻ ስርወ-ስያሜ ለመፍጠርና በበላይነት ለማስተዳደር ጥያቄ አቅርባለች።  በሰኔ 2004 ዓ.ም ማመልከቻ ያስገባችው፤ አሜሪካ ለሚገኘውና የኢንተርኔት አድራሻዎችን ለሚያስተዳድረው አትራፊ ያልሆነ አለማቀፍ ድርጅት ICANN ነው። ድርጅቱ ውስጥ በምክር ቤት አባልነት ትሰራ በነበረበት ወቅት ነው የዶትአፍሪካ ፕሮጀክቷን የጀመረችው። ዶትኮኔክትአፍሪካ የተሰኙ ተቋሞቿ፤ ለፕሮጀክቱ ስኬታማነት የሚያደርጉት አስተዋፅኦ ቀላል አይደለም። ተቋሞቿ Yes2dotAfrica  በሚል መሪ ቃል ለስድስት አመታት ያካሄዱት አለማቀፍ የግንዛቤ ማስፋፊያ ዘመቻ ተቀባይነትን አስገኝቶላቸዋል። ዘመቻው፤ በአፍሪካ ስም የኢንተርኔት አድራሻ የመፍጠር ጉዳይ ብቻ አይደለም። በመላው አለም የአፍሪካን መልካም ገፅታ ለመገንባት ልዩ እድል ይሰጣል። በዚያ ላይ፤ የአፍሪካ ሴቶችንና ወጣቶችን፣ በኢንተርኔት አብዮት ውስጥ በዋና ተዋናይነት የሚያሳትፉ በርካታ ፕሮጀክቶችንና እቅዶችን ለማፍለቅ ጥሩ መነሻ ይሆናል።
በአዲስ አበባ የተወለደችው ሶፊያ፣ በወላጆቿ የተደላደለ ኑሮና በጥሩ ትምህርት ነው ያደገችው። ኢትዮጵያ ውስት በተለያዩ የቢዝነስ መስኮች ስኬታማ በመሆን የሚታወቁት አባቷ አቶ በቀለ እሸቴ፤ የህብረት ባንክ እና የህብረት ኢንሹራንስ መስራችና የቦርድ አባል ነበሩ። በአገሪቱ በትልቅነታቸው ከሚታወቁ የገንዘብ ተቋማት መካከልት ህብረት ባንክና ኢንሹራንስ ተጠቃሽ ናቸው። ሶፊያ ከቢዝነሱ ዓለም ጋር የተዋወቀችው፣ ከአባቷ አፍ ነው። ስለ ራሳቸው ስራ ከጓደኞችና ከቤተሰብ አባላት ጋር ሲያወሩ እየሰማች፣ የቢዝነስን አሰራር ትምህርት ቀስማለች። ራስን ችሎ የመወሰንና የመኖር ጥቅምን ከአባቷ የተማረችው ሶፊያ፤ ከስጋት የፀዳ የቢዝነስ ሥራ እንደሌለና ከበርካታ ስጋት አዘል የቢዝነስ አማራጮች መካከል የተሻለውን መርጦ የመግባት ድፍረት አስፈላጊ እንደሆነም መሰረታዊ እውቀት አስጨብጠዋታል።
እናቷ ሲስተር ሙሉዓለም በየነ፣ በሙያቸው ለበርካታ ዓመታት የሰሩ ነርስ ሲሆኑ፣ የማምለክ ያህል በፍቅር ታከብራቸዋለች። ርህራሄንና ደግነትን የተላበሱ በጣም ሃይማኖተኛ ሴት ነበሩ።  በተደላደለ ኑሮ ውስጥ ምንም ሳይጎድልባት ያደገችው ሶፊያ፤ ጥራት ያለው ትምህርት በማግኘትም እድለኛ ነች። ከታላቅ እህቷ ጋር የመጀመሪያና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን የተከታተለችው በአዲስ አበባ ናዝሬት ስኩል ነው። የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን እንዳጠናቀቀች፣ ከታላቅ እህቷ ጋር አሜሪካ ሄደው ዩኒቨርስቲ እንዲገቡ ስፖንሰር ስለተገኘላቸው፤ ወደ ሳን ፍራንሲስኮ ካሊፎርኒያ በረረች። በእርግጥ የዩኒቨርሲቲ ወጪያቸውን የሸፈኑት ወላጆቻቸው ናቸው። ከአሜሪካ ኑሮ ጋር መላመድ ለእህትማማቾቹ ፈተና እንደነበር ሶፊያ ስታስታውስ፤ ከተማ ውስጥ ወዲህ ወዲያ ለማለት እንኳ እንደተቸገሩ ትናገራለች። ወቅት የሚከተል የአሜሪካ ዘመነኛ ባህልን በቅጡ ለመገንዘብና መውጪያ መግቢያውን ለማወቅ ጊዜ የፈጀባቸው ሶፊያና እህቷ፤ የራሳቸውን ባህል እንደያዙ የአሜሪካዊያን ሕይወት ውስጥ መቀላቀል ቀላል አልሆነላቸውም። ደግነቱ፤  ጥራት ባለው የናዝሬት ስኩል ትምህርት የታነፁት እህትማማቾች፣ በሳን ፍራንሲስኮ ስቴት ዩኒቨርስቲ ውስጥ ከሌሎች ተማሪዎች ልቀው ለመገኘት አልተቸገሩም። ለነገሩማ ለተወሰነ ጊዜ ቢደነጋገርባቸውም ከአሜሪካ ኑሮ ጋር መቀላቀላቸው አልቀረም። ከጊዜ በኋላማ ሶፊያ የአሜሪካን ሕይወት መውደድ ጀመረች። ለካ አሜሪካ ልዩ ፀጋ አላት። የአገሪቱ የነፃነት መንፈስ ግሩም ነው፤ ሕይወትን ለማሻሻልና ለመሥራት  ሰፊ እድል የሚገኝባት አገር መሆኗም ድንቅ ነው። ባየችውና ባስተዋለችው መልካም ህይወት ለአሜሪካ ፍቅር ያደረባት ሶፊያ፤ ወደፊትም ያንን አገር ሳትለቅ ነው አፍሪካ ውስጥ እግሯን መትከል የምትሻው። በቢዝነስ አናሊሲስና በመረጃ ሥርዓት (በኢንፎርሜሽን ሲስተምስ) የመጀመሪያ ዲግሪዋን ከያዘች በኋላ፤ በጎልደን ጌት ዩኒቨርስቲ በማኔጅመንት የመረጃ ሥርዓት ማስተርስ ዲግሪ አግኝታለች። ሥራ ፍለጋ ላይ ታች አላለችም። ሥራው ራሱ ነው እሷን ፍለጋ ዩኒቨርሲቲው ድረስ የመጣላት። በዩኒቨርስቲ እጅግ የላቀ ውጤት የሚያስመዘግቡ ተመራቂዎች፣ ከዩኒቨርሲቲው ሳይወጡ ነው በተለያዩ ምርጥ ኩባንያዎች ተመልምለው ሥራ የሚቀጠሩት። ሶፊያም በወቅቱ በግዙፍነታቸው ከሚታወቁ ባንኮች መካከል አንዱ በሆነው ባንክ ኦፍ አሜሪካ ለኮምፒዩተር ኦዲቲንግ ሥራ ተቀጠረች። በእርግጥ በቀጥታ ሥራ አልጀመረችም። የመረጃ ሥርዓት ደህንነትና ቅልጥፍና፣ በተለይ ደግሞ የመረጃ አጠቃቀምና ጥበቃ ላይ ያተኮረው የኮምፒዩተር ኦዲቲንግ ሥራ፣ ልዩ እውቀት የሚያስፈልገው በጣም አዲስ የሙያ መስክ ስለነበረ፤ ሶፊያና አብረዋት የተቀጠሩ ባልደረቦቿ ባንክ አሜሪካ ውስጥ ተጨማሪ ስልጠና ተሰጥቷቸዋል። እዚህ ወንዶች የገነኑበት ሙያ ውስጥ ነው፤ ሶፊያ ስለ ወንዶች ብዙ ማወቅ የጀመረችው። ወንዶች በበዙበት ድባብ ውስጥ እንዴት ስኬታማና ውጤታማ መሆን እንደምትችል ትምህርት የቀሰመችውም፤ በዚሁ ሥራዋ ነው። ዩኒየንባንካል ወደ ተሰኘው ኮርፖሬሽን ከተሻገረች በኋላ፣ ወደ ሥራ አስኪያጅ የሃላፊነት ደረጃ እድገት አግኝታ ሠርታለች። ከዚያም በአለም በትልቅነታቸው ከሚታወቁ የአካውንቲንግ አገልግሎትና የኢንቨስትመንት አማካሪ ድርጅቶች መካከል አንዱ በሆነው ኩባንያ ተቀጠረች - በፕራይስ ወተርሃውስ ኩፐርስ። ኢንሹራንስና ባንክ የመሳሰሉ ድርጅቶች ገንዘብ ወይም የዋስትና ሰነድ ታቅፈው አይቀመጡም፤ በትርፋማ ነገር ላይ ሊያውሉት ይሞክራሉ እንጂ። ግን ደግሞ፤ ገንዘብ ሲፈልጉ ወዲያውኑ መልሰው ሊያገኙት ይገባል። መፍትሄው፤ ከበርካታ ኩባንያዎችና ተቋማት አክሲዮን ወይም ቦንድ መግዛት ነው። ገንዘባቸውን ትርፋማ ያደርግላቸዋል፤ በአፋጣኝ ገንዘብ ካስፈለጋቸውም የገዙትን አክስዮንና ቦንድ መሸጥ ይችላሉ። እንዲህ በአክስዮንና  በቦንድ ግብይት ገንዘብን ውጤታማ የማድረግ አሰራር፣ ፓርትፎሊዮ ኢንቨስትመንት ይሉታል። ነገር ግን እጅግ አዋቂነትንና ብልህነትን ስለሚጠይቅ፤ በባለሙያ አማካሪዎች አማካኝነት መመራት ይኖርበታል። ፕራይስ ወተርሃውስ ኩፐርስ በተሰኘው ኩባንያ ውስጥ የሶፊያ ዋና ሥራም፣ ለተለያዩ ደንበኞች የፖርትፎሊዮ ኢንቨስትመንት አማካሪ ሆና በበላይነት መቆጣጠር ነበር። የሶፊያን ምክር ከሚቀበሉ ደንበኞች መካከልም በእንግሊዝ ከአራቱ ትልልቅ ባንኮች መካከል አንዱ የሆነው በርክለይ ባንክ ይገኝበታል። ከጤና አገልግሎት ኢንሹራንስ ጋር ለተያያዙና ለሌሎች ኩባንያዎችም የአማካሪነትን ስራ በበላይነት መርታለች። እዚህ ነው ሥራ መምራትን የተካነችው። በአይነትና በመጠን ከሚለያዩ በርካታ ባለሙያዎችና ቡድኖች ጋር የመስራት ችሎታዋ፣ ውስብስብና ግዙፍ ፕሮጀክቶችን የመምራት ጥበቧና ብቃቷ ወደ ላቀ ደረጃ ተሸጋገረ። ይሄኔ ነው የራሷን ድርጅት ለመክፈት የሚያስችል ክህሎትና በራስ የመተማመን መንፈስ መጎናፀፏን እርግጠኛ የሆነችው።
ኩባንያውን ከለቀቀች በኋላ፣ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ስትዟዟር አንድ አመት አሳለፈች። የሥራ ፈት ዙረት አይደለም። ከአሜሪካ አውሮፓ፣ ከኤስያ ላቲን አሜሪካ ድረስ ወደ ተለያዩ አገራት የተጓዘችው፣ በየአገሩ ያለውን የቢዝነስ አሰራርና ባህል እንዲሁም፤ የኢንተርኔትና የቴክኖሎጂ ደረጃ ለመመልከት ነው። አሜሪካ ውስጥ ሆና በየአህጉሩ ገና በመመንደግ ላይ ለሚገኙ አገራት የቴክኖሎጂ ሽግግር የማካሄድ አላማና የቢዝነስ ውጥን የያዘችው ሶፊያ፣  በ1990 ዓ.ም ሲቢኤስ ኢንተርናሽናል በሚል ስያሜ የራሷን ኩባንያ መሰረተች። በተመሳሳይ አላማም ኢትዮጵያ ውስጥ በ”ሲስተም ኢንተግሬሽን” ሥራዎች ላይ ያተኮረ “ኤስቢኮሙኒኬሽንስ ኔትዎርክ” የተሰኘ ኩባንያ አቋቋመች። ለአፍሪካ ህብረት የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ለመዘርጋት በጨረታ ተወዳድራ ያሸነፈችው ሶፊያ፣ ለጨረታው የመረጠችው የቢዝነስ ዘዴ፣ በኢትዮጵያ ያን ያህልም የተለመደ አልነበረም። የፕሮጀክት አመራር ላይ በተመሰረተ የቢዝነስ ዘዴ ከአገር ውስጥና ከውጭ ባለሙያዎችንና የተለያዩ ድርጅቶችን አሰባስባ በማስተባበር ጨረታውን ካሸነፈች በኋላ፤ ስራውንም በተመሳሳይ መንገድ አጠናቅቃ ለአገልግሎት አብቅታለች። ገና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ባላደገበት አገር፣ በግዙፍነቱ ተጠቃሽ የሆነ የአፍሪካ ህብረት ፕሮጀክት ላይ ውጤታማነቷን ያስመሰከረችው ሶፊያ፤ ወደ ሌላ ትልቅ ፕሮጀክት አመራች። ለኢትዮጵያ ፓርላማ የመረጃ አያያዝና አጠቃቀም ስርዓት ለመዘርጋት፤ እንደገና ዳይሜንሽን ዳታ የተባለ የደቡብ አፍሪካ ኩባንያን ጨምሮ ከተለያዩ አገራት የተውጣጣ ቡድን በመፍጠር ጨረታ አሸንፋ ፕሮጀክቱን በስኬት ፈፅማለች። ከፕሮጀክቱ ጋር ተያይዞ በተፈጠረ ውዝግብ የተነሳ በአገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን በሰፊ መዘገቡ የሚታወስ ሲሆን፣ የውዝግቡ መነሻ አድሎአዊ አሰራርን በመቃወም ሶፊያ ያቀረበችው ጥያቄ ነው። የግዢና የኮንትራት ሥርዓቱ ላይ ፍትሃዊነት የጎደለው አሰራር መኖሩን በመቃወም ተከራክራ ለማሸነፍ የበቃችው ሶፊያ፤ የመንግስት የግዢና የኮንትራት አሰራር እንዲሻሻል፣ ግልፅነትና ተጠያቂነትንም እንዲላበስ ክርክሯ አስተዋፅኦ እንዳደረገ ታምናለች። በ1994 ዓ.ም በግሉ ዘርፍ የተቋቋመ ቡድን ኢትዮጵያ ውስጥ የአክሲዮን ገበያ ለመመስረት በማቀድ ለመንግስት ያቀረበው ሃሳብ ስህተቶችና ጉድለቶች እንደነበሩት የምትገልፀው ሶፊያ፣ በመርህ ላይ የተመሰረተ ተቃውሞ እንዳስተጋባች ታስታውሳለች። በዚያው አመት መጨረሻ ላይም ለአክሲዮን ገበያ የቀረበው ሃሳብ በመንግስት ውድቅ ተደርጓል። ምናልባትም በወቅቱ ባስተጋባችው አቋም፣ የኋላ ኋላ የኢትዮጵያ እህል ገበያ እንዲመሰረት መንገዱን የሚጠርግ ነበር ብላ ታስባለች። ኢትዮጵያ ውስጥ አዘውትራ የሰራችበት ያንን ጊዜ ትወደዋለች። ከዘመድ አዝማድም ጋር ጥሩ ጊዜ ለማሳለፍ አስችሏት ነበር። በእርግጥ እያሰለሰች ወደ አሜሪካ መመላለሷ አልቀረም። ኩባንያ ወደሚገኝበት ወደ ካሊፎርኒያ እንዲሁም የቴክኖሎጂ ቁሳቁስ አቅራቢዎቿ ወደሚገኙበት ሚያሚ በተደጋጋሚ ተመላልሳለች። እዚህ ኢትዮጵያ ውስጥ ለአገሯ ተጨባጭ አስተዋፅኦ የሚያበረክት ፕሮጀክት ያከናወነችበት ወቅት ስለሆነ ግን ያንን ጊዜ ትወደዋለች።
ኢትዮጵያ ውስጥ የጀመረችውን የፓርላማ ፕሮጀክት እንዳጠናቀቀች፣ ብዙም ሳይቆይ አሜሪካ ውስጥ ሌላ የቢዝነስ እድል ታያት። በአሜሪካ በግዙፍነቱ 7ኛ ደረጃ ላይ የነበረው ኢንሮን ኩባንያ እንዲሁም በቴሌኮሙኒኬሽንና በኢንተርኔት ቢዝነስ በትልቅነቱ የሚታወቀው ዎርልድኮም ኩባንያ በኪሳራ መዘፈቃቸው በድንገት ይፋ የወጣበትና የዓለም መነጋገሪያ የሆኑበት ወቅት ነበር - ጊዜው።  በእርግጥ ኩባንያዎቹ በድንገት አልከሰሩም። ቅጥ ባጣ የኩባንያ አመራርና በአሳሳች የመረጃ አቀራረብ ለበርካታ አመታት ኪሳራቸው እንዲደበቅ ተደርጓል። የተደበቁት ጉዶች ሲያብጡ ከርመው ድንገት ሲፈነዱ፤ በቢዝነስ ዓለም ከታዩት ትልልቅ ቅሌቶች ተርታ የሚመደቡ ሆነው አረፉት። ታዲያ ለእንዲህ አይነት የመረጃ አጠቃቀምና የኩባንያ አመራር ችግሮች መፍትሄያቸው ምንድነው? ችግሮች ሲኖሩ፣ መፍትሄ ይዞ የሚመጣ ሰው የቢዝነስ እድል ያገኛል።  ሶፊያም በዚህ ምክንያት ነው የቢዝነስ እድል የታያት። የመረጃ ስርዓት ቅልጥፍናንና አጠቃቀምን የመመርመር ሙያዋ ይታወቃል። በትልልቅ ኩባንያዎች ውስጥ በሥራ አመራር የሃላፊነት ደረጃ ሠርታለች። የኩባንያ ንብረቶችን በአግባቡ ለማስተዳደርና ለመምራት፤ የመረጃ ሥርዓት የቱን ያህል ቁልፍ እንደሆነ ታውቃለች። በዚህ ዙሪያ በአማካሪነት ለመስራት በከፈተችው የቢዝነስ ሥራ፣ ካሊፎርኒያ ውስጥ ለሚገኙ በርካታ የሲልከን ቫሊ ኩባንያዎች የምክር አገልግሎት ሰጥታለች - ለኢንተል፣ ጀኔነቴክ፣ ኦንስክሪን ወዘተ።  ለአገሪቱ ብሄራዊ ባንክ (ፌደራል ሪዘርቭ ባንክ) እንዲሁም ለሌሎች ተቋማትም አገልግሎቷን በማስፋፋት ስኬታማ ቢዝነስ ገንብታለች። በኩባንያ ግንባታና በኮሙኒኬሽን እቅዶች ላይም ለበርካታ የአሜሪካ ኩባንያዎች በአማካሪነት የሰራችው ሶፊያ፣ የሥራ ፈጠራ ኢንቨስትመንት (ቬንቸር ካፒታል)፣ የኮንትራት ሃላፊነትና አፈፃፀም፣ የገበያ እድል ማመቻቸትና ማስፋት፣ የገበያ ድርድር፣ የቢዝነስ እቅድ አመዛዘንና አፈታተሽ፣ የዓለማቀፍ  ትስስር ስትራቴጂያዊ እቅድ አዘገዳጃጀት፣ የሕዝብ ግንኙነት ስትራቴጂ አዘገጃጀትና አፈፃፀም፣ እንዲሁም በሌሎች ጉዳዮች ላይ የአማካሪነት አገልግሎት አስፋፍታለች።
አዲሱ የአማካሪነት ቢዝነሷን እያስፋፋች ሳለ ነው ተጨማሪ የሥራ አቅጣጫ የሚፈጥርላት አጋጣሚ የተፈጠረው። የኢንተርኔት አድራሻዎችን በሃላፊነት ለማስተዳደር፣ በዓለማቀፍ ደረጃ በመንግስታዊና በግል ዘርፍ ተቋማት ትብብር የተመሰረተው ድርጅት (ICANN)  ውስጥ የምክር ቤት አባል እንድትሆን ተመረጠች። ምክር ቤቱ አንዱ ትኩረት የኢንተርኔት አድራሻ ስርወ-ስያሜ ነው። ለምሳሌ .com, .edu, .gov, .net, .org... የመሳሰሉ አዳዲስ ስርወ-ስያሜዎች ስራ ላይ የሚውሉት በምክር ቤቱ ከታዩና ውይይት ከተካሄደባቸው በኋላ ነው። በስርወ ስያሜዎች አጠቃቀም ላይ በአማካሪነት እንድትሰራ ሃላፊነት የተሰጣት ሶፊያ፣ የኢንተርኔት አድራሻ አሰያየም ላይ መላው የዓለም ማህበረሰብ የመሳተፍ እድል እንዲያገኝ የሚያግዝ የፖሊሲ መመሪያ በማርቀቅ አቅርባለች። ላበረከተችው አስተዋፅኦም በዓለማቀፍ ደረጃ እውቅና ተሰጥቷታል - Internationalized Domain Resolution Union (IDRU) በተሰኘ ቡድን። ሶፊያ የኢንተርኔት አድራሻዎች ላይ በአማካሪነት በምትሰራበት ወቅት ነው፣ ለአፍሪካ ልዩ ትርጉም የያዘ ሃሳብ የመጣላት። .africa የተሰኘ የኢንተርኔት አድራሻ ስርወ-ስያሜ መፍጠርና ሥራ ላይ ማዋል እንደሚቻል በመገንዘብም፣  በ1998 ዓ.ም ዶትኮኔክትአፍሪካ የተሰኘ እቅዷን ማስተዋወቅ ጀመረች። እቅዷም፣ በተለይም በተመድ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን፣ እንዲሁም በአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ፈጣን ድጋፍ አግኝቷል። የመሪነቱን ሃላፊነት በመውሰድ ከተለያዩ አገራት የተውጣጡ ባለሙያዎችን አሰባስባ ማመልከቻ በማዘጋጀት፣ በ2004 ዓ.ም ጥያቄዋን ICANN አስገብታለች። .africa የሚል የኢንተርኔት ስርወ-ሥያሜ ሥራ ላይ እንዲውል የቀረበው ማመልከቻ ላይ  በ2005 ዓ.ም የመጀመሪያዎቹ ወራት ላይ ውሳኔ ይሰጥበታል ተብሎ ይጠበቃል። ሶፊያና ባልደረቦቿ አወንታዊ ምላሽ ያግኙ እንጂ፣ የአፍሪካን መልካም ገፅታ በሚገነባ መንገድ ስርወ-ሥያሜውን ለማስጀመር ዝግጁ ነች። ከዚህም ጋር በማያያዝ፤ የአፍሪካ ሴቶችና ወጣቶች በቴክኖሎጂ መስክ ብቃትና አቅም የሚያዳብሩበት፣ እንዲሁም ቢዝነሳቸውን በቴክኖሎጂ የሚያጎለብቱበት ብዙ አይነት እቅዶችን ተግባራዊ ማድረግ ይቻላል እያለች በጉጉት ታስባለች። የተራቀቀ የኢንተርኔት አገልግሎቶችን ጨምሮ ዘመናዊ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂን የመሰለ ሃያል መሳሪያ ወደ ታዳጊ አገራት ለማሸጋገር ባከናወነችው ሥራ ላይ ገለፃ እንድትሰጥ በተደጋጋሚ እየተጋበዘች ተመክሮዋን በተለያዩ መድረኮች አካፍላለች። በኒውዮርክ በተካሄደ የተባበሩት መንግስትት ጠቅላላ ጉባኤ፣ ሩዋንዳ ኪጋሊ በተካሄደ የአፍሪካ መሪዎች የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ስብሰባ፣ እንዲህም በካሊፎርኒያ የስታንፎርድ ሴት የቢዝነስ ባለሙያዎች ስብሰባ ላይ ተሞክሮዋን አቅርባለች።
ሶፊያ ከሙያ ሕይወቷ በተጨማሪ በማህበራዊ አገልግሎቶች ውስጥም ለመሳተፍ ጊዜ አላጣችም። በሮታሪ ክለብ፣ በመረጃ ሥርዓት ኦዲትና ቁጥጥር ማህበር፣ በጎልደን ጌት ዩኒቨርሲቲ ተመራቂዎች ማህበር የዳሬክተሮች ቦርድ ውስጥ የምትሳተፈው ሶፊያ፣ የሳን ፍራንሲስኮ ቤይ የኢንተርኔት ማህበረሰብን ከመሰረቱት ሰዎች አንዷ ከመሆኗም በላይ የሥራ አስፈፃሚ ቦርድ አባል ናት።
በአብዛኛው ወንዶች በገነኑበት የሙያ ዘርፍ ውስጥ በመስራት ካስተዋለችው ተነስታ ስትናገር፣ ሴቶች ተቀባይነት ለማግኘት በላቀ ብልሃትና ትጋት መስራት ይጠበቅባቸዋል ትላለች። ዋናው ነገር፣ በቁርጠኝነት የሙጢኝ ብሎ መሥራት ነው። ከዚህም በተጨማሪ ሥራዎችሽ እንዲታወቁና እንዲታዩ ማድረግ ያስፈልጋል። ስራዎችሽ ተደብቀው ከቀሩ፣ መልካም ስምንና ዝናን መገንባት አትችይም። የራስሽን ታሪክና የራስሽን ስም ለመገንባት ኢንተርኔትና ማህበራዊ ድረገፆች በእጅጉ ጠቃሚ ናቸው በማለት እሷም እንደምትጠቀምባቸውና እንደምታደንቃቸው ትገልፃለች።
ሶፊያ ለኢትዮጵያ ያላት የወደፊት ተስፋ ብዙ ነው። ከፍተኛ የኢኮኖሚ እምቅ አቅሟን ተጠቅመው እድገትን እውን ሊያደርጉ የሚችሉ፣ በትምህርትና በፈጠራ ችሎታ የበለፀጉ ኢትዮጵያውያን ይታይዋታል። ኢትዮጵያዊያን ጥልቅ ሃይማኖታዊ ትውፊት የታደሉ በመሆናቸው፣  ስርዓትን የሚከተሉና የህግ የበላይነትን የሚያከብሩ ናቸው። ኢትዮጵያውያን ሰፊ የመናገር ነፃነት እንዲሁም ሰፊ የግል ኢንቨስትመንት ነፃነት እንዲኖራቸው ትመኛለች። በተለይ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን፤ አገራቸውን ለመጥቀም የሥራ ፍሬያቸውንና ትምህርታቸውን ይዘው መምጣት ይፈልጋሉ። የኢንቨስትመንት ነፃነት በተሻለ ደረጃ እንዲስፋፋላቸውም ምኞቷ ነው።
ምንጭ፤-
www.ethiopianwomenunleashed..org

Monday, 07 April 2014 15:42

ሃገሬ ትንሳኤሽ

ክፉ ግዜሽ አልቆ
እንባ ከአይንሽ ደርቆ
ሰቀቀንሽ አልፎ
ጥቀርሻሽ ተገፎ
ጉዳትሽ ታክሞ
አጉል ስምሽ ቀርቶ
ብሩህ ፀሐይ ወጥቶ
ማቅሽን አውልቀሽ
ጥበብሽን ለብሰሽ
ጎጆሽን አሙቀሽ
አደይ ተከናንበሽ
ጤናዳም፣ አሪቲ፣ ቄጤማ ጎዝጉዘሽ
በጎችሽ ሳይጎድሉ ሁሉንም ሰብስበሽ
ክብርሽ ተመልሶ
ቃል ኪዳንሽ ደርሶ
ልጆችሽ ተዋደው
ተስማምተው - ተግባብተው
ስትስቂ
ስትስቂ
ስትስቂ የማየው
ሃገሬ ንገሪኝ ዘመኑ መቼ ነው?
ተጻፈ፡- ፯/፯/፳፻፭ ንጋት ፲፪፡ ፭

የሁለት ታላላቅ ግድቦች ወግ
ታላቁ የህዳሴ ግድብ እና ታላቁ ‹‹ሁቨር ዳም››

   የህዳሴው ግድብ ግንባታ የተጀመረበት 3ኛ ዓመት ሲከበር፤ ከስድስት ወር በፊት በአሜሪካ በነበረኝ ቆይታ የተደነቅሁበትን የሁቨር ግድብ አስታወሰኝ፡፡
እኛ ኢትዮጵያውያን የገባንበት ያህል ችግርና ውድቀት ባይገጥማቸውም፤ አሜሪካዊያን ያኔ በ1923 ዓ.ም ከባድ ቀውስና ጭንቀት ውስጥ ነበሩ። እኛ ከስልጣኔ ማማ ላይ ሳናውቀው ተንሸራተትን ከወደቅን ወዲህ፣ ለሺ አመታት ከከበበን ድቅድቅ ጨለማ ለመገላገል ስንመኝ ኖረናል፡፡ ጥንታዊውን የስልጣኔ ጉዞ እንደገና የሚያድስና የብልፅግና ዘመንን የሚያበስር ነገር እንፈልጋለን - የህዳሴ ግድብ ትርጉምም የዚህን ያህል ግዙፍ ነው - ‹‹ታላቅ ነበርን፤ ታላቅም እንሆናለን›› እንዲሉ፡፡
የሁቨር ግድብም እንዲሁ ለአሜሪካውያን ተቀራራቢ ትርጉም አለው፡፡ እስከ 20ያኛው ክፍለ ዘመን መባቻ ድረስ ለመቶ አመታት በስልጣኔና በብልጽግና ጐዳና ታይቶ የማይታወቅ ታሪክ የሰራችው አሜሪካ፣ ብዙም ሳይቆይ ነው በታላቅ የኢኮኖሚ ቀውስ የተመታችው፡፡ የ1920ዎቹ ዓመታት ለአሜሪካ ክፉ ዓመታት ናቸው፡፡ ብርሃኗ የደበዘዘባት፤ ፋና ወጊ መንፈሷ የቀዘቀዘባት ዘመን!
የረሃብና የግጭት አዘቅት ውስጥ ባይዘፈቁም፤ የስልጣኔና የብልጽግና ጉዟቸው ተብረክርኮ፤ የ‹‹ይቻላል›› መንፈስ የተዳከመባቸው አሜሪካዊያን፣ የጨለማ ድባብ ሲያንዣብብባቸው ጊዜ ህዳሴ አስፈለጋቸው፡፡ “ሁቨር ዳም” የዚያ ፍላጎት ውጤት ነው፡፡ በትግል ቋንቋ እንግለፀው ቢባል፤ “ብሶት የወለደው ጀግናው የአሜሪካ ህዝብ” እንደማለት ነው! እኛ ለአባይ የዘፈንለትን ያህል አሜሪካዊያን ለኮሮላዶ ወንዝ አላዜሙም፡፡ ነገር ግን እኛ ለአባይ ስንቆጭ እንደኖርነው፤ እነሱም በኮሮላዶ ወንዝ መቆጨታቸው አያጠራጥርም፡፡
ወንዙ ከአፍንጫቸው ስር እንደ ጅብራ ተገትሮ ሳይጠቀሙበት መፍሰሱ ሳያንስ፤ በየአመቱ ገጠር ከተማውን ሲያማርጥ በጐርፍ ያጥባቸዋል፡፡ በሸለቋማው ወንዝ፣ ከፍቅረኛው ተለያይቶ የቅርብ ሩቅ ለመሆን የተገደደ ጎረምሳ፤ “አንቺ ከአባይ ማዶ” እያለ እንደሚያንጎራጉረው ሁሉ፣ የኮለራዶ ወንዝም አሜሪካያውንን ሲያራርቅ ኖሯል፡፡
አሪዞናን ከወዲህ ማዶ፣ የኔቫዶ በረሃን ወዲያ ማዶ ሰንጥቆ የሚያልፈው የኮለራዶ ሸለቋማ ወንዝ፤ በርካታ ግዛቶችን እያቆራረጠ ይገሰግሳል፡፡ ዛሬ ግን እልም ካለው የኔቫዳ በረሃ ላይ ጉብ ካለችው ሽቅርቅሯ ላስ ቬጋስ ከተማ፣ ወደ አሪዞና በሚወስደው ምቹ መንገድ በመኪና ለሰላሳ ደቂቃ እንደተጓዙ፤ ፊት ለፊት ከአይንዎ ጋር የሚጋጨው ተራራና ገደል ሳይሆን ሰማይ ጠቀስ ግድብና ድልድይ ነው፡፡
በኦሪዞና ግዛት የፊኒክስ ከተማንና በኔቫዳ ግዛት ላስ ቬጋስን የሚያገናኘው ሰማይ ጠቀስ ድልድይ በየእለቱ በሰዎች ሲጥለቀለቅ ይውላል፡፡ “ከወንዝ ማዶ ያለሽው” እና “ከወዲያ ማዶ ያለኸው” እያሉ ናፍቆታቸውን የሚያንጐራጉሩ ፍቅረኞች አይደሉም በድልድዩ የሚተላለፉት፡፡ ሁቨር ዳምን ለማየት የሚመጡ ጐብኚዎች፣ እንጂ፡፡ ግድቡን ለመመልከት በየቀኑ የሚመጡ በርካታ ሺህ የዓለም ጐብኝዎች ረዥሙን ግድብ ላይ ላዩን አይተው አይመለሱም፤ ውስጥ ለውስጥም ይጐበኙታል፡፡ የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ጣቢያዎቹ የሚገኙት ከግድቡ ስር መሬት ውስጥ በጥልቅ ቦታ ነው፡፡ በሊፍት ወደ መሬት ውስጥ ቁልቁል ብዙ ርቀት መግባት ያስፈልጋል፡፡
ሊፍት ከመያዛችን በፊት ከአስጐብኛችን አንደበት የወጡ ቃላት ፍርሃት ለቀቁብኝ፡፡ “ከመሬት በ5ሺህ ጫማ ርቀት ወደ ታች እንዘልቃለን፡፡ ይህ ግድብ ሲገነባ የዘጠና ስድስት ሰዎች ህይወት አልፏል” አለች፡፡
“አውቃችሁ ግቡበት” አይነት አባባልዋን እየሰማን በዝምታ ስንተያይ፤ እሷ በጣቷ የሊፍቱን መቆጣጠሪያ ተጫነች፤ ወደ መሬት እንብርት ይዞን እንዲሸመጥጥ፡፡ እንጀራዋ ነው፡፡ እንደ ባልደረቦቿ ጐብኚዎችን በቡድን እያሰባሰበች ስታስተናግድ ትውላለች፡፡ ከአንድ ሰዓት በላይ በሚፈጀው መስተንግዶ፤ በቀን አምስት ጐብኚ ቡድኖችን ተቀብላ ዙሪያውን ታስቃኛለች፡፡ ሰማይ ጠቀስ ግድቡንና ድልድዩን፤ እንደ አገር የተንሰራፋውን ሃይቅና ዙሪያ ገባውን ካስጎበኘች በኋላ፣ ነው የሃይል ማመንጫ ጣቢያውን ለማሳየት ቁልቁል ከአንድ ኪሎሜትር ጥልቀት በታች ይዛን የጠለቀችው፡፡ ወደ ምድር ስር የሚዘልቅ ባለ ሦስት መቶ ፎቅ ያህል እንደማለት ነው፡፡ ሳስበው አሁን ድረስ ያስፈራኛል። ከላያችን ላይ ግዙፍ ግድብ ብቻ ሳይሆን ግዙፍ ሃይቅ አለ፡፡ እዚያ ስር ነው፤ በየአመቱ 4.5 kwh የኤሌክትሪክ ሃይል የሚመነጨው፡፡ የኢትዮጵያ ጠቅላላ አመታዊ የኤሌክትሪክ ሃይል ከአንድ ግድብ ይመነጫል፡፡
በየአመቱ የ18 ሚሊዮን አሜሪካዊያን መኖሪያ አካባቢዎችን በጐርፍ እያጥለቀለቀ ከፍተኛ ጥፋት ሲያደርስ የነበረው ኮሎክራዶ ወንዝ፤ ዛሬ ለሚሊዮኖች የኤሌክትሪክና የብርሃን መፍለቂያ፤ ለሚሊዮኖች የመጠጥና የመስኖ ውሃ አስተማማኝ ምንጭ ሆኗል፡፡ እንደ አገር የሚሰፋው ሰው ሰራሽ ሃይቁም በዓለም ላይ የመጀመሪያው ትልቁ ሰው ሰራሽ ሀይቅ በመባል በመዝናኛነቱ ለመታወቅ በቅቷል፡፡ ነገር ግን፣ ግንባታው አልጋ በአልጋ አልነበረም፡፡ ለግድብ ግንባታ ተስማሚ የሆነ ቦታ ስላልተገኘ፣ የወንዙን አቅጣጫ ማስቀየር የግድ ነበር፡፡ የስራው ክብደት ራሱን የቻለ ፈተና ነው፡፡ ከሁሉም በፊት ግን የይገባኛል ውዝግቦችን በድርድር መፍታትና መስማማት ያስፈልግ ነበር፡፡ በርካታ ግዛቶችን የሚያካልለው ትልቅ ወንዝ፣ አቅጣጫውን እንዲቀይር ሲደረግ፤ በውሃ ክፍፍልና ድርሻ ላይ ከየግዛቱ ክርክሮች ተፈጥረዋል፡፡ እንዲያውም ውዝግቡ ከመካረሩ የተነሳ፣ የግድቡ ግንባታ ‹‹ህልም ሆኖ ይቀራል›› እስከመባል ደርሷል፡፡
ደግነቱ ስልጡን ሰዎች፣ እድሜ ልክ እየተወዛገቡ አይቀጥሉም፡፡ ይወያያሉ፤ ይደራደራሉ፡፡ ለዚህም ነው፤ የአሜሪካ 31ኛው ፕሬዚዳንት ኸርበርት ሁቨር ከየግዛቱ አስተዳዳሪዎችና ባለስልጣናት ጋር በመገናኘት ሚዛናዊ የውሃ ክፍፍል እንዲኖር የተወያዩት፡፡ አስጐብኚያችን ከ90 አመት በፊት ስለነበሩት ፕሬዚዳንት ስትናገር፤ የአጐቷን ታሪክ የምትተርክ ትመስላለች፡፡
“ኸርበርት ሁቨር ከፖለቲከኛነቱ በተጨማሪ መሃንዲስ ነው፡፡ ወግ አጥባቂ ቢሆንም ደግ ሰው ነው፡፡ የታታሪነቱ ያህል አሳ በማጥመድ መዝናናትን የሚወድ ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ፤ ‘የሰው ልጅ በአካባቢው የሚገኙ ተፈጥሯዊ ነገሮችን ወደ መልካምና ጠቃሚ ነገር የመለወጥ ችሎታ አለው’ የሚል ጠንካራ እምነትና ራእይ የያዘ ሰው ነው፡፡” … አስጎብኚያችን ፕሬዚዳንቱን በቅርብ የምታውቃቸው ሆኖ ሰተማኝ፡፡
የሆነ ሆኖ በውይይቱ ወደ ስምምነት ከተደረሰ በኋላ ነው፤ በአንድ በኩል ተራሮችን በድማሚት መናድና የወንዙን አቅጣጫ ማስቀየር፤ በሌላ በኩል በሸለቆ የተራራቁትን ተራሮችን ለማገናኘት የግድብ ግንባታ የተጀመረው፡፡
በሰው ልጅ ታሪክ ታላቁን ግድብ በመስራት እውቀትና ችሎታቸውን ለማሳየት የተዘጋጁት አሜሪካዊያን መሃንዲሶች ከፈተና አላመለጡም። የኔቫዳ በረሃ፣ የኛው ህዳሱ ግድብ ከሚገነባበት ከቤኒሻንጉል ክልል ባልተናነሰ የሙቀት መጠን የሚታወቅ ቦታ እንደመሆኑ፣ ለግዙፍ የኮንክሪት ስራ በፍፁም አይመችም፡፡ የፎቅ ግንባታ ላይ እንደሚታየው፤ ቀጫጭን ምሰሶዎችና ግድግዳዎችን በኮንክሪት መስራት አያስቸግርም፡፡ ትንሽ ውሃ ከተረጨበት ኮንክሪቱ ብዙም ሳይቆይ ይቀዘቅዛል። ግራና ቀኝ፣ ፊትና ኋላ፣ ላይና ታች የተደፈነ የኮንክሪት ተራራ ሲገነባ ግን፣ ኮንክሪቱ በፍጥነት የመቀዝቀዝ እድል የለውም፡፡
ኮንክሪቱ እስኪቀዘቅዝ እየጠበቀን እንስራ ከተባለ ግንባታው 100 ዓመት እንደሚፈጀ ነበር የተገመተው፡፡ የህዳሴው ግድብ ግንባታ ላይ ኮንክሪቱ እንዲቀዘቅዝ የሚደረገው ላዩ ላይ በረዶ በማፍሰስ ነው፡፡ የሁቨር ግድብ ሲገነባ ግን፣ እንደዛሬ በረዶ ማምረቻ ማሽን በቀላሉ የሚገኝ አልነበረም፡፡ ቢሆንም መሃንዲሶቹ ውሃ በመጠቀም ኮንክሪቱን የሚያቀዘቅዝ መላ ዘየዱ፡፡ ስራውም ሳይጓተት ቀጠለ፡፡ እንዲያውም ሰባት አመት ይፈጃል የተባለው ግንባታ ከታቀደለት ጊዜ ቀደም ብሎ በአምስት ዓመት ተጠናቀቀ፡፡  
ግድብ ለመስራት የፈሰሰው ሲሚንቶና ኮንክሪት፤ 4674 ኪሎ ሜትር ደረጃውን የጠበቀ ሰፊ የአስፓልት መንገድ ሊሰራ ይችላል፡፡ ከኢትዮጵያ እስከ ደቡብ አፍሪካ የሚዘልቅ አስፋልት መንገድ ማለት ነው፡፡ በምን ያህል ወጪ እንደተገነባ አትጠይቁኝ፡፡
ለካ በኛ አገር ብቻ ሳይሆን በአሜሪካም፣ ያኔ ድሮ ሁሉም ነገር ርካሽ ነበር፡፡ ለግድቡ የወጣው ገንዘብ 49 ሚሊዮን ዶላር ነው፡፡ በዛሬ ገንዘብ ቢሰላ ከቢሊዮን ዶላር ሳይበልጥ አይቀርም፡፡ በሦስት ፈረቃ ተፍ ተፍ ለሚሉት 3500 አሜሪካዊያን ሰራተኞች የሚከፈለው ደሞዝ፤ እንደ የሙያቸው ቢለያይም፣ ዝቅተኛው ክፍያ በቀን አራት ዶላር ነበር፡፡ ቀላል ይመስላል፡፡ በዛሬ ሂሳብ ከ100 ዶላር ሊበልጥ ይችላል፡፡
አስተማማኝ የኤሌክትሪክና የውሃ ምንጭ ከመሆን አልፎ፣ ለበርሃማው አካባቢ አዲስ ሕይወት የሚሰጥ ሰው ሰራሽ ሃይቅ ለመፍጠር የበቃው ግድብ ሲጠናቀቅ፤ ኸርበርት ሁቨር ስልጣን ላይ አልነበሩም። እንደመታደል ሆኖ የእኛው የቀድሞ ጠ/ሞኒስትር መለስ ዜናዊም የግድቡን የመሰረት ድንጋይ ጥለው ግንባታውን ቢያስጀምሩም መርቀው ለመክፈት ሳይታደሉ ህይወታቸው አልፏል፡፡
በኮሰራይ ወንዝ ላይ፣ በኛው ቋንቋ የመሰረት ድንጋይ በማስቀመጥ ግንባታውን ያስጀመሩት ሁቨር፤ የስልጣን ዘመናቸው በምርጫ ተቋጭቷል። በምትካቸው ስልጣን የተረከቡት ፕሬዚዳንት ፍራንክሊን ሩዝቬልት ናቸው፡፡ እ.ኤ.አ መስከረም 30ቀን 1935 ዓ.ም ግድቡን መርቀው ከፈቱት። “ቦልደርስ ዳም” ነበር የሚባለው፡፡ ስሙ የተለወጠው በ1947 የአሜሪካ ኮንግረስ ሁቨር ዳም ተብሎ እንዲሰየም ባሳለፈው ውሳኔ ነው፡፡ የኛ ግድብ ግን፣ ገና ሳይጀመር ነው ስሙ የተለወጠው፡፡ “ሚሌኒየም ግድብ” የሚለው ስያሜ ተቀይሮ “ህዳሴ” ግድብ ተብሎ የተሰየመ፡፡     
  አስጎብኛችን በመሬት ውስጥ ቆይታችን የአስራ ሁለት ደቂቃ ትንተናዋን ጨርሳ ወደ ምድር ወለል ለመውጣት ሽቅብ ስንገሰግስ ፍርሃቴ አላገረሸም። ‘አንድ ነገር ቢመጣኮ እዚሁ ድፍት ብለን መቅረታችን ነው’ የሚለው ስጋቴ ለቆኝ ወደሌላ ሃሳብ ተጉዣለሁ። ወደ ታላቁ የህዳሴ ግድብ!!  
የህዳሴው ግድብ ምርቱ ተትረፍርፎ፣ በድርቅና በረሃብ ለምትታወቀው አገራችን የጥንት ስልጣኔዋ እንዲታደስና የብልፅግና ዘመን እንዲበሰር ያደርግ ይሆን? የአገራችንን ገፅታ ይቀይር ይሆን? ግንባታው ሲጠናቀቅና እልፍ አእላፍት ሲጐበኙት፤ ኤሌክትሪክ ሲያመነጭና ለመስኖ ሲያገለግል ማየት ናፈቀኝ፡፡
“ይሁን!!” ብያለሁ፡፡ የህዳሴው ግድብ ሲጠናቀቅ ከአገር አልፎ ለጎረቤትም ያብራ!! ለመብላት የሚዘረጉ እጆች፣ ከአንድም ሶስት ጊዜ ጦም አይደሩ!! ስደትንና ድርቅን ያስወግዱ!!

        በአለም አቀፉ የሙዚቃ ኢንዱስትሪ የካበተ ልምድ ያላት አፍሪካ - አሜሪካዊቷ ኢትዮጵያ ሐብተማርያም፣ የታዋቂው የአሜሪካ የሙዚቃ ቀረጻ ኩባንያ የሞታውን ሪከርድስ ፕሬዚዳንት ሆና መሾሟን ዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ ገለጸ፡፡ የአለማችን ትልቁ የሙዚቃ ኩባንያ የሆነው ዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ፣ ከዚህ በፊት በስሩ ይተዳደሩ የነበሩትን ዴፍ ጃም ሪከርድስ፣ አይስላንድ ሪከርድስና ሞታውን ሪከርድስን እንደገና በማዋቀርና ራሳቸውን ችለው እንዲሰሩ በማድረግ፣ ኢትዮጵያ ሃብተማርያምን የሞታውን ሪከርድስ ፕሬዚዳንት አድርጎ በዚህ ሳምንት መሾሙን አስታውቋል፡፡እ.ኤ.አ በ2003 ታዋቂውን ዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ የተቀላቀለችው ኢትዮጵያ ሐብተማርያም፣ ጀስቲን ቢበርና ክሪስ ብራውንን ጨምሮ አለማቀፍ ዝና ያላቸውን በርካታ ታዋቂ ድምጻውያን፣ የሙዚቃ ደራሲያንና አርቲስቶችን ለኩባንያው በማስፈረም ተጠቃሽ ስራ የሰራች ሲሆን፣ ከ2011 አንስቶም የዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ ምክትል ፕሬዚዳንት እና የኧርባን ሚዩዚክ ሃላፊ በመሆን አገልግላለች፡፡
ዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕን በምክትል ፕሬዚዳንትነት በመራችባቸው አመታት፣ ሜሪ ጄ ብላይጄ፣ ፊፍቲ ሴንት፣ ኤሚኔየም፣ አሻንቲ፣ አይስ ኪዩብ፣ አር ኬሊና ሌሎች በርካታ የፕላቲኒየምና የግራሚ ተሸላሚ አርቲስቶችን ወደ ኩባንያው በመሳብ፣ ስኬታማነቷን ያስመሰከረችው ኢትዮጵያ ሐብተማርያም፣ ለረጅም አመታት በዘርፉ ተጠቃሽ ስራዎችን ሲያከናውን የቆየውን ሞታውን ሪከርድስ ወደተሻለ ትርፋማነት ታሸጋግራለች ተብሎ ስለታመነባት ነው በፕሬዚዳንትነት የተሾመችው፡፡
ሞታውን ሪከርድስ የማኔጅመንት፣ የማርኬቲንግና የማስታወቂያ ስራ አቅሙን የበለጠ በማሳደግ፣ ራሱን የቻለ አለማቀፍ የሪከርዲንግ ኩባንያ እንዲሆን ፣ ኢትዮጵያ ሐብተማርያም ከፍተኛ ሃላፊነት እንደተጣለባት የዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ መግለጫ ያሳያል፡፡
የዩኒቨርሳል ሚውዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሉቺያን ግሬንጅ እንደተናገሩት፣በኢትዮጵያ ሐብተማሪያም የሚመራው ሞታውን ሪከርድስ፣ ተቀማጭነቱን እ.ኤ.አ ከ1972 ጀምሮ ለ25 አመታት ያህል  በርካታ ስራዎችን አሳትሞ ለአድማጭ ሲያቀርብበት በነበረው ሎሳንጀለስ በማድረግ፣ በዘርፉ አያሌ  ስራዎችን ያከናውናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ኢትዮጵያ ሐብተማርያም ከአዲሱ ሹመቷ በተጨማሪ፣ በዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ የኧርባን ሚዩዚክ ሃላፊነት ስራዋን ጎን ለጎን እንደምትቀጥል ተነግሯል፡፡

        ቦታው ለልማት ይፈለጋል ተብሎ ቤት ሲፈርስ፣መጠለያ አጥተው ቤተ-መንግስት ስር መኖር የጀመሩት  48 ቤት አልባዎች፤ሰሞኑን “በጅብ መንጋ ልንበላ ነው” ሲሉ ምሬትና አቤቱታቸውን ገለፁ፡፡ ከጅቦቹ ይከላከሉናል ብለን የሰበሰብናቸው ውሾችም በወረዳው ባለስልጣናት በመርዝ ስለተገደሉብን ከፍተኛ ስጋት ላይ ነን ብለዋል - ቅሬታ አቅራቢዎቹ።
 የወረዳ ስምንት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ደሳለኝ ደበሌ ስለጉዳዩ ጠይቀናቸው ሲመልሱ፤በወረዳው ሸራተንና ፓርላማ በመባል የሚታወቁ ሁለት ፕሮጀክቶች እንዳሉ ገልፀው፤ በሸራተን ፕሮጀክት ለመልሶ ማልማት 1319 ቤቶች ሲፈርሱ፣ምትክና ካሳ እየሰጠን መመሪያው የሚፈቅድላቸውን አስተናግደናል ብለዋል፡፡ በወረዳው ረጅም ዓመት ለኖሩ ምንም መረጃ የሌላቸው ከ60 በላይ ሰዎችም አስተናግደናል ይላሉ- ሥራ አስፈፃሚው፡፡ በሸራተን ዙሪያ በጥገኝነትና በተከራይነት ከ15-23 ዓመት እንደኖሩና የቀበሌ መታወቂያ እንዳላቸው የነገሩን  ቤት አልባዎች የወረዳ ኃላፊዎቹን ይወቅሳሉ፡፡ “ከዛሬ ነገ ቤት ይሰራላችኋል፤መጠለያ ተፈልጎ ትገባላችሁ” ሲሉን ቢቆዩም እስካሁም መፍትሄ አላገኘንም ይላሉ፡፡ አሁን ከቤቱም በላይ ሃሳብ የሆነባቸው የጅቦቹ ጉዳይ ነው፡፡ ጅቦች ከነጋ በኋላም እየመጡብን ከፍተኛ ስጋት ፈጥረውብናል ብለዋል - ነዋሪዎቹ፡፡
“ወረዳው ቀደም ሲል በእኛው ጉዳይ ከአዲስ አድማስ ጥያቄ ቀርቦለት ‘ከክፍለ ከተማው ጋር ተመካክረን የመጠለያ ቦታ አፈላልገን አግኝተናል’ የሚል ምላሽ ቢሰጥም እኛ ግን እስካሁን መፍትሄ አላገኘንም” ያሉት ስማቸውን መግለፅ ያልፈለጉ የአምስት ልጆች አባት፤ በላስቲክ ቤት ውስጥ መኖራቸውን በመቀጠላቸው  ጅቦች ስጋት እንደፈጠሩባቸው ጠቁመው፣ “ዜጎች እንደመሆናችን መንግስት መፍትሄ ይፈልግልን” ሲሉ ተማፅነዋል፡፡
የወረዳ ስምንት ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ደሳለኝ በበኩላቸው፣ “ከዚህ በፊት ጉዳዩን እየተመለከትን በወረዳው እንደመኖራቸው መንግስት የእነዚህን ዜጎች ችግር የመፍታት አቅም ይኖረዋል አይኖረውም የሚለውን ለክ/ከተማው አቅርበናል” ካሉ በኋላ በክፍለ ከተማው ወረዳ 14 ባለወልድ ጀርባ የቆርቆሮ መጠለያ እንደነበረና መጠለያው ከተቃጠለ በኋላ ቦታው ባዶ መሆኑን በማስረዳት፣ እዚያ ቦታ ላይ የቆርቆሮ መጠለያ እንዲሰራ አመልክተን ነበር ይላሉ፡፡  “በወቅቱ የነበሩት የክ/ከተማው ዋና ስራ አስፈፃሚ፣ ከካቢኔ አባላት ጋር ተመካክረው ምን ያህል በጀት እንደሚፈጅ ሰርተን እንድናቀርብ ገልፀው ነበር” ያሉት ስራ አስፈፃሚው፣ በዚህ መሰረት የወረዳው ኮንስትራክሽንና ቤቶች ልማት ባለሙያዎች ምን ምን እንደሚያስፈልግ ሰርተው፣ ለክ/ከተማው አቅርበው ነበር ይላሉ፡፡ ይሁን እንጂ በ2005 ዓ.ም በተካሄደው ምርጫ የመዋቅር ለውጥ በመደረጉና የቀድሞው የክ/ከተማው ስራ አስፈፃሚ ከቦታው በመነሳታቸው፣ የእነዚህ ዜጎች ጉዳይ ሊቀጥል እንዳልቻለ አቶ ደሳለኝ አስረድተዋል፡፡
“በሸራተን ፕሮጀክት ውስጥ ቤት የሚጠይቁት ቤት የማግኘት መብት ኖሯቸው ሳይሆን በወረዳው ብዙ ጊዜ ስለቆዩ የሚቻል ነገር ካለ ብለን የጀመርነው ነበር” ያሉት ዋና ስራ አስፈፃሚው፣ ነገር ግን ገና ለገና ቤት እናገኛለን በሚል ከጎዳና ላይ እየገቡ ላስቲክ ቤት እየሰሩ እንደሚቀመጡና ረጅም አመት የኖሩትን ለመለየት በተደረገው ማጣሪያ 31 አባወራዎች መኖራቸውን፣እነዚህንም ከነቤተሰቦቻቸው በፎቶ አስደግፈው መያዛቸውን ተናግረዋል፡፡ የጅቦቹን ጉዳይ በተመለከተ፣ ኮተቤና በአካባቢው ለመንገድ ስራ ጫካ ሲነካ እየሸሹ የሚመጡ መሆኑን ገልፀው፣ በሸራተን ፕሮጀክት ብቻ ሳይሆን በባለወልድ አካባቢ ለነዋሪዎች ስጋት በመሆናቸው ወረዳው ከደንና የዱር እንስሳት ልማትና ጥበቃ ጋር በመመካከር፣መፍትሄ በመፈለግ ላይ እንደሆኑ ሥራ አስፈፃሚው ተናግረዋል፡፡
“ወደፊት በወረዳው ኮንዶሚኒየም ቤት ደርሷቸው የሚለቀቁ ቤቶች ሲኖሩ ቅድሚያ ይሰጣቸዋል” ያሉት ስራ አስፈፃሚው፤ በዚህ ጊዜ እንዲህ እናደርግላቸዋለን ለማለት እንደሚቸገሩና ለክ/ከተማው ሲወስን ጉዳያቸው እንደሚታይ ተናገረዋል፡፡
ሐምሌ 27 ቀን 2005 ዓ.ም ለንባብ በበቃው አዲስ አድማስ ጋዜጣ “ትራሳቸውን ቤተ-መንግስት ግርጌያቸውን ሸራተን ያደረጉ ቤት አልባዎች” በሚል ርዕስ ስለእነዚሁ 48 ቤት አልባ አባወራዎች መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን በወቅቱ የወረዳ ስምንት ዋና ስራ አስፈፃሚ ከክ/ከተማው ጋር በመነጋገር፤ ለቤት አልባዎች የቆርቆሮ መጠለያ ለመስራት ቦታ በመፈለግ ላይ እንደሆኑ ገልፀውልን ነበር፡፡