Administrator

Administrator

Saturday, 01 August 2015 14:47

የኪነጥበብ ጥግ

ስለ ኪነ - ህንፃ)
እኛ ህንፃዎቻችንን እንቀርፃለን፤ ከዚያም እነሱ እኛን ይቀርፁናል፡፡
ዊንስተን ቸርችል
ማናቸውም የገነባቸውና ጥሩ ነገሮች የማታ ማታ እኛን ይገነቡናል፡፡
ጂም ሮህን
ከተሞች የሰው ልጅ ድንቅ ፈጠራዎች ናቸው፡፡
ዳንኤል ሊቤስኪንድ
በአሜሪካ የቪክቶሪያን ኪነ - ህንፃ በቀጥታ የተቀዳው ከእንግሊዝ ነበር፡፡
ስቲፈን ጋርዲነር
ሎስ አንጀለስ ውስጥ 35 ዓመት ሲሞላችሁ፣ አብዛኞቹን ህንፃዎች በዕድሜ ትበልጧቸዋላችሁ፡
ዴልያ ኢፍሮን
ስለ ሙዚቃ ማውራት ስለ ኪነ-ህንፃ እንደ መደነስ ነው፡፡
ሉዊስ ካህን
ኪነ-ህንፃ ግግር ሙዚቃ ከሆነ፣ ሙዚቃ ፈሳሽ ኪነህንፃ መሆን አለበት፡፡
ኪውንሲ ጆንስ
ኪነ-ህንፃ ዘላለማዊነት ላይ ያለመ ነው፡፡
ክሪስቶፈር ሬን
ሙዚቃን እንደ ፈሳሽ ኪነ ህንፃ እቆጥረዋለሁ።
ጆኒ ሚሼል
ኪነ ህንፃ ጥበብ እንጂ ሌላ ምንም አይደለም።
ፊሊፕ ጆንሰን
ጥሩ ነገር መስራት ቀላል አይደለም፤ ነገር ግን መጥፎ ነገር መስራት እጅግ በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡
ቻርለስ ኧርነስ
ምንጊዜም ክብ ስሰራ፣ ወዲያውኑ ከዚያ ውስጥ መውጣት እፈልጋለሁ፡፡
አር. ቡክሚኒስተር ፉለር
ቤት የመኖሪያ ማሽን ነው፡፡
ሊ ኮርቡስየር
ልክ እንደ መድሃኒት (ኪነህንፃ) ከማዳን ወደ መከላከል መሻገር አለበት፡፡
ሴድሪክ ፕራይስ
እያንዳንዱ ህንፃ ልክ እንደ ሰው ነው፡፡ ብቸኛና የማይደገም፡፡
አየን ራንድ (ዘ ፋውንቴይንሄድ)

Saturday, 01 August 2015 14:44

የንባብ - አደባባይ!

    ቴክኖሎጂ ሲቀብጥ ትውልድም መልኩን ለቅቆ፣ ጨርቁን ጥሎ እንዳያብድ፣ በትይዩ ቦይ እንዳንለቀው፣ የሚተልምልን መሪ፤ መረን እንዳይወጣ የሚገታ የፍቅር ልጓም ያስፈልግ ይመስለኛል፡፡ ዕውቀትን በቅጡና በወጉ ለመጠቀም፣ በሥርዐት ለህይወት ጉልበት መስጫ ለማድረግ መማር አንዱ መንገድ ቢሆንም ቅርፅ ለመስጠት፣ ውበት ለማምጣት ደግሞ ንባብ ሻካራችንን እያለሰለሰ፣ ለማህበረሰቡ ምቹ እንደሚያደርገን ይታመናል፡፡  
ከሀገር ውጭም ሆነ በሀገራችን ውስጥ አያሌዎች እሳት የላሱ ጠቢባን ይሆኑ ዘንድ አእምሮዋቸውን ገርቶ፣ ላባቸውን አቅንቶ፣ዘመን የማያቆመው ድምቀት የሰጣቸው ንባብ እንደሆነ ደጋግመን ያወሳነው ጉዳይ ነው፡፡
በእኛም ሀገር የንባብ ባህል እንዲያድግና እንዲጎለብት የተለያዩ ግለሰቦችና ተቋማት ታላቅ ተጋድሎ አድርገዋል፡፡ ለዚህም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ የሀዋሳና የዲላ ዩኒቨርሲቲ በየራሳቸው ያደረጉትን ጥረት ልንዘነጋው የምንችል አይመስለኝም፡፡ ይበልጥ የሚመለከተው የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበርም ከነዚሁ ጎራ የሚመደብ ነው፡፡ በግለሰብ ደረጃ ደግሞ ደራሲ ዳንኤል ወርቁ “አዲስ አበባ ታንብብ”ን በመሳሰሉ ፕሮግራሞቹ የተቻለውን ያህል ተግቷል፡፡  በጥቅሉ ሲታይ በሀገራችን የንባብ ባህልን ለማበረታታት የሚደረገው ጥረት በእጅጉ እየበረታና እየደመቀ የመጣ ይመስላል፡፡ ሌላው ቀርቶ በቅርቡ ብቻ የተካሄዱትን የመጻህፍት አውደ ርዕዮች ስናይ ጉዳዩ ምን ያህል የልብ ትርታ እየሆነ መምጣቱን የሚያሳይ ነው፡፡
በተለይ ለዛሬ ጽሁፌ መነሻ የሆነኝ፣በማስተር ፊልምና ኮሙኒኬሽን አዘጋጅነት ከትላንት በስቲያ የተጀመረውና እስከ ነገ (»ሐምሌ 23-26 2007 ዓ.ም) የሚቆየው “ንባብ ለህይወት” የመፃህፍት አውደ-ርዕይ፤በዓይነቱና በይዘቱ ግዙፍና ታላቅ ነው፡፡ ምናልባትም ከዚህ ቀደም ከለመድናቸው የሚለዩ በርካታ አላባዎችን አጭቆ የያዘ ዝግጅት ነው፡፡ ከነዚህም ውስጥ አንዱና ዋነኛ ጠባዩ፣  አውደ ርዕዩ በየዓመቱ በቀጣይነት የሚካሄድ መሆኑ ነው። ከዚህም ሌላ በየክልሉ እንዲላመድ በማድረግ ሀዲዱን ቆንጥጦ ይቀጥላል፡፡
ብዙ ጊዜ ስለ ንባብ ስናወራ፣ ስለ ንባብ ስንሰብክ፣ በእዝነ ህሊናችን የሚመጡት ፊታቸው በጢም የተሞላ፣ ምናልባት ሽበት ጣል ጣል ያደረገባቸው አዛውንትና ጎልማሶች ናቸው፡፡ ንባብ ለህይወት ዓይኖቹን ወደ ችግኞቹም ላይ ጥሏል። ሕፃናት ከሥር ጀምረው እንዲኮተኮቱ፣ እኩይ መልኮችን እንዲዘልሉ ከአሁኑኑ ክትባት ያገኙ ዘንድ ለእነርሱም በቂ ዝግጅት አድርጓል፡፡ የሚመጥኗቸው መፃህፍት፣ የሚያጫውቷቸው አሻንጉሊቶችም ተዘጋጅተዋል፡፡
በዚህ አውደ ርዕይ፣120 ያህል የመፃህፍት አሳታሚዎችና የትምህርት ተቋማት በአንድ ዓላማና ድንኳን ስር ይተሳሰራሉ፡፡ እውነት ለመናገር የትምህርት ተቋማት ተሰባስበው በአንድ ሰፈር መች ተገኝተው ያውቃሉ! … ይኸው አሁን በንባብ ለህይወት ችቦዋቸውን እየለኮሱ ደመራውን ሊያደምቁት ታድመዋል፡፡
በንባብ ለህይወት፣ መጻሕፍት ቢያንስ በ10 በመቶ የዋጋ ቅናሽ ለገበያ የሚቀርቡ ሲሆን ቅናሹ  እስከ 50 በመቶ ሊዘልቅ እንደሚችል አዘጋጆቹ ይገልጻሉ፡፡ ስለዚህ መጻሕፍት ለመሸመትም ጥሩ አጋጣሚ ይሆናል ማለት ነው፡፡ የዘመኑ ቴክኖሎጂ በፈጠረው ዕድል ጎብኚዎች ከ100,000 ሺህ በላይ በመረጡት ርዕሰ ጉዳይ ላይ የተፃፉ መፃህፍትን ሶፍት ኮፒ በነፃ ያገኛሉ ተብሏል፡፡  
በዚህ ዐውደ-ርዕይ ባልተለመደ መልኩ አዳዲስ መጻህፍት ቬሎዋቸውን ለብሰው ብቅ እንደሚሉም ታውቋል፡፡ ከአዘጋጆቹ በተገኘው መረጃ መሰረት፤12 አዳዲስ መፃህፍት እዚያው ተመርቀው፣የደራስያኑ ፊርማ አርፎባቸው፣በትኩሱ ወደ ተደራሲያን እጅ ይገባሉ፡፡
ሌሎቹ ሁለት ታላላቅ የበዓሉ ድምቀቶችም እንደዚሁ ያልተለመዱ ናቸው፡፡ ከነዚህ አንዱ በየሙያ ዘርፉ “አንቱ” የተባሉና በአንባቢነታቸው የተመሰከረላቸው ሰዎች  የንባብ አምባሳደር ተብለው ዕውቅና የሚያገኙበት ሲሆን በቀጣዩ ጊዜ በየትምህርት ቤቱና በሌሎች ክበባት በመገኘት አንብበው የሚያስነብቡበት የኃላፊነት ሹመት ነው። ይህ ደግሞ ዓመቱን ሙሉ ለሚካሄደው የንባብ ልምድ ማበልፀጊያ ጉዞ ትልቁን ድርሻ ሊጫወት እንደሚችል እሙን ነው፡፡  ታዲያ ይህ ሁሉ ዘመቻ፣ ዕውቀትን ጓዳችን ለማስገባት፣ እንደ ሰው አውቀን፣ እንደ ሰው አስበንና የተሻለውን መርጠን እንድንኖር ነው። ማወቅን ካለማወቅ የሚለየው አንዱ፣ ህይወትን የምናጣጥምበትን ምላስ መንጠቁ ሲሆን ሌላኛው ህይወትን የምናጣጥምበትን አቅም መስጠቱ ነወ፡፡ ይህንንም እንድናውቅ የሚያደርገን በልብ አይኖቻችን ላይ የተጋረደው መጋረጃ መነሳቱ ነው፡፡ ይህ አውደርይ የማንበብ ጥቅምንና ወደዚህ የጥቅም እልፍኝ የምንገባበትን መንገድ ለመጥረግ ያዘጋጀው ሌላም ነገር አለ፡፡ በአንድ ወገን የተወዳጅ ደራስያንን ወግ እያነበቡ በማዝናናት፣ በሌላ ወገን ደግሞ የንባብን ጥቅምና ፋይዳ ወደ ኋላ እየፈተሹ፣ ታሪክ በማጣቀስ መወያየትም አለ፡፡
 ሙዚቃ የነፍስ ጥበብ ናት! … በጥበብ እልፍኝ ውስጥ ሽር ብትን እያለች የዓውደ ርዕዩን እልፍኝ ታድምቀው በሚል ጥንታዊውን የሙዚቃ ዓለም በቀደመው ዘመን ከያንያን ዜማ - ታንቆረቁረዋለች ይላሉ - የንባብ ለህይወት አዘጋጆች፡፡ ታዲያ ይህ ቀን አይናፍቅም? … ንባቡስ አይርብም? … የነፍሳችን ከንፈር እስኪላጥ እያፏጨን ብንጠራውስ? … እልልል!  

በአክመል ሺፋ የተፃፉ ግጥሞች የተሰባሰቡበት “ዝምታሽ አስፈራኝ” የተሰኘ የግጥም መድበል እየተሸጠ ነው፡፡
መምህር አይቸህ ሰይድ በመጽሐፉ ጀርባ ላይ ባሳፈረው አስተያየት፤ “አክመል የሰራቸው የግጥም ሥራዎች አብዛኞቹ አጫጭር ቢሆኑም መልዕክታቸው ሰፋ ያለና ጥልቅ ስሜትን የሚገዙ ሆነው አግኝቻቸዋለሁ” ብሏል፡፡ በ110 ገፆች የተመጠነው መድበሉ፤ ዋጋው 35 ብር እንደሆነ ታውቋል፡፡

 በዳንኤል ንጉሴና ዮሐንስ ሙሉጌታ ተፅፎ፣ በመልካሙ ማሞ ዳይሬክት የተደረገው “የነገርኩሽ ዕለት” ፊልም በነገው ዕለት ከቀኑ 10 ሰዓት ጀምሮ በሀገር ፍቅር ትያትር ቤት ይመረቃል፡፡
የፊልሙ ታሪክ፤ አባት ለልጁ የሚከፍለው መስዋዕትነት የሚታይበትና ጊዜያዊ ችግርን ለማለፍ ተብሎ የተዘየደው መላ ኋላ እውነቱ ሲታወቅ የሚያስከትለውን የህይወት ውጣ ውረድ የሚያስቃኝ ነው ተብሏል፡፡
በፊልሙ ላይ፤ ደሳለኝ ኃይሉ፣ አሸናፊ ማህሌት (ይበቃል)፣ ችሮታው ከልካይ፣ ዋሲሁን በላይና ሌሎችም ተውነውበታል፡፡ የ1፡38 ደቂቃ ርዝመት ያለውን ፊልም ሰርቶ ለማጠናቀቅ 1 ዓመት እንደፈጀ ፕሮዱዩሰሩ ደስይበልህ መልቲ ሚዲያ ፕሮዳክሽን ገልጿል፡፡

 በሩሲያ ህፃናት ከፍተኛ ተወዳጅነትን ያተረፉት “ዶ/ር አይቦሊት” እና “ቫክሳ ክሊያክሳ” የተሰኙ የህፃናት መፃህፍት ወደ አማርኛ ተተርጉመው በትላንትናው ዕለት ምሽት በሩሲያ የሳይንስና ባህል ማዕከል የተመረቁ ሲሆን በኢትዮጵያ ለሚገኙ ህፃናት እንዲደርሱ በየት/ቤቱ በስጦታ እንደሚበረከቱ ታውቋል፡፡
መፃህፍቱን ወደ አማርኛ የተረጎሙት በሞስኮ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት መምህር የሆኑትና በርካታ የሩሲያ ሥነ-ፅሁፎችን ወደ አማርኛ በመመለስ የሚታወቁት ፕሮፌሰር ንጉሴ ካሣዬ ወልደሚካኤል ናቸው ተብሏል። ሁለቱ መፃህፍት ወደ አማርኛ ተተርጉመው ለኢትዮጵያ ህፃናት እንዲዳረስ “ሩስኪ ሚር” የተባለ የሩሲያ ተቋም ድጋፍ ማድረጉ ተገልጿል፡፡  

  የዊሊያም ብሉም “Killing Hope” የተሰኘ መጽሐፍ በተርጓሚ ዳሩሰላም “የመንግስታት ዕንባ” በሚል ወደ አማርኛ ተመልሶ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡
መጽሐፉ፤በዓለም ላይ በሚገኙ ህጋዊ መንግስታት ላይ ስለደረሰው ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት፣ መፈንቅለ መንግስት፣ የሥነ ልቦና እና የስውር ጦርነቶች በደል የሚናገር ሲሆን አገራቱ በተገደለው የወደፊት ተስፋቸው ምክንያት መሪር እንባቸውን ሲረጩ ያሳያል፡፡ በመጽሐፉ ውስጥ ከ50 በላይ የሚሆኑ በሲአይኤ እና በወታደራዊ ጣልቃ-ገብነት የተደረጉ መፈንቅለ መንግስቶች፣ የፖለቲካ ሁከቶች፣ወረራዎች፣ ብጥብጦች እና ሌሎችም ቀርበውበታል ተብሏል፡፡
በ287 ገፆች የተቀነበበው መጽሐፉ፤በ55.80 ለገበያ ቀርቧል፡፡

 በፍልስፍና፣ ኪነጥበብና ማህበረሰባዊ ጉዳዮች ላይ በማተኮር፣በተለያዩ ጥልቀት ያላቸው ፅሁፎች በ72 ገፆ ያቀረበችው “ኃልዮ” መፅሄት ሰሞኑን በገበያ ላይ ዋለች፡፡ የመፅሄቷ አብይ እንግዳ ደራሲ አዳም ረታ ነው ተብሏል፡፡ በ50 ብር የምትሸጠው “ኃልዮ”፤ በዩኒቨርሳል የመፃህፍት መደብርና በሌሎችም እንደምትገኝ አዘጋጆቹ ጠቁመዋል። መፅሄቷ ከዚህ ቀደም “መዝገበኞች” እና “ኖህት” በሚሉ ስያሜዎች ለንባብ መቅረቧን ለማወቅ ተችሏል፡፡

 በአይናዲስ በላይ ተደርሶ፣ በመስፍን በላይ ዳይሬክት የተደረገውና በኤምቢ ፊልም ፕሮዳክሽን የቀረበው “ባንቺ የመጣ” የተሰኘ ፊልም ባለፈው ሰኞ ምሽት በብሄራዊ ቴአትር ተመረቀ፡፡
“ፊልሙ በሀገራችን እየተስፋፋና ሴት እህቶቻችንን ለሞት ጭምር እየዳረገ ባለው አስገድዶ መድፈር ላይ ትኩረት አድርጎ የተሰራ ሲሆን በተለይ በዩኒቨርሲቲዎቻችን አካባቢ በሚታየው የሴት ተማሪዎቻችን ህይወት ላይ ያጠነጥናል” ተብሏል፡፡
የፊልሙ ዓይነት በድርጊት የተሞላ ሰስፔንስ ድራማ ሲሆን ፊልሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ 1 ዓመት ከ2 ወር እንደፈጀ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ፊልሙን ለመስራት 780 ሺ ብር እንደፈጀme ተገልጿል፡፡ በፊልሙ ላይ ሳምሶን ታደሰ (ቤቢ)፣ ካሣሁን ፍስሃ (ማንዴላ)፣ ሉሊት ገረመው እና ሌሎችም ተውነዋል፡፡

 በፋሲል ጣሰው ታደሰ፤ ከዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ኢኮኖሚክስ ትምርት ክፍል

   1. መግቢያ
ይህ መጣጥፍ “ጳጉሜ ስድስት” ሥለየትኛው ዘመን መቁጠሪያ ነው የሚናገረው? በሚል ርዕስ በአቶ ሰሎሞን አበበ ቸኮል ተፅፎ ጥቅምት 23, 2006 ዓ.ም በአዲስ አድማሰ ህብረተሰብ አምድ ስር ለቀረበው ተቃውሞ ማፍረሻ የቀረበ ነው፡፡
በአጠቃላይ “ጳጉሜ ስድስት” ሥለየትኛው ዘመን መቁጠሪያ ነው የሚናገረው? በሚል ያነሱት የመከራከሪያ ርእስ ራሱ የሚያስተላልፈው ጠቃሚ መልእክት ነው፡፡ በመሆኑም ጳጉሜ 6 የተሰኘውን አዲስ የጊዜ መጽሐፍ የሚያነብ ሰው ስለ ኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ የሚያገኘው አዲስ ጭብጥ ከመጸሐፉ ጋር እየተነጋገረ መሆኑን የሚገልጽ መልእክት ነው፡፡ ስለዚህ የመረጡት ርእስ ጳጉሜ 6 ስለ ጊዜ ፍጹም የሚናገር መጽሀፍ መሆኑ የመጀመሪያ ማረጋገጫ ውጤት ነው። ምክንያቱም በየ4 አመት አንዴ ብቻ በሰሜንና ደቡብ ሰፊ ሞቃት ምድረ ሰማይ በመከሰት በእጅ ሰዓትና በኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ ላይ የሚመዘገበውን የጳጉሜ 6 እለት በጥንታዊው ሐሳበ ዘመን አስተምህሮት ዘዴ ውስጥ በፍጹም አለመታወቁን በሚመለከት (በተቃውሞ ስም) በጽሁፍ እንዲመሰከሩበት  ማስገደድ በመቻሉ  ነው።
እንዲሁም ጳጉሜ 6፣የኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ የማን ነው? የተሰኘው መጽሐፍ በእኔ ኢኮኖሚክስ መምህሩ ፋሲል ጣሰው መቅረቡን፣ ስለቀን መቁጠሪያው የማያጠያይቅ ደገኛ ሃሳብ ይዤ ማጥናቴንና መመርመሬን፣ በእጅጉ የለፋሁበትና አብዝቼ የተጠበብኩበት መሆኑንና የአመትና ወራቱንም እርዝማኔወች በማጥናት ጠለቅ ያለ አድካሚ ምርመር ማድረጌን ያረጋገጡበት የምስክርነት ቃል የሚያስመሰግኖዎት ቢሆንም በሌላበኩል (የተቃውሞ ፅሁፍ እንዲፅፉ የተገደዱበት) ጳጉሜ ስድስት መፅሀፍ በጭራሽ ስለኢትዮጵያ ዘመን መቁጠሪያ ነው ለማለት የሚከብድ የምርምርና የጥናት ስራ ነው ማለትዎ በእርግጥም ካለጥናትና ምርመር ዘዴ ባልገባዎት እና ባላወቁት ጉዳይ ወደ ክርክር መግባትዎን ያሳያል፡፡
ስለዚህ እጅግ ቀላል ነገር ግን ፍፁም አዲሱን አንጻራዊ የጊዜ የጥናትና ምርምር ስራ ውጤት የሆነውን ጳጉሜ 6 መፅሀፍ ደጋግመው ቢያነቡት ኖሮ የተከተልኩትን ዘመናዊ የጥናትና ምርምር አሰራር ዝርዝር ስልቶች (ጥናቱ የሚፈታቸው መሰረታዊ ተድጋራቶች፣ አላማው፣ ግቦቹ፣ ጊዜ ሽፋኖች፣ መረጃ አይነቶችና ምንጮች፣ የጥናቱ ግኝቶችና ትንተናዎች ወዘተ) ስለሚያውቁና ስለሚገባዎት ባልተቃወሙ ነበር ወይም መፍረስ የሚችልም ከሆነ የማፍረሻ መንገዱን ያውቁት ነበር፡፡
ስለዚህ ያደረጉት ክርከር በኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ መረጃ ላይ የተመሰረተ ባይሆንም ከዚህ ቀጥሎ በተመለከቱት 2 ነጥቦች ላይ መልስ መስጠት ተገቢ ነው፡፡ (1ኛ) በጳጉሜ 6 መፅሃፍ የቀን መቁጠሪያ ወሮች ትችታዊ ዳሰሳ ክፍል ስር ባለመካተቱ የተመሰከረበት ባህረ ሐሳብ፣ (2ኛ) የኢትዮጵያን ቀን መቁጠሪያ ተግባራዊ ጥቅም አውርደን ተጠቀምን ማለት የሚቻለው መቼ ነው?
2.. በጳጉሜ 6 መፅሃፍ የቀን መቁጠሪያ ወሮች ትችታዊ ዳሰሳ ክፍል ስር ባለመካተቱ የተመሰከረበት ባህረ ሐሳብ
“በ1990ዎቹና ከ2000 ዓ.ም ወዲህ ብቻ አስር የሚጠጉ ጽሑፍች በመጽሐፍ በድረ ገጽ እና የምርምርና ጥናት ሥራዎች፣ዓውደ ጥናቶችና ዓውደ ርዕይ ቢቀርቡበትም አለቃ ያሬድ ፈንታ ካሳተሙት ባህረ ሐሳብ መጽሐፍ በስተቀር ሁሉም እንክን አላባቸው”
ከላይ በጥቅስ የተመለከተው የአቶ ሰለሞን አበበ ድምዳሜ፤ ጳጉሜ 6፣ የኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ የማን ነው? የተሠኘውን አዲስ ሳይንሳዊ የጊዜ መጽሃፍ በተቃውሞ ስም እጅግ ተቀባይ መሆኑን ለማረጋገጥ የቀረበ ደጋፊ ክርክር ሁኖ ተወስዷል፡፡ ምክንያቱም የመሰከሩበት ባሕረ ሐሳብ የተሠኛው የአለቃ ያሬድ ፋንታ መፀሃፍ በጳጉሜ 6 መፅሐፍ የኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ ወሮች ትችታዊ ዳሰሳ ክፍል ውስጥ ባለመካተቱ ብቻ ሳይሆን ራሱ ያሉት ባሕረ ሐሳብ መጽሐፍ ጳጉሜ 6ን ስለማያውቅ ጭምር ነው፡፡ በመሆኑም  መከራከሪያ ሐሳቡ ቀጥለው የተመለከቱት አበይት እንከኖች አሉበት፡፡
ሀ). ከዚህ በፊት በቀን መቁመሪያው ዙሪያ የተደረጉት ሁሉም ጽሁፎች ውስጥ የሚታየው እንከን  የርሶዎ ግኝት አይደለም
ባለፋት 16 ዓመታት ውስጥ የኢትዮጵያን ቀን መቁጠሪያ በሚመለከት ወደ 10 ጽሁፎች በመፀሃፍ፣ በድረገፅ ፀዘተ ቢቀርቡበትም ከአንዱ መፀሃፍ በስተቀር ወደ ዘጠኝ ያህሉ ውድቅ ናቸው፤ የሚለው ሀሳብ የፀሃይ ቀን መቁጠሪያ እውቀት ፈጣሪና አረጋጋጭ ባለሥልጣን የሆኑ ያስመሥልብዎታል፡፡
እንዲሁም ከዚህ በፊት በቀን መቁመሪያው ዙሪያ የተደረጉት ሁሉም ጽሁፎች እንከን አለባቸው በሚል የሞገቱ መሆኑን አላሳወቁም፡፡ ስለዚህ የጳጉሜ 6 መፅሐፍ የኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ ወሮች ትችታዊ ዳሰሳ ክፍል ውስጥ ከዚህ በፊት በኢትዮጵያ ቀን መቁመሪያው ዙሪያ የተደረጉት ጽሁፎች እንከን ያለባቸው መሆኑን በተጨባጭ መረጃና ትንተና መረጋገጡን መጠቆም ሲገባዎት፤ “ከዚህ በፊት በቀን መቁመሪያው ዙሪያ የተደረጉት ሁሉም ጽሁፎች እንከን አለባቸው” በማለት ጉዳዩን የእርስዎ ግኝት አስመስለውታል፡፡
ለ.  የተመሰከረበት ባህረ  ሐሳብ፤
ለመከራከሪያ መሠረት ነው ብለው የመሰከሩበት ባህረ ሐሳብ የተሠኘው የአለቃ ያሬድ ፋንታ መፀሃፍ፤ በጳጉሜ 6 መፅሐፍ የኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ ወሮች ትችታዊ ዳሰሳ ክፍል ውስጥ ባለመካተቱ ነው። ምክንያቱም በእርስዎ ጥቆማ መሰረት፤ መጽሀፉን አግኝቼ ስመለከት ማስተዋል የቻልኩት መጽሐፉ የተጻፈው የኢትዩጵያ ወሮች በአመት ውስጥ የሚያሳዩትን የሞቃት ምድር አጭር ቀንና ለሊት ልዩነት ሰአቶች እና 4ቱን መካከለኛ ወቅቶች መነሻና ማብቂያ እለት መረጃዎች መሰረት አድርጎ ሳይሆን ልክ እንክን አለባቸው እንደተባሉት ሌሎቹ ፀሀፊዎች ሁሉ ማሳየት የማይችሉትን የሰሜን ቀዝቃዛ ምድረ ሰማይ ረጅም ቀንና ለሊትሰዓት ልዩነት  እና ከፍተኛ ወቅቶች መረጃዎችን ነው፡፡ ከዚያም በላይ ጳጉሜን በአጭር ቀንና ለሊት ሰዓት ልዩነት፤ በአመት 12ኛ ወር  እና 94 እለት በሚሸፍነዉ 4ኛዉ ወቅት (በሰሜን ሞቃት ክረምት እና በደቡብ ሞቃት በጋ) ውስጥ መገኘቱን ባለመካተቱ ምክንያት  አቶ ሰለሞን ጳጉሜ 6 የተሰኘውን አዲስ የጊዜ መጽሐፍ አልቀበልም በሚል አላግባብ ለሙግት የተጋለጡበትን ምክንያት ያሳያል፡፡
ሐ. ከፀሀይ አመት የተሰሩ 7ት ተግባራዊ የጊዜ መለኪያ አሐዶች፤
“በሐሳበ ዘመኑ ትምህርት ዘዴ ሰባት አዕዋዳት ውስጥ ሶስቱ በእለታት (ዐውደ እለት፣አውደ ወርሃና ዐውደ ዓመት) እና 4ቱ በአመታት (አውደ እበቅቴ፣ዓውደ ፀሃይ፣ዓውደ ማህተም እና አወደ ቀመር) መቆጠራቸውን፣ የአውደ አመት አሃድም (unit) እለት መሆኑን እና ሐሳበ ዘመኑ በአሐዶች እንኳን ልዩ ጥንቃቄ የሚያደርግ ነው”
የሚለው መከራከሪያ ሐሳብ ጳጉሜ 6 መፅሐፍ የጊዜ መለኪያ አሐዶችን አልተጠቀመም የሚል ይመስላል፡፡
ነገር ግን የኢትዮጵያ እየተባለ እዚህ ተሸሽጎ የሚገኘውን ቀን መቁጠሪ ከጠባብ ቀዝቃዛ ምድር አገሮቹ የግሪጎሪያን ቀን መቁጠሪያ ጋር በማገናዘብ የሰሜንና ደቡብ ሰፊ ሞቃት ምድር አገሮች ቀን መቁጠሪያ መሆኑን ያረጋገጥኩት በአመት ውስጥ የሚገኙትን 7 ተግባራዊ የጊዜ መለኪያ አሃዶችን በመጠቀም ነው። ከፀሀይ ዓመት የተሰሩት 7 የጊዜ መለኪያ አሃዶች በሁለት የተከፈሉ ናቸው፡፡ በእጅ ሰዓት ላይ በ12 ሰዓት ቀን እና በ12 ለሊት ተከፍለው የሚመዘገቡት  ሶስት ትናንሽ የጊዜ መለኪያ አሃዶች ማለትም (1ኛ) ሠከንድ (የደቂቃ አንድ 60ኛ ክፍል)፣ (2ኛ) ደቂቃ (60 ሰከንድ) እና(3ኛ) ሰዓት (60 ደቂቃ) ሲሆኑ፡ በቀን መቁጠሪያ ላይ የሚመዘገቡት 4 ትላልቅ የጊዜ አሃዶች፡- (4ኛ) እለት (24 ሰዓት)፣(5ኛ) ሳምንት (7 እለት) ፣(6ኛ) ወር 30፣35 እና 36 እለት (የኢተዮጵያ) እና 28፣29፣30 እና 31 እለት (የግሪጎሪያን) እና (7ኛ) ዓመት (365 እና በየአራት አመት 366 እለት) ናቸው፡፡
በመሆኑም በኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ የሚመዘገቡት የዓመተ ምህረት አመታት፣ ወራት፣ ሳምንታት፣ እለታት እና የየእለቱ አጭር የቀንና ለሊት ልዩነት በግሪጎሪያኑ ቀን መቁጠሪያ ከሚመዘገቡት የአመተ ምህረት ዓመታት፣ ወራት፣ሳምንታት፣ እለታት እና የየእለቱ እጅግ ረዥም የቀንና ለሊት ልዩነት የተለዩ መሆናቸውን በተጨባጭ ማስረጃና በአንጻራዊ የጊዜ ሂሳብ ትንተና ዘዴ ማረጋገጥ ተችሏል፡፡ ይህም በጳጉሜ 6 መፅሐፍ ውስጥ በጥልቀትና በዝርዝር ቢገኝም እርስዎ አልገባኝም ያሉበት ምክንያት ከላይ ጥንቃቄ ያደርጋል ያሉት ጥንታዊው የሐሳበ ዘመኑ ትምህርት አስተምሮት ዘዴ በዓመት ውስጥ ከሚገኙት 7ተግባራዊ የጊዜ መለኪያ አዕዋዳት ውስጥ 4ቱን መሰረታዊ የጊዜ መለኪያ አሀዶች ማለትም ሳምንት፣ሰዓት፣ደቂቃ እና ሰከንድን አካትቶ ባለማስተማሩ የተነሳ ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ ወሮች እና በግሪጎሪያን ቀን መቁጠሪያ ወሮች መካከል ያለውን ልዩነት አጢኖት ስለሚያውቅ ጭምር መሆኑን መገንዘብ ተችሏል፡፡
መ. በጳጉሜ 6 ቀን ፡5999 ዓመተ ዓለም፡
የጳጉሜ 6 ጥያቄ የርስዎም ጥያቄ ነው ማለት አስቸጋሪ ነው፡፡ ምክንያቱም ጳጉሜ 6 የማትታወቀው የክርክር መሰረት ነው ብለው በጠቀሱት የአለቃ ያሬድ ፈንታ “ባህረ ሐሳብ” መጽሐፍ ብቻ ሳይሆን  በንቡረ እድ ኤርሚያስ ከበደ ወልደ ኢየሱስ “ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት” በተሰኘው መጽሐፍ ጭምር ተጽፎ የሚገኘው ጳጉሜ 5 ብቻ ነው፡፡
“በኢትዮጵያን የዘመን አቆጣጠር ሥርዓት፤ እንዲሁም … ኢየሱስ ክርስቶስ፡ ከድንግል ማርያም የተወለደበት ጊዜ፡ በጳጉሜ 5 ቀን ፡5500 ዓመተ ዓለም፡ ከለሊቱ 6 ሰዓት ሞልቶ፡ አንዲት ካልዕት ለማትሞላ አፍታ፡ጥቂት እልፍ ብላ በነበረችው ቅጽበት ውስጥ መሆኑ ነው፡፡ መስከረም 1 ቀን፤ 1 ዓመተ ምህረት ተብሎ የዓመተ ምህረት ዘመን አቆጣጠር የጀመረው በዚያች፡ የዓመተ ኩነኔ፡ ወይም የዓመተ ፍዳ ማብቂያ ከሆነችው፡ ጳጉሜ 5 ቀን ፡5500 ዓመተ ዓለም፡ ከለሊቱ 6 ሰዓት በኋላ ከነበረችው ቅጽበት ጀምሮ ኾኗል፡፡” ንቡረ እድ ኤርሚያስ ከበደ ወልደ ኢየሱስ (1997፡306)፡፡
ስለዚህ ስለርሱ ከተጻፉት ውስጥ አንዳችም ስህተት የሌላቸው ስንቶቹ ይሆኑ? ለሚለው ጥያቄ መልሱ የጳጉሜ 6ን እለት ሳያካትቱ አጠቃላይ የጻፉት በስህተት የተሞላ ብቻ ሳይሆን ውጤቱም ያልተሟላ ነው፡፡ ከዚያም በላይ በእነርሱ ዘንድ በፀሐይ አመት 365.25 እለት ንድፈ ሐሳብ እና ይህንን ንድፈ ሐሳብ ወደ መሬት ባወረደው የኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ ጋር ያለመተዋወቅ መሰረታዊ ተግዳሮት መኖሩን ያሳያል፡፡
ስለዚህ ከላይ በጥቅስ ውስጥ የተመለከተው ሀሳብ ሦሥት መሰረታዊ እንከኖች አሉበት፡፡ (1ኛ) ጳጉሜ 6ን አያውቀውም በዚሁ ምክንያት የ6ኛ ሺህ ማብቂያ 5999 ዓመተ ዓለም መሆኑን አላወቀም፡፡ (2ኛ) በኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ ህግ መሰረት ኢየሱስ ክርስቶስ፡ ከድንግል ማርያም የተወለደበት ጊዜ ለሊት ሳይሆን ጧት ነበር፡፡ (3ኛ)  በሦሥት ምድብ አራት ዓመት የፀና ዙር መሰረት የመጀመሪያው ዙር አራት ተከታታይ ዓመተ ምህረት ዓመቶች 0 ምድብ አንድ፤1 እና 2 ምድብ ሁለት እና 3 ምድብ ሦሥት ነበሩ፡፡ 0፤1ና2 እያንዳንዳቸው ባለ 365 እለት ዓመት ሲሆኑ፤ 3 ዓመተ ምህረት ግን የመነሻ እምርታ አመት ባለ 366 እለት ነው፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ 1996፤1997 እና 1998 እና 1999 በሦሥት ምድብ አራት ዓመት የፀና ዙር መሰረት 500ኛ ዙር አራት ተከታታይ ዓመተ ምህረቶች ነበሩ፡፡ እንዲሁም 2004፤2005 እና 2006 እና አሁን የምንገኝበት አመት 2007 502ኛው ዙር የሶስት ምድብ አራት አመተ ምህረቶች ናቸው፡፡ ስለዚህ እየሱስ ክርስቶስ የተወለደበት ዓመተ ምህረት የመጀመሪያው ሦሥት ምድብ አራት አመት ሁለተኛ አመተ ምህረት (መስከረም 1 ቀን፤ 1 ዓመተ ምህረት) ላይ ሳይሆን መስከረም 1 ቀን 0 ዓ.ም. በኢትዮጵያ እና ሰብቴምበር 12 ቀን 7 ዓ.ም በግሪጎሪያን ላይ ነዉ፡፡
በመሆኑም ከላይ በጥቅስ የተመለከተው የንቡረ እድ ኤርሚያስ ከበደ ወልደ ኢየሱስ ሐሳብ ከዚህ እንደሚከተለው መጻፍ ነበረበት፡፡
በኢትዮጵያውያን የዘመን አቆጣጠር ሥርዓት፤ እንዲሁም … ኢየሱስ ክርስቶስ፡ ከድንግል ማርያም የተወለደበት ጊዜ፡ በጳጉሜ 6 ቀን ፡5999 ዓመተ ዓለም፡ ከጧቱ 12 ሰዓት ሞልቶ፡ አንዲት ካልዕት ለማትሞላ አፍታ፡ ጥቂት እልፍ ብላ በነበረችው ቅጽበት ውስጥ መሆኑ ነው፡፡ መስከረም 1 ቀን፤ 0 ዓመተ ምህረት ተብሎ የዓመተ ምህረት ዘመን አቆጣጠር የጀመረው በዚያች፡ የዓመተ ኩነኔ፡ ወይም የዓመተ ፍዳ ማብቂያ ከሆነችው፡ጳጉሜ 6 ቀን ፡5999 ዓመተ ዓለም፡ ከጧቱ 12 ሰዓት በኋላ ከነበረችው ቅጽበት ጀምሮ ኾኗል፡፡
ሥለዚህ በጳጉሜ 6 እለት ተፈጥሮ መሰረት ጊዜ ማለት ዘላለም ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ከላይ የተገለጹት 7 ተከታታይ የጊዜ መለኪያ አሃዶች  ውስጥ 3ቱ  በእጅ ሰኣት እና 4ቱ በቀን መቁጠሪያ ላይ በቁጥር እየተሰፈሩ በመመዝገብ ላይ ናቸው፡፡ በመሆኑም በእጅ ሰኣት ላይ የሚመዘገቡትን የእለት አሀድ መሰረት የሆኑትን ሰዓት፣
ደቂቃ እና ሰከንድን እና በቀን መቁጠሪያው ላይ የሚመዘገቡትን የአመተ ምህረት ዓመት፡ 12 ወራት፤ 52 ሳምንት ከ 1 እና 2 እለት ሳይገነዘቡ ወደማይገባ ክርክር መግባትዎትን ያሳያል፡፡ በመሆኑም የ7ቱም ተግባራዊ የጊዜ መለኪያ አሃዶች  እና የሶስት ምድብ አራት አመት፤ 28 አመት እና ሚሊኒየም (1000 ዓመት) መሰረት ምንጭ የሆነችውን ጳጉሜ 6 ሳያውቁና ሳይቀበሉ፤ የሐሳብ ዘመኑ ትምህርት ዘዴ ሰባት አዕዋዳት አሉት የሚለውን የጨበጣ ሀሳብ መቀበል እጅግ አስቸጋሪ መሆኑን መጠቆሙ አስፈላጊ ነው፡፡
የኢትዮጵያን ቀን መቁጠሪያ ተግባራዊ ጥቅም አውርደን ተጠቀምን ማለት የሚቻለው መቼ ነው?
“አንፃራዊ ጊዜን /ዘመንን፣ እንደነ አልበርት እና ስቴፊንግ ሆውኪንግ ያሉ የሳይንስ ጭንቅሌዎች በ20ኛው መቶ ክ/ዘመን ከልደት ወዲህ ሊደርሱባት የቻሉትን የጊዜ ዘመን ፍቺ ከጥንት ጀምሮ ይዞ፣ ተግባራዊ ጥቅም ላይ በሚውልበት አያያዝ አውርዶ ሲጠቀምበት የኖረ የዘመንና የዓለም ሐሳብ ነው”
ከላይ በተገለጸው መከራከሪያ ሀሳብ መሰረት የአንፃራዊ ጊዜን ትርጉም  የሚያውቁ ከሆነ፤የኢትዮጵያን ቀን መቁጠሪያ ለምን ጥንታዊ ብቻ አድርገዉ ደመደሙ የሚለውን ጥያቄ መመለስ አለብዎት፡፡ጥንት ማለት ዛሬንና ነገን ማየት የማይችል ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የአንፃራዊ ጊዜን ትርጉም ሳይረዱ ስለጊዜ መናገር ኢሳይንሳዊና ኢተፈጠሮዋዊ ነው፡፡ ማነጻጸር ማለት ምን ማለት ነው? ጳጉሜ 6 የኢትዮጵያን ቀን መቁጠሪያ ከግሪጎሪያን ቀን መቁጠሪያ ጋር በ7 ተግባራዊ የጊዜ መለኪያ አሃዶች በግልጽና ለማንም በሚገባ ሁኔታ በማነጻጸሩ ምክንያት  የሚናገር መጽሐፍ ነው ብለው የምስክርነት ቃል አልሰጡምን?
ስለዚህ ከላይ  የገለፁት … ተግባራዊ ጥቅም ላይ በሚውልበት አያያዝ አውርዶ ሲጠቀምበት የኖረ የዘመንና የዓለም ሐሳብ ነው የሚለው ሐሰት ቢሆንም፤ የሚከተለውን አዲስ ጥያቄ በመፍጠሩ እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ የኢትዮጵያን ቀን መቁጠሪያ ተግባራዊ ጥቅም አውርደን ተጠቀምን ማለት የሚቻለው መቼ ነው?  
የኢትዮጵያን ቀን መቁጠሪያ ተግባራዊ ጥቅም ላይ ልናውል የምንችለው በዚህ በኢትዮጵያ ውስጥ ከማንኛውም ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ እና ፖለቲካዊ እሴት የተዘለለችውን ጳጉሜን ማግኘት ብቻ ሳይሆን የግሪጎሪያኑን ቀን መቁጠሪያ ኢ-ተፈጥሮዊና ኢ-ሳይንሳዊ ጥቅም በማስቀረት በሰሜንና ደቡብ ሰፊ ሞቃት ምድር ውስጥ የሚከሰቱት መካከለኛ የተፈጥሮ ወቅቶች፣ አጭር ቀንና ሌሊት ሠዓት ልዩነት እና ማናቸው ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ፣ፖለቲካዊ እና ሃይማኖታዊ ሥራዎች ሲመዘገቡበት ብቻ ነው፡፡ ስሊዚህ ይህን አዲስ ስራ የመተግበርና ማስተግበር አመራር በኛ ኢትዮጵኖች እጅ እና በመላዉ የአለም ህዝብ እጅ ላይ የወደቀ መሆኑን ማወቅ ይገባል፡፡
በመጨረሻ የባሕረ ሐሳብ አስተምሮት ዘዴ በፀሐይ አመት 365.25 እለት ንድፈ ሐሳብ እና ይህንን ንድፈ ሐሳብ ወደ መሬት ባወረደው የኢትዮጵያ ቀን መቁጠሪያ ጳጉሜ 6 ጋር ፍጹም ያለመተዋወቅ መሰረታዊ ተግዳሮት እንዳለበት በጉልህ እንዲታይ አድረገዋል፡፡ በመሆኑም ላደረጉበት የተቃውሞ ተሳትፎ አመሰግናለሁ፡፡

Saturday, 01 August 2015 14:26

የፀሐፍት ጥግ

(ስለ ተፈጥሮና ውበት)
ተራሮቹ እየተጣሩ ነው፤ እናም መሄድ አለብኝ፡፡
ጆን ሙይር
ውበት እውነት ነው፤ እውነትም ውበት፡፡
ጆን ኪትስ
ማናቸውም ውብ ነገሮችን የማየት ዕድል አያምልጣችሁ፡፡ ውበት የእግዚአብሄር የእጅ ፅሁፍ ነውና፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኢመርሰን
ዛፍ ብሆን ኖሮ ሰውን የምወድበት ምክንያት አይኖረኝም ነበር፡፡
ማጊ ስቲፍቫተር
ተፈጥሮ የሚጎበኝ ሥፍራ አይደለም፡፡ ቤታችን ነው፡፡
ጌሪ ስኒደር
አንገቴ ላይ አልማዝ ከማደርግ ይልቅ ጠረጴዛዬ ላይ ፅጌረዳ አበባ ቢኖረኝ እመርጣለሁ፡፡
ኢማ ጎልድማን
ቅድመ አያትህ እንደ ምግብ ያልተቀበሉትን ምንም ነገር አትብላ፡፡
ማይክል ፓላን
በዓለም ላይ ያለውን ውበት መመልከት፣ አዕምሮን የማጥሪያ የመጀመሪያው እርምጃ ነው፡፡
አሚት ሬይ
ተፈጥሮን በጥልቀት ተመልከት፤ ያን ጊዜ ሁሉንም ነገር የተሻለ ትረዳለህ፡፡
አልበርት አነስታይን
በምድር ላይ ገነት የለም፤ ነገር ግን የገነት ሽርፍራፊዎች አሉ፡፡
ጁሌስ ሬናርድ
ከእያንዳንዱ ደመና ጀርባ ሌላ ደመና አለ፡፡
ጁዲ ጋርላንድ
ምድር ባዶ እግራችሁን ስትዳስሳችሁ እንደሚያስደስታትና ነፋስ ከፀጉራችሁ ጋር መጫወት እንደሚናፍቀው አትርሱ፡፡
ካሊል ጂብራን
ፊታችሁን ለመመልከት በመስተዋት ትጠቀማላችሁ፤ ነፍሳችሁን ለመመልከት በጥበብ ሥራዎች ትጠቀማላችሁ፡፡
ጆርጅ በርናርድ ሾው