Administrator

Administrator

አንድ የፈረንጆች ተረት አለ፡፡
ኮረዶች በማፍቀር ዕድሜ ላይ ያሉ ጐረምሶች፤ “የት ሄደን ነው ራት የምንገባበዘው?” ሲባባሉ፤ አንደኛው፤
“ኦሽን-ቪው ሆቴል እንሂድ” አለ
“ለምን?” ሲሉት፤
“እዚያ ቆንጆ ቆንጆ፣ የሚታዩ ኮረዶች አሉ!” አለ፡፡
ሁሉም ተስማሙና ሄደው በርቸስቸስ ሲሉና ሴት ሲያጫውቱ አመሹ፡፡
ይህ በሆነ ከአሥር ዓመት በኋላ እንደዚሁ ተገናኙ፡፡ “የት እናምሽ?” የሚል ጥያቄ ተነሳ!
“ኦሸን-ቪው ሆቴል” አለ አንዱ፡፡  
“ለምን?” አሉት፡፡
“ጥሩ ራትና ጥሩ መጠጥ አለ” አለ፡፡
ይህ በሆነ ከአሥር ዓመት በኋላ ዳግም ተገናኙ፡፡ አሁን ወደ ሰባ ዓመት ተጠግቷቸዋል እንግዲህ
“የት እንብላ ራት?” ተባለ፡፡
“ኦሺን ቪው ሆቴል” አለ አንደኛው፡፡
    *    *     *
“ለምን?” አሉት፡፡
“በጣም ፀጥ ያለ፣ የውቂያኖሱን ሰላምና ነፋሻ አየር የምናገኝበት ቦታ ነዋ!” አላቸው፡፡
ተያይዘው ነፋሻውንና ፀጥ ያለውን አየር ሲኮመኩሙ አመሹና ተለያዩ፡፡
ይሄ በሆነ ከአሥር ዓመት በኋላ እንደገና ተገናኙ፡፡ አሁን ጎብጠዋል፡፡ ከዘራ ይዘዋል፡፡ ባርኔጣ አድርገዋል፡፡ በጣም በዝግታ ነው የሚራመዱት፡፡ እየተደጋገፉ እየተቃቀፉ ነው የሚቆሙት፡፡
“ዛሬስ ለእራት የት እንሂድ?” አለ አንደኛው፡፡
“ኦሽን ቪው ሆቴል” አለ ሌላው፡፡
“ለምን?” ብለው ጠየቁ ሌሎቹ፡፡
ሰውዬውም፤
“እዛ ሆቴል ሄደን አናውቅማ!”
“ብራቮ! አዲስ ሆቴል ማየት በጣም ደስ ይላል” አለ አንዱ፡፡  
“ድንቅ ሀሳብ!”
“አስገራሚ ሀሳብ!”
“ጉደኛ ሀሳብ!” እየተባባሉ እየተጓተቱ፣ እየተገፋፉ፣ መሰሰሰስ እያሉ፤ ወደ ኦሽን ቪው ሆቴል አመሩ፡፡
*   *   *
የተፈጥሮን ሂደት ለማቆም አይቻልም፡፡ ይህን የተፈጥሮና የዕድሜ መሰላል፤ በየዕለቱ ከሚገጥመን አገራዊ ችግርና አፈታቱ ጋር ለማስተያየት ብንሞክር፤ አርጅተን ጃጅተን የሠራነውንና ያልሠራነውን፣ የሄድንበትንና ያልሄድንበትን ለመለየት የማንችልበት የመርሳት ዕድሜ እስከምንደርስ ንቅንቅ አልልም ብለን፤ በያዝነው ሥልጣንና ሹመት ሙጭጭ ካልን፤ በዚያውም ለተተኪው ትውልድ ቦታ ካልለቀቅን፤ የአገር- ለውጥ- ቀን እየራቀ ነው የሚሄደው፡፡ በእርግጥም ይሄ ቦታን በሰላም የመልቀቅ ባህል የዋዛ ነገር አይደለም፡፡ ፖለቲካዊ-ገፅ አለው፡፡ የኢኮኖሚ-ገፅ አለው፡፡ የግል ጥቅም-ገፅ አለው፡፡ ከፓርቲ ጋር፣ከራስ ጥቅም ጋር፣ ከራስ ህሊና ጋር መሟገትንና መታገልን ይፈልጋል፡፡ ይህን ዋጋ ለመክፈል ፈቃደኛ የሆነ በማይገኝበት ዘመን የአገር ምጧ ብዙ ነው፡፡
ወጣቱ ላይ ዕምነት ይኑረን፡፡ ያለ ጥርጥር ወጣቱ አሸናፊ ነው፡፡ The New is invincible ይሉ ነበር የጥንት ፖለቲከኞች፡፡ ዛሬም ይሄ ዕውነታ አይሻርም፡፡ አዲስ ኃይል መፍጠር የአገር አቅም መፍጠር ነው። ይህ ማለት ግን የግድ በፖለቲካ የሚታቀፍ ወጣት ይኑረን ማለት አይደለም፡፡
“ያፈረሰ ቄስ ተመልሶ አይቀድስ፣ የሸሸ ንጉሥ ተመልሶ አይነግሥ” በሚባልበት አገር የማይሻሩና በልብ ፅላት ላይ የተፃፉ ህግጋት አሉ፡፡ እነዚህ በባህልና በማህበራዊ ልምድ የዳበሩና የታመኑ ናቸው! አገር ያወቃቸውና ያመነባቸው የወል ህግጋት እንዳሉ ሁሉ፤ ሰው በግሉ በራሱ ላይ የሚወስንባቸው ግለ-ደንቦችም አሉ፡፡ እንዲህ ያሉት ህገ-ደንቦች ሲበራከቱ ስደት ልጓም ያጣል፡፡ ስደተኛው የትየለሌ ቢሆን የማይገርመው ለዚህ ነው! ውጤቱን እንደ ዛሬው በአስከፊ መልኩ ባንቀምሰውም በውሱን መልኩ የምናውቀው ስደትና አስከፊ ውጤት ነበር፡፡ “የራሱን ጭራ ሳያይ ውሻ ፍየልን ጭራሽን ዝቅ አድርጊ” ይላል የሚል ኦሮምኛ ተረት አለ፡፡ የራሳችን ነውር ሳይታየን ስለ ሌላው አስነዋሪ ነገር መናገር ክፉ እርግማን ነው! የሌሎቹን አገሮች፤ ፓርቲዎች፣ ግለሰቦችም ሆኑ ቡድኖች ስንተች እኛስ? የእኛስ? ብለን መጠየቅን አንርሳ! ልማዶቻችንን፣ በዓሎቻችንን ስብሰባዎቻችንን እንገምግም፣ እንመርምር፣ እናሻሽል፡፡ በዓላት በራሳቸው ግቦች አይደሉም፡፡ ወደፊት መራመጃ እንጂ!  
ከፖለቲካ ባህላችን ውስጥ እጅግ ሚዛን የሚደፋ አንድ ባህል አለ፡፡ ብዙ ሊጤን ይገባል! የይቅር መባባል ባህል!  ቂም፣ የወንጀለኝነት-ስሜት፣ ብድር-የመመለስ ፍላጎት፤ አጥፊ ናቸው፡፡ ዴቪድ ሀውኪንስ እንዲህ ይለናል፡፡ “የ2ኛው የዓለም ጦርነት አንጋፋ ተሳታፊዎች አሰቃቂውንና አንገፍጋውፊን ጦርነት ከተወጡ በኋላ አብዛኞቹ የጠላት ተፋላሚዎች በፍጥነት ይቅርታ ተደራረጉ፣ ይቅር ተባባሉ፡፡ ሰላምታ ተሰጣጡ፡፡ የፍልሚያውን ፍፃሜም በዓል አከበሩ፡፡ በአዲስ የመተሳሰብ መንፈስ ተጨባበጡ፡፡ አሜሪካኖች አቶሚክ ቦምብ የጣሉና በሺዎች የሚቆጠሩ ሲቪሎችን የቀጠፉ ነበሩ፡፡ ጦርነቱ ካበቃ በኋላ ግን “በቃ ጦርነትኮ ይሄው ነው” ተባለ! የትላንት ተፋላሚዎች የዛሬ ጓደኛ ሆኑና ይጠያየቁ ጀመር፡፡ ይሄው እስካሁንም የተረፉት ታላቁን የጦርነት ቀን ያከብራሉ”
በአያሌ ሰዎች በተግባር እንደተረጋገጠው፤ አሉታዊ አመለካከትና የወንጀለኛነት ስሜት ፤በአዎንታዊ የመረዳት ስሜት፣ በመረዳዳትና በትውስታ ስሜት፤ ሊተካ ይችላል፡፡ … በዚህ ስሜት ሲታይ ከዚህ ቀደም ይጠሉ የነበሩ ሰዎች ይቅርታን ሊያገኙ ይችላሉ፡፡ ከዚህ ቀደም ያስፈሩ የነበሩ ሰዎችም አሁን ሰላማዊ ሆነው ሊታዩ ይችላሉ፡፡ ዋናው ራስን ለማየትና ጥፋትን ለመቀበል ዝግጁ የመሆን ጉዳይ ነው። እርግጥ እንደኛ በፊውዳሊዝም ለተተበተበ፣ ባልለየለት ካፒታሊዝም ለታጠረና ሁሉን ጥፋት በሌሎች ላይ መላከክን ሥራዬ ብሎ ለያዘ ህብረተሰብ ፤ ከአባዜው በቀላሉ ለመገላገል አይቻልም! ሆኖም ይቻላል ብለን አዕምሮአችንንና ልቡናችንን ክፍት እናድርግ፡፡ ለዚህ ቁልፉ ነገር፤ አንዱ ከሌላው መማሩ ነው፡፡ ችግሩ ግን ያልተማረው የተማረውን ካላስተማርኩ፣ አላዋቂው አዋቂው ካላዳመጠኝ የሚልበት፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ በአዕምሮም በአካልም ያልዳበረው ሰው፤ ልምድ ያለውንና የዳበረውን ሰው፤ ዘራፍ ሲልበት፣ ሲፎክርበት፣ ከእኔ ወዲያ ላሣር ሲለው የታየበት አገር መሆኑ ነው! “አውራ ዶሮ ፈረሱን ረግጦ፤ ‘እርግጫ ከእኔ ተማር!’” አለው፤ የሚለው የኦሮምኛ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው!!

“አገራችን ታላቅ ልጇን አጥታለች፣ ህዝባችን አባቱን ተነጥቋል፣ ይህቺ ቀን መምጣቷ እንደማይቀር ብናውቅም የዛሬዋ እለት ይዛው የመጣችው ሃዘን ፍጹም ጥልቅና በምንም ነገር የማይሽር ነው!!” የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ጃኮቭ ዙማ፣ ጥቁር ለብሰው በአገሪቱ ብሄራዊ ቴሌቪዥን መስኮት ብቅ አሉና መሪር ሃዘን ባጠላበት ፊት፣ በተሰበረ አንደበት ተናገሩ፡፡ ይህ ደቡብ አፍሪካን ብቻ ሳይሆን መላውን አለም ያስደነገጠ፣ የብዙዎችን ልብ ክፉኛ የሰበረ ትልቅ መርዶ ነው - ብሄራዊ ሃዘን፡፡ ከትናንት በስቲያ እኩለ ሌሊት ገደማ አለም የማዲባን መፈጸም ተረዳ፡፡ የጸረ አፓርታይድ ታጋዩ፣ የመብት ተሟጋቹ፣ የነጻነት ተምሳሌቱ፣ የይቅርታ ምልክቱ፣ የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ኔልሰን ሮሊህላላ ማንዴላ በተወለዱ በ95 አመታቸው ሃሙስ ሌሊት ተፈጸሙ፡፡ ትራንስኪ ላይ የጀመረው የማንዴላ የህይወት ጉዞ፣ ዘመናትን ከዘለቀ የትግል፣ የፈተና፣ የድል… የክፉና የደግ፣ የዳገትና የቁልቁለት ፍሰት በኋላ፣ ከትናንት በስቲያ ጆሃንስበርግ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው ተቋጨ፡፡ የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚደንት ኔልሰን ማንዴላ ጤና ከራቃቸው አመታት ተቆጥረዋል። የጤናቸው ጉዳይ አልሆን ብሏቸው ከአደባባይ የራቁትና ቤት መዋል የጀመሩት እ.ኤ.አ በ2004 የመጀመሪያዎቹ ወራት ገደማ ነበር፡፡ ጤና ውሎ ማደር ያቃታቸው ማንዴላ፣ ከዚህ በኋላ ያሉትን አመታት በቤታቸውና በሆስፒታሎች መካከል እየተመላለሱ ነው ያሳለፉት፡፡ የጤናቸው ጉዳይ እየዋል እያደር አሳሳቢ መሆኑን የቀጠለው ማንዴላ፣ እስካለፈው መስከረም የነበሩትን ሶስት ወራት ፕሪቶሪያ በሚገኝ ሆስፒታል ውስጥ ተኝተው ክፉኛ የጸናባቸውን የሳንባ ኢንፌክሽን በመታከም ነበር ያሳለፉት፡፡ ህክምናው ተስፋ እማይሰጥ መሆኑ ታውቆ በመስከረም ወር መጀመሪያ ወደ መኖሪያ ቤታቸው እንዲመለሱ የተደረጉት ማንዴላ፣ ዙሪያቸውን በቤተሰቦቻቸው ተከበው በተኙበት ነው ሃሙስ ምሽት ይህቺን አለም የተሰናበቱት፡፡ የማዲባን ህልፈት በውድቅት ሌሊት የሰሙት ደቡብ አፍሪካውያን፣ በእንቅልፍም ሆነ በእረፍት የሚያሳልፉት ቀሪ ሌሊት አልነበራቸውም፡፡ መሪር ሃዘን ልባቸውን የሰበረው ደቡብ አፍሪካውያን ስለ ማንዴላ እንባቸውን አፈሰሱ፡፡ ከሶዌቶ እስከ ፕሪቶሪያ፣ ከኬፕታውን እስከ ጆሃንስበርግ በመላ አገሪቱ ሃዘን ሆነ፡፡ “ማዲባ!... ማዲባ!... ማዲባ!...” ሁሉም ይህን ስም መጥራት፣ ይህን ሰው ማሰብ ያዘ፡፡ ደቡብ አፍሪካውያን ስለ ጀግናቸው ሻማ ለኩሰው አደባባይ ወጡ፡፡ በጥቁሩ ጨለማ ውስጥ ‘የጥቁሩን ብርሃን’ ፎቶግራፎች ይዘው ጎዳናዎችን ሞሏቸው፡፡ “ማንዴላን አላየነውም የታሰረበት ሄደን ማንዴላን አላየነውም!...” እያሉ የክፉ ቀን ዜማቸውን አቀነቀኑ፡፡ የአፓርታይድ አገዛዝ ዘመን መዝሙሮችን ከፍ ባለ ድምጽ ዘመሩ፡፡ የደቡብ አፍሪካ ሰንደቅ ዓላማ፣ በትግልና በመስዋዕትነት ከፍ ላደረጓት የአርነት ታጋዩዋ ዝቅ ብላ ተውለበለበች፡፡ ሀዘኑ የደቡብ አፍሪካውያን ብቻ አይደለም፡፡ አለማቀፍ መገናኛ ብዙሃን ከጃኮቭ ዙማ አንደበት የተሰማውን መርዶ እየተቀባበሉ አስተጋቡት። የአለም ህዝቦች በሰሙት ነገር ክፉኛ ደነገጡ፣ አብዝተው አዘኑ፡፡ “እሳቸው የሰሩት፣ ከማንኛውም ሰው ከሚጠበቀው በላይ ነው፡፡ ስራቸውን ፈጽመው ወደማይቀረው ቤታቸው ቢሄዱም፣ ማንዴላ የዘመናት ሁሉ ሃብት ናቸው” አሉ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤ ከወደ ኋይት ሃውስ ባሰሙት የሃዘን መግለጫ ንግግራቸው፡፡ በሞታቸው ጥልቅ ሃዘን እንደተሰማቸው በስሜት ተውጠው የተናገሩት ኦባማ፤ የአሜሪካ ሰንደቅ ዓላማዎች በሙሉ እስከ ሰኞ ድረስ ስለማንዴላ ክብር ዝቅ ብለው እንዲውለበለቡ ትዕዛዝ ሰጥተዋል፡፡ የአሜሪካም ብቻ ሳይሆን የፈረንሳይና ሌሎች አውሮፓ አገራት፣ የአውሮፓ ህብረት እና የፊፋ ባንዲራዎችም ዝቅ ብለው እንዲውለበለቡ ተወስኗል፡፡ ከአፍሪካ እስከ አውሮፓ፣ ከእስያ እስከ መካከለኛው ምስራቅ በአለም ዙሪያ ያሉ የሌሎች በርካታ መንግስታትም ስለ ማንዴላ ሞት የተሰማቸውን ጥልቅ ሃዘን መግለጽ ይዘዋል፡፡ “እጅግ እጅግ አዝኛለሁ! ለአገሩ በጎ ነገር ለማምጣት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል ሲሰራ የኖረ ታላቅ ሰው ነው፡፡ የማንዴላን ታላቅነት የምትመሰክረው፣ ሰላም ውላ የምታድረው ደቡብ አፍሪካ ናት!” ብለዋል የእንግሊዟ ንግስት ኤልዛቤጥ መርዶውን እንደሰሙ ከቤኪንግሃም ቤተመንግስት ባስተላለፉት የሃዘን መግለጫ መልዕክት፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሃፊ ባንኪ ሙን በበኩላቸው፣ “ለፍትህ የተጋ ታላቅ ሰው፣ ለሰው ልጆች የበጎነት ምሳሌና የመነቃቃት ምንጭ” በማለት ነው ማንዴላን የሚገልጹዋቸው፡፡ “በታሪካችን ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ተገኝቶ ይመራን ዘንድ ማንዴላን የፈጠረልን አምላክ፣ እኛን ደቡብ አፍሪካውያንን አብዝቶ ይወደናል” ያሉት ደግሞ ታዋቂው ጳጳስ ዴዝሞን ቱቱ ናቸው፡፡ ከነገ በስቲያ ሰኞ ጆሃንስበርግ ውስጥ በሚገኘውና 90 ሺህ ሰው በሚይዘው ኤፍ ኤን ቢ ስቴዲየም በሚከናወን ብሃራዊ የሃዘን ስነስርዓት በድምቀት የሚዘከሩት ማንዴላ አስከሬን፣ ለሶስት ቀናት ያህል በመዲናዋ ፕሪቶሪያ በህዝብ ሲታይ ይቆያል፡፡ በመጪው ሳምንት መጨረሻም በብሄራዊ ክብር ታጅቦ በምስራቃዊ ኬፕታውን አቅራቢያ በምትገኘው የዕድገት መንደራቸው ኮኑ ወደሚማስለት መቃብር ይሸኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ የተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል፡፡

በኢትዮጵያ የብሪጅስቶን ጎማ ብቸኛ አስመጪና አከፋፋይ ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር በ15 ሚሊዮን ብር ወጪ በአዲስ አበባ ቃሊቲ መናኸሪያ አካባቢ ያስገነባው ‘ብሪጅስቶን ትራክ ታየር ሴንተር’ (BTTC) የተሰኘ አዲስ የጎማ ጥገና ማዕከል ትናንት ተመርቆ ተከፈተ፡፡ ላለፉት አስራ ሶስት አመታት ጥራታቸውን የጠበቁ የብሪጅስቶን ጎማዎችን በማስመጣት የሚታወቀው ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር፤ በአገሪቱ የትራንስፖርት ዘርፍ ውስጥ የራሱን ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንዳለ ይታወቃል፡፡ አገራት በሚጠቀሙበት ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ ዘርፈ ብዙ የተሽከርካሪ ጎማ ጥገናና ተያያዥ አገልግሎት ለመስጠት በማሰብ ማዕከሉን እንደገነባ የብሪጅስቶን ኢትዮጵያ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ሁሴን አህመድ በምረቃ ሥነሥርዓቱ ላይ ተናግረዋል፡፡

ደንበኞች የተለያዩ አገልግሎቶችን በምቹ ሁኔታ በሚያገኙበት መልኩ በ6 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የተገነባውና በዘመናዊ ቁሳቁስ የተደራጀው ማዕከሉ፣ ከፍተኛ የጥራት ደረጃ ያላቸውን የጎማ ምርቶች ከማቅረቡ በተጨማሪ፣ የካበተ ልምድ ባላቸው ባለሙያዎች አማካይነት ሰባት አይነት የተለያዩ የተሽከርካሪ ጎማ ጥገናና ተያያዥ አገልግሎቶችን እንደሚሰጥም ገልጸዋል፡፡ ማዕከሉ ከዚህ በተጨማሪም፤ ከጎማ አጠቃቀም፣ ከአጠቃላይ የተሽከርካሪዎች ደህንነት አጠባበቅና ጥገና ጋር በተያያዘ ለአሽከርካሪዎችና ባለሃብቶች የተሟላ መረጃና ሙያዊ ምክር ይሰጥበታል ተብሏል። ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ በጥናት ላይ ተመስርቶ ባቋቋመው በዚህ ማዕከል ሊሰጣቸው ያቀዳቸው በቴክኖሎጂ የታገዙና የተሻሻሉ አገልግሎቶች፣ የተሽከርካሪዎችንና የጎማዎችን ዕድሜ ከማራዘም ባለፈ ለአዳዲስ ጎማዎች ግዢ፣ ለጥገናና ለእድሳት የሚወጣውን ወጪ በመቀነስ ረገድም የጎላ ሚና እንደሚጫወት በማዕከሉ ምረቃ ላይ ተነግሯል።

ከካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የኩባንያው ዋና ስራ አስኪያጅ ከአቶ ሰኢድ አል አሙዲ ጋር በመሆን ማዕከሉን መርቀው የከፈቱት የዕለቱ የክብር እንግዳና የብሪጅስቶን ኩባንያ የአፍሪካና የመካከለኛው ምስራቅ ፕሬዚዳንት ሚስተር ሳኩማ በበኩላቸው፤ የማዕከሉ መገንባት ለተሽከርካሪዎች ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ተናግረዋል፡፡ ኩባንያው ለወደፊትም ከካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ ጋር ያለውን የስራ ግንኙነት በማጠናከር፣ የተሻሻሉ አሰራሮችንና ጥራታቸውን የጠበቁ የጎማ ምርቶችን ለደንበኞች ማቅረቡን እንደሚቀጥልበትም ሚስተር ሳኩማ ገልጸዋል፡፡ ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ፣ ከብሪጅስቶን ጎማ አስመጪነት በተጨማሪ በቡና ኤክስፖርት፣ በሲኖትራክ ተሽከርካሪዎች አስመጪነትና በሳኡዲ ኤርላይንስ ብቸኛ ወኪልነት ሰፋፊ የንግድና ኢንቨስትመንት ስራዎችን በማከናወን ላይ የሚገኝ ድርጅት ነው፡፡

Saturday, 30 November 2013 11:18

መነሻ ስዕል

አያልቅም ይህ ጉዞ…
ማስመሰል - መተርጐም
በቀለም መዋኘት
ከብርሃን መጋጨት
ለማወቅ ለመፍጠር ባዶ ቦታ መግባት፡፡
መፈለግ… መፈለግ
አዲስ ነገር መፍጠር
ከማይታየው ጋር ሄዶ መነጋገር፡፡
ህይወትን መጠየቅ
ሃሳብን መጠየቅ
መሄድ መሄድ መሄድ…
ከጨረቃ በላይ
ከኮኮቦች በላይ
ከሰማዩ በላይ፡፡
መጓዝ ወደ ሌላ - ባዶ ቦታ መግባት፡፡
በሃሳብ መደበቅ
መፈለግ ማስገኘት፡፡
አያልቅም ይህ ጉዞ…

ከከተማዋ ነዋሪ ውስጥ ከአንድ ሚሊየን በላይ የሚሆነው ሜዳ ላይ ይፀዳዳል

ለ62 ዓመታት አዲስ አበባን ኖረውባታል፡፡ ከልጅነት እስከ ዕውቀት የሚያውቋት ይህቺው ከተማ በዘመን ብዛት እየዘመነች፣ እያደገችና እየተሻሻለች መሆኗን ባይክዱም በንጽህናዋ ረገድ ዕለት ተዕለት ቁልቁል መሄዷ ሁሌም ያስገርማቸዋል፡፡ በተለይ በተለይ ልጅነታቸውን ያሳለፉበትንና ወጣትነታቸውን ያጣጣሙበትን የከተማዋን እምብርት ፒያሣን ፈጽመው አይዘነጉትም፡፡
በዘመናቸው አራዳ እየተባሉ ይጠሩ የነበሩት እኒህ አካባቢዎች፣ እንደሣቸው ባሉ ዘመነኞች እጅግ ይዘወተሩ ነበር፡፡ አካባቢዎቹ የመጠጥ እና የጭፈራ ቤቶች የሚበዙባቸው ሥፍራዎች ቢሆኑም ሁልጊዜም ንፁህና ለአይን ማራኪ እንደነበሩ ያስታውሳሉ፡፡ “አራዳው ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ዙሪያ የነበሩ የመናፈሻ ሥፍራዎች የስንቶቻችን መቀጣጠሪያና የእርቅ ሽምግልና መፈፀሚያ ቦታ ነበር መሰለሽ፤ ያኔ እንዲህ እንደዛሬው ቅጥ አንባሩ የጠፋበት ዘመን አልነበረም፡፡ ያኔ እንዲህ እንደአሁኑ በቤተክርስቲያን ደጃፍ እንደልብ መፀዳዳት ፈጽሞ የማይታሰብ ነገር ነበር፡፡ በየጥጋጥጉና በየሜዳው የሚፀዳዱ ሰዎችን ይዘው የሚያስቀጡ ደመወዝተኛ የሚባሉ ሰዎች ነበሩ፡፡ ግን ህብረተሰቡም እራሱ ፈሪሃ እግዚአሃብሔር ያደረበት፣ ሜዳ ላይ መፀዳዳት የሚያሳፍረውና እርስበርሱ የሚከባበር ስለነበር ከተማዋ እንዲህ እንደዛሬው የህዝብ መፀዳጃ ቤት አትመስልም፡፡ አሁን አሁንማ አፍንጫው ሥር ሲፀዳዳ እፍረት የማይሰማውን የከተማ ነዋሪ ማዘጋጃ ቤቱ የሚያበረታታውና አይዞህ የሚለው ይመስላል። ማዘጋጃ ቤቱ እንኳንስ የከተማዋን ጽዳትና ውበት ሊጠብቅና ሊቆጣጠር ቀርቶ የራሱን ደጃፍ ከህዝብ መፀዳጃ ቦታነት ሊከለክልና ሊያስጥል አልቻለም። አላሙዲን የልጆቻችን ኳስ መጫወቻ የነበረውን ሰፊ ሜዳ ወስደው ሲያጥሩ እንዴት ያለ ሆቴልና መዝናኛ ቦታ ሠርተው አካባቢውን ሊያሣምሩልን ነው፡፡ ተመስገን አይናችን ጥሩ ነገር ሊያይ ነው ብለን ተደስተን ነበር፡፡ ምን ዋጋ አለው፡፡ ይኸው ሃያ ዓመት ሙሉ በአጥር ተከልሎ የመፀዳጃና የመዳሪያ ቦታ ሆኗል፡፡ እኔ የሚገርመኝ ማዘጋጃ ቤቱ እዚሁ ዓይኑ ሥር ያለውን የሠገራ ክምር ማጽዳት አቅቶት፣ የከተማ ጽዳት፣ የአካባቢ ጽዳት እያለ መለፍለፉ ነው፡፡ ለነገሩ የሰው አይን ላይ ያለች ጉድፍ እንደሚታይሽ በራስሽ ፊት ላይ ያለው ትልቅ ግንድ መች ይታይሻል።”
 ገዳም ሰፈር ተወልደው ላደጉትና የከተማዋ ጽዳት በእጅጉ ለሚያሳስባቸው አቶ አሰፋ ታዬ፤ የከተማዋ አስተዳደር የከተማዋን ንጽህናና ጽዳት በመጠበቁ ረገድ ምን እየሠራ እንደሆኑ ፈጽሞ አይገባቸውም። በከተማዋ ዋና ዋና ጐዳናዎች ላይ ተከምረው ሃላፊ አግዳሚውን የሚያሰቅቁ የቆሻሻ ክምሮች ማንን እየጠበቁ እንደሆነም ግራ ይገባቸዋል። “የድሮዎቹ ደመወዝተኞች የአካባቢውን ንጽህና ለመጠበቅና ህብረተሰቡ በተገቢው ቦታ መፀዳዳት እንዳለበት በማስተማሩ ረገድ ሰፊ ሥራን ይሰሩ ነበር። የዛሬዎቹ ደንብ አስከባሪዎች ግን ከሱቅ በደረቴዎች ጋር ሌባና ፖሊስ ሲጫወቱ ነው የሚውሉት፡፡ ‘መሽናት ክልክል ነው’ ብሎ በመፃፍና በመለጠፍ ብቻ ምንም ለውጥ ማምጣት አይቻልም። የግንዛቤ ለውጥ ለማምጣት መስራት አለበት፡፡ እንደውም እኮ ሰው የሚፀዳዳው “መሽናት ክልክል ነው” የሚሉ ጽሑፎች በተለጠፋባቸው ቦታዎች ላይ ነው፡፡
እናም ባለስልጣናቱ በዚህ ጉዳይ ላይ ቢያስቡበት ጥሩ ነው፡፡ ፎቅና መንገድ መሥራት ብቻ አንድን ከተማ ሊያሣድጋት አይችልም፡፡ ንጽህናዋም ወሳኝ ነው፡፡ የከተማዋ አስተዳደር በዚህ ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥቶ ካልሰራ በስተቀር አሁን እንዲህ ከፍተኛ ወጪ እየወጣበት የሚሰራውና ብዙ የተባለለት አዲሱ የባቡር ሐዲድ መፀዳጃ ላለመሆኑ ማረጋገጫ የለንም፡፡” የአቶ አሰፋን ትዝብትና ሥጋት የሚጋሩ የከተማዋ ነዋሪዎች ቁጥር በርከት ያለ ነው፡፡ ከተማዋ ያለ ፕላን የተሰሩ መንገዶችና ቤቶች የሚበዙባት፣ የፍሳሽ ማስወገጃዎች በአግባቡ ያልተሰራባትና አሮጌ መንደሮች የተበራከቱባት እንደመሆኗ በቂ የመፀዳጃ ቤቶች የሏትም፡፡ አብዛኛው የከተማዋ ነዋሪ የሚፀዳዳው በየመንገዱና በየጥጋጥጉ ላይ ነው፡፡
የህብረቱ መቀመጫ፣ የአፍሪካ መዲና፣ የታላላቅ አለምአቀፋዊ ድርጅቶችና ሆቴሎች መናኸሪያ እየተባለች የምትሞካሻው ከተማችን አዲስ አበባ፤ እጅግ ደካማ የንጽህና አጠባበቅ እንዳላትና በሚሊዮን የሚቆጠረው ነዋሪ ህዝቧ ዛሬም በሜዳ ላይ እንደሚፀዳዳ አንድ መረጃ ይፋ አድርጓል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ይፋ ያደረገው ይኸው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በከተማዋ ከሶስት ሚሊዮን በላይ ህዝብ የሚኖር ሲሆን ከዚህ ቁጥር ውስጥ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ወይንም 25 ከመቶ የሚበልጠው የከተማዋ ነዋሪ የመፀዳጃ ቤት የለውም፡፡ ይኸው መፀዳጃ ቤት አልባ የከተማዋ ነዋሪ በየመንገዱ ላይ እና በየቤቶቹ ጥጋጥግ ይፀዳዳል፡፡
የመኖሪያ ቤቶች ተጠጋግተው በተሰሩባቸውና እጅግ በርካታ ህዝብ በሚኖርባቸው አካባቢዎች፣ ነዋሪዎቹ በአብዛኛው የመፀዳጃ ቤት አገልግሎት ለማግኘት አለመቻላቸውን መረጃው አመልክቶ ሜዳ ላይ የመፀዳዳት ሂደቱም በእነዚህ አካባቢዎች ላይ ጐልቶ እንደሚታይ ጠቁሟል፡፡
ይህንን ችግር ለማስወገድ ህብረተሰቡ ከመንግስት ጋር መተባበርና በሜዳ ላይ መፀዳዳት እጅግ አሣፋሪ ተግባር እንደሆነ ተገንዝቦ፣ ከድርጊቱ መቆጠብ ይገባዋል ሲልም መረጃው አመላክቷል። ለነዋሪው ህብረተሰብ በቂ የመፀዳጃ ቤት ሊገነባ እንደሚገባም አስገንዝቧል፡፡
ሰሞኑን በ(Wash Ethiopia movement) አስተባባሪነት በአዳማ ከተማ ውስጥ በተከበረው አምስተኛው አገር አቀፍ የሃይጂንና የአካባቢ ጤና አጠባበቅ ፌስቲቫልና አለም አቀፍ የመፀዳጃ ቤት ቀን በዓል ላይ እንደተገለፀው፤ በአገሪቱ ከ60-80 በመቶ የሚሆነው የጤና ችግር ተላላፊ ሲሆን ከዚህ ውስጥ ደግሞ 75 በመቶ የሚሆነው በንፁህ የመጠጥ ውሃ እጥረትና በአካባቢ ንፅህና ጉድለት ሣቢያ የሚከሰት ነው፡፡ በአገራችን የህፃናት ገዳይ በሽታዎች ከሆኑ የጤና ችግሮች መካከል ግንባር ቀደም የሆነው የተቅማጥ በሽታም ከንፅህና ጉድለት ጋር ተያይዞ የሚከሰት እንደሆነ ተጠቁሞ፤ በአፍሪካ ከንፁህ መጠጥ ውሃ እጥረትና ከግልና ከአካባቢ ንፅህና ችግር ጋር በተያያዙ የጤና ችግሮች በየሰዓቱ 115 ሰዎች እንደሚሞቱ በዚሁ ፌስቲቫል ላይ ተገልጿል፡፡
የአገሪቱ ርዕሰ መዲና የሆነችው አዲስ አበባ፤ በዚህ መልኩ ሜዳ ላይ የሚፀዳዳ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ህዝብ እንዳለባት ስሰማ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል ውስጥ የምትገኘው የዶርዜ ሃይዞና የሸበዲኖ ወረዳ ነዋሪዎች ይህንን ሲሰሙ ምን እንደሚሉ ማሰቡ አቃተኝ፡፡ በእነዚህ ወረዳዎች እጅግ አሣፋሪው ተግባር ሜዳ ላይ መፀዳዳት ነው፡፡ እነዚህ ቦታዎች “ሜዳ ላይ ከመፀዳዳት የነፃ” (Open deification Free) ተብለው በተለያዩ መንግስታዊና መንግስታዊ ባልሆኑ ተቋማት ሽልማት ተሰጥቷቸዋል፡፡ የአካባቢው ነዋሪዎች ሜዳ ላይ መፀዳዳት እጅግ አሣፋሪ ተግባር መሆኑን ያምናሉ፡፡ ይህንን አሣፋሪ ተግባር ላለመፈፀም በእጅጉ ይጠናቀቃሉ፡፡ ይህንን እምነታቸውን ጥሶ መንገድ ላይ የሚፀዳዳ ሲያዩ በዝምታ አያልፉትም፡፡ ነዋሪዎቹ እንዲህ አይነት “አደጋ” በአካባቢያቸው ሲፈፀም የሚጠራሩበት የራሣቸው የሆነ የኮድ መጠራሪያ ድምፅ አላቸው። ይህንን ጥሪ የሰማ የአካባቢው ነዋሪ ሁሉ ጥሪው ወደተደረገበት ቦታ በፍጥነት ይሄዳል፡፡ ሰውየው (ሴትየዋ) መፀዳዳታቸውን እስኪጨርሱ ድረስ ይጠብቁና ሠገራውን በፕላስቲክ ከረጢት ውስጥ እንዲከት ያስገድዱታል፡፡ በሠገራው ላይ የሰውየው ሙሉ ስም ይፃፍበትና በዋናው መንገድ ላይ ይንጠለጠላል፡፡ “የእከሌ ሰገራ ነው” የሚለውን ፅሁፍ የሚያነበው የአካባቢው ነዋሪ ህዝብ ለሰውየው የሚሰጠው ግምት እጅግ ያነሰና የወረደ ይሆናል፡፡ ይህም ድርጊቱን በፈፀመው ሰው ሞራልና ስብህዕና ላይ ከፍተኛ ውድቀትና በአካባቢው ነዋሪዎች ዘንድም መገለልን ያስከትልበታል፡፡ ማንም ሰው ይህ እንዳይደርስበት  ሜዳ ላይ ከመፀዳዳት ይቆጠባል፡፡ አዲስ አበቤዎች ከዚህ ምን ይማሩ ይሆን?  

በመካከለኛው ምስራቅ በፐርሺያን ገልፍ ሰሜን ምእራብ ጫፍ የምትገኝ በረሀማ ነገርግን ስትራቴጂካዊ እና በነዳጅ ሀብት የበለፀገች አገር ናት። ለዜጎቿም ሆነ ለሌሎች አገሮች ዜጎች በነፃ ህክምና ትሰጣለች፡፡ የአገሪቱ ዜጎች ከመንግስታቸው ሌሎች የተለያዩ ጥቅማጥቅሞችን ያገኛሉ፡፡ የኩዌት ዲናር አቅም ካላቸው ገንዘቦች በቀዳሚነት የሚመደብ ሲሆን አንዱ ዲናር ሶስት ብር ከሀምሳ የአሜሪካን ዶላር ይመነዘራል፡፡ ኩዌት በህገመንግስታዊ የንጉስ ስርአት የምትመራ አገር ናት፡፡
ባለፈው ሳምንት ባዘጋጀችው ሶስተኛው የአፍሪካ አረብ ጉባኤ 34 የአገር መሪዎችን፤ 7 ምክትል ፕሬዚደንቶች፣ 71 አገሮች እና ድርጅቶች ተሳትፈዋል። የጉባኤው ዋና አጀንዳ በአፍሪካ እና በአረብ መካካል ያለውን ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት ማጠናከር ነበር። ጉባኤውን በንግግር የከፈቱት የኩዌት አሚር ሼክ ሰባህ አሀመድ አል ሰባህ የሁለቱ አካባቢ ህዝቦች ቆየት ያለ ታሪካዊ እና ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት እንዳላቸው በመግለፅ በዝቅተኛ የወለድ መጠን የሚከፈል  በአፍሪካ አህጉር ለተለያዩ ኢንቨስትመንት የሚውል አንድ ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር በቀጣዩ አምስት አመት እንደሚሰጥና ለተለያዩ የምርምር ስራዎች የሚውል  አንድ ሚሊዮን ዶላር ከኩዌት ለአፍሪካ እንደሚለግስ ቃል ገብተዋል፡፡ በሁለቱም አካባቢ ህዝቦች የምግብ ዋስትና  እና የፀጥታ እና የደህንነት ጉዳዮች  ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫዎች  ሊሆነ እንደሚገባ በአፅንኦት የተናገሩት አሚሩ፣ ነገር ግን አንዱ ወገን እርዳታ እየሰጠ ሌላው ወገን ምንም አስተዋፅኦ የማያደርግበት አካሄድ መስተካከል እንዳለበት በንግግራቸው አስምረውበታል፡፡ የጉባኤው ትኩረት ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ቢሆንም አሚሩ የሶሪያን ጉዳይ በተመለከተ የመንግስታቱ ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ሀላፊነቱን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበው እስራኤል የምትወስዳቸው እርምጃዎች እንደሚያሳስቧቸው ተናግረዋል፡፡
ሁለተኛው አፍሮ አረብ ጉባኤ በሊቢያዋ ስርት ከሶስት አመት በፊት ሲካሄድ ከ2001 እስከ 2016 ይተገበራሉ የተባሉ የተለያዩ ፕሮጀክቶች ተቀርፀው የነበረ ቢሆንም ቱኒዚያን፣ ሊቢያን፣ ግብፅን እና የመንን ያናወጠው ህዝባዊ አመፅ እና የመሪዎች ከስልጣን መውረድ  እንዲሁም እስከ አሁን የቀጠለው የሶሪያ ቀውስ ፕሮጀክቶቹ ብዙም እንዳይራመዱ ቀስፈው የያዙ ምክንያች ናቸው፡፡
ጉባኤውን በሊቀመንበርነት የመሩት የኢትዮጲያ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ለቀመንበር አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ በበኩላቸው፣ የስደተሦች ጉዳይ የጉባኤው አጀንዳ መሆኑ ተገቢ እና ወቅታዊ እንደሆነ በመግለፅ ጉዳዩ አሳሳቢ በመሆኑ ሁሉን አቀፍ እና ዘላቂ  መፍትሄ መፍትሄ እንደሚያስፈልገው አስቀምጠዋል፡፡ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ካለ ችግሩን መፍታት ይቻላል ያሉት አቶ ሀይለማርያም ጉዳዩ እንደ ከዚህ ቀደም ዝም ብሎ የሚታይ አይደለም ብለዋል፡፡ የጉባኤውን ዋና አጀንዳ አስመልክቶም በአረብ በኩል ያለው አቅም እና በአፍሪካ በኩል ያሉ የተለያዩ  እምቅ ሀብቶች ሁለቱን አካባቢዎች እንደሚያስተሳስሯቸው ተናግረዋል። ከመሪዎቹ ስብሰባ ቀደም ብሎ በተካሄደው የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሮች ስብሰባ ላይ የስደተኞችን በሚመለከት ይቋቋማል የተባለው የአፍሮ አረብ የተቀናጀ ኮሚቴ ጥሩ ውጤት ያመጣል በለው እንደሚጠብቁ ተናግረዋል፡፡
ከጉባኤው ጎን ለጎንም ከሰላሳ በላይ ውይይቶች የተካሄዱ ሲሆን ከግጭቶች እና ከኢንቨስትመንት ጋር የተያያዙ አጀንዳዎች አብላጫውን ቁጥር ይይዛሉ።  የኢትዮጲያ እና የግብፅ መሪዎች መሀመድ ሙርሲ ከስልጣን ከተወገዱ በኋላ ለመጀመሪያ ግዜ ተገናኝተው  ኢትዮጲያ  እየገነባች ስላለው የታላቁ የህዳሴ ግድብ ተወያይተዋል፡፡ የግድቡን ግንባታ አስመልክቶ በግብፅ በኩል የቀረበው ግንባታው ላይ የመሳተፍ ጥያቄ በኢትዮጲያ በኩል ተቀባይነት ያላገኘ ሲሆን ግድቡን አስመልክቶ በያዝነው ወር ግብፅ፣ ኢትዮጵያ እና ሱዳን ካርቱም ላይ ተገናኝተው ውይይት ያደረጉ ሲሆን ቀጣዩ ስብሰባም  በታህሳስ ወር ካርቱም ይደረጋል፡፡
ጉባኤው ባወጣው የአቋም መግለጫ በአፍሪካ እና በአረብ አገሮች መንግስታት እና ህዝቦች መሀል የቀረበ ትስስር መፍጠር፣ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶችን ማጠናከር፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን እና የአረ ሊግ የአፍሮ አረብ የድርጊት መርሀ ግብሮች እና ፕሮጀክቶች ተግባራዊ እንዲሆኑ የሚያግዝ ግብረ ሀይል እንዲያቋቁሙ፣ የአፍሪካ እና የአረብ አገሮ የገንዘብ ተቋሞች የግሉን ዘርፍ እና  የሲቪል ማህበራትን በማጠናከር የሁለቱን አካባቢዎች የንግድ ትስስር እንዲያፋጥኑ ማስቻል፣ የአፍሪካ እና የአረብ የንግድ ምክር ቤቶች እና የኢንዱስትሪው ዘርፍ እነዲሁም ሌሎች የግል ተቋሞች ተከታታይ የሆነ የምክክር መድረኮችን በመፍጠር የሁለቱን አካባቢዎች ትስስር ለማፋጠን እገዘ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡
በሁለቱም አካባቢዎች ያሉ መንግስታት፣ የግሉ ዘርፍ እና የሲቪል ማህበራት የግብርናውን ዘርፍ እንዲያሳድጉ ማበረታታት፣ የገጠርልማት፣ የግብርና እና የምግብ ዋስትና ላይ የሚሰሩ ስራዎችን አጠናክሮ መቀጠል፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን እና የአረብ ሊግ ይህ የአቋም መግለጫውም ሆነ የአፍሮ አረብ የአጋርነት ስትራቴጂ ተግባራዊ እንዲሆኑ በገንዘብም ሆነ በቴክኒክ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል። ፍልሰትን በተመለከተም የተቋቋመው የአፍሮ አረብ የቴክኒክ እና የቅንጅት ኮሚቴንም ሆነ ከጉዳዩ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን ስትራቴጂዎች ሁለቱ አካባቢዎች በቅንጅት እንዲሰሩ፣ ለፈለሱ ሰዎች የደህንነትና ማህበራዊ ጥበቃ ማድረግ፣ ስደተኞችን፣ ተፈናቃዮቸችን  እንዲሁም የፈለሱ ሰዎችን ለሚቀበሉ አገሮች በተለይም ለቡርኪናፋሶ እና የመን እገዛ ማድረግ እንደሚገባና ህገወጥ ፈላሾችን ለመለየት የአፍሮ አረብ የመረጃ ልውውጥ ማእከል እንዲቋቋም ስምምነት ላይ መደረሱን መግለጫው ያሳያል፡፡
የባህር ላይ ውንብድና እና የካሳ ጥያቄ፣ ህገወጥ የሰዎች ዝውውር፣ የአደንዛዝ እፅ ዝውውር  እና የህገወጥ የመሳሪያ ዝውውር ላይ በጋራ ለመሥራትም ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
አንድ የኩዌት ከፍተኛ ባለስልጣን የፍልሰት ጉዳይ አሳሳቢ ችግር ነው ያሉ ሲሆን በጉባኤው ላይ ያነጋገርኳቸው ተንታኝም፣ የፍልሰት ጉዳይ ትኩረት ተሰጥቶት ካልተሰራበት እና መፍትሄ ካልተሰጠው የአፍሪካን እና የአረቡን አለም ግንኙነት እስከማቋረጥ ሊደርስ እንደሚችል አስቀምጠዋል፡፡ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በአሁኑ ወቅት ከአምስትመቶ ሺህ በላይ አፍሪካውያን ወደ አረብ አገሮች ፈልሰዋል።
ሁለቱ አካባቢዎች በፀጥታ እና አሸባሪነትን በጋራ ለመከላከል ለዚህመም መረጃ ለመለዋወጥ  የተስማሙ ሲሆን በሁለቱ አካባቢዎች ለሚገኙ ግጭቶች እና አለመረጋጋቶች ለዜጎች አመቺ ሁኔታን በሚፈጥሩና ለደህንነታቸው ትኩረት በሰጠ መልኩ እልባት እንዲያገኝ መግባባት ላይ ተደርሷል፡፡  
የኩዌቱ አሚር ሼክ ሰባህ በጉባኤው መዝጊያ ላይ ባደረጉት ንግግር ከፊታችን ረጅም እና አስቸጋሪ መንገድ ይጠብቀናል፡፡ ለዚህ ደግሞ ዋናው ምክንያት በሁለቱም አካባቢዎች ያለው ያለመረጋጋት ነው። ስለዚህ ያቀድናቸውን ለማሳካት ብዙ ጥረት ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡
በአፍሪካ ርካሽ የሰው ጉልበት፣ ለእርሻ የሚውል ሰፊ የሚታረስ መሬት፣ አፋጣኝ የመሰረተ ልማት ፍላጎት  ይገኛል፡፡ ይህን እድል ሁለቱም አካባቢዎች ሚዛኑን በጠበቀ የዜጎቻቸውን ፍላጎት በተከተለ መንገድ እንዴት ሊወጡት ይችላሉ የሚለው ጥያቄ ምላሽ ለግንኙነቱ ምላሽ ይሰጣል ያሉት የጉባኤው ተሳታፊ፣ በተለይ በአፍሪካ በኩል ጥንቃቄ የተሞላበት እርምጃ ግድ ይላል ይላሉ፡፡
ቀጣዩ የአፍሮ አረብ ጉባኤ በአፍሪካ እንዲዘጋጅ የተወሰነ ሲሆን ሰባተኛውን የአፍሮ አረብ ንግድ ትርኢትም  ሞሮኮ በቀጣዩ አመት እንድታስተናግድ ተወስኗል፡፡

(የአዲስ አበባ 22ተኛ ከንቲባ)

መጋቢት በቀድሞው ሐረርጌ ክፍለ ሀገር ኤጀርሳ ጐሮ በተባለ ገጠራማ መንደር ነው የተወለዱት - በ1928 ዓ.ም፡፡

አባታቸው በአርበኝነት ከሞቱ በኋላ፣ መንግሥት የባለውለታ ልጆችን ሰብስቦ ሲያስተምር፣ ሐረር ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ

ትምህርት ቤት ገብተው የመማር ዕድል አገኙ፡፡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ሲያጠናቅቁ፤ በ1945 ዓ.ም ተግባረ ዕድ

ኮሌጅ ገቡ፡፡ ሕንፃ ኮሌጅ ሲከፈት ከመጀመሪያዎቹ ተማሪዎች አንዱ ሆነው ለአራት ዓመት የሚሰጠውን ትምህርት

የተከታተሉ ሲሆን ለተጨማሪ ትምህርትም ወደ ዩጐዝላቪያ ሄደዋል፡፡ ከትምህርት በኋላ በበርካታ መንግሥታዊ መሥሪያ

ቤቶች አገልግለዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ 22ተኛ ከንቲባ ሆነውም ሠርተዋል፡፡ “የፖለቲካ ፍላጐት የለኝም፤ ኖሮኝም

አያውቅም” የሚሉት ኢንጂነር ዘውዴ ተክሉ፤ አሁን የአዲስ አበባ ከተማ የነዋሪዎች ፎረም ሰብሳቢ በመሆን ማህበራዊ

ተሳትፎ እያደረጉ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ጋዜጠኛ ብርሃኑ ሰሙ ስላሳለፉት ህይወትና የሥራ ዘመን አነጋግሯቸዋል፡፡


ዩጐዝላቪያ የሄዱበትን የትምህርት ዕድል እንዴት አገኙ?
የሕንፃ ኮሌጅ ትምህርታችንን ስናጠናቅቅ የማዕረግ ሁለተኛ ተሸላሚ ነበርኩ፡፡ ለምረቃ እየተዘጋጀን እያለ የትምህርት ቤቱ

አስተዳዳሪ፤ “የውጭ አገር ትምህርት ዕድል መጥቷል፤ መሄድ ትፈልጋለህ ወይ?” ሲሉኝ ተስማማሁ፡፡ ከእኛ ኮሌጅ

ሁለት፤ ከሌሎች ቦታ የተመረጡ አራት ልጆች ተጨምረው ወደ ዩጐዝላቪያ ሄድን፡፡ በወቅቱ ዩጐዝላቪያ የኢትዮጵያ

ትልቋ ወዳጅ አገር ነበረች፡፡ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ቲቶም ብዙ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ይመጡ ነበር፡፡
በሕንፃ ኮሌጅ የተማርኩት ቢዩልዲንግ ቴክኖሎጂ ቢሆንም ተጨማሪ ትምህርትም ይሰጠን ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ታሪክ፣

ፖለቲካ ሳይንስና የኦርቶዶክስ ሃይማኖትን ተምረናል፡፡ በአገራችን ያለውን የሕንፃ አሰራር ጥበብን ለማየት የተለያዩ

አካባቢዎች እየሄድን እንጐብኝ ነበር፡፡ ጅማ፣ ሐረር፣ ጎንደር፣ ትግራይና ኤርትራ ወደመሳሰሉት ቦታዎች ሄደናል፡፡ እኔ

ለኪነ ህንፃ (አርክቴክቸር) ትምህርት ልዩ ፍላጎት ስለነበረኝ፣ ዩጐዝላቪያ ስሄድ አርክቴትር ፋኩልቲ ነው የገባሁት።

የትምህርት ጊዜ ለእረፍት ሲዘጋ የተለየዩ አገራትን እየዞርኩ እጎበኝ ነበር፡፡ ጀርመንን፣ ኦስትሪያን፣ ቡልጋሪያን፣ ሀንጋሪን

በዚያ አጋጣሚ ነበር ያየኋቸው። በ1961 ዓ.ም ትምህርቴን አጠናቅቄ መጣሁ፡፡
የት የት ሰርተዋል?
ከውጭ እንደመጣሁ ሥራ የጀመርኩት ሥራና ውሃ ሚኒስቴር በሚባል መሥርያ ቤት ነው - በሙያዩ ተመድቤ ምክትል

ዋና አርክቴክት ሆንኩ፡፡ በ1965 ዓ.ም ወደ አስመራ ተቀይሬ ሄድኩ፡፡ አብዮቱ የፈነዳው እዚያ እያለሁ ነበር፡፡ ከአብዮቱ

በኋላ ወደ አዲስ አበባ ተመልሼ ቀድሞ በነበረኝ ኃላፊነት ተመድቤ መሥራት ቀጠልኩ፡፡ ከዚያ በኋላ በተለያዩ መሥሪያ

ቤቶች እየተመደብኩ ሠርቻለሁ፡፡ የዚያ ዘመን አንዱ ችግር ሙያህም ባይሆን “ተመድበሀል። ገብተህ ሥራ፡፡ ሁላችንም

ተመድበን እየሰራን ነው ያለነው” ይባል ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት በሙያዬ ብቻ ሳይሆን እየተመደብኩም በተለያዩ ቦታዎች

ሠርቻለሁ፡፡ በብሔራዊ ሀብት ልማት ሚኒስቴር በመምሪያ ኃላፊነት፤ በከተማ መሬት አስተዳደር በሥራ አስኪያጅነት፤

በኪራይ ቤቶች አስተዳደር ተጠባባቂ ሥራ አስኪያጅነት፤ በከተማ ፕላን በዋና ኃላፊነት፤ በምርት ዘመቻና ማዕከላዊ

ፕላን በቡድን መሪነት … በተለያዩ ቦታዎችና ኃላፊነቶች ሠርቻለሁ።
በከንቲባነት ሊመረጡ የቻሉት እንዴት ነበር?
ለከተማ ፕላንና አስተዳደር ጥናት ተሰርቶ አዋጅ እንዲወጣ ሲታሰብ የቴክኒክ ሪፖርቱን ያቀረብኩት እኔ ነበርኩ፡፡

ከተሞች እንዴት እንደሚለሙና እንደሚደራጁ ነበር ያጠናነው፡፡ በዚያ አጋጣሚ ለከንቲባነት እንድወዳደር መታሰቡን

ሰምቻለሁ፡፡ የከተማ አስተዳደር ምርጫ ሲደረግ ግባና ተወዳደር ተባልኩ፡፡ በሙያዬ ብሰራ ይሻለኛል ብዬ ተቃውሜ

የነበረ ቢሆንም “ያው ነው፤ ምርጫውን አሸንፈህ የምትገባ ከሆነ እዚያም የምትሰራው ተመሳሳይ ነው” ተባልኩ፡፡
የምርጫው ሂደት ምን ይመስል ነበር?
አዲስ አበባ ከጃንሆይ ጊዜ ጀምሮ በቻርተር ነው የምትተዳደረው፡፡ በዘመኑ የምርጫ ውድድሩ የሚጀምረው ከቀበሌ

ነው፡፡ ያንን ያሸነፉ በከፍተኛ ደረጃ ይወዳደራሉ፡፡ ከከፍተኞቹ ቀጥሎ ዞን ቢኖርም ዞኖቹ ምርጫውን የማስተባባር ሥራ

ነበር የሚሰሩት። በዚህ መልኩ ተወዳድሬ ነው ከንቲባ ለመሆን የቻልኩት፡፡  
የአዲስ አበባ ስንተኛው ከንቲባ ነዎት?
22ተኛው ነኝ፡፡ በዚህ ኃላፊነት ከ1973 እስከ 1981 ዓ.ም ድረስ ነው የሠራሁት፡፡ ሥራ ስንጀምር ቀደም ብሎ ታቅዶ፤

ጠረጴዛ ላይ ካገኘነው ሥራ አንዱ የሌኒን ሐውልት ግንባታን የሚመለከት ነበር፡፡ እቅዱ ሞዴል የተሰራለትና ብዙ ደረጃ

የተጓዘ ነበር፡፡ ሞዴሉ ሁለት ሐውልቶችን ይዟል፡፡ አንዱ የሌኒን ሐውልት ሲሆን ሁለተኛው 30 ሜትር ርዝመት

የሚኖረውና ከሌኒን ሐውልት በስተጀርባ የሚቆም የአክሱም ሐውልት አምሳያ እንደሚኖር ያሳያል፡፡ ለዚህ ሥራ ደግሞ

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሲመሠረት 30 የተለያዩ አገራት መሪዎች የተከሏቸው ባህር ዛፎች ሙሉ ለሙሉ ይመነጠራሉ

ይላል፡፡ በሐውልቶቹ ዙሪያ ፏፏቴ እንደሚኖርም ተመልክቷል፡፡
እኛ ሥራ ስንጀምር በእቅዱና በሞዴሉ ዙሪያ አስተያየችሁን አቅርቡ ተባልን፡፡ የአክሱም ሐውልት የአርክቴክት ሚስጢሩ

ያልታወቀ፤ የኢትዮጵያና የዓለምም ትልቅ ቅርስ ነው፡፡ ሌኒን የወዛደር መሪ ነው፡፡ ሁለቱን ነገሮች የሚያገናኝና

የሚያመሳስል ምንም ነገር የለም፡፡ ሐውልቶችን ማዳቀልም በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት የሌለውና የተከለከለ ነው።

ከዚህም ባሻገር የ30 አገራት መሪዎችን ሥም የያዘ ዛፍ አጥፍቶ፣ ሌላ ታሪክ መሥራት አሳማኝ አይደለም ብለን

አስተያየታችንን አቀረብን፡፡
ሪፖርቱን ያቀረብነው ለከተማው ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ነበር፡፡ አስተያየታችንን ለሊቀመንበር መንግሥቱ ኃይለማርያም

እንድናቀርብ ታዘዝን፡፡ ቀጠሮ ተይዞልን ሄደን ሀሳባችንን ስንነግራቸው “እነዚህ ሰዎች የሚሉት ትክክል ነው፡፡ እኛ

በጊዜው እንደዚህ አላሰብንበትም ነበር፡፡ የሶቪየት መሪ ሲመጡ ለሌኒን ሐውልት መሥሪያ ቦታ አዘጋጁ ሲባል ነው

ቦታው ተመርጦ የመሠረት ድንጋይ የተቀመጠበት …” ስላሉ ሐውልቶቹን ማዳቀሉ ቀርቶ፤ ታሪካዊ ዛፎች ሳይቆረጡ

የሌኒን ሐውልት ተሰራ፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ 100ኛ ዓመት ኢዮቤልዩ በዓልም የተከበረው በእናንተ የስልጣን ዘመን ነው፡፡ ዝግጅቱ ምን ይመስል

ነበር?  
የከተማዋን 100ኛ ዓመት የማክበር እቅድም እኛ ከመምጣታችን በፊት የታቀደ ነበር፡፡ ሊከበር የታሰበው ግን በ1976

ዓ.ም የነበረ ቢሆንም እኛ ከመጣን በኋላ ተክለፃዲቅ መኩሪያን የመሳሰሉ የታሪክ ምሁራንን በመጠየቅ ማስተካከያ

ተደርጐ በዓሉን በ1979 ዓ.ም አክብረናል፡፡ አዲስ አበባ ከአፄ ምኒልክና ከእቴጌ ጣይቱ ጋር የተያያዘው ታሪኳ የቅርብ

ቢሆንም ከአብርሐ አጽብሃና ከንጉሥ ዳዊት ጋር የሚያያዝ ጥንታዊ ታሪክ እንዳላትም ይታወቃል፡፡ ከተማዋ

የተመሠረተችበትን 25ተኛ፣ 50ኛና 75ተኛ ኢዮቤልዩ ስለማክበሯ የሚገልጽ መረጃ አላገኘንም ነበር፡፡ 100ኛው ኢዮቤልዮ

የመጀመሪያ ነበር፡፡
ለበዓሉ ምን አቀዳችሁ? ምን ተሳካ? ያልተሳካውስ?
ለበዓሉ ብሔራዊ ኮሚቴ እንዲዋቀር ስንጠይቅ፣ ከእናንተ ውጭ ማንም አይመጣም፤ ሥራችሁን ቀጥሉ ተባልን፡፡ የአዲስ

አበባ ከተማ አስተዳደር የሥራው ባለቤት ሆኖ የተለያዩ ባለድርሻ አካላትንና ባለሙያዎችን እያሳተፍን መሥራት

ጀመርን፡፡ እንጦጦ ማርያም ቤተክርስቲያንን ስንጐበኝ በዕቃ ማስቀመጫ ክፍል ውስጥ ብዙ ታሪካዊ ቅርሶችን ስላየን፣

ከባህል ሚኒስቴር ጋር በመተባበር እንጦጦ ላይ ሙዚየም አሰርተን ቅርሶቹ እዚያ እንዲቀመጡ አደረግን፡፡
መስቀል አደባባይ በራስ ብሩ ቤት ለተመሳሳይ አገልግሎት የሚውል ሙዚየም አደራጀን፡፡ ከቤተመንግሥት በውሰት

ያመጣናቸው ቅርሶችንና ከግለሰቦች የተበረከቱልንን ይዘን ነው ሙዚየሙን ያቋቋምነው፡፡ ከሽሮ ሜዳ እስከ እንጦጦ

ያለውን መንገድ በአፋልት ያሰራነው የመቶኛ ዓመቱን በዓል ምክንያት በማድረግ ነው፡፡ ከራጉኤል እስከ ጐጃም በር

ፍተሻ ጣቢያ ያለውን ጥርጊያ መንገድንም አስፋልት ለማድረግ አቅደን የነበረ ቢሆንም በገንዘብ እጥረት ምክንያት

አልተሳካም፡፡
ሌላው ያልተሳካልን እቅድ እንጦጦ ራጉኤል ቤተክርስቲያን አጠገብ፣ አዲስ አበባንና በዙሪያዋ ያሉ አካባቢዎችን

የሚያሳይ ማማ ሬስቶራንት መስራት አለመቻላችን ነው፡፡ 50 ሜትር ከፍታ ያለውን ሕንፃ ለመሥራት ከማሰብም በላይ

የመሠረት ድንጋይ ተቀምጦለት ነበር፡፡ ቦታውን የመረጥንበት ምክንያት አፄ ምኒልክ ከባለስልጣኖቻቸውና ከአገር

ሽማግሌዎች ጋር ተቀምጠው የሚመክሩበት መስክ መሆኑን ስለተነገረን ነበር፡፡
ቦታው ላይ ለሕፃናት መዝናኛ አምባ የመሥራት ዕቅድም ነበረን፡፡ ይህም አልተሳካም፡፡ ከተሳኩልን ሥራዎች ሌላኛው

ለከተማዋ ስድስት አዳዲስ ፓርኮችን አዘጋጅተን ማስመረቅ መቻላችን ነው፡፡ ሐምሌ 19፣ ፒኮክ፣ የካ ማካኤል፣ መርካቶ

ራጉኤል፣ ጐላ ሚካኤል መናፈሻ ቦታዎች የዚያ ዘመን ውጤት ናቸው፡፡ አራቱ የመናፈ ቦታዎች አሁንም አገልግሎት

በመስጠት ላይ ይገኛሉ፡፡ በአዲስ አበባ ታሪክ ዙሪያ ምሁራን የሚወያዩበት ሲምፖዚየምም ተካሂዷል፡፡ ታስበው

ያልተሳኩ ነገሮች ቢኖሩም የከተማዋ 100ኛ ዓመት ኢዮቤልዮ በደመቀና በተሳካ ሁኔታ ነበር የተከበረው፡፡
በ1981 ዓ.ም የከንቲባነት ዘመንዎ ሲያበቃ የት ገቡ?
ቀድሞ ወደነበርኩበት ማዕከላዊ ፕላን ተመልሼ፣ በኮሚሽነርነት የአንድ መምሪያ ኃላፊ ሆኜ መሥራት ቀጠልኩ፡፡ እዚያ

እያለሁ ነው የስርዓት ለውጥ የተካሄደው፡፡ ከደርግ ባለስልጣናት  አንዱ ስለነበርኩ ‘ትፈልጋላችሁ’ ተብለው ከታሰሩት

አንዱ ሆኜ በሰንደፋ ፖሊስ ማሰልጠኛ ለተወሰነ ጊዜ ታስሬያለሁ። በኋላ በነፃ ተሰናበትኩ፡፡ ከዚያ በኋላ በግልም በጋራም

የራሴን ሥራ ሞክሬያለሁ፡፡ በተለያዩ ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ መሳተፍ ያስደስተኛል፡፡
አሁን የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች ፎረም ሰብሳቢ ነዎት፡፡ እንዴት ወደዚህ ኃላፊነት መምጣት ቻሉ?
መንግሥት ወይም የአገር መሪ የሚኮነው በሦስት መንገድ ነው፡፡ አንዱ ከንጉሳዊያን ቤተሰብ መወለድ ነው፡፡ ሌላኛው

በምርጫ ተወዳድሮ መመረጥ ሲሆን ሦስተኛው አንዱ ሌላውን ታግሎ በማሸነፍ ነው፡፡ ኢሕአዴግም ከእነዚህ በአንዱ

መንግሥት ሆኗል፡፡ እኔ አንድ መሠረታዊ የሆነ የግል እምነት አለኝ፡፡ የአካባቢዬ የስልጣን አካል ሲጠራኝ መሄድ አለብኝ

ብዬ አምናለሁ፡፡ ቀበሌ ማለት መንግሥት ነው፡፡ ከቀበሌው ጋር ያልተገናኘ ከላይኛው አካል ጋር እንዴት ሊገናኝ

ይችላል? በዚህ እምነትና አቋሜ ምክንያት በተጠራሁባቸው መድረኮች እየተገኘሁ የተሰማኝን አስተያየት አቀርባለሁ፡፡ ይህ

ደግሞ የምጋበዝባቸውን መድረኮች ቁጥር አበራከተው፡፡
መሠረታዊ የሆነው የሕዝብ አደረጃጀት የሚፈጠረው በጉርብትና ነው፡፡ በጉርብትና ለመገናኘት ደግሞ መሠረታዊ የሆነ

የጋራ ነገር ያስፈልጋል፡፡ መሠረታዊው ነገር በቦታ፣ በጊዜና በአገልግሎት ይገለፃል፡፡ እያንዳንዳችን በየዕለቱ ሦስት

ተግባራትን በተደጋጋሚ እንፈጽማለን፡፡ 8 ሰዓት በሥራ፣ 8 ሰዓት በእንቅልፍና 8 ሰዓት ደግሞ በእረፍት ወይም

በመዝናናት እናሳልፋለን፡፡
በአንድ ከተማ ውስጥ የሚኖሩ ሕዝቦች እርስ በእርስ ካልተገናኙ፣ ካልተወያዩና በጋራ ካልተዝናኑ ከተማ ነው አይባልም፡፡

የከተማ ሕዝብ አደረጃጀት ፍልስፍና መሠረቱም አብሮነትን የሚያጐላ ነው። ይህንን አመለካከትና ፍልስፍና

ስለማምንበት ባለፉት 12 ዓመታት ለሊዝ ፖሊስ የማሻሻያ ውይይት ሲደረግ፣ የአዲስ አበባ ተሐድሶ ኮንፈረንስ ሲጠራና

በመሳሰሉት መድረኮች እየተጋበዝኩ ተሳትፌያለሁ፡፡ በእነዚህ መድረኮች ተገኝቼ ሃሳቤን መግለጽ በመቻሌ ደስተኛ ነኝ፡፡
ይህንን ተሳትፎ የማደርገው በጡረታ ዕድሜዬ ነው፡፡ ልማት የጋራ ነው፡፡ ብንወድም ብንጠላም እየሰራን ነው

ልዩነታችንን ወደ አንድ ለማምጣት መጣር ያለብን፡፡ ሥራና ልማትን ትቶ መሟገትና መጨቃጨቁ የሚያስገኘው ጥቅም

የለም፡፡ በአሰራሮች ላይ ችግሮች እንዳሉ አያለሁ፡፡ ለምሳሌ ለልማት እንዲነሱ የሚደረጉ ሰዎች የሚከፈለው ካሳ

የገበያውን ዋጋ መሠረት ያደረገ አለመሆኑ ትክክል አይደለም፡፡
የከተማ መሬት በመንግሥት መያዙ ብዙ ጥቅም እንዳለው አምናለሁ፡፡ በደርግ ዘመንም መሬት የመንግስት ነበር፡፡

በከተሞች መሬት በነፃ እናድል ነበር፡፡ ኢሕአዴግ በሊዝ አለ፡፡ ይህ ደግሞ ገንዘብ በማስገኘት ብቻ ሳይሆን መንግሥት

ለከተማው ፕላን መሥራት እንዲችልም አድርጎታል፡፡ ነገር ግን ለሕዝብ አገልግሎት፡- ትምህርት ቤት፣ ገበያ፣ መዝናኛ፣

ጤና ጣቢያ ሊሰራባቸው የተከለሉ ቦታዎች ላይ ማስተር ፕላኑ ባስቀመጠው መሠረት ለምን እንዳልተሰሩ

የሚመለከታቸው አካላትን በሕግ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ለምን እንዳልተሰሩ ይህን መሰል ሀሳብና አስተያየቼን በየመድረኩ

እየተገኘሁ መግለፄ በሂደት የከተማ ነዋሪዎች ፎረም ሰብሳቢ ሆኜ እንድመረጥ ምክንያት ሆኗል፡፡
ተቃውሞ አልገጠመዎትም?
ከ1997 እስከ 1999 ዓ.ም መንግሥት ከአዲስ አበባ ሕዝብ ጋር ቅሬታ ላይ በነበረበት ጊዜ እንዴት አብረህ ትሰራለህ?

የሚሉኝ ነበሩ፡፡ አሁን ግን ይህንን መሰል ጥያቄ የሚያቀርብልኝ የለም፡፡ የሚጠይቀኝ ከመጣም ‘አገሬ አይደለም ወይ?

ለምንድነው በልማት ሥራ የማልሳተፈው?’ ብዬ መልሼ መጠየቄ አይቀርም፡፡ ይህንን ተሳትፎ በነፃና በፍላጐቴ ነው

የማከናውነው፡፡ የፖለቲካ ፍላጐት የለኝም፤ ኖርኝም አያውቅም፡፡
ቤተሰባዊ ሕይወትዎ ምን ይመስላል?
የማከብራት ባለቤትና ሦስት ሴት ልጆች አሉኝ፡፡ ቤተሰቤ የተባረከ ነው፡፡ እኔም ሰላምና እርጋታ ያለኝ ሰው ነኝ፡፡

በደስታና በሰላም ነው የምንኖረው፡፡  


ከዕለታት አንድ ቀን ሶስት ትላልቅ ገበሬዎች በጣም አባያ ሆነው በየጫካው እየደነበሩ እፅዋቱን እየረመረሙ አገር-ምድሩን እያመሱ አስቸገሩ፡፡ የዱር አራዊቱ ሁሉ በግዙፍነታቸውና በጉልበተኝነታቸው ፈሯቸው፡፡ የደኑ አራዊት አንድ ቀን ተሰበሰቡና
“እነዚህን በሬዎች ምን ብናደርግ ነው በቀላሉ ልንበላቸው የምንችለው?” ይባባሉ ጀመር፡፡ ሆኖም ሁሉም ፈሩ፡፡ የበሬዎቹ ትላልቅ መሆን ከወኔያቸው በላይ ሆነ፡፡ ስለዚህም ምንም ሳያረጉዋቸው ቆዩ፡፡
አንድ ቀን አንድ ብልጥ ጅብ መጣና “ቆይ ግዴላችሁም፤ እኔ እነዚህን በሬዎች እነጣጥልላችኋለሁ” አለ፡፡ ከዚያም ወደ በሬዎቹ ሄደና እንዲህ አላቸው፡-
“እባካችሁ ተራ በተራ ላናግራችሁ እፈልግ ነበር፡፡ ትፈቅዱልኛላችሁ?”
በሬዎቹም፤
“እንደፈለክ ልታናግረን ትችላለህ” አሉት፡፡
አያ ጅቦም በመጀመሪያ ጥቁሩን በሬ ጠርቶ፤
“ከእናንተ መካከል የነጩ በሬ ነገር ያሳስበኛል”
“ለምን ያሳስብሃል?” አለና ጠየቀ ጥቁሩ በሬ፡፡
“ጠላቶች ከሩቁ በነጩ ቆዳው ምክንያት ይለዩታል፡፡ ስለዚህም በቀላሉ ስለሚለዩዋችሁ ያጠቋችኋል፡፡ የሚሻለው ገለል ብታደርጉት ነው-ተመካከሩበት” አለው፡፡
በሬዎቹ ተመካከሩና ነጩ በሬ ለብቻው ራቅ ብሎ እንዲኖር አደረጉ፡፡ የደኑ አውሬዎች፤ ብቻውን ያገኙትን በሬ አድነው፣ አሳድደው በሉት፡፡ አያ ጅቦ ቀጠለና ጥቁሩን በሬ እንደገና ጠራው፡፡
“የዚህ የጓደኛህ የቀዩ በሬ ነገር በጣም አሳሳቢ ሆኖብኛል” አለው፡፡
“ለምን አሳሳቢ ሆነብህ?” አለው፡፡
“ምክንያቱም፤ ደም የመሰለ ቀይ በመሆኑ፤ ሰዎች ከሩቅ ይለዩታል፡፡ ስለሆነም ባንድ አፍታ የት እንዳላችሁ ይለዩና ይከታተሉዋችኋል! ራቅ አርገህ ብትልከው አንተ እንደዛፍ ወይም እንደዛፍ ጥላ የጠቆርክ በመሆንህ አይለዩህም” አለው፡፡
ጥቁሩ በሬም ሄዶ ለቀዩ በሬ ስለተባለው አደጋ አዋየው፡፡ ቀዩ በሬ ተስማማና ራቅ ወዳለ ቦታ ሄደ፡፡
ቀዩ በሬ ብቻውን ሲሆንላቸው የዱር አውሬዎቹ አሳደው ሰፈሩበት፡፡
በመጨረሻም ወንድም የሌለው ጥቁሩ በሬ በግላጭ ተገኘና የዱር አውሬዎች ሁሉ ተቀራመቱት፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አያ ጅቦ “የአፍ-አጣፋጭ” የሚል ስም ወጣለት፡፡  
*   *   *
የባለተራ ደወል የሚለውን አለማሰብ የዋህነት ነው፡፡ አዳዲስ አካሄዳችንን አለማስተዋልም ጅልነት ነው! “እኔ እዚህ መሆኔ በቂ ነው” ከማለት ባሻገር፤ “እገሌ የት ደረሰ?” ማለት ያባት ነው፡፡ የኃይል ሚዛንን አውቆ ማን ምን እያደረገ ነው? ምን ዘዴ እየተጠቀመ ነው? ማለት ደግ ነው፡፡ “የከፋፍለህ ግዛውን መርህ የምንንቀውና የምንሳለቅበትን ያህል፤ ዕውነት ቢሆንስ? ማለት ከማኪያቬሊ ጀምሮ የኖረ ያለ፤ “ደባ” መሆኑን ማስተዋል ታላቅነት ነው፡፡
የሀገር፣ የህዝብ እና የተቋም ሚሥጥር ግራ ሊያጋባን አይገባም፡፡ የሚሥጥር ትርጉም ብዙዎችን ቢያወዛግብም፤ የግል - ሚሥጥርና የአገር ሚሥጥር ግን መለየት ይኖርበታል፡፡
ስልክ ወይም ኢሜይል ጠለፋ አዲስ ኃይላዊ ማረጋገጫ (Coerced confession) ነው ይባላል፡፡ አዲስ ሚሥጥር መያዣ ዘዴ ነው፡፡ ዱሮ፤ በጉልበት በማገት የምናደርገውን፤ ዛሬ በሽቦና በኤሌክትሪክ ኃይል ጠለፋ ላይ መፈፀም ማለት ነው፡፡ ይሄ እንግዲህ “ተመርማሪውን ከማስገደድ፣ ቢያስፈልግም በቶርቸት (በወፌ-ላላ)፤ ከማወጣጣት ዶክመንቶቹን ከመውረስ፣ የግል መረጃዎችን ከመውሰድ፣ ቤቱን ሰብሮ ከመግባት ይልቅ፤ ሌላ ዘዴ መተካት ማለት ነው፡፡ ይሄ በዘመናዊ መንገድ ሲታሰብ፣ የኢ-ሜይል መዛግብት መውረስ ማለት ነው፡፡
ይሄ ደሞ፤ የኤሌክትሮኒክ መገናኛ ዘዴዎችን የፈጠሩት ሰዎች ራሳቸው፤ የማያውቁት ዘዴ የለም ብለን እንመን እንደማለት ነው፡፡
“ፖስታህ ከተከፈተ አለቀልህ፡፡ ገበናህ ተቀደደ፡፡ ፈረሱ ከጋጣው ወጥቷል”
 “ዱሮ ሚሥጥር የቤተ ክህነት ነበር፡፡ ዛሬ ቴክኖሎጂ ወርሶታል፡፡ ነገር ከካህን ወደ ልዑል ካለፈ - ነገር ጠፋ” ይላል - ዘ ኒውዮርከር፡፡ ገዢ የማያቀው ሚሥጥር የለም ነው ቁም ነገሩ፡፡
ከግልጽነት ይልቅ ሚሥጥራዊነትን የሚፈልግ ወገን - ባሁኑ ዘመን ቀልጧል፤ የሚል እሳቤ ቢኖረን ይሻላል፡፡ “ሚሥጥር ከኮተኮታችሁ ሁሉ ነገር ተጀመረ፡፡ ጐበዝ! ሚሥጥራዊነት የሤራ መሣሪያ ናት (ጄሬሚ ቤንታም)” በድብቅነትና በሚሥጥራዊነት መኖር አይቻልም፡፡ ከህዝብ የምትደብቀው ሚሥጥር በተለይ፤ ውሎ አድሮ መሸማቀቂያህ ነው!
ድብቅነት ነገ ከነግ - ወዲያ ይገለጣል፡፡ ሚሥጥራዊነት ግን የጥብቅነቱን ያህል ይቆይ እንጂ የሚታወቅ አደጋ ይሆናል፡፡ ሚሥጥራዊነት ብዙ ሽፋን አለው:- የሉዓላዊነት ሽፋን፣ የመንግሥት ደህንነት ሽፋን፣ የተቋም ህልውና ሽፋን፣ ያለመከሰስ መብት ሽፋን…ምኑ ቅጡ! ዜጋ የግል - ሚሥጥሬ ነው ቢል ግን፤ በብዳቤ፣ በኢ-ሜይል፣ በሞባይል፣ በአካል ሊያስጠይቅህ ይችላል የሚባለው ሚሥጥር የመብቱን መገፈፍ አያመላክትም፡፡
“መንግሥት ዜጐቹን ላለመሰለል መጠንቀቅ ይገባዋል” ይላሉ ፀሐፍት፡፡ “እኛ ብቻ ነን መሪዎች” የሚሉ ህዝቡን እንዲህ ይላሉ:- “ለማመዛዘንና ለመፍረድ አትችሉም፡፡ ደንቆሮ ናችሁና፡፡ ያም ሆኖ፤ ደንቆሮ ሆናችሁ መቀጠል ይኖርባችኋል - ምነው ቢሉ ማመዛዘንና መፍረድ እንዳትችሉ ይፈለጋልና፡፡” ይላል /ቤንታም/፡፡
ፖስታ እየገለጡ ሚሥጥር ስለሚያዩ ፖስታ ቤቶች፣ ዲዝሬኤሊ እንዲህ ይላል፤ “ደብዳቤዬን ክፈቱ ግን መልስ መስጠት ቻሉ!”
ዋናው ጥያቄ ግን በግል - ሚሥጥር (Privacy)፣ በግልጽነት  (Publicity) መካከል ልዩነት እንዳለ ልብ - ማለት ያሻል የሚለው ነው፡፡
ሆኖም እንደ ኤድጋር አላን ፖ - አመለካከት፤ “ሁሉም ድብቅ ነገር (mystery) ነገ ተገላጭ ነው፡፡ ምንም ነገር ተሸሽጐ አይቀርም፡፡ ወንጀሎች መፈታት አለባቸው፡፡ ግርግዳዎች መፍረስ አለባቸው፡፡ መቃብሮች ይፈነቀላሉ፡፡ ፖስታዎችም ተቀደው ይታያሉ” ይላል፡፡
ሙሰኛን፣ ኢፍትሐዊን፣ ሃሳዊ - መሲህን፣ ደካማ - ፖለቲከኛን፣ አድርባይን፣ አሻጥረኛን፣ አስመሳይ ተራማጅን የሚያውቅና የሚከስ፤ በዚህም ሆነ በዚያ ዕውቀቱ ያለው ነው፡፡ “ሰርቆ የሚያውቅ፣ በምልክት ያሰራል” የሚለው የወላይትኛው ተረት ይሄው ነው፡፡   

ከ120 በላይ ኢትዮጵያውያን ከሊቢያ ይመለሳሉ

እስራኤል ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ 60ሺህ የሚጠጉ አፍሪካውያን ስደተኞችን ከሃገሯ እንደምታስወጣ ያስታወቀች ሲሆን በህገወጥ መንገድ በሊቢያ የሚኖሩ ከ120 በላይ የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን ደግሞ ወደ ሃገራቸው ይመለሳሉ ተብሏል፡፡ የእስራኤል ካቢኔ ባለፈው እሁድ ስደተኞቹን የሚያስወጣ አዲስ ህግ ካፀደቀ በኋላ የሃገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያዊን ኔትያሁ፣ ህገወጥ ስደተኞቹን ከሀገራቸው እንደሚያስወጡ አስታውቀዋል፡፡ የአገሪቱ ካቢኔ ባፀደቀው መመሪያ መሰረት እስራኤል በመጀመሪያው ዙር 4ሺ ስደተኞችን የምታስወጣ ሲሆን በቀጣይም በዘላቂነት ህገወጥ ስደተኞች ወደ ሀገሯ እንዳይገቡ በዘላቂነት ለመከላከል ከግብጽ የምትዋሰንበትን ድንበር ጥበቃ እንደምታጠናክር ገልፃለች፡፡ ከሀገሪቱ ይወጣሉ ተበለው የሚጠበቁት አብዛኞቸ ሱዳናውያንና ኤርትራውያን ሲሆኑ ኢትዮጵውያኑም የገፈቱ ቀማሽ እንደሚሆኑ ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል ወደ አውሮፓ ለመሻገር ሊቢያን ማረፊያ ያደረጉ ከ120 በላይ ኢትዮጵያውያን በግብጽ ካይሮ ባለው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ትብብር የጉዞ ሰነዳቸው ተዘጋጅቶላቸው በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና በአለማቀፍ የስደተኞች ተቋም (IOM) ትብብር እንደሚመለሱ ታውቋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በባህሬን በቤት ሠራተኝነት ተቀጥራ ትሠራ የነበረች ኢትዮጵያዊት በሶስት ወንዶች ተጠልፉ መደፈሯንና በሴተኛ አዳሪነት እንድትሰራ መገደዷን ገልፃ፤ ድርጊቱን ፈጽሟል የተባለውን ባንግላዲሻዊ እንደከሰሰች ሰሞኑን ተዘግቧል፡፡ የ28 አመቷ ኢትዮጵያዊት ቆሻሻ ለመድፋት ወደ ውጪ ስትወጣ ሁለት ማስክ ያጠለቁ ወንዶች አፍነው በመውሰድ አፓርታማ ቤት ውስጥ ከነበሩ አራት የተለያዩ አገራት ሴቶች ጋር በሴተኛ አዳሪነት እንድትሰራ መደረጓን ገልፃለች፡፡ በቀን አስር ጊዜ ያህል ከተለያዩ ወንዶች ጋር ወሲብ እንድትፈጽም ትገደድ እንደነበርም ለፍ/ቤት አስረድታለች፡፡

መልስ አልባ ጥያቄ መልስ እንዳለው ያውቃል
ምልእቲ ኪሮስ
ምስልሽን ለመሳል መች አልወጠርኩ ሸራ
ዓይንሽን ለማየት መች አጣኝ መከራ
የዓይንሽን ብሌን ቅንድብሽን አስታውሶ
የስዕልን ብሩሽ በፍቅር ቃል ለውሶ፤ ቀለም ማንጠባጠብ
በመውደድሽ ምትሀት በፍቅርሽ መተብተብ
ከዚያም ቀለም ማፍሰስ …….
ማፍሰስ … ማፍሰስ … ማፍሰስ …
በማፍቀር መ ኮ ፈ ስ!!
ከጠጉሮችሽ መሀል ገብቶ መንፈላሰስ
ድንገት ያምረኝና … ድንገት ያምረኝና
ከበድን ሸራዬ ጠጉር እስልና
ዕልመት እስልና
ከብርሀን ግንባርሽ፣ ከዕድሜ ቀጣይ ዓይንሽ፣ ድንገት እደርስና
ከጠጉርሽ ጥቁር ፅልማት ቀላቅዬ ብሌንሽን ቀባለሁ … ደሞ ፀልያለሁ
ጥቁርሽን ‘ሚያሳዬኝ ዓይኔን አጥፋ እላለሁ
ብሌንሽ ተቀባ ዳር ዳሩ ተኳለ
የእግዚሀር መልኩ ጠፋ
ከኔ ምስልሽ አለ ፊቴ ካለው ፊትሽ
ምስልሽ ሸራዬ ላይ ቡሩሼ ላይ ወዝሽ
ድምፅሽ ላይ ትዝታ … ድምጼ ላይ ስቅታ
ስቅታዬ ደስታሽ ሳጌ ደማቅ ሳቅሽ
ታዲያ እንዲ አይደል ስዕል?
ካንቺ እየተያዩ ቀለም መቀላቀል
ሰማያዊ ህብር ከቀዩ መቀየጥ
ከጥቁሩ ነክሮ ነጩ ላይ መገልበጥ
ከስዕል ሸራ ላይ ዓይንን ተክሎ ማደር
ኋላም መጮህ ማበድ በቀለማት መስከር
ማይታወቅ ቀለም እስኪመጣ ድረስ
አንዱን ካንዱ መድፋት እላዩ ላይ ማፍሰስ
በእጅ እያፈሱ ወደ ሰማይ መርጨት
ምስልሽን ሽቶ ከአምላክ መጋጨት
ጠያቂን መጠየቅ … ጥያቄን … ማስጨነቅ
የቆዳዋን አይነት ቀለም ደባልቄ
ይሄው ከትቤያለሁ ልቤ ውስጥ አርቅቄ
እንድትፈርድ እያት
የአንገቷን ጠረን በምን ልሳላት?
የማይተው ሆኖ ክፉ ዝቋን መግለጥ
እስኪ በል ንገረኝ ምን ከምን ልቀይጥ?
ከሸራዬ ሸራ የሷን ድምፅ መስማት
ምን ይሉት መቀደስ እንዴት ያለ ምትሀት
የዕድሜ ልክ እርግማን ሴት የመሳል ምክንያት!!!
መልስ አልባ ጥያቄ
ሀዘንተኛ ሳቄ
ያውም በኮሳሳ በደሳሳ ጎጆ
ከየዋህ አፍቃሪ ብርታቱን ኮርጆ
ሽንቁሩ በበዛ በተሰበረ በር
ከነብሴ ሚነጣ ውብ ሸራ መወጠር
ከደሜ ቀይ ቀለም ከላቤ ወዝ መንከር
ከድሜ እየቀነሱ እሷ ላይ መከመር
በነገረ ነብሷ ጠልቆ መመራመር
በቃል ኪዳን አስሮ ቀለማት ማጋባት
እ…ሰይ…!! ብዙ ብሎ ንግስናን መቀባት
ከዚያ … …
ከቆሙበት ብሩሾችን ማንሳት
እልባት እስኪገኝ ላመታት መረሳት
ከሸራው ምስልሽን ከምስልሽ ላይ አንቺን እያነቡ … መቅደድ
ወደ ማይታወቅ ወደ ሩቅ መስደድ
ቀለማት አርግዘው ቀለም እስኪወለድ
ምስልሽን ሚተካ፣ ዓይን ሚሞላ ውበት፣ በጣት የሚነካ፣ ህብር ቅኔ እስኪገኝ
ምስልሽና ነብስሽ ከሸራ እስኪገናኝ
ውበትሽን ሸርፌ አላጓድልሽም
እስከጊዜው ድረስ ተይኝ አልስልሽም!!!
…….//……