Administrator

Administrator

ጭቆና ትግልን ያጠነክራል እንጂ አይገድልም...
ኢህአዴግን በምርጫ ለማሸነፍ የአንድ ወር ሥራ በቂ ነው….
ኢህአዴግ ሁልጊዜ የትግራይ ህዝብ በስጋት እንዲኖር ነው የሚፈልገው

 በቅርቡ ለፓርቲዎች የውህደት ጥያቄ አቅርባችኋል፡፡ ለየትኞቹ ፓርቲዎች ነው ጥያቄውን ያቀረባችሁት? መስፈርታችሁስ ምን ነበር? እኛ እንግዲህ ያሰብነው በመድረክ ውስጥ ካሉት ፓርቲዎች ጋር ውህደት ለመፈፀም ነው፡፡ ግን ከመድረክ ውጪም ቢመጣ ችግር የለብንም፡፡ እንግዲህ በጠየቅናቸው ፓርቲዎች ሙሉ ፈቃደኝነት በቅርቡ ከግንባር ወደ ውህደት እንሄዳለን የሚል እምነት ነው ያለኝ። ጥያቄውን ለኦፌኮ፣ ለአንድነት እና ለደቡብ ህብረቶች አቅርበናል፡፡ እነሱም በጐ ምላሽ እየሰጡን ነው፡፡ ውህደት የተጠየቁት ፓርቲዎች የመድረክ አባል ከሆኑ ለምን ራሱን መድረክን አልጠየቃችሁም? ፓርቲዎቹን በተናጠል መጠየቅ ለምን አስፈለገ? ሁለት አቅጣጫ ነው ያለው፡፡ እንዳልከው በቀጥታ መድረክንም መጠየቅ ይቻል ነበር፤ ግን በተናጠል የመጠየቁን መንገድ ነው የመረጥነው፡፡ ይሄን ጥያቄ ያነሳሁት “አረና በመድረክ ላይ እምነት የለውም” የሚሉ አስተያየቶች ስለሚሰነዘሩ ነው… በተናጠል መጠየቁን በመድረክ ህልውና ካለማመን የመጣ ነው የሚሉ ወገኖችም አሉ… እኛ እኮ ሁሉንም ነው የጠየቅነው፡፡ ነጥለን የተውነው ፓርቲ ቢኖር ሊያስብል ይችላል፡፡ ግን የጠየቅናቸው በአጠቃላይ በመድረክ ውስጥ ያሉትን ነው:- አረና፣ ኦፌኮ፣ አንድነት እና የደቡብ ህብረት፡፡ አረና ተነሳሽነቱን ወስዶ ነው የእንዋሃድ ጥያቄውን ያቀረበው፡፡

ስለዚህ መድረኩን አይፈልጉትም የሚያስብል ሁኔታ አይፈጥርም፡፡ ይሄኛውን መንገድ መምረጣችን ብዙም ችግር አለው ብዬ አላስብም፡፡ ለውህደቱ ጥያቄ መነሻችሁ ምንድን ነው? እንዴትስ ይሄኛውን ጊዜ መረጣችሁ? ምናልባት ምርጫውን አስባችሁ ይሆን? እኛ የተቋቋምነው በክልላዊ ፓርቲነት ነበር፡፡ ህወኃት ቅድሚያ ለትግሬነት ስለሚሰጥ ነው እኛም በክልላዊ ፓርቲነት የተቋቋምነው፡፡ በቀላሉ ተቀባይነትን ለማግኘት በመሻት ነው እንጂ የአረና የመጀመሪያ አላማው ሀገራዊ እሳቤን ያዘለ ነው፡፡ ክልላዊነታችን የአጀማመር ጉዳይ ነው እንጂ ለዘለቄታው ያነገብነው አላማ ሀገራዊነትን ነው፡፡ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ውህደት መፍጠራችንም ሀገራዊ አላማ አንግበው የሚታገሉ ፓርቲዎች፣ በትግራይ ህዝብ በቀላሉ ተሰሚነት እንዲያገኙም አጋዥ ይሆናል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ለዚህች ሀገር ሁነኛ መፍትሄ የሚሆነው ትግራይ ለብቻው፣ ኦሮሞው ለብቻው፣ አማራው ለብቻው፣ ሌላውም ለብቻው ሊታገል ሳይሆን ሁሉም በአንድነት ተዋህዶ ተስማምቶ ሲታገል ነው፡፡

እኛ ኢህአዴግ በህገ መንግሥቱ አንቀፅ 39 ያስቀመጠውን የመገንጠል መብት እንቃወማለን፡፡ መነሻችን ለጊዜው ክልላዊ ይሁን እንጂ ይሄም ያስቀመጥነው አላማ ሀገራዊነት ነው፡፡ አረና በህወሐት ውስጥ የተፈጠረውን አለመግባባት ተከትሎ በተፈጠረ የግለሰቦች ኩርፊያ የተመሰረተ እንጂ ከህወሓት የተለየ አጀንዳ የለውም የሚሉም አሉ፡፡ ይሄን እንዴት ያዩታል? ይሄን የሚለው ፓርቲው ውስጥ ያሉትን አባላት ማየት ያልቻለ ሰው ይመስለኛል፡፡ በሚዲያም ብዙ ጊዜ ወጣቶቹ አይወጡም፡፡ እኔ በፊት የህወሓት አባል አልነበርኩም፡፡ ብዙዎቹም አባል ያልነበሩ ናቸው፡፡ እነ አቶ ገብሩ ደግሞ ከህወሐት ጋር መሰረታዊ ልዩነት አላቸው፡፡ ያንን ልዩነታቸውን በግልፅ አስቀምጠው ነው የወጡት፡፡ ፓርቲ ያቋቋሙት ስላኮረፉ ነው ማለት ከባድ ነው፡፡ ስንት ሰዎች ናቸው ያኮረፉት? አቶ ገብሩ፣ ወ/ሮ አረጋሽና አቶ አውአሎም ናቸው፡፡ ግን እኮ እነዚህ ግለሰቦች ናቸው የፓርቲው ጠንሳሾችና መስራቾች። እነዚህ ሰዎች ደግሞ በኢህአዴግ የብሄር ፌደራሊዝም፣ የመሬት ፖሊሲና በመሳሰሉት የሚያምኑ ናቸው፡፡ በወቅቱ የልዩነታቸው አንዱ መነሻ በኤርትራ ላይ የተያዘው አቋም ነው፡፡

ፓርቲውን ካቋቋሙ በኋላ ከህወሓት ጋር ያላቸውን ልዩነት በነጥብ ማስቀመጥ ይቻላል? በመሰረቱ ከህወሓት ለመለየት ተብሎ የብሄር ፌደራሊዝም ትክክለኛ አይደለም፣ ከህወሐት ለመለየት ተብሎ የብሄር ብሄረሰብ መብት አይከበርም ማለት ተገቢ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ለልዩነታችን መነሻ ከሆኑት መካከል ለምሳሌ የአሰብ ወደብ ጉዳይ አለ፡፡ በሰላማዊ መንገድ መንግሥት መቀየር በሚለውና በዲሞክራሲና ሰብአዊ መብቶች ላይ ልዩነት አለን፡፡ ህወሓት ትልቁ የታገልንለት አላማ አንቀፅ 39 ነው ይላል፡፡ እሱ አንቀፅ ይሻሻል ሲባል ግን ህገ መንግሥቱ አይሻሻልም ይላል፡፡ ይሄ በፖለቲካ ስርአት ውስጥ ያልተለመደ ነው፡፡ እኛ ህገ መንግስቱ መሻሻል እንዳለበትና መሻሻልም እንደሚችል እናምናለን። በተቃራኒው ህወሐት ህገ መንግስቱ ፈፅሞ መሻሻል እንደማይችል ያምናል፡፡ በኢኮኖሚው አካሄድ ላይም ልዩነት አለን፡፡ እኛ ቅይጥ የሚለውን የኢኮኖሚ ስልት ሀገሪቱ መጠቀም አለባት እንላለን፡፡ እነሱ አንዱን መስክ መሪ፣ ሌላውን ተመሪ አድርገው ያስቀምጣሉ፡፡ በመሬት ፖሊሲው ላይም ልዩነት አለን፡፡ እኛ መሬት የመንግስት ሆኖ ከግለሰቡ ጋርም የጋራ የሚሆንበት መንገድ አለ ብለን እናምናለን፡፡ በፖለቲካ አካሄዳችን ደግሞ የስልጣን ገደብ ሊኖር ይገባል እንላለን፡፡ አንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ሀገር እየመራ የሚሞትበት ስርአት መቀጠል የለበትም ባይ ነን፡፡ በብሄር ፌደራሊዝም ላይ ያላችሁ አቋምስ? እኛ በብሄር ፌደራሊዝም አናምንም፤ ነገር ግን ፌደራሊዝም ለዚህች ሀገር ይጠቅማል የሚል እምነት አለን፡፡

ምን አይነት ፌደራሊዝም ይሁን በሚለው ጉዳይ አቋም ላይ አልደረስንም፤ ነገር ግን ያለውን ነባራዊ ሁኔታ እያዩ ማስተካከል ይቻላል የሚል እምነት አለን፡፡ በፕሮግራማችን ፌደራሊዝም ለኢትዮጵያ እንደሚጠቅም ያለጥርጥር አስቀምጠነዋል፡፡ የውህደት ጥያቄ ካቀረባችሁላቸው ፓርቲዎች መካከል የፌደራሊዝም አስፈላጊነት ላይ ጥርጣሬ ያላቸው አሉ፡፡ ከነዚህ ፓርቲዎች ጋር ይህን አቋማችሁን እንዴት ነው የምታስታርቁት? በእርግጥ አንዳንዶች የሚያስቀምጧቸው ሃሳቦች አሉ፡፡ ይህን እንግዲህ ወደፊት በውይይት የምንፈታው ነው የሚሆነው፡፡ ለምሳሌ አንድነት የተወሰነ የሄደው ነገር አለ፡፡ የቡድንና የግለሰብ መብትን ሳይነጣጠሉ ማስከበር የሚለውን እንደተቀበሉ አውቃለሁ፡፡ ይህን ሲቀበሉ እስከምን ድረስ ነው የሚለው እንግዲህ ሌላ ውይይት የሚያስፈልገው ነው፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው በቋንቋው የመፃፍ፣ የማንበብ፣ የመማር መብቱ ከተረጋገጠለት የቡድን እና የግል መብት የሚባለው ከዚህ በላይ ትርጉም ይኖረዋል ብዬ አላምንም፡፡ እንደ ግለሰብ መብቱ ይከበርለታል፡፡ እንደ ቡድንም እንግዲህ የዘር ልዩነት ሳይሆን የቋንቋ ልዩነት ብቻ ነው ሁላችንም ያለን፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው በቋንቋው ከተማረ፣ በቋንቋው መተዳደር ከቻለ፣ መብቱ ከተከበረለት ሌላ ምን ይፈልጋል፡፡ ከዚህ በፊት በመድረክ ስብስብ ውስጥ በመካተታችሁ “የነፍጠኛ ስርአት አቀንቃኞችና ተላላኪዎች” በሚል ስትፈረጁ ነበር፡፡ አሁን ደግሞ ውህደት ካልፈፀምን እያላችሁ ነው፡፡

ውህደቱ ለበለጠ ፍረጃ አይዳርጋችሁም፡፡ በፖለቲካ እንቅስቃሴያችሁ ላይስ ተፅእኖ አይፈጥርም? ከነፍጠኛ ስርአት ናፋቂዎች ጋር እየሰራችሁ ነው የሚባለውን እኛ ሚዲያ ባለማግኘታችን ነው እንጂ ማስረዳት እንችላለን፡፡ እኩል የሆነ የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ እድል ቢከፈት፣ በእርግጠኝነት የኛ ሃሳብ የበላይ ይሆን ነበር፡፡ ከአንድነት እና ከሌሎች ጋር መስራታችንን እንደ ነፍጠኛ ስርአት ናፋቂነት እየቆጠረ፣ እራሱ አማራውንና ኦሮሞውን እንወክለዋለን ከሚሉት ጋር እየሰራ፣ ራሱን ለትግራይ ህዝብ ታማኝ እንደሆነ አድርጐ ማቅረቡ ስህተት ነው፡፡ ይህን ስህተቱን ግን ሚዲያ በመከልከላችን ለህዝቡ ማስረዳት አልቻልንም፡፡ እንዲህም ሆኖ ግን ሲመሰረት ቅዠት ነው የተባለው አረና፤ ጫናውን ሁሉ ችሎ ዛሬ ተቀባይነትን በስፋት እያገኘ ነው፡፡ መጀመሪያ በክልሉ ግዙፍ ነኝ ከሚለው ህወሐት ጐን የሚቆም ተገዳዳሪ ፓርቲ ማፍራት መቻሉ ተረጋግጧል፡፡ አሁን ደግሞ ሀገራዊ ሆኖ የበለጠ ተወዳዳሪነቱ የሚጨምር መሆኑን አባሎቻችንን አሳምነን እየተንቀሳቀስን ነው፡፡ እና ለውህደት ከጋበዝናቸው ፓርቲዎች ውስጥ ደግሞ እንዳለፉት ስርአቶች በቋንቋህ መናገር፣ መግባባት፣ መማር አትችልም የሚል አቋም ያላቸው የሉም፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሃይላት ለኢትዮጵያ ፖለቲካ አስጊ ናቸው ብዬ አላምንም፡፡ ይልቁኑ አስጊ የሚሆኑት ህወሐት እና ኢህአዴግ ናቸው፡፡ ህወሐት ትግሉ መካን እንዲሆን ጠንክሮ እየሰራ ነው ብዬ አምናለሁ። የትግራይ ህዝብ በሌላው ተገዝቷል፣ በተራውም ገዝቶ ያውቃል፣ አሸንፎ ያውቃል፤ ተሸንፎም ያውቃል፤ ያ እንግዲህ በጦርነት የታየ ነው፡፡

ዛሬ ግን የሚያስፈልገው ሰላማዊ ትግል ነው ተብሎ እስከታመነበት ድረስ ለሰላማዊ ትግሉ በር የመክፈትና ሜዳ የማመቻቸት ተነሳሽነቱን ሊወስድ የሚገባው ህወሐት-ኢህአዴግ ነው፡፡ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ካሉት የሰላማዊ ትግል አቀንቃኝ ፓርቲዎች የበለጠ ለዚህች ሀገር ስጋት የሚሆነው ኢህአዴግ ነው፡፡ የዚህች ሀገር ትልቁ ስጋት ኢህአዴግ ነው፡፡ ለትግራይ ህዝብ ይሄን ማስረዳትና ማሳመንም ቀላል ነው፡፡ በየመግለጫዎቻችሁ ኢህአዴግ አላፈናፍን ብሎ መንቀሳቀስ እንዳልቻላችሁ ትናገራላችሁ፡፡ በሌላ በኩል በትግራይ ህዝብ ሰፊ ተቀባይነት አግኝተናል ትላላችሁ፡፡ እንደውም በጥቂት ቀናት ቅስቀሳ ብቻ በምርጫ ኢህአዴግን ከስልጣን ልናወርደው እንችላለን ብላችኋል። እነዚህን ሃሳቦች እንዴት ነው ማስታረቅ የሚቻለው? እንግዲህ ኢህአዴግ ሁልጊዜ የትግራይ ህዝብ በስጋት እንዲኖር ነው የሚፈልገው፡፡ ከሌላው ህዝብ ተነጥሎ ፈርቶ እንዲኖር ነው የሚፈልገው፡፡ ኢህአዴግ ከሌለ የትግራይ ህዝብ እንደማይኖር አድርጐ ነው የሚቀሰቅሰው፡፡ በውስጥ ደግሞ የአረናን አባላት ለማጥላላት “አሸባሪ ናቸው፤ ከነፍጠኛ ጋር ነው የሚሰሩት፤ አኩርፈው ነው እንጂ የተለየ አጀንዳ የላቸውም” የመሳሰሉትን እያለ በፓርቲያችን ላይ ዘመቻውን ያጧጡፋል፡፡ ይህን አላምንም ያለውን ደግሞ በግልፅ ያስራል፡፡ አባሎቻችን በየጊዜው እየተሸበሩ ነው፡፡ ይታሠራሉ፣ ይገረፋሉ፣ አካላቸው ይጐድላል፡፡ ባስ ሲልም በ2002 ምርጫ ያጋጠሙ አይነት የአባላት ግድያ አለ፡፡ እኛ ግን ይህ በደል ስለደረሰብን እጃችንን አጣጥፈን አልተቀመጥንም፡፡

ትግሉን ወደፊት ማስኬድ ይህን መሰሉን ጭቆና ለማስቆም ብቸኛው አማራጫችን እንደሆነም እንገነዘባለን። በዚህ ስሌት ዱላው ሲበረታብን፣ እኛም እየበረታን ትግላችንን እናስቀጥላለን። ደርግም የወደቀው በዚህ መንገድ ነው፡፡ ጭቆና ትግልን ያጠነክራል እንጂ ትግልን አይገድልም፡፡ ህዝቡም ይሄን ያውቃል፡፡ የትግራይ ህዝብ፤ ህወሓት ለትግሉ የተሠው ሠማዕታትን አላማ እንደካደ በሚገባ ተገንዝቧል፡፡ የብሄር ተዋፅኦ ተመጣጣኝ እንዲሆን ተብለው ህወሓትን ባለመደገፋቸው ብቻ ከጦር ሠራዊት እንዲቀነሱ የተደረጉ አሉ፡፡ በመከላከያ ሠራዊት ውስጥ የብሔር ተዋጽኦ ይኑር የሚለውን አትደግፉም ማለት ነው? በሠራዊት ግንባታው ላይ አሁንም የትግራይ ህዝብ ከከፈለው መስዋዕትነት አንፃር ተጠቃሚ አይደለም፡፡ ይሄን የምልህ እንደግለሰብ ባለኝ አቋም ነው እንጂ በፓርቲያችን የተያዘ አቋም አይደለም፡፡ በየግንባሩ ሲዋጉ የወደቁት ወንድሞቻችን አሉ፡፡ ሌላው በገበያ ላይ ተደብድቦ፣ ተገደሎ ህዝቡ የከፈለው መስዋዕትነት አለ፣ እንዲሁም በከተማ የነበረው ትግል አለ፡፡ እነዚህ መስዋዕትነቶች አጉል መቅረት የለባቸውም፤ ወደላቀ ደረጃ መሸጋገር አለባቸው፡፡ በእርግጥም ኢህአዴግ እንደሚለው የተመጣጠነ ሠራዊት ለመገንባት እነዚህን ለትግሉ መስዋዕት የሆኑ ወገኖችን መቀነስ ተገቢ አይደለም፡፡ በቀጥታ ነበር መቀጠል የነበረባቸው፡፡ ቅነሣው ሲካሄድ ደግሞ የእነሱ ታዛዥ ያልሆኑትንና በኤርትራ ላይ ከነሱ የተለየ አቋም ያላቸው ተመርጠው ነው፡፡ ለነገሩ አጠቃላይ የስርአቱ ስትራቴጂ የታዛዥነትን መንፈስ ማስረጽ ነው፡፡ ለነሱ ታዛዥ ያልሆነ ምክንያት ተፈልጐለት ይገለላል፡፡

እኛ እንደ አቋም የግድ ከዚህኛው ብሔር ይሄን ያህል እያልን ቀመር ባናወጣለትም ሠራዊቱ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ተዋጽኦ እንዲኖርበት እንፈልጋለን፡፡ የፓርቲያችሁ አንዳንድ አባላት የነበሩ ከሠላማዊ ትግል ወደ ትጥቅ ትግል ለመግባት ኤርትራ ሄደው ስልጠና እየወሰዱ ነው ይባላል? ይሄን መደበቅ አይቻልም፡፡ ከኛ የፓርቲው ማዕከላዊ ኮሚቴ አመራር የነበረ ጐይቶም በርሄ የሚባል ሰው የትኛውን ቡድን እንደተቀላቀለ ባላውቅም ወደ ኤርትራ እንደሄደ ይታወቃል፡፡ እኔ ይሄ አካሄድ ይጠቅማል የሚል እምነት የለኝም፡፡ እዚሁ የኢህአዴግን ጫና ተቋቁሞ ትግል ማድረግ አሁንም ይቻላል፡፡ በኢህአዴግ ውስጥም ሁሉም ክፉዎች ናቸው ብዬ አላምንም፡፡ የዲሞክራሲ ምህዳሩ መጥበብ የሚያሳስባቸው ይኖራሉ የሚል ግምት ነው ያለኝ፡፡ የተከፈለውን መስዋዕትነት እና አሁን እየተደረገ ያለውን እያዩ የሚብከነከኑ የኢህአዴግ አባላት እንደሚኖሩ ጥርጥር የለውም። ስለዚህ መሣሪያ ማንሣትን አማራጭ የሚያደርጉ ወገኖች ተቀባይነት የላቸውም፤ ዞሮ ዞሮ በጠላት ሃይል ነው የሚደገፉት፡፡

የሠላማዊ ትግላችሁ እርምጃ ለውጤት ያበቃናል ብላችሁ ታምናላችሁ? ኢህአዴግ የፖለቲካ ሜዳውን ከከፈተው አሁን ያሉት ተቃዋሚዎች እንደሚያሸንፉት ጥርጥር የለውም፡፡ ህዝቡ ከሚገባው በላይ ኢህአዴግን ጠልቶታል ብዬ ነው የማስበው፡፡ የኢህአዴግ የመከፋፈል፣ አንድን ህዝብ አንዱ በጥርጣሬ አይን እንዲመለከተው የሚያደርገው ሁሉ በህዝቡ ተነቅቶበታል፡፡ በተቃዋሚዎች በኩል ደግሞ ወደ አንድ አቅጣጫ የመምጣት ሂደቱ አሁን ላይ የተሻለ ይመስላል፡፡ ተቃዋሚዎች ያለንን የፖሊሲ ልዩነት እያጠበብን፣ ወደ አንድ አቅጣጫ እየመጣን ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ለውጡ በዚህ ብቻ አይደለም የሚመጣው፡፡ በኢህአዴግ ውስጥም ቅን አሣቢ የሆኑ፣ ለህዝብ የሚቆም ህሊና ያላቸው ወገኖች ይኖራሉ ብዬ እገምታለሁ፡፡ ሸምቀቆው እየበረታ ሲሄድ “ይሄማ ትክክል አይደለም” ብለው የትግሉ አላማ መካዱን የሚያስታውሱ ሰዎች ይፈጠራሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡ ኢህአዴግን መቀየር አለበት። ህዝብ እየጠላው ነው ብለው የሚያምኑ ወገኖች በራሱ በኢህአዴግ ውስጥም እንዳሉ ጥርጥር የለኝም፡፡ መሠረታዊ ጥያቄው ኢህአዴግ እንዴት ስልጣን ይልቀቅ የሚለው ነው፡፡ በመሣሪያ ከሆነ ለሃገሪቱም ለሁላችንም ኪሣራ ነው፡፡ በሠላማዊ መንገድ ከሆነ ግን ለኢህአዴግም ወርቃማ ታሪክ፣ ለአገሪቱም ታላቅ ድል ነው፡፡ እኔ አቶ መለስ በስልጣን ላይ እያሉ በመሞታቸው በጣም ነው የማዝነው፡፡ በጣምም ይቆጨኛል፡፡ የትግሉ አላማ ይሄ አልነበረም፡፡ እሣቸው ግን የእነ አፄ ዮሐንስን፣ ሚኒልክን፣ ሃይለስላሴን ታሪክ ነው የደገሙት። አዲስ ነገር አላመጡም፡፡

ከስልጣኑ ገለል ብለው ህልፈታቸው ቢሆን ደስታዬ ነበር፡፡ በዚህች ሀገር ታሪክ ውስጥ በጣም የተከበሩ የመሆን እድልም ያገኙ ነበር፡፡ ኢህአዴግ ከአቶ መለስ ተምሮ ታሪኩን ላለማበላሸት መስራት አለበት እላለሁ፡፡ እሱም እንደመሪው ሞቴን በስልጣን ላይ ያድርገው ካለ፣ በገዛ እጁ ታሪኩን እንዳበላሸ እቆጥረዋለሁ። ራሱን ተቃዋሚ ሆኖ ለማየት መጓጓት እንዳለበት ይሠማኛል፡፡ ከኢህአዴግ ውስጥ ለውጥ እንደሚጀምር ያያችሁት ፍንጭ ይኖር ይሆን በተለይ በህወሓት በኩል የመከፋፈል ነገር አለ ማለት ነው? ይፋ የወጣ ነገር ባይኖርም በግሌ ከአንዳንዶች ጋር ስንወያይ “አቶ መለስ በስልጣን ላይ ሙጭጭ እንዳሉ ህይወታቸው ማለፉ የትግሉ አላማን የሣተ ነው፤ በእርግጥም ከስልጣን ወርደው ህይወታቸው ቢያልፍ ለራሳቸውም ለሀገራቸውም ታሪክ ይሆን ነበር፡፡ የትግሉ ፍሬም ውጤቱ ያምር ነበር” እያሉ የሚቆጩ ሰዎች አሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች በዚህ የሚቆጩ ከሆነ፣ ህወሓት ኢህአዴግ በስልጣን ላይ እንዳለ እንዲሞት አይፈልጉም ማለት ነው፡፡ እኔ በ2007 ምርጫ ኢህአዴግ በምርጫ ተሸንፎ በሠላም ከስልጣን ይለቃል የሚል ተስፋ አለኝ፡፡ ከለቀቀ በኋላ ደግሞ ሰዶ ማሳደድ ሣይሆን እንደማንኛውም ተቃዋሚ ሆኖ እናየዋለን ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ እንደምትሉት ግን ኢህአዴግን በምርጫ አሸንፎ ስልጣን መያዝ ቀላል ነው? በሚገባ ማሸነፍ ይቻላል፡፡ ዋናው የሠላማዊ ትግል መንገድ የተደላደለ ይሁን፣ ተቃዋሚዎችም ከልባቸው ከታገሉ በእርግጥም ኢህአዴግን በምርጫ ለማሸነፍ የአንድ ወር ስራ በቂ ነው፡፡ ተቃዋሚዎች ውስጥም ሃገር ለመምራት፣ ሚኒስትር ለመሆን እና ህዝብን ለማስተዳደር አቅም ያላቸው ሰዎች እንዳሉ እንኳን ህዝቡ ኢህአዴግም በሚገባ ይገነዘበዋል፡፡ ኢህአዴግ እኮ ውጤቱን የሚለካው ግሎባላይዜሽን ባመጣቸው ነገሮች ነው፡፡ ሞባይል ለገበሬው አከፋፈልኩ፣ መብራት አስገባሁ ነው የሚለው፡፡ አረና የግንቦት 20 በዓልን ያከብራል? ሠማዕታትንስ እንደ ህወሓት በየአመቱ ይዘክራል? ትግሉ የተጀመረበት የካቲት 11 እና ትግሉ ፍፃሜ ያገኘበት ግንቦት 20 በህወሓት ኢህአዴግ የሚከበሩ ናቸው፡፡ አረና እንደፓርቲ እስካሁን ግንቦት 20ን ለይቶ አክብሮ አያውቅም፡፡ ግን እንደ ግለሰብ የምኮራበት ሊሆን ይችላል፡፡ በግንቦት 20 ምክንያት ቀለበት መንገድ ተሠራ፣ በግንቦት 20 ምክንያት የባቡር ሃዲድ እየተሠራ ነው፣ የአባይ ግድብ የግንቦት 20 ፍሬ ነው ከተባልኩ ግን ፈጽሞ አልቀበለውም። በተለያዩ የቀደሙ መንግስታትም ቢሆን እነዚህን የመሠሉ የልማት አቅጣጫዎች ነበሩ፡፡

አሁን በዚህ ዘመን አፄዎቹ መሪ ቢሆኑም የሚሠሯቸውን ነው ኢህአዴግ እየሠራ ያለው፤ የተለየ ታሪክ አልፈጠረም፡፡ የግንቦት 20 ፍሬን በዚህ አይደለም የምለካው፡፡ ኢህአዴግ በሠላማዊ መንገድ ከስልጣን ሲወገድ ነው ትግሉ ፍሬ አፍርቷል የምለው፡፡ በሠላማዊ መንገድ ስልጣን ማሸጋገር ከተጀመረ የካቲት 11 እና ግንቦት 20 ልዩ ይሆናሉ ብዬ አስባለሁ፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ከመስከረም 2 የሚለዩብኝ አይሆንም፡፡ ስለዚህ ግንቦት 20 ፍሬ አፍርቷል ብዬ አላምንም፡፡ ግን ሠላማዊ ሽግግር የሚደረግና የሠማዕታቱ ህልም የሚፈታ ከሆነና ግንቦት 20 ትልቅ በአል ይሆናል ብዬ አምናለሁ፡፡

በደሌ ለኮንሰርቶቹ 25 ሚ.ብር መድቦ ነበር ኮንሰርቶቹ ቢሰረዙም ውዝግቡ አልተቋጨም የቴዲ ደጋፊዎች የአፀፋ ዘመቻ ጀምረዋል

አለማቀፉ የኔዘርላንድ ኩባንያ ሄኒከን ከሚያስተዳድረው በደሌ ቢራ ጋር በመሆን በበርካታ ከተሞች ሊካሄዱ የነበሩ የቴዲ አፍሮ ኮንሰርቶች ቢሰረዙም፣ ቴዲ አፍሮ በውላቸው መሰረት 4.5 ሚ. ብር እንደሚከፈለው ምንጮች ገለፁ፡፡ እስካሁን በአገር ውስጥ ከተካሄዱ ኮንሰርቶች በላቀና ደረጃውን በጠበቀ መንገድ በድሬዳዋ ተጀምሮ በርካታ ከተሞችን እንዲያዳርስ ታስቦ የተፈረመው የቴዲ አፍሮና የበደሌ ቢራ ስምምነት፤ በኢንተርኔት በተካሄደ የተቃውሞ ዘመቻ ታውኮ ነው ሳምንት ሳይሞላው የፈረሰው፡፡ ከ20ሺ በላይ ሰዎች በኢንተርኔት በተሰባሰበ ድምጽ ለተካሄደው የተቃውሞ ዘመቻና ውዝግብ እንደመነሻ ሆኖ የሚጠቀሰው ዐረፍተ ነገር “የአፄ ምኒልክ ጦርነቶች ቅዱስ ናቸው” የሚል አባባል ሲሆን፤ ቴዲ አፍሮ የኔ አባባል አይደለም በማለት ማስተባበሉ ይታወሳል፡፡ በምኒልክ ጦርነት ብዙ ሰው አልቋል በሚል የገፋው ተቃውሞ፤ በደሌ ከቴዲ አፍሮ ኮንሰርት ጋር እንዳይተባበር ለሄኒከን ኩባንያ ጥያቄውን በማቅረብ እንዲሰረዝ አድርጓል፡፡

የቀድሞ የአገሪቱ ነገሥታትን በተመለከተ፣ በተለይም በአፄ ምኒልክ ዙሪያ ከየአቅጣጫው “መልካም ወይም መጥፎ ናቸው” የሚባሉ የንጉሱ ድርጊቶች እየተጠቀሱ በተደጋጋሚ የፖለቲካ ጭቅጭቆች፤ መነሳታቸው አዲስ አይደለም፤ በአንድ በኩል ምኒልክ ለአገሪቱ ነፃነት፣ አንድነትና ሥልጣኔ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል የሚሉ እንዳሉ ሁሉ፤ ስልጣናቸውን ለማስፋፋት ባካሄዱት ጦርነት ግፍ ተፈጽሟል፤ ብዙ ህዝብ አልቋል ብለው የሚያወግዙም ጥቂት አይደሉም፡፡ በመሃል ደግሞ፣ በታሪክ የተከሰቱ ነገሮችን ወደኋላ ተመልሶ መለወጥ እንደማይቻል የሚገልፁ ወገኖች፤ መጥፎ ነገሮችን እያስተካከልን መልካም ነገሮች ላይ አተኩረን እየወረስን ማሳደግ አለብን በማለት ለማስታረቅ የሚሞክሩ አሉ፡፡ ከተለያዩ አካባቢዎችና ብሔረሰቦች የፈለቁ ጀግኖች ከአፄ ምኒልክ ጋር ለአገራቸው ነፃነትና ስልጣኔ ተጣጥረዋል በማለት ከአስታራቂዎቹ ወገን የተሰለፈው ቴዲ አፍሮ፤ የምኒልክን መቶኛ ሙት ዓመት በማስመልከት ለ“እንቁ” መጽሔት በሰጠው ቃለ ምልልስ፣ ካለፈው ዘመን የሚወረሱ መልካም ታሪኮችን ጠቅሶ፣ የስህተቶችና የጥፋቶች መድሃኒት ፍቅር ነው በማለት የዘረዘራቸው ሃሳቦች ታትመው ወጥተዋል፡፡

“የአፄ ምኒልክ ጦርነቶች ቅዱስ ናቸው” የሚል ሃሳብ ግን እንዳልተናገረና በመጽሔቱ እንዳልታተመ በመጥቀስ ያስተባበለው ቴዲ አፍሮ፤ በኢንተርኔት የተሰራጨው አባባል እኔን አይወክልም ማለቱ ይታወሳል፡፡ የበደሌ ቢራ ባለቤት የሆነው የአለማችን ታዋቂ ቢራ አምራች ኩባንያ ሄኒከን፤ የበደሌ ቢራ ፋብሪካ እና የቴዲ አፍሮ ስምምነት እንዲሰረዝ የወሰነው፤ እንደብዙዎች ኩባንያዎች ሁሉ አደባባይ በወጣ ውስብስብ የፖለቲካ ውዝግብ ውስጥ መዘፈቅ ባለመፈለጉ እንደሆነ ምንጮቹ ተናግረዋል፡፡ እነዚሁ ቅርበት ያላቸው ምንጮች እንደገለፁት፤ በደሌ ቢራ “የፍቅር ጉዞ” በሚል ስያሜ ከዚህ ሳምንት ጀምሮ በበርካታ ከተሞች በተከታታይ ለሚካሄዱ ኮንሰርቶች 25ሚ. ብር ገደማ መድቦ ነበር፡፡ በደሌ 4.5 ሚ. ብር ለቴዲ አፍሮ ለመክፈል ተስማምቶ ውል ሲፈራረም 1.5 ሚ ብር የመጀመሪያ ክፍያ እንደፈፀመ የገለፁት እነዚሁ ምንጮች፤ በተለያዩ ከተሞች የሚቀርቡት ኮንሰርቶች ደረጃቸውን የጠበቁና ድምቀትን የተላበሱ ለማድረግ ከ20 ሚ. ብር በላይ ወጪ ለማድረግ ተዘጋጅቶ ነበር ብለዋል፡፡ በደሌ ቢራ በራሱ መሪነት በሚያዘጋጃቸው ኮንሰርቶች ላይ፣ ከትኬት ሽያጭ የሚሰበሰበውን ገቢ ለበጐ አድራጐት ድርጅቶች ለመለገስ ሃሳብ እንደነበረውም ምንጮቹ ጠቅሰዋል፡፡

በደሌ ከኮንሰርቶቹ ዝግጅት ራሱን ለማግለል ሲወስን፣ ቀደም ሲል የተፈራረመውን ውል በሚመለከት ከቴዲ አፍሮ ጋር ተደራድሮ የውል ማፍረሻ ስምምነት መፈራረሙንም ምንጮቹ ገልፀዋል፡፡ የስምምነት ማፍረሻ ስምምነቱንና የክፍያውን መጠን በተመለከተ በደሌ እና ቴዲ አፍሮ ዝርዝር መግለጫ ካለመስጠታቸውም ባሻገር፣ ከሁሉም ወገኖች መረጃ ለማግኘት የተደረጉ ሙከራዎች አልተሳኩም። በድርድር የተቋጩ ጉዳዮች ላይ ተዋዋይ ወገኖች ጉዳዩን በተናጠል በይፋ ላለመግለጽ መስማማታቸው የተለመደ እንደሆነ ምንጮቹ ጠቅሰው፤ በደሌ የመጀመሪያ ክፍያውን ጨምሮ ለቴዲ አፍሮ 4.5 ሚ. ብር የሚከፍል መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ ብለዋል፡፡ በኢንተርኔት ሲካሄድ የነበረው ዘመቻ፣ የበደሌ እና የቴዲ አፍሮ የስምምነት ውል ከፈረሰ በኋላ ቢረግብም፤ ያንን ተከትለው የመጡ ሌሎች ዘመቻዎች መፈጠራቸው አልቀረም፡፡ የቴዲ አፍሮን ኮንሰርት ለመቃወም የተጀመረው ዘመቻ፣ በተቃራኒ ኮንሰርቱን በመደገፍ ከተፈጠረው ሌላ ዘመቻ ጋር እንካ ሰላንቲያው ቀጥሏል፡፡ በቅርብ ጊዜ የሚካሄድ ኮንሰርት ባለመኖሩ ጭቅጭቁና ዘመቻው ምን ያህል የፌስቡክ ዕድምተኞችን ሳያሰለች ሊቀጥል እንደሚችል ገና አልታወቀም፡፡

ደቡብ ሱዳንን ለመገንጠል የትጥቅ ትግሉን የመሩት ጆን ጋራንግ ከሞቱ በኋላ፤ ስልጣኑን እያጠናከረ በመጣው የሳልቫ ኪር ቡድን እና ከስልጣን በተገለለው የሬክ ማቻር ቡድን መካከል በተፈጠረው ግጭት፣ ኢትዮጵያዊው አምባሳደር ስዩም መስፍን ከቻይና ተጠርተው እያደራደሩ ሲሆን ሰሜን ሱዳን እንደ ኡጋንዳ ወደ ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር አዘነበለች፡፡ ሳልቫ ኪር የዲንቃ ጐሳ ተወላጅ፣ ተቃዋሚያቸው ሬክ ማቻር ደግሞ የኑዌር ተወላጅ እንደመሆናቸው ግጭቱም የጐሳ ልዩነት የተራገበበት እንደሆነ ቢገለጽም የሟቹ መሪ የጆን ጋራንግ ሚስት እና ልጃቸውን ጨምሮ ከስልጣን የተገለሉ የዲንቃ ጐሳ ተወላጆች ከተቃዋሚው ወገን ጋር እንደተሰለፉ ታውቋል፡፡

ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር፣ ምክትላቸው የነበሩት ሬክ ማቻርን ጨምሮ በርካታ የትጥቅ ትግል ዘመን አንጋፋ መሪዎችን ከስልጣን በማግለል፣ በትጥቅ ትግል ያልነበሩ ባለሙያዎችን መሾማቸው የእርስ በርስ ቅራኔን እንዳባባሰ ይገለፃል። በሌላ በኩል ሬክ ማቻር ያቀነበባበሩት መፈንቅለ መንግስት መክሸፉን ተከትሎ ግጭቱ ሲፈነዳ፤ የኑዌር ጐሳ ተወላጅነታቸውን ከሳልቫኪር የዲንቃ ጐሳ ተወላጅነት ጋር በማነፃፀር የእርስ በርስ ግጭቱ ጐሳን የተከተለ ነው በማለት ሚዲያዎች ዘግበዋል፡፡ ነገር ግን፣ የሟቹ መሪ የጆን ጋራንግ ሚስትና ወንድ ልጃቸው እንደ ፕሬዚዳንቱ የዲንቃ ጐሳ ተወላጆች ቢሆኑም፤ ከተቃዋሚው ሬክ ማቻር ጐን እንደተሰለፉ ታውቋል፡፡ በአምባሳደር ስዩም አስታራቂነት በሚካሄደው ድርድር ላይ ሬክ ማቻርን በመወከል ከመጡት ተደራዳሪዎች መካከል አንዱ የጆን ጋራንግ ልጅ ናቸው ተብሏል፡፡

ሳልቫ ኪርን ለመደገፍ ጦራቸውን እንደላኩ ከሚነገርላቸው የዩጋንዳው ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቪኒ ጋር ለመነጋገር፣ ሬክ ማቻርን በመወከል ወደ ካምፓላ የተጓዙትም የጆን ጋራንግ ሚስት እንደሆኑ ታውቋል፡፡ ድርድሩን ከምትመራው ኢትዮጵያ ጋር ኬንያ በድጋፍ ሰጪነት የተሰለፈች ሲሆን፤ ሰሜን ሱዳን ከኡጋንዳ በተቃራኒ ተቃዋሚውን ወገን ትደግፋለች ተብሎ ሲነገር እንደነበር ይታወሳል፡፡ ነገር ግን የሱዳኑ ፕሬዚዳንት አልበሽር በድንገት ወደ ጁባ በመሄድ ከሰሜን እና ከደቡብ ሱዳን በተውጣጣ ጦር የነዳጅ ማውጫ አካባቢዎችን እንዲጠብቅ ከሳልቫኪር ጋር መስማማታቸው የብዙዎችን ግምት የሚያፈርስ ሆኗል። በትጥቅ ትግሉ መሪዎች መካከል ፀብ በተነሳ ቁጥር ወደ አልበሽር በመሄድ ይጠለሉ የነበሩት ሬክ ማቻር፤ ሰሞኑን በተፈጠረው የአልበሽር የሳልቫ ኪር ሽርክና ቅር እንደተሰኙ ተገልጿል፡፡

ከድርድሩ ጐን ለጐን የኢጋድ አደራዳሪ በመሆን የተሾሙት አምባሳደር ስዩም መስፍን ሬክ ማቻር ለተኩስ አቁም ስምምነት ባቀረቡት ቅድመ ሁኔታ መሰረት ወደ ጁባ በመሄድ እስረኞችን አነጋግረዋል፡፡ በሌላ በኩል በደቡብ ሱዳን በተፈጠረው ግጭት በተለያዩ የንግድ ዘርፎች ተሠማርተው የነበሩ ኢትዮጵያውያን ንብረታቸው አደጋ ላይ መውደቁን ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡ በጋምቤላ በኩል የገቡት ኢትዮጵያውያን፤ ጊዜያዊ መጠለያ ከቆዩ በኋላ ወደየአካባቢያቸው እየሄዱ ሲሆን በማላካ እና ናስራ በተባሉ የደቡብ ሱዳን አካባቢዎች መጋዘኖች እንደተዘረፈባቸው እና ያልተዘረፉ መጋዘኖቻቸውንም ጥለዋቸው እንደመጡ ተናግረዋል፡፡ በደቡብ ሱዳን አለመረጋጋት ምክንያት ብዙ ደቡብ ሱዳናውያን ወደ ጋምቤላ እየገቡ ሲሆን ቁጥራቸው ከእለት ወደ እለት እየጨመረ ይገኛል፡፡

ባሎች ለሚሰቶቻቸው ሊሉት የማይገባቸው ነጥቦች ምንድናቸው? በእርግጥ ይህ ሁሉንም አስፈላጊ ነገር ያንትታል ባይባልም በመጠኑ ለጠቅላላ እውቀት ስለሚረዳ ለንባብ ብለነዋል፡፡ፀሐፊዋ ጂሊ ስሞክለር ትባላለች፡፡  
ጂሊ ስሞክለር እንደምትለው ከባለቤትዋ ጋር ከአስር አመት ላላነሰ ጊዜ አብራ ኖራለች፡፡
ነገር ግን ከዚህ ሁሉ አመታት በሁዋላም ባልዋ ባህርይዋን ስላልተረዳው እኔ ምን መስማት እንዳለብኝና እንደሌለብኝ ብነግረው ብነግረው ሊሰማኝ አልቻለም፡፡ የተከበርክ ባለቤቴ እባክህን እኔን በሚመለከት እነዚህን አስር ነጥቦች አትናገራቸው... አልወዳቸውም ብዬ በፍሪጅ ላይ በግድግዳ ላይ ሁሉ ቦታ ለጠፍኩዋቸው፡፡ ነገር ግን ትላለች ጂሊ... እሱ ምን በወጣው ዞር ብሎም አያያቸውም፡፡ ስለዚህ ሌሎች ሚስቶችም ልክ እንደእኔ ተበሳጭተው ሊሆን ስለሚችል ለንባብ ብያቸዋለሁ ብላለች፡፡ ሰዎች  በአለም ዙሪያ በብዙ ጎናቸው ይመሳሰላሉ፡፡ እናም  ትዳሩ ...ወልዶ ማሳደጉ ... ፍቅሩ...ጸቡ...ብቻ ብዙው ነገር ይመሳሰላል፡፡ምናልባትም የአንዱ ሀገር ህዝብ ከሌላው ጋር የሚለያይባቸው ነገሮች ቢኖሩም ሰው በመሆናቸው ብቻ የሚጋሩዋቸው ነገሮች ይኖራሉ፡፡ ለዚህም ነው መረጃዎች ከአለም አለም በተመሳሳይ ድህረ ገጽ ለንባብ የሚቀርቡት፡፡
                                                 -------////-------
ባሎች ለሚስቶች ወይንም ለፍቅረኞች ሊናገሩዋቸው የማይገባቸው ነጥቦች...
1/ መታጠቢያ ቤት አጠቃቀም፣
እኔ ወደ መታጠቢያ ቤት ስሔድ ትክክል ልሁን ወይንም አልሁን ባለቤቴ ሊነግረኝ አይገባም፡፡
የመታጠቢያ ቤት ጉዞ ለግለሰቡ የግል ጉዳይ ተደርጎ መተው ያለበት ጉዳይ ነው፡፡ ወደ መታጠቢያ ቤት  መሔድሽ ልክነው ወይንም ልክ አይደለም የሚለው አስተያየት በሌላው ሰው ወይንም በባል  ቢሰነዘር የተጠቃሚውን  ሞራል ሊነካ ይችላል፡፡ ይሄንን በሚመለከት በባልና በሚስት ብቻም ሳይሆን በማንኛውም ሰው ቢሆን አስተያየት ሊሰጥበት የማይገባ ነው ትላለች ፀሐፊዋ፡፡ ስለዚህ ባሎችም ሆኑ ሚስቶች በእንደዚህ ያለው የግል ጉዳይ ላይ አስተያየት እንዲሰጡ ካልተጋበዙ በስተቀር ጣልቃ በመግባት አስተያየት ባይሰጡ ይመከራል ትላለች ጂሊ።
እንደዚህ ያለው ጉዳይ ለዚህ አገር ሰዎች ይሆናል አይሆንም የሚባል ሳይሆን ለሁሉም የሰው ልጅ የሚሆን አስተያየት ነው፡፡
2/ ምግብ፣
እኔ ቀኑን ሙሉ ለፍቼ የሰራሁትን... ቀኑን ሙሉ የደከምኩበትን ምግብ ባሌ እንዲበላ ሳቀርብለት ... የምግብ ጠረኑን ማሽተት...ወይንም አሁን ይሄ ምግብ ነው? ብሎ መተቸት እጅግ ያማር ራል፡፡ በእርግጥ ምግቡ የጎደለው ነገር ቢኖር በግልጽ መነጋገር ይቻል ይሆናል። ነገር ግን በደፈናው መተቸት አይገባም ትላች ጂሊ... አንዳንድ ጊዜ ወንዶች ለቤት ወጪ የሚሰጡት ገንዘብ ምግብን አጣፍጦ ለመስራት አይበቃ ይሆናል ብለው ቢገምቱ ምናልባት አስከፊውን ነገር ያስወግድ ይሆናል፡፡
-------////-------
“...ባለቤቴ ለእኔ የሚሰጠው የቤት ወጪ እና እሱ በኪሱ የሚያስቀረው ገንዘብ አኩል ነው፡፡ ለቤት ወጪ የሚሰጠው ገንዘብ አራት ልጆችን እሱንና እኔን ጨምሮ የተተመነ ነው፡፡ በሱ ኪስ የሚቀረው ግን ለእሱ ብቻ ነው። እሱ ቁርሱን እራቱን ምሳውን የሚበላው ከቤቱ ነው፡፡ በኪሱ የሚቀረው ገንዘብ ግን ለመጠጥ ብቻ የሚሆን ነው፡፡ ታድያ ሁልጊዜ የሚናገረው ነገር ምግቡ እንደማይጣፍጥ ነው፡፡ አንድ ሊትር ዘይት ለአስራአምስት ቀን ካልበቃ ምን ኑሮ ነው? ይላል በሌላ በኩል ደግሞ ወጡ ዘይት የለውም አይጣፍጥም ይላል፡፡ ግራ የገባ ነገር ነው...”
    ኢትዮጵያዊት ሴት የሰጠችው አስተያየት
3/ የልጆች መስተንግዶ፣
ጂሊ እንደምትገልጸው...እኔ እናታቸው ቀኑን ሙሉ አብሬአቸው ውዬ ነገር ግን አመሻሹ ላይ እሱ ሲመጣ ሶስት ሴኮንድ ባልሞላ ጊዜ ውስጥ የእሱ አድናቂዎች እንዲሆኑ...እሱ እንደሚ ወዳቸው... አንዳንድ ቀለብ ወይንም ልብስ የማይሆኑ ነገሮችን ይዞ መጥቶ በማባበል... ወይንም በማታለል ከእኔ ጋር ጭቅጭቅ መፍጠር አይገባም፡፡ እኔ እናታቸው ምግባቸውን አብስዬ አቅርቤ ልብሳቸውን አጥቤ ትምህርት ቤት እንዲሄዱ አድርጌ… እነዚህንና የመሳሰሉትን መሰረታዊ ስራዎች ሰርቼ ስለማሳድጋቸው አባትየው የበለጠ ተወዳጅ ለመሆን የማያስፈልግ ጥረት ማድረግ አይገውባም፡፡ ነገር ግን አለች... ጂሊ ...በትክክለኛው መንገድ ከእናትየው ጋር በመተባበር ልጆችን ማስተናገድ ከአባትየው ይጠበቃል፡፡ እናትየው አባታቸውን እንዲጠሉ ወይንም አባትየው እናታቸ ውን እንዲጠሉ ማድረግ ትክክል አይደለም፡፡
4/ አጉዋገል ቀልዶች፣
አንዳንድ ጊዜ በስራ ቦታ የሚቀለዱ ደርቲ ጆክ የሚባሉ አጉዋጉል ቀልዶችን በቀጥታ ወደቤት ማምጣት እና ከሚስት ጋር ለመቀለድ መሞከር ደግ አይደለም፡፡  ለእንደዚህ ያለው ጨዋታ እነዚያኑ ጉዋደኞችህን ጥራቸው ብላለች ጂሊ ለባልዋ ...ይሄንን የሚያደምጡ ሁሉ ቀልዶቹ ምን አይነት እንደሆኑ መገመት አያቅታቸውም። እውነትም ከሚስት እና ከባል ጋር የሚቀለዱ ቀልዶችን መለየት ይገባል፡፡
5/ ቅያሬ ካልሲ ማጣት፣
ምነው ካልሲዎቼ በሙሉ ቆሸሹ? ይሄ ጥያቄ በጭራሽ ሊነሳ አይገባም፡፡ ምክንያቱም ባል ካልሲ እንኩዋን በማጠብ እራሱን አይረዳም እንዴ? ስትል ትጠይቃለች ጂሊ ስሞክለር፡፡  ካልሲውን ባጥብ... ባጥብ ...ሁልጊዜ ችግር መሆኑ አይቀርም፡፡ እኔ ከአቅሜ በላይ ስለሆነ ብትፈልግ አንዱን ካልሲ ከአንዱ አዛምደህ አድርግ ...አረ ብትፈልግ አታድርግ ብዬ መልስ ሰጠሁ፡፡ በዚህ ብቻም አላቆምኩም ትላለች ጂሊ፡፡ እንዲያውም ከዚያ በሁዋላ ወደካልሲ ፊቴን ማዞር ትቻለሁ፡፡ በገዛ እጁ በቅንነት ማገልገሌን እንድተው አድርጎኛል ትላለች፡፡
በእርግጥ ይህ ብዙ ወንዶችን አይመለከትም፡፡ በዛሬ ጊዜ ወንዶች ከዚህም ባለፈ ቤታቸውን ልጆቻቸውን ሲረዱ ስለሚታዩ ለሚስቶቻቸው እንዲህ ያለ ጥያቄ ያቀርባሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡ ከሆነም ይታረም ይላሉ ሚስቶች፡፡
6/ የሰውነትን ቅርጽ በሚመለከት ፣
ምነው በየቀኑ ትወፍሪያለሽ? ይህ ጥያቄ በጣም ነው የሚያበሳጨኝ፡፡ ምናልባት ወፍሬም ቢሆን እኔ እንዲነገረኝ አልፈልግም፡፡ ይልቁንም ይህ አይነት ቀለም ልብስ  አይስማማሽም ወይንም ይሄኛውን ለውጠሸ ልበሽ ብባል እወዳለሁ፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን ስለውፍረቴ መስማት ያበሳጨኛል፡፡ እኔ ወድጄ ያደረግሁት ስላልሆነ ልወቀስበት አልፈልግም ትላለች ጂሊ፡፡  
7/ የሰውነት ጠረን፣
በስራ እና በተለያዩ ምክንያቶች ጊዜ አጥቼ ልብሴን ለሁለት ቀን ወይንም ከዚያ በላይ አልለወጥኩ ይሆናል። እንግዲህ ልብስ ካልተለወጠ ሰውነት ምን ምን ሊሸት እንደሚችል የታወቀ ነው፡፡ይህንን እኔም አላጣሁትም፡፡ ግን ጊዜ አጥቼ ወይንም ሳይመቸኝ ቀርቶ ነው፡፡
የተከበረው ባለቤቴ በፍቅር መንገድም ሳይሆን በማጥላላት ኡፍ… ምን ምን ትሸቺያለሽ? አትታጠቢም እንዴ ቢለኝ እና ቢያጥላላኝ በጣም ነው የሚከፋኝ። ቢታገሰኝ ግን እኔ እራሴ ጥሩውን ነገር ለማድረግ ጭንቅላቴ ዝግጁ ስለሚሆን አርመዋለሁ፡፡
8/ ኩርፊያ፣
አንተ የሚያስገርም ኩርፊያ እያኮረፍክ ጥሩ እንቅልፍ ትተኛለህ፡፡ እኔ ግን በአንተ ኩርፊያ ምክንያት ቁጭ ብዬ አድራለሁ፡፡ እስቲ ምን ይባላል? ኩርፊያን የሚያመጡ ነገሮችን ለማረም ምንም ዝግጁ አይደለህም፡፡ አመጋገብ አስተኛኘት የመሳሰሉት ነገሮች ላይ ግድ የለህም፡፡ ታዲያ እንደዚህ ያለውን ጥፋት ለማረም ካልቻልክ ምናለበት ወደዚያችው ወደምትችልህ እናትህ ብትሄድ ወይንም እሱዋን ወደ አንተ ብትጠራት የወለደ እንግዲህ እዳ አለበት አይደል? ትላለች ሚስት...
...በአገራችንም ይብላኝ ለወለደህ ያገባህስ ይፈታሀል ተብሎ የለ?
9/ ሙድ፣
አንተን ደስ ባለህ ወይንም ሙድህ በተስተካከለ ጊዜ የሚስትህን መደሰትና አለመደሰት ወይንም ሙድ ሳትገነዘብ ምንም ነገር አትጠይቅ፡፡ የስዋ ስሜት እስኪስተካከል ጠብቅ፡፡ አለበለዚያ እንደመጣልህ የምትገልጸው ወይንም ስሜትህን የምታሳይ ከሆነ ሚስትህ ልታስቀይምህ ትችላለች፡፡ ምክንያቱም አልተዘጋጀችበትማ...
10/ ልጆን ማዝናናት፣
ልጆችህን ከቤት ውጭ የማዝናናት ስራ እንዳለብህ አትዘንጋ... ወደሲኒማ ቤት ወይንም መታጠ ቢያ ቦታ፣ ስፖርት ቦታ፣ ዋና ቦታ ፣ከውጭ ምሳ መጋበዝ የመሳሰሉትን ከሚስትህ ጋር አብረህ ማድረግ አለብህ። ምናልባትም ሚስትህ በአንዳንድ ስራዎች እንኩዋን ብትያዝ መስተንግዶው እንዳይቋረጥባቸው ልጆችህን መንከባከብ ትልቁ ስራህ መሆኑን እንዳትረሳ፡፡

የአፍሪካ 100 ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ሰሞኑን ይፋ የተደረጉ ሲሆን የደቡብ አፍሪካዎቹ - ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ሳውዝ አፍሪካ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኬፕታውንና ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ስቴሌንቦስች ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ያለውን ደረጃ እንደወሰዱ “ፎር አይሲዩ” የተባለው ተቋም አስታወቀ፡፡
የታንዛኒያው ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ዳሬሰላም በአራተኛነት ጣልቃ ቢገባባቸውም፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኩዋዙሉ ናታል እና ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ፕሪቶሪያ አምስተኛና ስድስተኛ ደረጃን  ይዘዋል፡፡ የግብጹ ካይሮ ዩኒቨርሲቲ ሰባተኛ፣ የደቡብ አፍሪካዎቹ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ዊትዋተርስራንድ እና ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ዌስተርን ኬፕ ስምንተኛና ዘጠነኛ ደረጃን ሲይዙ የናይጀሪያው ኦባፌሚ አዎሎሎ ዩኒቨርሲቲ አስረኛ ሆኗል፡፡ የአገራችን አንጋፋው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ደግሞ  የ53ኛ ደረጃ እንደተሰጠው ለማወቅ ተችሏል፡፡
ግብጽ 20፣ ደቡብ አፍሪካ 19 ዩኒቨርሲቲዎችን በምርጥ መቶዎቹ ውስጥ በማስመረጥ፣ ቀዳሚነቱን የያዙ  ሲሆን  ኬኒያ 6፣ ሱዳን 2 ዩኒቨርስቲዎች ተመርጦላቸዋል፡፡
“ፎር አይሲዩ” የተባለው ተቋም በአህጉራት ደረጃ ምርጥ የሚላቸውን ዩኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች እየመረጠ በየስድስት ወሩ ይፋ ማድረግ የጀመረው እ.ኤ.አ ከ2004 ጀምሮ ነው፡፡ የዓለም ዩኒቨርስቲዎች የፈጠሩትን ተጽዕኖና በድረ ገጾች ላይ ያላቸውን የመረጃ ሽፋን መሰረት በማድረግ የምርጥ ዩኒቨርሲቲዎችን ዝርዝር ይፋ የሚያደርገው ተቋሙ፣ ተዓማኒ፣ ጠቃሚና መልከ ብዙ መረጃዎችን የመስጠት ዓላማ አለው፡፡ የትምህርትና የምርምር ተቋማት  የህትመት ስራዎችንና የምርምር ውጤቶችን በድረ ገጾች እንዲያሰራጩ የበለጠ ተነሳሽነት የመፍጠር ተጨማሪ አላማ እንዳለውም ለማወቅ ተችሏል፡፡

አንዳንድ ተረቶች በሂደት የዕውነታ ትንቢት ይሆናሉ፡፡ ቻይናዎች ዛሬ የደረሱበት ሁኔታ በሚከተለው ተረታቸው ላይ የተመሠረተ ሳይሆን አልቀረም፡፡
እነሆ፡-  
አንድ የቻይና ሊቅ-አዋቂ፣ አንድ ቀን በተከሰተለት ራዕይ ላይ ተመሥርቶ እንዲህ የሚል ሀሳብ ለህ/ሰቡ ያቀርባል፡-  
“ጐበዝ በመጪው ዘመን የሚመጣው ውሃ የተበከለ ነው የሚሆነው፡፡ ስለዚህ ካሁኑ በእጃችሁ ያለውን ንፁህ ውሃ ብታከማቹ ደግ ነው፡፡ መጪው ውሃ ከቶም ጥራት ያለው ስለማይሆን በጊዜ ውሃችሁን አጠራቅሙ፡፡”
ይህን በየቦታው እየዞረ መስበኩን ቀጠለ፡፡
ከፊሉ፤
“አጭበርባሪ ነው፡፡ አዋቂ ነኝ በማለት አዲስ ነገር ለማስመሰል የቆመ ነው፡፡”
ግማሹ፤
“ጊዜው እያለፈ ሲሄድ ፈላስፋ ነን የሚሉ መምጣታቸው አይቀሬ ነው፤ ተውት አትስሙት” የሚል እሳቤ አቀረበ፡፡
አዋቂው ግን፤
“ግዴላችሁም እኔ እምላችሁን ስሙ፡፡ ስለ ውሃ የወደፊት ሁናቴ የሚጠቅማችሁ ይሄ እኔ የምላችሁ ነገር ነው” ማለቱን ቀጠሉ፡፡
ሰው ሁሉ አዋቂውን ናቀ፡፡ ዘለፈ፡፡
ስለሆነም፤ አሮጌውን ውሃ ትቶ አዲስ ውሃ መጠጣት ፈቀደ፡፡ ጠጣ ጠጣና ሰው ሁሉ አበደ!
ከማ/ሰቡ መካከል አንድ ሰው ግን፤ አዋቂው ያለውን ተቀብሎ ውሃ ማጠራቀም ጀመረ፡፡ ሆኖም፤ የሰው ሁሉ መሳቂያ መሳለቂያ ሆነ፡፡ “ዕብድ ነው!” ተባለ፡፡ ይብስ ብሎ ተቃዋሚ አፈራ፡፡ ተቃዋሚው በዛ በዛና አገሩ ሁሉ ተቃዋሚው ሆነ፡፡ በዚህም ምክንያት ሰው ሁሉ፤
“ይሄ ሰው ጤና ቢጐለው ነው እንጂ የዱሮ ውሃ አያጠራቅምም ነበር፤ እያለ ክፉኛ ወሬውን ነዛው”
ሰውዬው፤ ከነጭራሹ በህብረተሰቡ ተተፋ፡፡ ንክ ነው፣ ዕብድ ነው ተባለ! የሚጠጋውም ሆነ የሚያወራው ወዳጅ በማጣቱ ይጨነቅ፣ ይጠበብ ጀመር፡፡ ያበደ አገር፤ እሱን ዕብድ ነው እያለ አገለለው!
ስለዚህ ዋለ አደረና ተስፋ ሲቆርጥ ያጠራቀመውን ውሃ ሁሉ ደፋው፡፡ ከዚያም እንደሰው አዲሱን ውሃ መጠጣት ጀመረ፡፡ ይሄኔ አገሬው፤ “ይሄ ዕብድ ጤናው ተመለሰ፡፡ ደህና ሰው ሆነ!” እያለ እያወደሰው፣ ቀርቦ ያጫውተው ጀመር፡፡ ያ ዕብድ የተባለ ሰው ከአገር ተደባለቀ፡፡ ከዕድር ተዋሃደ፡፡ ካበደው አበደ፡፡ ነባሩን ጽዱ ውሃ ያጠራቀመ ሰው በአገሩ ባለመኖሩ፤ ሰው ሁሉ የተመረዘው፣ አዲስ ውሃ ሰለባ ሆነ!!
*    *    *
ከመንገደኝነት አስተሳሰብ ካልወጣን ንፁህ ውሃ አንጠጣም፡፡ በአንድ አሸንዳ የመፍሰስ አባዜ ለለውጥ አያዘጋጅም፡፡ የተለየ አስተሳሰብ ያላቸውን ወገኖች እህ ብለን ካላዳመጥን ለውጥ አናመጣም። ምክንያቱም፤ አንቻቻልምና ሰላም አይኖረንም፡፡ አንተራረምምና ከስህተት ክብ ቀለበት ለመውጣት አይቻለንም፡፡
ሀገራችን፤ ሁለመናቸው ዓይን ብቻ የሆኑ (እለ ኩለንታሆሙ መሉዐነ ዓእይንት እንዲል ግዕዙ) ሰዎች የሚያስፈልጓት ሰዓት ላይ ናት፡፡ ደራሲ ብርሃኑ ድንቄ በ “አልቦ ዘመድ” እንደገለፁት፤ “የኢትዮጵያን ታሪካዊ ባህል አስፋፍቶ ለማሳደግና መሠረቱንም ለማጠንከር የደከሙት፤ “እብነ ማዕዘንት” የሚባሉት አባቶች ሁሉ አልቀው፤ ዛሬ ኮረቶቹና ጠጠሮቹ መሠረት ነን እያሉ ሲፎክሩ መስማት ‘ትራጀዲ’ ብቻ አይባልም፡፡ ‘ኮሜዲም’ መሆን አለበት፡፡ ይህን ዝብርቅርቅ ሳስብ በማልቀስ ፈንታ አንዳንድ ጊዜ ያስቀኛል፡፡ ‘እንዳላለቅስ ብዬ በመፍራት ሁልጊዜ እስቃለሁ’ ብሎ የተናገረው ማነው?” ይሉናል። ጥቅሱ የፀሐፌ-ተውኔቱ የቦማርሼ ነው፡፡ አፍንጫችን ሥር ያለውንና የፊት የፊታችንን ብቻ ስንመለከት መሠረታችንን እንዳንስት በቅጡ ማስተዋል ይገባናል፡፡ መሠረቱ የላላ ህብረተሰብ የኋላ ኋላ፤ ራሱንም አጥቶ የሌላውንም መቀበል ሳይችል አየር ላይ ተንገዋሎ ይቀራል፡፡ ለጊዜው የሥልጣኔ የሚመስሉን፣ ከነስውር - ደባቸው ማንነታችንን ሊያጨነግፉ የሚባትቱ አያሌ መጤ የካፒታሊዝም ሳልባጅ አስተሳሰቦችን በጥንቃቄ ማየት አለብን፡፡ እነዚህን ትውልድ ሳንገነባ ልንታገላቸው አንችልም። የሚከተለው ቃል ትውልዳችንን ለማየት ይጠቅማልና እነሆ፡- “ያለፈውን ትውልድ የሚያደንቁበት፣ የዛሬውን ትውልድ የሚፈርዱበት ዋናው ምክንያት ምንድን ነው? …” ተብለው አንደኛው ገፀ - ባህሪ ይጠየቃሉ፡፡ ሌላው ሲመልስ -  
“በነዚህ ሁለት ቃላቶች ላይ የእኔን ምክንያቶች ተንጠልጥለው ያገኙዋቸዋል፡-
፩ መስዋዕትነት ፪ ራስን መውደድ፡፡ ያለፈው ትውልድ መስዋዕትነት ምን እንደሆነ ደህና አድርጎ ያውቃል፡፡ የዛሬው ትውልድ ደህና አድርጎ የተማረው ራስን መውደድ ነው!!” (አልቦ ዘመድ)
አንድ ትውልድ መስዋዕትን ሳያቅ ጥቅም እንደሚያገኝ ሲያስብ ሐሳቡ እንደጧት ጤዛ እየተነነ፣ የጨበጠው የመሰለውና ያዝኩት የሚለው ነገር ሁሉ እየበነነ፣ መንፈሰ - ባዶነት ስለሚያጠቃው፣ መቦዘን፣ መንገዋለልና የማናቸውም አዲስ ሀሳብ፣ አዲስ ግጭት ሰለባ የመሆን ዕድሉ ሰፊ ነው፡፡ ስለሆነም በብሔር-ብሔረሰቡም፣ በሃይማኖቱም፣ በፍልስፍናውም፣ በማህበራዊ ቀውሱም፣ እንዲያው ባገኘው ክስተት ውስጥ ሁሉ ጠብ-ያለሽ-በዳቦ ማለትን፣ ተንኳሽነትን፤ ሽፋጭነትን፣ ዘራፊነትን ያስተናግዳል። ሰከን፣ ጠንፈፍ ብሎ ስለማይቀመጥ ትግሉ ሁሉ ብትን ይሆናል፡፡ የመደራጀት፣ የመሰባሰብ የመወያየት፤ መላ ይጠፋበታል! ጊዜ ወስዶ የመብሰል ነገር ይሳነዋል፡፡ ኑሮ ያራውጠዋልና መንፈሱ እየባዘነ ያገኘውን ሁሉ ቀጨም የማድረግ ፈሊጥን ብቻ ያዘወትራል፡፡ የበለጠ ከሥሩ ይነቀላል። ንቀትን እንደዕውቀት ምንጭ ስለሚይዝ፤ ሁሉን ነገር በቅድመ-ፍርድ (bias) ወስኖ፤ አዕምሮውን ዘግቶ፣ ፋይሉን ወደ መዝገብ ቤት መልሶ፣ ስለሚቀመጥ የመለወጥ ዝግጁነት ከቶ ያጣል፡፡ ስለሆነም ከጥቅም ማጋበስ ውጪ የሚታየው ነገር አይኖርም፡፡ በአፉ ይራገማል፣ ድርጊቱን ግን ራሱ ሲፈፅመው ይታያል፡፡ የህ/ሰብ ዝቅጠት (degeneration) ምልክት ነው፡፡ የንቅዘት (decadence) መገለጫው ነው፡፡ ከዚህ ሁሉ ባሻገር ደግሞ የአንጎላችን ባዶነት ሳያንስ፣ በድህነታችን ጥልቀት ሳቢያ ሆዳችን ባዶ ሆኖ ሲጮህብን፣ ጉሮሮአችን ደርቆ ሲሰነጣጠቅብን ዓመት በዓል ሲመጣብን፣ ሌማታችን ባዶ ሲሆን፣ ህይወት የምሬት ሬት ወደመሆን ያመራና፤ ዕቅዱ፣ ራዕዩ፣ ስትራቴጂው፣ ታክቲኩ፣ ፖለቲኩ፣ ምርምሩ ሁሉ፤ ይቀርና ከልቡናችንም ይፋቅና፣ ይጠፋና፤ “ነገ ነዳጅ ሊወጣ ነው”፣ “ተቆፍሮ ወርቅ ሊፈልቅ ነው” ቢባል፣ “ከሚመጣው ዓመት ዶሮ፣ ዕንቁላል ዘንድሮ!” ማለት ብቻ ይሆናል ቋንቋችን! ለማንኛውም መልካም የገና (“ገ” ጠብቆም ላልቶም) በዓል ይሁንልን!!
እንኳን ለልደት በዓል አደረሳችሁ!

          የአፍሪካ ነባር ባህል፣ ባለፉት 25 አመታት ምን ያህል እንደተረዘ በግልፅ አየነው - በደቡብ ሱዳን። ተቀናቃኞቹ ወገኖች፣ ገና ተኩስ ከመጀመራቸው፣ በጦርነት የመቀጠል ፋታ አልተሰጣቸውም። በቃ፣ በድንበር መዋጋት ወይም እርስበርስ እንደልብ መፋጀት ከእንግዲህ ለአፍሪካዊያን አይፈቀድም ማለት ነው?
ድሮኮ እንዲህ አልነበረም። ግጭትን ከትውልድ ትውልድ ማውረስና ማሸጋገር የለመደ አህጉር፣ አሁን ጦርነት ተከልክሎ ምን ሊውጠው ነው? ቢያንስ ቢያንስ፣ አስር አመት ወይም ሃያ አመት መዋጋት ለአፍሪካ ብርቅ አልነበረም፡፡ ኢትዮጵያ፣ አንጎላ፣ ሞዛምቢክ፣ ደቡብ አፍሪካ... እና ሌሎች ከደርዘን የሚበልጡ የአፍሪካ አገራትን መጥቀስ ይቻላል። አይገርምም? ዛሬ ከሶማሊያና ከኮንጎ በስተቀር፣ የያኔዎቹ የጦርነት አውድማዎች ከሞላ ጎደል ሰላም አግኝተዋል። የብዙዎቹ አገራት የእርስ በርስ ጦርነት እየከሰመ ጠፍቷል ወይም ረግቧል። በአንዱ ወይም በሌላው አገር አዲስ ግጭት ስንለኩስም፣ በጦርነት በርካታ ወራትና አመታት ሳይቆጠሩ ፍጅቱን በአጭሩ ለመቅጨት መሯሯጥ ተለምዷል።
አሁን አሁንማ፣ ፈፅሞ ለጦርነት ጊዜ የሚሰጠን ሰው እየጠፋ ነው። ደቡብ ሱዳንን ተመልከቱ። ለአዲስ ጦርነት የተነሳሱት ባላንጣዎች፤ የአንድ ሳምንት የውጊያ ጊዜ እንኳ አላገኙም። ከግራና ከቀኝ፣ ከጎረቤትና ከሩቅ፣ ከጓዳና ከአደባባይ... አለም ሁሉ “ተረጋጉ፣ እረፉ፣ አደብ ግዙ” እያለ ዘመተባቸው። “ጦርነት ካልቆመ እመጣላችኋለሁ” የሚል ማስፈራሪያ ከሰነዘረችው ከኡጋንዳ ጀምሮ እስከ አሜሪካ፣ ከአፍሪካ ህብረት እስከ ዩኤን፣ ከኢትዮጵያ እስከ ቻይና፣ ከኢጋድ እስከ አውሮፓ፣ በግልና በቡድን ድምፁን ያላሰማ የለም ማለት ይቻላል። እንደየዝንባሌው፣ ገሚሱ ሸምጋይና አደራዳሪ፣ አንዳንዱ ተቆጪና መካሪ፣ ሌላኛው ገላጋይና ሰላም አስከባሪ እየሆነ፣  አለማቀፉ ማህበረሰብ (አዳሜ በሙሉ) ከየአቅጣጫው ሲያጣድፋቸው፣ ደቡብ ሱዳኖች ሳይደነግጡ አይቀሩም።
በቃ፣ “እንደልብ መዋጋትና እድሜ ልክ መፋጀት ድሮ ቀረ!” ልንል ነው? ድሮ ድሮኮ፣ አፍሪካዊያን እንዳሻቸው በጦርነት ቢፋጁ ከልካይ አልነበራቸውም። ደግሞም አይገርምም። በብዙ የአፍሪካ አገራት፣ የአንዱ ጎሳ ተወላጆች፣ በሌላ ጎሳ ተወላጆች ላይ እየዘመቱ፣ ከብት መዝረፍና መንደር ማቃጠል፣ አካል መቁረጥና በጅምላ መግደል፣ ከጥንት ጀምሮ የተለመደ ነባር ባህል ነው። ስሙን እናሳምረው ካልን፣ “ቱባ ባህል” ልንለው እንችላለን - ለረዥም ዘመን ዛይበረዝና ሳይከለስ የዘለቀ! ጥንታዊው የጎሳ ዘመቻ፣ በሃያኛው ክፍለዘመንም ቢሆን፣ ከዘመኑ አኗኗር ጋር መልኩ ቢቀየርም ጨርሶ አልቀነሰም። እንዲያውም ይበልጥ ሲጧጧፍና ዘግናኝነቱ ሲብስበት ነው ያየነው። በቋንቋና በብሄረሰብ ወይም በፖለቲካ ድርጅት ተቧድኖ መጨፋጨፍ፣ የአፍሪካ መለያ ባህርይ እስከመሆን የደረሰው በ20ኛው ክፍለዘመን አይደል?
ኢትዮጵያ ውስጥ በእርስበርስ ጦርነት ከ150 ሺ ሰው በላይ፣ በኢትዮኤርትራ የድንበር ጦርነትም ከ70 ሺ ሰው በላይ አልቋል። በላይቤሪያ የሰባት አመታት ጦርነትም እንዲሁ 150 ሺ ሰው ሞቷል። የአፍሪካውያን የጦርነት ሱስና የፍጅት ባህል ባይቀየርም፤ ፍጅቱ እየበዛ የመጣው አለምክንያት አይደለም። ዛሬ በዘመናችን፣ እንደጥንቱ በጎራዴና በጦር ሳይሆን፣ በክላሺንኮቭና በታንክ ነው የሚጨፋጨፉት። አንጎላዊያን ለሃያ አመታት ባካሄዱት የእርስ በርስ ጦርነት፣ የግማሽ ሚሊዮን ሰዎች ህይወት ጠፍቷል። በሱዳን የዳርፉር ግዛት፣ በሁለት አመታት ግጭት ሰበብ ሁለት መቶ ሺ ሰዎች ሞተዋል። በሴራሊዮንም እንዲሁ፣ ከሞተው ህዝብ የማይተናነስ ቁጥር ያላቸው ሰዎች፣ በጭካኔ እጃቸው ተቆርጧል።
ታዲያ፣ ያ ሁሉ ሰው ያለቀው፣ “ሕዝቡን ከቅኝ ግዛት ነፃ አውጥተናል” በሚሉ ሶሻሊስት መሪ፣ ወይም “ሕዝቡን ከአምባገነን መሪዎች ነፃ እናወጣለን” በሚሉ ሶሻሊስት አማፂዎችና አገር ወዳድ አርበኞች አማካኝነት ነው። እርስ በርስ ሲጨፋጨፉ፣ “አለማቀፉ ማህበረሰብ” ምን ይሰራ ነበር ትሉ ይሆናል። አንዳንዱ፣ በእሳት ላይ ቤንዚን በማርከፍከፍ ጦርነቱን ያባብሳል። አንዳንዱ፣ “እንደፍጥርጥራቸው” ብሎ አይቶ እንዳላየ ኑሮውን ይቀጥላል። ነገር ግን፣ ተግሳፅና ምክር ለመለገስ የተጣጣሩ አልነበሩም ማለት አይደለም። ገላጋይና አስታራቂ ለመሆን የሞከሩ አልጠፉም። ቢሆንም ሰሚ አላገኙም። እንዲያውም ስድብ ነው የተረፋቸው። “በውስጥ ጉዳያችን ላይ ጣልቃ አትግቡብን፤ የእጅ አዙር ቅኝ ገዢዎች ናችሁ” ተብለው ይዘለፋሉ። የአፍሪካ አንድነት ድርጅት፣ ዋነኛ መርህ “በአገራት የውስጥ ጉዳይ ላይ ጣልቃ አለመግባት” የሚል እንደነበረ አታስታውሱም? አፍሪካዊያን “ጣልቃ አትግቡብን” እያሉ የሚከራከሩት፤ እያንዳንዱ አገር የውስጥ ጉዳዩን በራሱ ምርጫ እየመራ ተከባብሮ ለመኖር በማሰብ እንዳይመስላችሁ። ያለከልካይ እርስ በርስ ለመተላለቅ ነው።
የአፍሪካዊያን እልቂት ከጣሪያ በላይ አልፎ አለምን ለማስደንገጥ የበቃው ግን፣ በሩዋንዳ ከዚያም በኮንጎ በተከሰቱ ዘግናኝ ጦርነቶችና ግጭቶች ነው። በአንድ አመት የእርስ በርስ ፍጅት ነው፣ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሩዋንዳዊያን የረገፉት። የኮንጎ ደግሞ የባሰ ነው። ጦርነትና ረሃብ ተደማምሮ፣ በአስር አመታት ውስጥ፣ 5.4 ሚሊዮን የኮንጎ ሰዎች መሞታቸውን አለማቀፉ የቀይመስቀል ድርጅት ገልጿል።
ደግነቱ፣ ከቅርብ አመታት ወዲህ፣ አፍሪካዊያን ጥንታዊ የጦርነት ሱሳቸውንና የፍጅት ባህላቸውን የሙጢኝ ይዘው መቀጠል አልቻሉም። ምክንያቱ ሚስጥር አይደለም፡፡ የጥንቱ የፍጅት ባህል እና ዘመናዊ የጦር መሳሪያ ሲቀላቀሉ ነው፤ አህጉሪቱ በደም የታጠበችው። በጥንቱ ዘመን፣ አፍሪካዊያን ብዙ ሰውዎችን የመግደል ፍላጎት እንጂ ብዙ ሰዎችን የመግደል አቅም አልነበራቸው። ሹል እንጨት ቀስሮ ለጦርነት የሚዘምት ተዋጊ፣ አገር ምድሩን የመጨፍጨፍ እድል አያገኝም። እንጨቱ ይዶለዱማል ወይም ይሰበራል። አልያም እያሳደደ ሲገድል ውሎ፣ አመሻሹ ላይ ደክሞት ይዝለፈለፋል። ባደክመው እንኳ ጊዜ አይበቃውም - እያንዳንዱን ሰው ማሳደድና በእንጨት መውጋት ከባድ ፈተና ነው። ክላሺንኮቭ ታጥቆ በእሩምታ ደርዘኖችን መረፍረፍ፣ በታንክ መንደሮችን ማረስ የቻለ ጊዜ ነው፤ ጥንታዊ የፍጅት ባህል ምን ያህል ዘግናኝ እንደሆነ ጎልቶ መታየት የጀመረው። ጥንታዊ ባህልን ይዞ ዘመናዊ የጦር መሳሪያ የታጠቀው የአፍሪካ ሕዝብ፣ ብዙም በሕይወት የመቆየት እድል እንደሌለው በአህጉሪቱ ከተከሰቱ እልቂቶች መረዳት ይቻላል።
እናስ ምን ተሻለ? ያለከልካይ የመጨፋጨፍ ቱባ ባህል የግድ ተወግዶ፣ በምትኩ ተከባብሮ የመኖር ባህል መፈጠር አለበት። በዚህ ምክንያት፣ “ወግና ልማድ ተሻረ፤ ቱባ ባህል ተበረዘ” የሚል ቁጭት የሚያድርባቸው ሰዎች ይኖሩ ይሆን? የሚኖሩ ከሆነ፤ “ነገር የተበላሸው በ1980ዎቹ መጀመሪያ ነው” ማለታቸው አይቀርም። እውነትም፤ ኢትዮጵያንና ጎረቤቶቻችንን ጨምሮ፣ በአህጉሪቱ አራት አቅጣጫዎች፣ የጥንቱን ባህል የሚቃረን የለውጥ አየር ከዳር እስከ ዳር የነፈሰው፣ ያኔ ነው። የለውጡ መጠንና የነፋሱ ጉልበት፣ እንደየአገሩ ሁኔታ ይለያያል። የአንዳንዶቹ ፈጣን ሲሆን፣ የሌሎቹ ዘገምተኛ ነው። ገሚሶቹ፣ በእመርታ ሲራመዱ፤ ገሚሶቹ ይንፏቀቃሉ። ከፊሎቹ ያለማቋረጥ ሲሻሻሉ፤ ከፊሎቹ መነሳትና መውደቅ ያበዛሉ። ጠንካራ መሠረት የተከሉ እንዳሉ ሁሉ፣ ከአፍታ እልልታ በኋላ ወደ ዋይታ የተመለሱም አሉ። ከጦርነት ለመላቀቅ ጊዜያዊ መፍትሄ ማበጀትና የተኩስ አቁም ስምምነት መፈረም ብቻውን በቂ አይደለማ፤ ተከባብሮ ለመኖር ዘላቂ መላ መፍጠር ያስፈልጋል።
የሆነ ሆኖ፣ መጠኑና ደረጃው ቢለያይም፤ በ80ዎቹ ዓ.ም መግቢያ ግድም፣ በአዲስ የለውጥ ነፋስ ያልተነካ የአፍሪካ አገር የለም ማለት ይቻላል። በአፍሪካ የለውጥ አየር የነፈሰው፤ በራሺያ መሪነት አለምን ሲያተራምስ የነበረው የሶሻሊዝም ስርዓት በተፈረካከሰ ማግስት መሆኑ አይገርምም። ያው እንደምታውቁት፣ በሶሻሊዝም ስርዓት ተከባብሮ መኖር አይቻልም።
ሶሻሊዝም ማለት የአንድ ፓርቲ፣ የአንድ ቡድን ወይም የአንድ ግለሰብ አምባገነንነት ስለሆነ፤ የፈላጭ ቆራጭነትን ስልጣን ለመያዝ፣ የግድ መጠፋፋትና መፋጀት ያስፈልጋል። ብዙዎቹ የአፍሪካ መንግስታትና አማፂ ሃይሎች፣ ሶሻሊስት ለመሆን የተሯሯጡት ለምን ሆነና! ሶሻሊዝም ከጥንታዊው አፍሪካዊ የፍጅትና የጦርነት ባህል ጋር ይጣጣማላ። ደግነቱ፣ በ1980 ዓ.ም መፍረክረክ የጀመረው የሶሻሊዝም ስርዓት፣ በ1983 ዓ.ም ሶቭየት ዩኔን ስትበታተን ነው ተፈረካክሶ አበቃለት። ይሄው የለውጥ ነፋስ፣ አፍሪካን ለማዳረስ ጊዜ አልፈጀበትም። እንዴት በሉ።
ከዚያን ጊዜ በፊት፣ በአፍሪካ ለስም ያህል፣ የፓርቲዎች ፉክክርና የምርጫ ውድድር የሚያካሂዱ አገራት ከሁለትና ከሶስት አይበልጡም ነበር። አንዷ ቦትስዋና ናት። በተወሰነ ደረጃ ደግሞ፣ ሴኔጋል ትጠቀሳለች።
ሌሎቹ አገራት በሙሉ ማለት ይቻላል፤ የአንድ ፓርቲ አገዛዝ የነገሰባቸውና፣ “ተቃዋሚ ፓርቲ ማቋቋም በእስር ወይም በሞት የሚያስቀጣ ወንጀል ነው” የሚል ህግ ያወጁ፤ ከዚህም ጋር ተያይዞ፣ ለበርካታ አመታት በእርስ በርስ ጦርነት የሚታመሱ አገራት ነበሩ። አማፂው ሃይል፣ በጦርነት አሸንፎ ስልጣን ሲቆናጠጥም፣ በተራው የአንድ ፓርቲ አምባገነንነትን ስለሚያሰፍን ሌላ ዙር ጦርነት ይቀጣጠላል። ማብቂያ በሌለው የአምባገነንነትና የፍጅት አዙሪት ውስጥ በነበረችው አህጉር ላይ፣ አዲስ የለውጥ አየር ሲነፍስ ይታያችሁ። በጦርነት ብዛትና በአንድ ፓርቲ አገዛዝ የተጥለቀለቀችው አህጉር፣ በሰላም ድርድርና በአዳዲስ የህገመንግስት ረቂቆች ተጥለቀለቀች።
ለምሳሌ ለረዥም አመታት በአንጎላ፣ በሞዛምቢክና በኢትዮጵያ ሲካሄዱ የነበሩ ጦርነቶች እልባት ያገኙት በተመሳሳይ ጊዜ ነው። እነዚህ ሶስት የጦርነት አገራትን ጨምሮ፣ ኬንያና ደቡብ አፍሪካ፣ ጋና እና ናይጄሪያ፣ ኒጀር እና ዛምቢያ፣ ታንዛኒያና ኬኒያን…ምን አለፋችሁ? ከሰሃራ በታች፣ 25 ገደማ አገራት፣ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ለማቋቋም የሚፈቅድ ህገመንግስት ያዘጋጁትና ፓርቲዎች የሚፎካከሩበት ምርጫ ማካሄድ የጀመሩት ከ1982 እስከ 1987 ዓ.ም ባሉት አምስት አመታት ነው። በቃ፤ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ነው፣ የነፃነት ሜዳው ሰፊም ሆነ ጠባብ፣ የፖለቲካ ምርጫ የማያካሂድ አገር እንደ ነውረኛ መታየት የጀመረው። አሁን እንደ ኤርትራና ሱዋዚላድ ከአለም የተገለሉ አገራት ካልሆኑ በቀር፤ የአንድ ፓርቲና የአንድ ግለሰው አምባገነንነትን በአዋጅ የሚያሰፍን የአፍሪካ አገር የለም ማለት ይቻላል። ከዚሁ ጎንም ነው፤ “ያለከልካይ እንደልብ በእርስበርስ ጦርነት የመፋጀት ባህል” የተበረዘው።
የምታስታውሱ ከሆነ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ለሃያ አመታት ያህል፣ የእርስ በርስ ጦርነት ሲካሄድ፣ አለም “እሪ” አላለብንም። ሊያስቆመን አስቦ እጁን ያስገባ ማንም የለም። የሰላም አስከባሪ ሃይል ማሰማራትማ ጨርሶ አይታሰብም ነበር። ያለገላጋይ እስኪለይለት ድረስ መፋጀት ነው። ከ1980ዎቹ ዓ.ም ወዲህ፣ በተለይ ከርዋንዳው እልቂት በኋላ ግን፣ አዲስ ጦርነት በተቀሰቀሰ ቁጥር፣ አለም እሪ ይላል። ሳምንት ሳይሞላው፣ ጎረቤት አገራት አደራዳሪ ቡድን ያቋቁማሉ። የአፍሪካ ህብረት የአቋም መግለጫና ውሳኔ ያስተላልፋል። ዩኤን በበኩሉ፣ በኬንያና በሱዳን፣ በላይቤሪያና በርዋንዳ እንደታየው፣ የጅምላ ጭፍጨፋ ያካሄዱ መሪዎች ላይ ምርመራ ለማካሄድና ወደ አለማቀፉ የወንጀል ፍ/ቤት ለመውሰድ ይዝታል፡፡ አሜሪካና አውሮፓ በፊናቸው የዲፕሎማሲ ዘመቻ ይከፍታሉ።
በዚህ መሃል፣ “አልደራደርም፤ እንዳሻኝ እዋጋለሁ፤ በውስጥ ጉዳይ ጣልቃ አትግቡብኝ” ለማለት የሚደፍር ማን ነው? ዋጋውን ያገኛታላ። ጎረቤት አገራት ጦር ይልካሉ። የምዕራብ አፍሪካ አገራት ወታደሮቻቸውን ወደ ላይቤሪያ አዝምተው አልነበር? ኢትዮጵያና ኬንያም፣ ጦራቸውን ወደ ሶማሊያ አስገብተዋል። አሜሪካና አውሮፓም፣ እንደሁኔታው፣ ሊቢያ ላይ እንዳደረጉት የጦር አውሮፕላን ይልካሉ። ወይም እንደ ፈረንሳይ እግረኛና ኮማንዶ ጦር ያዘምታሉ። የተባበሩት መንግስታት እንኳ፣ እንደድሮው፣ ሰላምን የሚጠብቅ (Peace Keeping) ታዛቢ ሃይልን አይደለም የሚያሰማራው። በእርግጥ ስሙ አልተለወጠም። ተግባሩ ሲታይ ግን፤ “ሰላም አስከባሪ ተዋጊ ሃይል” ብለን ልንጠራው እንችላለን። በኮንጎ፣ በሴራሊዮንና በላይቤሪያ እንዳየነው፤ የተባበሩት መንግስታት ጦር፣ ለእርቅ እምቢተኛ ሆነዋል የተባሉ አማፂ ቡድኖችን እያሳደደ ወግቷል። አንዳንዳችን አስሮ ለፍርድ አቅርቧል፡፡ በተባበሩት መንግስታት ድጋፍ ወደ ሶማሊያ የዘመተው የአፍሪካ ህብረት ጦርም፣ ከአልሸባብ ጋር ይዋጋል።
በአጭሩ፣ ጊዜው ተለውጧል። እንደ ድሮ አይደለም፣ ዛሬ “አለከልካይ መፋጀት ለአፍሪካዊያን አይፈቀድም” የሚል ስሜት በርክቷል። ይሄውና የደቡብ ሱዳን ተቀናቃኝ ወገኖች፤ ገና ወደ ጦርነት በገቡ ሳምንት፣ በሰላም ጥሪ መውጪያ መግቢያ አጥተዋል።

በዕውቋ ድምፃዊት ዘሪቱ ከበደ ተፅፎ የተዘጋጀው “ቀሚስ የለበስኩለት” የተሰኘ ፊልም በሚቀጥለው ሳምንት እሁድ በአፍሪካ ህብረት አዳራሽና በአዲስ አበባ ሲኒማ ቤቶች  ይመረቃል፡፡ የድራማ ዘውግ ባለው  የ1፡40 ደቂቃ ፊልም ላይ፤ ድምፃዊቷ ዘሪቱ ከበደ፣ የንግድ ም/ቤት ፕሬዚዳንቷ ሙሉ ሰለሞን፣ የጃኖ ባንዱ ድምፃዊ ዲበኩሉ ታፈሰ፣ ሙዚቀኛው ሄኖክ መሐሪ፣ ይስሃቅ ዘለቀና ሌሎችም እንደተወኑበት ታውቋል፡፡ ፊልሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ ሁለት ዓመት የፈጀ ሲሆን ቀረፃውን “የሳቢሳ ፊልሞች” እንዳከናወነው ለማወቅ ተችሏል፡፡

የአፍሪካ ሞዛይክ የፋሽንና የባህል ትርኢት በሚቀጥለው አርብ ምሽት በሸራተን አዲስ የሚካሄድ ሲሆን በዝግጅቱ አለማቀፍ የፋሽን ሞዴሎችና ዲዛይነሮች ይሳተፋሉ፡፡ የአፍሪካን ሞዛይክ ዳይሬክተር አና ጌታነህ እንደገለፀችው፤ አስራ አምስት የውጪና የሀገር ውስጥ ዲዛይነሮች በሚሳተፉበት ትርኢት፤ እውቅ የዘርፉ  ባለሞያዎች ከኒውዮርክ፣ ከደቡብ አፍሪካና ከሴኔጋል ይመጣሉ፡፡ የኢትዮጵያ ምርጥ ሃያ ሞዴሎች የሚሳተፉበት የፋሽን ትርኢት ምሽት የመግቢያ ዋጋ 500 ብር ሲሆን ገቢው ከአዲስ አበባ 55 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በምትገኘው አለልቱ ከተማ ለሚካሄደው የተቀናጀ ልማት ፕሮጀክት ይውላል ተብሏል፡፡ የአፍሪካ ሞዛይክ የፋሽንና የባህል ትርኢት በአዲስ አበባ ሲካሄድ የአሁኑ ለአስራ አራተኛ ጊዜ መሆኑ ታውቋል፡፡

በእናቱ ኢትዮጵያዊ፣ በአባቱ ሆላንዳዊ በሆነው ዳንኤል ጁፕሁክ የተፃፈውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥነው “አመፀኛው ክልስ” የተሰኘ መጽሐፍ ሰሞኑን በገበያ ላይ ዋለ፡፡ ደራሲው በ12 ዓመት የእስር ቤት ቆይታው ያሳለፈውን ህይወት ከወህኒ ቤት ከወጣ በኋላ በደች ቋንቋ እንደፃፈው፣ ከዚያም ወደ አማርኛ በመተርጎም እንዳሳተመው ታውቋል፡፡
በአማርኛ ቋንቋ የተተረጐመው መጽሐፍ፤ በአገር ውስጥ በ70 ብር እየተሸጠ ሲሆን በደች ቋንቋ የተዘጋጀው ደግሞ በደቡብ አፍሪካና በአውሮፓ በመሸጥ ላይ እንደሆነ ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል፡፡