Administrator

Administrator

“ተጨባጩንና እውነተኛውን ነገር በጠበቃዬ በኩል ለፍ/ቤት አቅርቤያለሁ”

በተለይ “ገመና” በተሰኘው ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ ላይ የዶ/ር ምስክርን ገፀ-ባህሪ ተላብሶ በመጫወት እውቅናን ያተረፈው አርቲስት ዳንኤል ተገኝ፤ የ600 ሺህ ብር ክስ የተመሠረተበት ሲሆን አርቲስቱ ለተከሰሰበት ጉዳይ ምላሽ እንዲሰጥ ፍ/ቤቱ ለትላንትና ትዕዛዝ አስተላልፎ ነበር፡፡
ክሱ መመስረቱን ያልካደው አርቲስት ዳንኤል፤ ሆኖም “ክሱ መሰረተ ቢስና ከእውነት የራቀ መሆኑን በመግለፅ ተጨባጩን እውነታ አስፍሬ በጠበቆቼ በኩል ለፍ/ቤት ምላሽ ሰጥቻለሁ” ብሏል - ጉዳዩ በፍ/ቤት የተያዘ በመሆኑ ከዚህ በላይ ለመናገር እንደማይፈልግ በመግለፅ፡፡
አርቲስት ዳንኤልና ወ/ሮ ቤተልሄም አበበ፤ “ፋየር ፕሩቭ” የተሰኘ የእንግሊዝኛ ፊልም ወደ አማርኛ በመመለስ አብረው ለመስራት ውል ተፈራርመው የነበረ ሲሆን “አርቲስቱ በገባው ውል መሰረት ስራውንም አልሰራም ብሬንም አልመለሰም” በማለት ወ/ሮ ቤተልሄም የ662 ሺህ 120 ብር ክስ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 6ኛ ፍትሀ ብሔር ቢፒአር ችሎት መመስረታቸው  ታውቋል፡፡
አርቲስት ዳንኤል “ፋየር ፕሩቭ” የተሰኘ የእንግሊዝኛ ፊልም ወደ አማርኛ በመመለስ ስምንት ያህል ትዕይንቶችን ከቀረፀ በኋላ አቋርጦ “የሴም ወርቅ” የተሰኘ ሌላ ፊልም መስራት የጀመረ ሲሆን በዚህ ወቅት ነበር ወ/ሮ ቤተልሔም እሱ የጀመረውን ፊልም “አብረን  እንስራ” የሚል ጥያቄ ያቀረቡለት- አርቲስቱ በቅርቡ ለአዲስ አድማስ እንደተናገረው፡፡
አርቲስቱ የጀመረውን “ፋየር ፕሩቭ” የተሰኘ ፊልም ከወ/ሮ ቤተልሔም ጋር አብረው ለመስራት ተስማምተው ከተዋዋሉ በኋላ ወደ ሥራው የገቡ ቢሆንም በኋላ ላይ “ወ/ሮዋ የስነ ምግባር ጉድለት ስላለባቸው አብሬያቸው መስራት አልቻልኩም” በሚል ዳንኤል ስራውን ያቆመ ሲሆን ወ/ሮ ቤተልሄም በበኩላቸው፤አርቲስቱ በውሉ መሰረት ፊልሙን በጊዜ ሰርቶ ባለማስረከቡ ብሩን እንዲመልስ መጠየቃቸውንና እሱም ብር አልወሰድኩም በማለቱ ግጭቱ እንደተካረረ መዘገቡ  ይታወሳል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ የኢትዮፒካሊንክ የሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጆች ከወ/ሮ ቤተልሄም ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ፣“የስም ማጥፋት ዘመቻ አካሂደውብኛል” ያለው አርቲስቱ፤በግለሰቧና በአዘጋጆቹ ላይ ክስ መመስረቱን ታህሳስ 12 ቀን 2006 ዓ.ም ለንባብ በበቃው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ተናግሯል፡፡
ወ/ሮ ቤተልሔም የካቲት 7 ቀን 2006 ዓ.ም በአርቲስት ዳንኤል ላይ የ662ሺህ 120 ብር ክስ መመስረታቸውን የጠቆሙት ምንጮቻችን፤ ከሳሿ የቼክ ቁጥሮችን በማስረጃነት አያይዘው ለፍ/ቤቱ እንዳቀረቡ ገልፀዋል፡፡ ምንጮች እንደሚሉት፤ ወ/ሮ ቤተልሄም አበበ ወደ ክስ ለመሄድ የተገደዱት ለፊልሙ መስሪያ ብለው ለአርቲስቱ የሰጡትን ገንዘብ እንዲመልስ ሲጠይቁት “ብር አልወሰድኩም” በማለቱ ነው፡፡ ፍ/ቤቱ አርቲስት ዳንኤል ለቀረበበት ክስ በትላንትናው እለት ምላሽ እንዲሰጥ  ትዕዛዝ አስተላልፎ የነበረ ሲሆን አርቲስቱም ምላሹን በጠበቆቹ በኩል ለፍ/ቤት ማስገባቱን ገልጿል። ፍ/ቤቱ ግራ ቀኙን ተመልክቶ ብይን ለመስጠት ለሚያዚያ 12 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡  

ከግብጽና ከአልጀሪያ ቀጥላ በአፍሪካ 3ኛ ናት

ኢትዮጵያ ከሰሃራ በታች ከሚገኙ የአፍሪካ  አገራት ጠንካራ ወታደራዊ ሃይል በመገንባት የመጀመሪያውን ስፍራ እንደምትይዝ በ“ግሎባል ፋየር ፓወር” የተሰራ ጥናት አመለከተ፡፡
 “ግሎባል ፋየር ፓወር” 40 ያህል የተለያዩ መስፈርቶችን በመጠቀም የአገራትን ወታደራዊ አቅም ለመፈተሽ  የሰራው አዲስ ጥናት እንደሚያሳየው፣ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት 182 ሺህ ያህል በስራ ላይ የሚገኙ ወታደሮች ያሏት ሲሆን  ከ24 ሚሊዮን የሚበልጡ ዜጎቿም በውትድርና መስክ ለመሰማራት አቅም ያላቸው ናቸው፡፡
ከ560 በላይ ታንኮችና ከ780 በላይ የወታደራዊ ተሸከርካሪዎች ያሏት ኢትዮጵያ፣ በአህጉሩ ጠንካራ ከሚባሉ አየር ሃይሎች የአንዱ ባለቤት መሆኗን የሚጠቅሰው ጥናቱ፣ አየር ሃይሉ ከ81 በላይ የጦር አውሮፕላኖችና 8 ተዋጊ ሂሊኮፕተሮች እንዳሉትም ገልጿል፡፡
አገሪቱ ለመከላከያ የምትመድበው አመታዊ በጀት 340 ሚሊዮን  ዶላር መድረሱን የጠቆመው ጥናቱ፣ ኢትዮጵያ ከግብጽና ከአልጀሪያ ቀጥላ በአፍሪካ አህጉር ጠንካራ የመከላከያ ሃይል ያላት ሶስተኛዋ አገር ናት ብሏል፡፡

የማስተር ፊልምና ኮሙኒኬሽን ማሰልጠኛ ተቋም የቀድሞ ተማሪዎች የፎቶግራፍ ስራዎች አውደ ርዕይ የፊታችን ረቡዕ ከቀኑ በ10፡30 በብሔራዊ ትያትር አርት ጋላሪ ይከፈታል፡፡ በአውደ ርዕዩ በአስራ ሶስት የፎቶግራፍ ባለሞያዎች የተነሱ ፎቶግራፎች የሚቀርቡ ሲሆን አውደ ርዕዩ እስከሚቀጥለው ቅዳሜ ድረስ ለህዝብ ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ የማስተር ፊልምና ኮሙኒኬሽን ማሰልጠኛ ተቋም ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ አዜብ ከበደ ገልፀዋል፡፡

Monday, 07 April 2014 16:00

33ኛው “ግጥም በጃዝ”

ረቡዕ ይካሄዳል
33ኛው የ“ግጥም በጃዝ” ምሽት የፊታችን ረቡዕ ከምሽቱ 11፡30 ጀምሮ በራስ ሆቴል አዳራሽ እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ ግጥሞች፣ ወጎችና ዲስኩር በሚቀርብበት ዝግጅት፤ አርቲስት ግሩም ዘነበ፣ ገጣሚ ምስራቅ ተረፈ፣ ምንተስኖት ማሞ፣ በረከት በላይነህ እና ሚሊቲ ኪሮስ ሥራዎቻቸውን ያቀርባሉ ተብሏል፡፡ የመግቢያው ዋጋ በነፍስወከፍ 50 ብር ነው።

በፊልም ባለሙያዋ መቅደስ በቀለ (ማክዳ) ደራሲነትና ዳይሬክተርነት ተሰርቶ በኤራሶል ፊልም ፕሮዳክሽን የሚቀርበው “ሊነጋ ሲል” የተሰኘ አዲስ ፊልም በቅርቡ ለእይታ ሊበቃ ነው፡፡ የፊልሙ ዘውድ ፍቅር ድራማ ሲሆን በ “ባለታክሲው” ፊልም ላይ በመሪ ተዋናይነት የተወነው ሚኪያስ መሐመድ፣ ታዋቂዋ ተዋናይት ማህደር አሰፋ፣ ቃል ኪዳን አበራ፣ ቢንያም በቀለና ሌሎች አንጋፋና ወጣት ተዋንያኖች ተውነውበታል፡፡ ፊልሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ 11 ወራት የፈጀ ሲሆን በሚያዝያ ወር በግል ሲኒማ ቤቶችና በብሔራዊ ትያትር እንደሚመረቅ ታውቋል፡፡

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተመራቂዎችና የዩቶፒያ ክለብ አባላት፤ በቢዝነስና በስራ ፈጠራ መስክ ለስኬት በማነሳሳት የሚታወቁ ሰዎችን በመጋበዝ አነቃቂ ፕሮግራም አዘጋጁ፡፡ ለአርብ መጋቢት 28 ልዩ ዝግጅት የተመረጠው ቦታ የዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሲሆን፣ ከዩኒቨርሲቲው አመራሮች በተጨማሪ የ“ባለራዕይ ቶክሾው” ባለቤት ዶ/ር ኢ/ር ሳሙኤል ዘሚካኤል እና ዶ/ር ወረታው በዛብህ እንዲሁም የሰንሻይን ኮንስትራክሽን ባለቤት አቶ ሳሙኤል ታፈሰ በእንግድነት ተጋብዘዋል፡፡ ውጤታማው የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ አቶ ሰውነት ቢሻው እንዲሁም ታዋቂ አርቲስቶች ግሩም ኤርሚያስ እና ሰለሞን ቦጋለ እንደተጋበዙም አዘጋጆቹ ገልፀው፤ ተማሪዎችን ለቢዝነስና ለስራ ፈጠራ በማነሳሳት መልካም ስነ-ምግባርን የሚያላብስ ዝግጅት ነው ብለዋል፡፡

በአንተነህ ግርማ ተፅፎ በኪሩቤል አስፋው ዳይሬክት የተደረገው ‹‹ፍቅር ሲመነዘር›› ፊልም ነገ በ11ሰዓት በሀርመኒ ሆቴል በቀይ ምንጣፍ ሥነ ሥርዓት ይመረቃል፡፡ የ1ሰዓት ከ42 ደቂቃ ርዝመት ያለው ‹‹ፍቅር ሲመነዘር››፤ ሮማንስ ኮሚዲ ፊልም ሲሆን፤ በነገው ዕለት በኤድናሞልና በሀርመኒ ሆቴል እንደሚመረቅ ካም ግሎባል ፒክቸርስ አስታውቋል፡፡ ኩባንያው ‹‹አማላዩ››፣ ‹‹ስውሩ ሰይፍ››፣ ‹‹በራሪ ልቦች››፣ ‹‹ሼፉ››፣ ‹‹ወደ ገደለው›› እና ‹‹አማረኝ›› የተባሉ ፊልሞችን ሰርቶ ለእይታ ማቅረቡ ይታወሳል፡፡

መርሴ ሐዘን ወ/ቂርቆስ “ትዝታዬ፤ ስለ ራሴ የማስታውሰው (1891-1923) በሚል ርዕስ የህይወት ታሪካቸውን የተረኩበት መጽሐፍ ላይ ነገ ውይይት ይካሄዳል፡፡ በብሔራዊ ቤተ-መጻሕፍትና ቤተ-መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ፣ ከቀኑ 8 ሰዓት አንባቢዎች እንዲገኙለት የግብዣ ጥሪውን ያስተላለፈው ሚዩዚክ ሜይዴይ፤ የውይይት መነሻ ሃሳብ በአቶ መኮንን ተገኝ እንደሚቀርብ ገልጿል፡፡”

በኤርትራዊው ሠዓሊ ሰለሞን ኣብርሓ የተዘጋጁ ሥዕሎች የሚቀርቡበት ያልታ የ“ዕይታ” የሥዕል አውደርዕይ ባለፈው ማክሰኞ በጣልያን የባህል ማዕከል የተከፈተ ሲሆን በነገው ዕለት እምደሚዘጋም ታውቋል፡፡ በኤርትራዊው ስደተኛ የተሳሉ በርካታ ሥእሎች የተካተቱበት አውደርዕይ ዓላማ “የኢትዮጵያ እና ኤርትራ ህዝቦችን በማቀራረብ ወደ አንድነት ለማምጣት የበኩሌን አስተዋፅኦ ለማበርከት ነው” ብሏል፤ ሰዓሊው፡፡ሠዓሊው ካሁን ቀደም በኤርትራ የደቀመሃሪ መንደፍራ እና ሳዋ ከተሞች ሽልማት ባስገኙለት የሥዕል ትርኢቶች አውደርዕዮች ለይ መሳተፉን ለማወቅ  ተችሏል፡፡

Monday, 07 April 2014 15:56

ህልመኛው ክንፈኛ

ከትከሻዬ ጫፍ ግራና ቀኝ ካለው፣
ጉቶ የመሳሰለ ብቅ ያለ መሰለኝ፣
ይኸ እንግዳ ነገር እጅጉን ገረመኝ፡፡
የህልም ነገር ሆኖ መች አድሮ መች ውሎ፣
አየሁታ ወዲያው ጉቶው ክንፍ አብቅሎ፡፡
ወደፊት ወድሬ ሁለቱን እጆቼ፣
እግሬን ወደ መሬት ወደታች ዘርግቼ፣
በእነዚህ ረጃጅም ሰፋፊ ክንፎቼ፣
ከፍ ከፍ ወደ ላይ፣
ወዲያ ወደ ሰማይ!
አየሩን ቀዝፌ፣
ሄድሁ ተንሳፍፌ፡፡
ዕድሜዬን በሙሉ መሬት ተጣብቄ፣
አንድ ሜትር እንኳ ከፍ ያላልሁ ርቄ፣
ይኸው አየሩ ላይ ቀጨሁት ዓለምን፣
ያከራርመውና ዕድሜ ይስጥልኝ ህልሜን፡፡
እያደር ግን ኋላ ስካነው መብረሩን፣
ልክ እንደ ጭልፊቷ ሽው እልም ማለቱን፣
ጅው ብዬ ወርጄ ልክ እንደ የሎሱ፣
ወይ እንደ ድራጎን ያየር ላይ ንጉሱ(ሡ)፣
ይመስለኛል ያሰብሁ ልመካ በክንፌ፣
ያሻኝኝ ለመውሰድ ከመሬት ጠልፌ፡፡
አንዳንዱን ክፉ ሰው ላጥ አደርገውና፣
አንጠልጥዬ ወደ ላይ ርቄ እወስደውና፣
እንደ ሥራው መጠን ከድንጋይ ዓለቱ፣
ከጥልቅ ውቅያኖስ አልያም ከጅረቱ፣
ለቅቄ ስተወው ላይመለስ ከቶ፣
እረካለሁ መሰል ሳየው ሲቀር ሞቶ፡፡
ደግሞም ሆዳሙን ሰው ብድግ አደርግና፣
ፊቱን ወደ መሬት ዘቅዝቄ አይና፣
እጥለው መስሎኛል ጭው ካለው መሬት፣
አራዊት አምባ ምድር ሰው ከማይኖርበት፡፡
ይኸ ባለጌውን አለብላቢት ምላስ፣
የባጡን የቆጡን ቀባጥሮ የሚላላስ፣
ሳያስበው ድንገት ሁለት እጁን ይዤ፣
ከሰዎች መካከል ይህን ሰው መዝዤ፣
ወደ ላይ ወስጄው እዚያ ላይ አምጥቄ፣
ያዝ ለቀቅ አድርጌው ነፍሱን አስጨንቄ፣
ለቅቄ ስተወው ከላይ ደመናው ጥግ፣
ወደ ታች ወረደ ሄደ ሲምዘገዘግ፡፡
የሞተ መሰለኝ ምላሱን ጎልጉሎ፣
ብረት ምሰሶ ላይ በልቡ ተተክሎ፡፡
ሃይ የሚል የሌለው ከልካይም ተቆጪ፣
እኔው ራሴ ሆኜ ፈራጅ ዳኛ ቀጪ፣
ክንፎቼ እንዳይረግፉ እየለመንሁ ዕድሜ፣
እየቀጣሁ አለሁ ባለጌውን በህልሜ፡፡
ደግሞስ ማን ደርሶብኝ እንዴት ተነክቼ፣
ሽው ነው ወደ ላይ እብስ በክንፎቼ፡፡
ይህን ህልም እያየሁ ሳልነሳ ካልጋ፣
ሌቱ በረዘመ ጨርሶ ባልነጋ፡፡
ምን እንደ ህልም አለ፣ ከቶ ሌላ የለም፤
ህልመኛው ክንፈኛ አድራጊ ፈጣሪ …
        የሆነበት ዓለም፡፡
ይዘቱም መጠኑም የተስተካከለ፣
እንደዚህ እንደኔው ያለመ ሰው ካለ፣
ወደኔ ብቅ በሉ ሰማችሁኝ ሰዎች?
በጉዳዩ እናውራ የሌት አላሚዎች፡፡
በዝርዝር እንንገር ይህንን ሁኔታ፣
ምስጢሩን ገላልጦ ህልም ለሚፈታ፡፡
    ከአምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
የካቲት 2006 ዓ.ም