Administrator

Administrator

         ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ በስፖርቱ ላይ አዎንታዊም አሉታዊም ሚና ይኖራቸዋል፡፡ የተሻለ ለውጥ ወይም የባሰውን ውድቀት ይፈጥራሉ፡፡ በዓለም ዙርያ በርካታ ስፖርት አፍቃሪዎች እግር ኳስ በቀላል እና ተፈጥሯዊ ባህርያቱ እንዲቀጥል ቢፈልጉም፤ የስፖርቱ ባለሙያዎች በሳይንስ እና ቴክኖሎጂ መታጀቡ የእድገት መገለጫ ነው ብለው ይከራከራሉ፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ የሚሰሩ በርካታ አሰልጣኞችና የእግር ኳስ ባለሙያዎች በዘንድሮው በዓለም ዋንጫው ተግባራዊ ለሆኑ ቴክኖሎጂዎች ጠቀሜታ ድጋፋቸውን እንደገለፁ፣ የሊግ አሰልጣኞች ማህበር በቅርቡ የሰራው ጥናት አረጋግጧል፡፡ በጥናቱ እንደተገለፀው ለዳኞች ውድድር የመምራት ብቃትን ለማሳደግ ተግባራዊ የሆኑት ቴክኖሎጂዎች በ20 አገራት የሚገኙ በተለይም በአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች የሚሰሩ አሰልጣኞች በእግር ኳስ ስፖርት የቴክኖሎጂ ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል 93 በመቶው ድጋፍ ሰጥተዋል፡፡

በክሪኬት፤ በራግቢ እና በሜዳ ቴኒስ የስፖርት ውድድሮች ተግባራዊ የሆኑት የዳኞችን ውሳኔ አሰጣጥ የሚደግፉ ቴክኖሎጂዎች በእግር ኳስ መስፋፋታቸው ተፈላጊ ቢሆንም፣ አንዳንዶች ሳይንስና ቴክኖሎጂ የስፖርቱን መሰረታዊ ተፈጥሮ እያደበዘዘው እንዳይቀጥል ስጋት አለን ይላሉ፡፡ ጎል ላይን፣ ውሃ እና ‹ቫኒሺንግ ስፕሬይ› ቫኒሺንግ ስፕሬይ አሁን የኢንተርኔት ቴክኖሊጂ በስፖርቱ ላይ አዎንታዊ ሚና የሚኖራቸውንና የተሻለ ለውጥ በመፍጠር ለእድገት ምክንያት የሆኑ አገልግሎቶቹን እየሰጠ ይገኛል፡፡ የስፖርቱን አሃዞች አቀናብሮ በማከማቸትና በተለያያ ስሌት መረጃ እንዲሆኑ በማስቻል የኮምፒውተር ቴክኖሎጂዎች የላቀ አስተዋፅኦ እየፈጠሩ ናቸው፡፡ እያንዳንዱን ጨዋታ በዋዜማው እና ባለቀ ማግስት ለመተንተን፤ በአሃዛዊ ቁጥሮች ለማነፃፀር፤ ለመለካትእና ለማስላት ተግባራዊ የሆኑት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂዎች ዓለም ዋንጫውን ከመቼውም የላቀ አድርገውታል፡፡ የዓለም ዋንጫው የፍፃሜ ጨዋታ 360 ዲግሪ በሚሽከረከር እና ከፍተኛ የማጉላት እና የጥራት ደረጃ ባለው አልትራ ኤችዲ ኦምኒካም ካሜራ መቀረፁ ትልቅ ስኬት ተብሏል፡፡

ይህን ዘመናዊ የካሜራ ቴክኖሎጂ ያቀረበቡት የበርሊን ዩኒቨርስቲ ሳይንቲስቶች ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ሶኒ ኩባንያ ከፊፋ ጋር በመተባበር በመላው ዓለም የሚሰራጩት ምስሎች በ4ሺ ፒክስልስ የጎላ ጥራት እንዲኖራቸው አድርጎ ተሳክቶለታል፡፡ በእያንዳንዱ የዓለም ዋንጫ በቀረፃ ላይ የሚሰማሩት 34 ግዙፍ ካሜራዎች ከ5ሺ ሰዓታት በላይ ሰርተዋል፡፡ የግብ ማረጋገጫ ቴክኖሎጂውን አስፈላጊነት ፈረንሳይ 3ለ0 ኢኳዶርን ባሸነፈችበት የ20ኛው ዓለም ዋንጫ የምድብ ጨዋታ ማጋጠሙ ይታወሳል፡፡ በዚሁ ቴክኖሎጂ አፈፃፀም ላይ መላው ዓለም የታዘበው የቴክኖሎጂውን ወሳኝ ጠቀሜታ ነበር፡፡ የጎል ላይ ቴክኖሎጂን መላው ዓለም ተቀብሎታል፡- የእግር ኳስን ተፈጥሯዊ ባህርይ ሊበርዝ ይችላል የሚል ስጋት ቢኖርም፡፡ የእግር ኳስ ደጋፊዎች ዳኞች በሚሰሯቸው ስህተቶች እና ጥፋቶች መወዛገብ ለሽንፈታቸው ምክንያት መደርደራቸውን የስፖርቱን ድባብ እና ተፈጥሯዊ ባህርይ ይገልፃል በሚል በቴክኖሎጂ እንዲቀር መደረጉን ይነቅፉታል፡፡

የጎል ላይን ቴክኖሎጂ በሚቀጥሉት ዓለም ዋንጫዎች በፍፁም ቅጣት ክልል ውስጥ በሚፈፀሙ ጥፋቶች ላይ ዳኞች ሳይታለሉ የኢሊጎሬ ውሳኔ እንዲሰጡ ለማድረግ ተግባራዊ እንዲሆን ጥሪ ያቀረቡም ነበሩ፡፡ በኳስ ግጥሚያ ላይ የቴክኖሎጂዎች ትግበራ የጨዋታውን የተሟሟቀ ሂደት፤ የፉክክር ደረጃ እና ግለት የሚያበርዱ እና የሚያስተጓጉሉ ከሆኑ ቢቀር ይሻላል በሚል የተሟገቱም አሉ፡፡ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ከባዱን ሙቀት ለመከላከል ተጨዋቾች በመሃል ግጥሚያ ላይ አቋርጠው ውሃ እንዲጠጡ የሚያስገድድ ሳይንስ ነበር፡፡ ይህ ተግባር ግን ከጥቅሙ ጉዳቱ እንደሚያመዝን ማስረጃ በመጥቀስ የተቃወሙት ጥቂት አይደሉም፡፡ በቅጣት ምት ላይ ተጨዋቾች የሚሰሩትን የመከላከያ ግድግዳ ለማስመር ዳኞች መገልገል የጀመሩት ቫኒሺንግ ስፕሬይም ብዙም ጠቀሜታው ያልጎላ ነው፡፡ ይህ ቴክኖሎጂ በሜዳ ላይ የጨዋታን ግለት የሚያበርድ ከመሆኑም በላይ በዳኛው ላይ አላግባብ ጥቃት እንዲፈፀም የሚያግዝ መሳርያ ነው በሚልም ነቅፈውታል፡፡ ይሁንና ቫኒሺንግ ስፕሬይ ቅጣት ምቶች ያለአንዳች ግርግር እንዲመቱ ሁኔታዎችን በማመቻቸቱ የሚያደንቁት አልጠፉም፡፡ ቴክኖሎጂ - ከ‹ማልያ› እስከ ‹ታኬታ› በዓለም ዋንጫው ማልያዎች፤ ሙሉ የስፖርት ትጥቆች የመጫወቻ ታኬታዎች አቅራቢ የሆኑት ሶስቱ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች አዲዳስ፣ ናይኪና ፑማ ዘንድሮ ለየብሄራዊ ቡድኖቹ ያቀረቧቸው ማልያዎች በከፍተኛ ቴክኖሎጂ የተመረቱ ናቸው፡፡

ማልያዎቹ ለከፍተኛ ደረጃ በበለፀጉ እና ሪሳይክልድ በሚሆኑ ‹‹ፖሊቲክ ፋይበርስ›› የተሰሩ፤ ተለብሰው የማያስጨንቁ፤ አየር ማስገቢያ ያላቸው፣ እንደ ቆዳ ልጥፍ ያሉ እና ቅለት ያላቸው፣ ጡንቻዎችን እንደተፈለገ ለማዘዝ የተመቹ፣ ከልክ ያለፈ ሙቀትን ለመከላከል የሚያስችሉ ናቸው፡፡ እነዚህ ብቃቶቻቸው በከፍተኛ ሳይንሳዊ ምርምርና ቴክኖሎጂ የተዘሰራላቸው ናቸው፡፡ዓለም አቀፍ የትጥቅ አቅራቢ ኩባንያዎቹ ለዓለም ዋንጫው ያቀረቧቸው ማልያዎች ርጥበት እና ላብ የሚችሉ፤ ለአተነፋፈስ የማያስቸግሩ፤ ክብደት የሌላቸው እና እንደልብ ተቀላጥፎ ለመጫወት የሚመቹ ናቸው፡፡ ናይኪ በአልባሳት የስፖርት ትጥቆቹ በርካታ የባዮ ሜካኒካል ምርምሮችን አድርጓል፡፡ አዲዳስ ደግሞ ባቀረባቸው የብሄራዊ ቡድን ማልያዎች የተጨዋቾች ስም፤ መለያቁጥር እና ልዩ ልዩ አርማዎች ከመለጠፍ ይልቅ፣ ከማልያው ጋር ተዋህደው እንዲሰሩ አድርጓል፡፡ የመጫወቻ ታኬታዎችም በቴክኖሎጂ ረቀቅ ብለው በመሰራታቸው በተለያዩ ደማቅና ሳቢ ቀለማት በጥናት እና በምክንያት ተመርተው አሽብርቀዋል፡፡ አንዳንዶቹ በክብደታቸው ቀለል ተደርገዋል፡፡

አንዳንዶቹ እንደቡትስ በቁርጭምጭሚት ላይ ሊደርስ የሚችልን ጉዳት የሚከላከል ተቀጥሎባቸዋል፡፡ በዓለም ዋንጫው በተሳተፉ 32 ብሄራዊ ቡድኖች እስከ ስምንት ትጥቅ አቅራቢዎች ቢኖሩም በቴክኖሎጂያቸው ተራቅቀው እና ገበያውን ተቆጣጥረው ያሉት ዋናዎቹ አዲዳስ እና ናይኪ ናቸው፡፡ ፑማ በቅርበት ይከተላቸዋል፡፡ ሁለቱ ኩባንያዎች ገበያውን ለመቆጣጠር የሚያደርጉት ትንቅንቅ በቴክኖሎጂ የተሻለ ሆኖ መገኘትን በማቀድ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ደግሞ በእግር ኳሱ ላይ በየዓለም ዋንጫው አዳዲስ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂን በማፈራረቅ ተፅእኖ መፍጠሩ የማይቀር ይመስላል፡፡ ብራዙካ የተባለችው የአዲዳስ ኳስ ውድድሩ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ምንም አይነት ቅሬታ ስላልቀረበባትም አዲዳስን ገበያውን እንዲቆጣጠር ያስችለዋል፡፡ አዲዜሮ ኤፍ50 የተባለው የአዲዳስ ታኬታ ባደረጉ ተጨዋቾች በዓለም ዋንጫው ከገቡት 171 ጎሎች 41 በመቆጠራቸውም የምርቱን ስኬታማነት መለኪያ ሆኗል፡፡ በናይኪ ሜርኩርያል ቡት የተመዘገቡት 35 ጎሎች ናቸው፡፡ አዲዳስ ብራንድ የሆኑ ታኬታዎች 74 የናይኪ ብራንድ የሆኑ ታኬታዎች 73 ጎሎች ተቆጥሮባቸዋል፡፡ በሁለቱ ኩባንያዎች የቀረቡ ታኬታዎች በአንፀባራቂ እና ደማቅ ቀለማት መሰራታቸው ጠቃሚ ነው በሚል ኮሜንታተሮች አመስግነዋል፡፡ የታኬታዎቹ ቀለማት የተጨዋቾችን ማንነት ለመለየት ያግዛል በሚል ተደንቋል፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጭዎች ታኬታዎቹ ቡትስ መምሰላቸውን ያልወደዱት ሲሆን ከቦክስ ጓንቲዎች ጋር አመሳስለዋቸዋል፡፡

         አንዳንድ ዘገባዎች በሚቀጥሉት 20 ዓመታት በዓለም እግር ኳስ ስፖርት የሮቦት ዳኞች እና የሮቦት ተጨዋቾች ማሰለፍ የሚቻልበት የስልጣኔ ደረጃ ይመጣል ይላሉ፡፡ ምናልባትም የቴክኖሎጂ ድጋፍ አስፈላጊነቱ ከታመነበት ፊፋ የተርመጠመጠበትን የሙስና ችግር የሚያጋልጥ ቴክኖሎጂ ቢፈለሰፍ ብለው የማጣጣያ ትችት ያቀረቡ መረጃዎች፤ በሚቀጥሉት ሃምሳ ዓመታት ዓለም ዋንጫ በጨረቃ ላይ ሊስተናገድ ይችላል ብለው አሹፈዋል፡፡ኤችቲቢ ኤንድ ፊልቸር ቦነስ የተባለ ተቋም የዓለማችን የእግር ኳስ ስፖርት የወደፊት አቅጣጫዎች ብሎ በሰራው ምርምር ይፋ እንዳደረገው በሚቀጥሉት 50 ዓመታት ስፖርቱ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ከፍተኛ ለውጦች ማሳየቱ የማይቀር ይመስላል፡፡ ብዙዎቹ ቴክኖሎጂዎች እስከ 2022 እ.ኤ.አ ተግባራዊ ሊሆኑ እንደሚችሉም ድምዳሜ ላይ ደርሷል፡፡

እንደተቋሙ ሪፖርት ከሆነ በሚቀጥሉት 15 ዓመታት በእግር ስፖርት በተጨዋቾች ማልያ ላይ ማንኛውንም እንቅስቃሴ ለመቅረጽ የሚችሉ በዓይን የማይታዩ ካሜራዎች ይለጠፋሉ፤ የመጫወቻ ታኬታዎች ኳስን ለመቆጣጠር መጥኖ ለመምታትና አቅጣጫ ለመገመት የሚያስችሉ ይሆናል፤ የውድድር ዳኞች ማናቸውን የጨዋታ እንቅስቃሴ ለመበታተን እንዳይገባቸው ልዩ የካሜራ ሄልሜት ሊገጠምላቸውም ይችላል፡፡ ከስምንት ዓመታት በኋላ ኳታር በምታስተናግደው 22ኛው ዓለም ዋንጫ ዙርያ ከተነሱ አከራካሪ ጉዳዮች ዋንኛው የአገሪቱ ሙቀት ለውድድሩ አይመችም የሚለው ነው፡፡ የኳታር ዓለም ዋንጫ አዘጋጆች ግን ይህ ችግር በቴክኖሎጂ የሚፈታ ነው ብለው ተከራክረዋል፡፡

እስከ 45 ዲግሪ ሴንቲግሬድ የሚደርሰው የኳታር ሙቀት በስታድዬሞች በሚገጣጠሙ እና በሚሰሩ የማቀዝቀዣ ምሰሶዎች ለእግር ኳስ ጨዋታ የተመቹ እናደርጋቸዋለን በሚል ከወዲሁ ቃል ገብተዋል፡፡ ሰሞኑንም እስከ 7.4 ሚሊዮን ዶላር የወጣበትን የማቀዝቀዣ ቴክኖሎጂን የፈተሹበት የሙከራ ተግባራትን አከናውነዋል፡፡ በርካታ ተመራማሪዎች እና ሳይንቲስቶች እግር ኳስ ከቴክኖሎጂ ጋር ተሳስሮ መቀጠሉን በመደገፍ የተለያዩ አዳዲስ ሃሳቦችን በማፍለቅ ላይ ናቸው፡፡ በሚቀጥሉት ዓለም ዋንጫዎች ተግባራዊ ቢሆኑ ተብለው ሃሳብ ከተሰጠባቸው የቴክኖሎጂ ግኝቶች የመጀመርያው ኦፍሳይድ እና ኦንሳይድ የሆኑ ኳሶችን ለመለየት እንደ ግብ ማረጋገጫ ቴክኖሎጂ አዲስ አሰራር መፈልሰፉን የጠየቁ ናቸው፡፡ ሌላው ተጨዋቾች በተጋጣሚያቸው ፋውል ሲሰራባቸው በትክክል መሰራረቱን ወይም ለማታለል መወደቁን ለማረጋገጥ የሚያስችል መሳርያም ቢኖር ተመኝተዋል፡፡ በራግቢ እና በአሜሪካን ፉትቦል ተግባራዊ የተደረገውና የሜዳ ላይ ትዕይንት በቀጥታ ተመልካች በቅርበት እየሰማ እንዲከታተል የታቀደው የቀረፃ ቴክኖሎጂም አለ፡፡ ይህ ቴክኖሎጂ በተጨዋቾች ማልያዎች ላይ በሚለጠፉ ልዩ ካሜራዎች ወይንም ደግሞ በነፍሳት መልክ በሚሰሩ እና ኳስ ጨዋታውን በመካተል በሚቀርፁ ልዩ ካሜራዎች ይህን ተግባር ለማከናወን እንደሚቻልም ይገለፃል፡፡

          በዓለም የወጣቶች የአትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ለመካፈል ወደ አሜሪካ አቅንተው ከነበሩ አትሌቶች መካከል ባለፈው ቅዳሜ ድንገት ከተሰወሩትና ከቀናት ቆይታ በኋላ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ከዋሉት አራት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች መካከል ሁለቱ ከታዋቂዎቹ ‹ናይኪ›ና ‹አዲዳስ› ኩባንያዎች ጋር ስምምነት መፈራረማቸውን ኦሪጎን ላይን ድረገጽ ትናንት ዘገበ። አማኑኤል አበበ፣ ዱሬቲ ኢዳኦ፣ መዓዛ ከበደና ዘይቱና ሞሃመድ የተባሉት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች፣ ባለፈው ቅዳሜ ከልዑካን ቡድኑ ተለይተው መጥፋታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ የኦሪጎን ፖሊስ ትናንት በሰጠው መግለጫ ከጠፉት አትሌቶች መካከል ዘይቱና ሞሃመድ ከናይኪ፣ ዱሪቲ ኢዳኦ ደግሞ ከአዲዳስ ጋር የኮንትራት ስምምነት መፈራረማቸውን ከቡድኑ አሰልጣኞች ማረጋገጡን ገልጿል፡፡ የኦሪጎን ፖሊስ አትሌቶቹ ይህንን ስምምነት የተፈራረሙት ሊጠፉ አንድ ቀን ሲቀራቸው እንደነበር መግለጹን የጠቆመው ዘገባው፣ ጉዳዩን በተመለከተ ሁለቱንም ኩባንያዎች ለማነጋገር ያደረገው ሙከራ አለመሳካቱን ጠቅሷል፡፡ 

        ፖሊስ አትሌቶቹ በአሜሪካ የመቅረት ዕቅድ ይዘው እንደጠፉ ከአሰልጣኞቹ መረጃ እንዳገኘና አትሌት ዱሪቲም የፓስፖርቷን ኮፒ ለአዲዳስ ኩባንያ የኮንትራት ስራ አስኪያጅ ለመላክ እንደምትፈልግ ለአሰልጣኞቿ ጥያቄ ማቅረቧንና አሰልጣኞቹም የቡድኑ አባላት ፓስፖርት የሚገኝበትን ክፍል ቁልፍ እንደሰጧት አረጋግጫለሁ ብሏል፡፡ አሰልጣኞቹ፤ አትሌቶቹ ከጠፉ በኋላ ፓስፖርታቸውን ካስቀመጡበት እንዳጡት ተናግረዋል ያለው ዘገባው፤ ፖሊስ በደረሰው ጥቆማ መሰረት ባከናወነው ቀናትን የፈጀ ፍለጋ አትሌት ዘይቱናን በዋሽንግተን፣ ሌሎቹን ሶስት አትሌቶች ደግሞ ቤቨርተን ውስጥ እንዳገኛቸው አስረድቷል፡፡ አትሌቶቹ በአሜሪካ ለምን ያህል ጊዜ እንደሚቆዩም ሆነ ቀጣይ ዕጣ ፋንታቸው ምን ሊሆን እንደሚችል ፖሊስ ምንም አይነት መረጃ አለመስጠቱን ዘገባው ጠቁሟል፡፡

         በእንግሊዝ መንግስት የገንዘብ ድጋፍ በጋምቤላ ክልል በተከናወነ አስገዳጅ የሰፈራ ፕሮግራም፣ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ደርሶብኝ፣ ለስደት ተዳርጊያለሁ ያሉ አንድ ኢትዮጵያዊ ገበሬ፤ በአገሪቱ ላይ የመሰረቱትን ክስ ያዳመጠው የለንደን ከፍተኛ ፍርድ ቤት፤ እንግሊዝ ለኢትዮጵያ የምትሰጠው እርዳታ የዜጎችን ሰብዓዊ መብቶች ለሚጥሱ ፕሮግራሞች መዋል አለመዋላቸው እንዲጣራ መወሰኑን የኢትዮጵያ መንግስት ተቃወመ፡፡ ብሉምበርግ ኒውስ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፣ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጉዳዩን በተመለከተ ለንደን በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ በኩል በላከው መግለጫ፤ ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን ማስተላለፉ አግባብነት እንደሌለው ገልጾ፣ ክሱ የተመሰረተው ያለምንም ተጨባጭ መረጃና የራሳቸውን ፖለቲካዊ ጥቅም ለማስከበር በሚፈልጉ ሃይሎች አነሳሽነት እንደሆነ ገልጿል፡፡

በክልሉ የተከናወኑ የሰፈራ ፕሮግራሞች በነዋሪዎች ፈቃደኝነት ላይ የተመሰረቱና ማህበራዊ አገልግሎቶችን በማሻሻል የተበታተነ አሰፋፈር ባለባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ማህበረሰቦችን ተጠቃሚ የማድረግ ግባቸውን በማሳካት ረገድም ውጤታማ እንደነበሩ መግለጫው አስታውሷል፡፡ መንግስት ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ በሚያከናውነው በዚህ የሰፈራ ፕሮግራሞች ላይ መሰል ውንጀላዎችና የተዛቡ አመለካከቶች እንዲፈጠሩ ከሚያደርጉ ምክንያቶች አንዱ የሰፈራ ፕሮግራሙን ዓላማ በአግባቡ አለመረዳት ነው ብሏል፡፡ ‘ሂዩማን ራይትስ ዎች’ የተባለው አለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅት በጋምቤላ ክልል የተከናወነው የሰፈራ ፕሮግራም፣ አስገዳጅና በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን ለከፋ ስቃይና የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት የዳረገ ነው ማለቱን የዘገበው ብሉምበርግ ኒውስ፤ ፍርድ ቤቱ ይህን ውሳኔ ማስተላለፉ ይበል የሚያሰኝ ነው ሲል እንዳሞካሸውም ጠቁሟል፡፡

የእንግሊዝ ዓለምአቀፍ የልማት ተቋም በበኩሉ፣ “በጋምቤላ ክልል ብዙ ዜጎችን ያለፍላጎታቸው ከቀያቸው አፈናቅሏል፣ ለእስራት፣ ለድብደባና ለስቃይ ዳርጓል ለተባለው የሰፈራ ፕሮግራም” የገንዘብ እርዳታ እንዳልሰጠ መናገሩን ገልጿል፡፡ ከጋምቤላ ክልል ተፈናቅለው በኬኒያ በስደት የሚገኙ ስማቸው ያልተገለጸ ገበሬ፤ በእንግሊዝ መንግስት ላይ የመሰረቱትን ክስ የተቀበለው የለንደን ከፍተኛ ፍርድ ቤት፤ የእንግሊዝ የእርዳታ ድርጅት ለኢትዮጵያ የሚያደርገው ድጋፍ የአገሪቱን ዜጎች የሰብዓዊ መብቶች በማይጥስ ሁኔታ ጥቅም ላይ ስለመዋሉ ይጣራ ሲል ከሁለት ሳምንታት በፊት መወሰኑን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

       የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለአብራሪዎች የሚሰጠውን ስልጠና ለማሳደግ ሴስና ከተባለው አውሮፕላን አምራች ኩባንያ የገዛቸውን ‘ሴስና 172’ የተሰኙ ሶስት ተጨማሪ የስልጠና አውሮፕላኖች ባለፈው ሳምንት ወደ አገር ውስጥ ማስገባቱን ገለጸ፡፡ አየር መንገዱ ባወጣው መግለጫ፤ በቅርቡ ዲያመንድ ከተሰኘው የኦስትሪያ አውሮፕላን አምራች ኩባንያ 12 አውሮፕላኖችን ገዝቶ ማስገባቱን ጠቁሞ፣ ከሰሞኑ ያስገባቸው አዳዲስ አውሮፕላኖችም አራት መቀመጫዎች ያሏቸውና ባለ አንድ ሞተር እንደሆኑና በአሜሪካና በአውሮፓ ከአስር አመታት በፊት የጥራት ማረጋገጫ አግኝተው በተለያዩ አገራት ለስልጠና አገልግሎት በመዋል ላይ እንደሚገኙ ገልጿል፡፡ የአየር መንገዱን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረ ማርያም በመግለጫው ላይ እንዳሉት፣ አየር መንገዱ እ.ኤ.አ በ2025 እደርስበታለሁ ብሎ ባስቀመጠውና በመተግበር ላይ በሚገኘው ስትራቴጂክ እቅድ ውስጥ ለሰው ሃይል ልማት ትኩረት የሰጠ ሲሆን፣ አውሮፕላኖቹም አየር መንገዱ የሚሰጠውን የአብራሪዎች ስልጠና ዘመናዊና ጥራቱን የጠበቀ ለማድረግ የሚያግዙ ናቸው፡፡

በስትራቴጂክ ዕቅዱ የመጨረሻ አመት በአፍሪካ መሪ የሆነ የአቪየሽን ስልጠና ማዕከል ባለቤት የመሆን ግብ አስቀምጦ በመስራት ላይ የሚገኘው አየር መንገዱ፣ አውሮፕላኖቹ በዘርፉ የሚሰጠውን የስልጠና አቅም እንደሚያሳድጉለት ገልጿል፡፡ አየር መንገዱ ከ80 ሚሊዮን ዶላር በላይ በጀት በመመደብ አካዳሚውን የማስፋፋት ፕሮጀክት በመተግበር ላይ እንደሚገኝ የጠቆመው መግለጫው፤የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአቪየሽን አካዳሚ በአፍሪካ ትልቁ የአቪየሽን ስልጠና ማዕከል መሆኑና በያዝነው የፈረንጆች አመት፣ በአፍሪካ የአየር መንገድ ማህበር ‘የአመቱ አገልግሎት ሰጪ የአቪየሽን አካዳሚ’ ተብሎ መሰየሙንም አስታውሷል፡፡ የስልጠና አካዳሚው ተማሪዎችን የመቀበል አቅም ባለፉት አራት አመታት ከፍተኛ እድገት ማሳየቱንና በአሁኑ ሰአትም አመታዊ የመቀበል አቅሙ ከ1ሺህ በላይ መድረሱን ገልጿል፡፡ በዕቅድ አመቱ መጨረሻ ይህን ቁጥር ከ4ሺህ በላይ ለማድረስ ዕቅድ ይዞ እየሰራ እንደሚገኝም ጠቁሟል፡፡

           በአሜሪካ ዳላስ አካባቢ ከፍተኛ ተወዳጅነት ካላቸውና የተለያዩ አገር ዜጎች አዘውትረው ከሚመገቧቸው የአመቱ 100 ምርጥ የምግብ አይነቶች ውስጥ፣ ክትፎ አንዱ መሆኑን ዳላስ ኦብዘርቨር ድረገጽ ዘገበ፡፡ ዳላስ ኦብዘርቨር በተለያዩ ሬስቶራንቶች በመዘዋወር የሰራውን ጥናት በመጥቀስ፣ከትናንት በስቲያ በድረ-ገጹ እንዳስነበበው፣ ዳላስ ውስጥ በሚገኘው ሼባ የተሰኘ የኢትዮጵያውያን ሬስቶራንት ውስጥ እየተዘጋጀ የሚቀርበው ክትፎ፣ በአመቱ የዳላስ አካባቢ ተወዳጅ 100 የምግብ አይነቶች ዝርዝር ውስጥ የ50ኛ ደረጃን ይዟል፡፡ ከሁሉም የምግብ አይነቶች በቀዳሚነት የተቀመጠው ኦይስተር ተብሎ የሚጠራው የባህር ውስጥ ምግብ ሲሆን፣ በተከታይነት የተቀመጠው ደግሞ፣ በባህላዊ አሰራር የሚዘጋጀው የቱርኮች ሳንዱች ነው፡፡

ቺክን ሺሽ ከባብ የተባለው ከዶሮ ስጋ የሚሰራ ምግብ በሶስተኛነት ተቀምጧል፡፡ ዝርዝሩ በዳላስ አካባቢ የሚኖሩ የስጋም ሆነ የአትክልት ተመጋቢዎች በአመቱ የበለጠ የተመገቧቸውንና ያዘወተሯቸውን የተለያዩ የዓለም አገራት የምግብ አይነቶች የያዘ ሲሆን፣ በዝርዝሩ ውስጥ የተካተቱት ምግቦች የሚገኙባቸውን ሬስቶራንቶች፣ አሰራራቸውን፣ የተለዩ የሚያደርጓቸውን መገለጫዎች ወዘተ ጠቁሟል፡፡ በዘንድሮው የዳላስ ተወዳጅ የምግብ አይነቶች ዝርዝር ውስጥ ከስጋ፣ ከእንቁላል፣ ከአትክልትና ከመሳሰሉት ምግቦች የተካተቱ ሲሆን፣ የአሳና የፓስታ ምግቦችም ተጠቅሰዋል፡፡ የሳንዱችና የበርገር አይነቶችም ከአመቱ ተወዳጅ ምግቦች ተርታ ተሰልፈዋል፡፡

    “የተባረሩት ሙስና መኖሩን በመጠቆማቸው አይደለም”- ድርጅቱ

   በ“የእለት ደራሽ የእርዳታ ትራንስፖርት ድርጅት ሙስና እየተፈፀመ ነው” በሚል ርዕስ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በወጣ ዘገባ ምክንያት የድርጅቱ የህግ አገልግሎት ክልል ኃላፊ፤ ከስራ እንዲሰናበቱ መደረጋቸውን የገለፁ ሲሆን የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ በበኩላቸው፤ ስንብቱ የሙስና ጥቆማ ከማቅረባቸው ጋር የተያያዘ አይደለም ብለዋል፡፡ የእለት ደራሽ የእርዳታ ትራንስፖርት ድርጅት ህግ አገልግሎት ኃላፊ የሆኑት አቶ ያለው አክሊሉ፤ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ከድርጅቱ የስነ-ምግባር መኮንን አቶ ሰማህኝ ተፈሪ እና ከመሰረታዊ ሰራተኛ ማህበሩ ም/ሊቀመንበር ጋር በመሆን በተቋማቸው ከፍተኛ ሙስና እየተፈፀመ መሆኑንና የፌደራል የስነ-ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ጉዳዩን በቸልተኝነት እየተመለከተው መሆኑን መግለፃቸው ይታወሳል፡፡ አቶ ያለው አክሊሉ ሰኔ 30 ቀን 2006 በተፃፈ ደብዳቤ ከስራ በቀጥታ እንዲሰናበቱ መደረጉን ጠቁመው፤ ስነ ምግባር መኮንኑ አቶ ሰማኸን ተፈሪ በተፃፈ ደብዳቤ ለአዲስ አድማስ በሰጡት መግለጫ በድርጅቱ ውስጥ ያለው የኢንዱስትሪ ሰላም አንዲናጋና ሽብር እንዲፈጠር ማድረጋቸው ተገልፆ፤ በ3 ቀን ውስጥ አለኝ የሚሉትን የሰውና የሰነድ ማስረጃ ለድርጅቱ እንዲያቀርቡ፤ ይህ ባይሆን እርምጃ ሊወሰድባቸው እንደሚችል የሚያመለክት ደብዳቤ ደርሷቸዋል፡፡

ባለፉት ሁለት አመታት በድርጅቱ ይፈፀማሉ ያልናቸውን የሙሰና ተግባራት ለህይወታችን ሳንሳሳ ለማጋለጥ ከፍተኛ ጥረት አድረገናል የሚሉት አቶ ያለው፤ “የፀረ- ሙስና ኮሚሽን ጥቆማችንን በቸልታ ስለተመለከተው ጉዳዩን ወደ ሚዲያ ማቅረብ አስፈላጊ ነው ብለን በማመን ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዝርዝር መረጃውን ልንሰጥ ተገድደናል ብለዋል፡፡ ዘገባው በጋዜጣው ከተስተናገደ በኋላ የድርጅቱ ስራ አመራሮች ሠራተኞችን ስብሰባ ጠርተው በዘገባው ላይ ውይይት ማድረጋቸውን የጠቀሱት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ በስብሰባው ላይ የድርጅቱን ስም እንዳጠፋን ተደርጐ በሁለት ቀናት ውስጥ እርምጃ እንደሚወሰድብን ለሠራተኛው ተገልጿል ይላሉ፡፡ ስብሰባው በተካሄደ በሁለተኛው ቀን “የስራ ሪፖርት ሲጠየቁ ስርአት የጐደለው ምላሽ አቅርበዋል” በሚል ምክንያት የስራ ስንብት ደብዳቤ እንዲደርሳቸው መደረጉን አቶ ያለው አስታውቀዋል፡፡ የተሰናበቱበት ምክንያትም ቀደም ሲል ለሠራተኞች ቃል በተገባው መሠረት ሳይሆን ስራ አስኪያጁ “የ5 ወራት የስራ ሪፖርት ይቅረብልኝ” ሲሉ በዘለፋ የታጀበ ያልተገባ ምላሽ ሰጥተሃል፤ በሚል ምክንያት እንደሆነ ያብራሩት አቶ ያለው፤“የተፈፀመብኝን በደል በድርጅቱ የስነምግባር መኮንን በኩል ለፌደራል የስነምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን የምርመራና አቃቤ ህግ ዳይሬክቶሬት ባመለክትም ኮሚሽኑ እስካሁን ምላሽ አልሰጠኝም” ብለዋል፡፡

ቀደም ሲል ለፀረ - ሙስና ኮሚሽን በድርጅቱ ተፈጽመዋል ያልናቸውን 56 አይነት ወንጀሎች በማስረጃ አስደግፈን አቅርበናል ያሉት አቶ ያለው፤ አሁንም ቢሆን ከዚህ ትግል የሚገታኝ የለም ብለዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ ያነጋገርናቸው የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ጀማል መሃመድ በበኩላቸው፤ ግለሰቡ ከስራ እንዲሰናበቱ የተደረገው የ5 ወራት የስራ ሪፖርት በአግባቡ እንዲያቀርቡ ሲጠየቁ፣በዘለፋ የታጀበና ከተጠየቀው ጋር ያልተገናኘ ምላሽ በመስጠታቸው የተወሰደ እርምጃ እንጂ የሙስና ጥቆማ ከማድረጋቸው ጋር የተያያዘ አይደለም ብለዋል፡፡ “ሠራተኛው ስብሰባ ተጠርቶ በዘገባው ላይ ውይይት ተካሂዷል የተባለው፣በወጣው ዘገባ ሠራተኛው ሳይረበሽና ሳይደናገጥ ስራውን እንዲያከናውን መመሪያ ለመስጠት ነው” ሲሉ መልሰዋል - አቶ ጀማል፡፡ የፌደራል የስነ - ምግባርና የፀረ - ሙስና ኮሚሽን የትምህርትና የስልጠና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ብርሃኑ፤“አንድ የሙስና ጠቋሚ ከስራው ከተሰናበተ አሊያም ጥቅማ ጥቅሙን ካጣ፣በኮሚሽኑ ይህ የተደረገበት ምክንያት በሚገባ ከተጣራ በኋላ፣ ወደ ስራው እንዲመለስ አሊያም ያጣውን ጥቅማጥቅም መልሶ እንዲያገኝ ይደረጋል” ካሉ በኋላ “እንዲህ ያለ ጥቃት ደርሶብኛል የሚሉ ግለሰቦች በየድርጅቶቹ ካሉ የስነምግባር መኮንኖች ጋር በመሆን ወደ ኮሚሽኑ መጥተው ቢያመለክቱ ይመረጣል” ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ከ612 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ከአላማጣ - መሆኒ - መቀሌ ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ሃይል ማስተላለፊያ መስመር ሠርቶ አጠናቀቀ፡፡ በየካቲት 2004 ዓ.ም ስራው የተጀመረው የኤሌክትሪክ ማስተላለፊያ መስመር፤ 141 ኪሎ ሜትር የሚረዝም ሲሆን 230 ኪሎ ቮልት ኤሌክትሪክ ይሸከማል፡፡
ሙሉ ለሙሉ ስራው የተጠናቀቀው ይህ ፕሮጀክት፤ ከተከዜ ሃይል ማመንጫ 300 ሜጋ ዋት፣ ከአሽጐዳ ንፋስ ሃይል ማመንጫ 120 ሜጋ ዋት የሚመነጨውን የኤሌክትሪክ ሃይል ያስተላልፋል፡፡
በአምስት አመቱ እድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድና ትግበራ በአጠቃላይ 10ሺህ ሜጋ ዋት ኤሌክትሪክ ለማመንጨት መታቀዱን የጠቆመው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን፤ የህዳሴው ግድብ ከ35 በመቶ በላይ፣ የጊቤ 3 ግድብ ከ86 በመቶ በላይ፣ የገናሌ ዳዋ ከ56 በመቶ በላይ ግንባታቸው መጠናቀቁን ገልጿል፡፡

Wednesday, 30 July 2014 07:56

ሌላው ጦርነት

“ሃሎ?! ኮሎኔል ሙሳ ነኝ! ማን ልበል?”
“ሃሎ! ጓድ ኮሎኔል…ይቅርታ! ከሆቴሉ እንግዳ መቀበያ ክፍል ነው!”
“ለምንድነው ከእንቅልፌ የምትቀሰቅሱኝ?! ለራሴ የበላሁት ምሳ አልፈጭ ብሎኝ መከራዬን ያሳየኛል! ከጓድ ሊቀመንበሩ ቢሮ በስተቀር ከየትም ቢደወል እንዳትቀሰቅሱኝ አላልኩም?!”
“ይቅርታ ጓድ ኮሎኔል! አንዲት ባልቴት እዚህ ሆቴሉ በር ላይ ቆመዋል…እናቱ ነኝ ይላሉ!”
“የማን እናት?”
“የእርስዎ መሰለኝ…በጦርነቱ ተፈናቅዬ ከምስራቅ ጦር ግንባር ነው የመጣሁት ይላሉ ጓድ ጌታዬ!”
“ለመሆኑ ማን እባላለሁ አለች?”
“በላይነሽ እባላለሁ ይላሉ ጓድ ኮሎኔል! የእርስዎ ወላጅ እናት ነኝ ይላሉ…”
“ልትሆን ትችላለች…ማነው ያለሁበትን ያሳያት ግን? እኔ እናት አገርና አብዮት እንጂ ሌላ እናት አላውቅም!”
“ምን ልበላቸው ታዲያ ጓድ ኮሎኔል?”
“በቃ አላውቃትም አልኳችሁኮ! እናቴ ብትሆን ባትሆንም ግድ የለኝም! ማነው ግን ያለሁበትን ቦታ ያሳያት? ይሄ የአናርኪስቶች ሴራ መሆን አለበት!”
“ማን እንዳሳያቸው አይታወቅም ጓድ ኮሎኔል!”
“አስር ብር ስጧትና እንደዚህ የሚባል ሰው እዚህ የለም ብላችሁ ሸኟት! ይልቁኑ ያቺን የማታዋን ቆንጅዬ ልጅ የሆቴል ታክሲ ልካችሁ አሁኑኑ አስመጡልኝ! እዚህ ሌላ ጦርነት ውስጥ ነው ያለሁት! ይገባችኋል?”
“ይገባናል ጓድ ኮሎኔል! በደንብ ይገባናል!”
“አልገባ ካላችሁ ደግሞ መጥቼ በሚገባችሁ ቋንቋ አነጋግራችኋለሁ!! አናርኪስት ሁላ! ልክ ነው የማስገባሽ!”
“ይገባናል ጓድ ኮሎኔል! ልጅቷን አሁኑኑ እናስመጣታለን!”
“በጓድ ሊቀመንበርና በአብዮቱ ቀልድ የለም! ይገባችኋል?”
“ይገባናል ጓድ ኮሎኔል! በደንብ ይገባናል!”
(ከደራሲ ሙሉጌታ ጉደታ “ያልተሸነፈው”
የአጭር ልብወለድ መድበል የተወሰደ፡፡
ሰኔ 2006 ዓ.ም)

Wednesday, 30 July 2014 07:54

ብረር ብረር አለኝ

       ናፍቆት ደጋግማ ስትመጣ ደጋግሜ የለም አስባልኩ፡፡ ጋሎይስን ለሦስተኛ ጊዜ ማንበቤ ነው። አንዳንዴ መንገዱ መንገዴ ይመስለኛል፡፡ ሌላ ጊዜ በእልሁ ከእኔ ይልቅ አሰፋ ጢሪሪን ወይም ንዳዴን መስሎ ይታየኛል፡፡
መኝታ ክፍሌ ተዘግቶ ማንበብ ስለሰለቸኝ ወጥቼ ካክስቴ ቤት ሥር የቱሪማንቱሪ ቅጠል አንጥፌ ተቀመጥኩ፡፡ መጽሐፉ የተዘጋጀው ለመኝታ ቤት ውስጥ ይመስላል፡፡ ሌላ ቦታ ለማንበብ አይመችም። በደረት አልጋ ላይ ተንበልብሎ በግራ በኩል መጽሐፉን፣ በቀኝ በኩል መዝገበ ቃላቱን አድርጐ በብዙ ማስታወሻ ወረቀቶች ተከብቦ ሲነበብ የበለጠ ይገባል፡፡ ግን ሰለቸኝ፡፡
ልዑል መውደቂያ ዘወትር ጭር እንዳለች ነው። አሁን ግን አንድ ናዝሬት ሚሽን የሚማር ልጅ ለክረምት ዕረፍት ወላጆቹ ጋ መጥቶ ይረብሻታል። ግራር ላይ ወይም የቱሪማንቱሪ ጫፍ ላይ ወጥቶ የተለያዩ ዘፈኖችን በረጅሙ ይለቅቃል፡፡ አሁንም አለ። የት እንደሆነ ግን ላየው አልቻልኩም፡፡ ዘፈኑ ብቻ እየመጣ ከጆሮዬ ጋር ይላጋል፡፡
“ልቤ ቢቀርበት ምነው
ልቤ ቢቀርበት ምነው
ምኞት እኮ ህልም ነው፡፡”
አባቴ በልጅነቱ ይኼን ልጅ ሳይሆን አይቀርም ስል አሰብኩ፡፡ ዘፈኑን ማስታወስ ከማልፈልገው አባቴ መንጭቄ የምጥልበት ስፈልግ ጋሽ በረደድ ትዝ አሉኝ። አክስቴ ላይ ያላቸው ምኞት ህልም እንደሆነ ከዚህ ዘፈን ሊማሩ ይገባቸዋል፡፡ መኖሪያቸው ከአክስቴ ቤት መደዳ ጫፍ ላይ ነው፡፡ ቤታቸው በእኛ ቤት ላይ ምኞት ያለው ይመስል ከሰልፉ አፈንግጦ በመቆልመም በአንድ ዓይኑ ወደዚህ ይመለከታል፡፡ የጋሽ በረደድ ሚስት አጐንብሰው ወጥተው አጐንብሰው ይገባሉ፡፡ ኅይለኛ ናቸው፡፡ የባላቸው ማጋጣነት ወሬ ሲደርሳቸው፣ ወይም ደስ የማይል አዝማሚያ ባላቸው ላይ ሲመለከቱ ቱግ ይላሉ፡፡ ቱግታቸው ፈር የለቀቀ አይደለም፡፡ የባላቸውን አንቱታን አይዘነጉም፤ ግን ይሳደባሉ፡፡
“አንቱ ሸርሙጣ” ይላሉ በእጃቸው ጭብጥ ጀርባቸውን እየደቁ፡፡ “አንቱ ሸርሙጣ፣ አንቱ ሸርሙጣ፣ አንቱ ሸርሙጣ….”
እኔ ጋሽ በረደድ ላይ እስቃለሁ፡፡ ጋሽ በረደድ አይናደዱም፡፡ ለኔ ምላሽ የሰጡ ሳያስመስሉ፤
“አጤ ቴዎድሮስም የተቸነፉ በሚስታቸው ነው፡፡ ለሚስት መቸነፍ የጀግና ወጉ ነው…ምናምን” ይላሉ፡፡
የልዑል መውደቂያ አባወራዎች ጥቂት ናቸው። ግማሽ ክብ ቅርጽ ላይ በድጋሚ የሚጠመጠምባት ሌላ የቤት መቀነት አለ፡፡ እያንዳንዱ ቤት ፀሐይ እንዳይገባበት ደጃፉ ላይ ቱሪማንቱሪ ዛፍ ተተክሏል፡፡ የጋሽ ጥበቡ ቤት እነዚህ መደዳ ጫፍ ላይ ከጋሽ በረደድ ቤት አጠገብ ይገኛል፡፡ የጋሽ ጥበቡ ሚስት ሲበዛ ተፀያፊ ናቸው፡፡ ጋሽ ጥበቡ ከዓይጥ አደን ሲመለሱ፤
“እዛው፣ እዛው….” እያሉ ያንቋሽሿቸዋል፡፡ የአይጥ ማስገሪያቸውን ማዶ አስጥለው ሳሙናና ውኃ ያመጡላቸዋል፡፡ እየተነጫነጩ ዕቃ ሳያስነኩ እራሳቸው ያስታጥቧቸዋል፡፡ ይህን ስመለከት ምናልባትም ባልና ሚስቱ አብረው ማዕድ ከቆረሱ ብዙ ዓመታቸው ሳይሆን አይቀርም እላለሁ፡፡
“በኑሮ ላይ ተቸግሮ ሰው ሲጐዳ፣
መልኩን ጥሎት ገሸሽ ይላል እንደባዳ”
ልጁን እንደ ጥንብ አንሳ ከተንሿጠጠ እራሱ ጋር ግራሩ ላይ አየሁት፡፡ ሹል አፉን እየከፈተ ሲታይ የሚዘፍን ሳይሆን የሚያንቋርር ይመስላል፡፡
በዚህ መካከል ከየት እንደመጣች ያላየኋት ናፍቆት ፊቴ ተገተረች፡፡ ያለወትሮው እግሯ ንፁህ ሆኖ አየሁት፡፡ በስሱ ቅባት የተባበሰሰ ቢሆንም የሞዶ እንኩሮአማ አቧራ አላንዣበበበትም፡፡ በአየር ላይ ተንሳፋ ካልመጣች በቀር እንዲህ ንፁህ ሊሆን እንደማይችል የታመነ ነው፡፡ የእግሯ ጣቶች በሽብር ዓይንን እንዲያፈገፍግ ያስገድዳሉ፡፡  
(ከደራሲ ዓለማየሁ ገላጋይ
“የብርሃን ፈለጐች” የተቀነጨበ