Administrator

Administrator

Saturday, 12 July 2014 12:44

የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቅሌት

    መንግስታት ከምንጊዜውም በበለጠ ቅሌት ውስጥ የሚዘፈቁበት ጊዜ አለ ከተባለ በምርጫ ወቅት ነው። የየሀገሮቻቸው ብሄራዊ የምርጫ ጊዜ ሲቃረብ ጀምሮ እስከሚጠናቀቅበት ጊዜ ድረስ መንግስታት የማይሰሩት ቅሌት የለም፡፡ አንዳንዱ መንግስት ያሰጉኛል የሚላቸውን ተፎካካሪዎቹን እዚህ ግባ የማይባል ሰበብ አስባብ በመፍጠር ከያሉበት ለቃቅሞ ወህኒ ያጉራል፡፡
አንዳንዱ መንግስት ደግሞ ተቃዋሚዎቹን ብቻ ሳይሆን ጋዜጠኞችንም ጨምሮ ያስራል፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ግንባር ቀደም ተፎካካሪያቸውን ብቻ ለይተው ከጨዋታ ውጭ የሚያደርግ ኮሚክ የምርጫ ህግ ያወጣሉ፡፡ ለምሳሌ የምያንማር (በርማ) ወታደራዊ ደርግ በ2008 ዓ.ም ያወጣው የምርጫ ህግ፣ የውጪ ሀገር ዜጋ ባል ያላቸው በርማውያን ፖለቲከኞች ለፕሬዚዳንታዊ ምርጫ መወዳደር እንደማይችሉ ይደነግጋል፡፡
ይህ አስቂኝ የምርጫ ህግ ለየትኛው ፖለቲከኛ ተብሎና የትኛውን ፖለቲከኛ ከምርጫ ጨዋታ ውጭ ለማድረግ ታስቦ እንደወጣ በጣም ግልጽ ነው። በሚቀጥለው አመት በምያንማር በሚደረገው ምርጫ ከፍተኛ የማሸነፍ እድል ያላቸው ዝነኛዋ የነፃነትና የመብት ታጋይ ኦንግ ሳን ሱኪ ብቻ ናቸው። እንግሊዛዊ ባል ያላቸው ፖለቲከኛም ከእሳቸው ውጭ ማንም አልነበረም፡፡ እናም የምርጫ ህጉ ታቅዶና በሚገባም ታስቦበት የወጣው፣ ምርጫውን በቀላሉ እንደሚያሸንፉ የታመነውን ኦንግ ሳን ሱኪን ከጨዋታ ውጪ ለማድረግ ነው፡፡
እንደ ፖላንድ አይነት መንግስቶች የሚሰሩት ቅሌት ደግሞ ትንሽ ረቀቅ ያለ ነው፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ የፖላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶናልድ ተስክ፤ በሚቀጥለው አመት በሚደረገው ጠቅላላ ምርጫ ፓርቲያቸው “ሲቪክ “ፕላትፎርም” ፓርቲ ማሸነፍ እንዲችል የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትራቸውን ይጠሩና ከወዲሁ አንድ ነገር እንዲያደርጉ ያዟቸዋል፡፡
ምኒስትሩም በጉዳይ ላይ ካሰቡበት በኋላ አሁን ባለው የፖላንድ የኢኮኖሚ ሁኔታ በሀገሪቱ የወለድ መጠን ላይ መጠነኛ ቅናሽ ማድረግ ከተቻለ፣ ገዢው የሲቪክ ፕላትፎርም ፓርቲ በቀጣዩ ምርጫ የተሻለ ድጋፍ ማግኘት እንደሚችል ይገምታሉ፡፡   
ከዚያም ቀጥ ብለው ወደ ፖላንድ ማዕከላዊ ባንክ ዋና መስሪያ ቤት ያመራሉ፡፡ የባንኩ ገዢ ከሆኑት ከማሪክ ቤልካ ጋር እንደተገናኙም ቀጣዩ ምርጫ ከመካሄዱ በፊት በወለድ መጠኑ ላይ መጠነኛ ቅናሽ በማድረግ ገዢው ፓርቲ በምርጫው እንዲያሸንፍ የበኩላቸውን እገዛ እንዲያደርጉ ጥያቄአቸውን ያቀርቡላቸዋል፡፡
የባንኩ ገዢ ማሪክ ቤልካም በበኩላቸው፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶናልድ ተስክ የገንዘብ ሚኒስትሩን ከስልጣናቸው ካባረሩላቸው የተጠየቁትን እንደሚፈጽሙ ለሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትሩ አረጋገጡላቸው፡፡ የጉዳዩ ዝርዝር ሪፖርት የቀረበላቸው ጠቅላይ ምኒስትር ዶናልድ ተስክም ለአፍታም እንኳ ሳያመነቱ ኢኮኖሚውን በወጉ መምራት ተስኖታል የሚል መናኛ ሰበብ በመፍጠር የገንዘብ ሚኒስትሩን ከስልጣኑ አባረሩ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩና የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትሩ ይህን ሁሉ ነገር የሰሩት በከፍተኛ ጥንቃቄና ምስጢር ነበር፡፡ ሆኖም ግን ባለፈው ሳምንት አንድ ጉድ ወጣ። የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከጠቅላይ ሚኒስትሩና ከማዕከላዊ ባንክ ገዢ ጋር ያደረጉት ንግግር በምስጢር ቴፕ ተቀርፆ ይፋ ወጣ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶናልድ ተስክም ስልጣን እንዲለቁ ተጠየቁ፡፡ እሳቸው ግን ስልጣን መልቀቁን በጄ አላሉም፡፡ ይልቁንም የሀገሪቱን ርዕሰ መንግስት ንግግር በድብቅ መቅዳት ከመፈንቅለ መንግስት የማይተናነስ ወንጀል መሆኑን በመግለፅ ክስ ለመመስረት እንደሚገደዱ አስጠነቀቁ፡፡ የሌባ ዓይነ ደረቅ…ይሏል ይሄ ነው!!

አንደኛው የአለም ጦርነት የተጀመረበትና እንግሊዝ ወደ ጦርነቱ የገባችበት 100ኛ ዓመት፣ በመላው እንግሊዝ መብራት በማጥፋት፣ በጨለማ ውስጥ በሚከናወኑ የተለያዩ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶችና ፌስቲቫሎች እንዲሁም በዌስት ሚንስቴር አቤይ በሚከናወን የሻማ ማብራት ስነ-ስርዓት እንደሚከበር ቢቢሲ ዘገበ፡፡ በመጪው ነሃሴ 4 ሊካሄድ በታሰበው በዚህ ዝግጅት፤ በመላው እንግሊዝ የሚገኙ የመንግስትና የግል ድርጅቶች፣ የግለሰብ መኖሪያ ቤቶች፣ የንግድ ተቋማትና የተለያዩ ኩባንያዎች በዕለቱ ለአንድ ሰዓት ያህል አምፖሎቻቸውን አጥፍተው ሻማ በመለኮስ የጦርነቱን መጀመር እንዲያስታውሱ አዘጋጆቹ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
እንግሊዝ በጀርመን ላይ ጦርነት ያወጀችበትን ይህን ዕለት በአገሪቱ የሚገኙ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች መብራት በማጥፋት እንደሚዘክሩት ተስፋ አለን ያሉት አዘጋጆቹ፣ ይህ ፕሮጀክት በኪነጥበባዊና ባህላዊ ስራዎች የጦርነትን አስከፊነት የመግለጽ ዓላማ ይዞ መነሳቱን ተናግረዋል፡፡
ጦርነቱ በይፋ በታወጀበት ዕለት ዋዜማ፣ የወቅቱ የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ጸሃፊ ሰር ኤድዋርድ ግሬይ “በመላ አውሮፓ የሚገኙ አምፖሎች ሁሉ ሊጠፉ ነው፤ በህይወት ሳለን ዳግም ተመልሰው ሲበሩ ላናያቸው እንችላለን!” በማለት ለህዝቡ መልዕክታቸውን ማስተላለፋቸውን ያስታወሰው የቢቢሲ ዘገባ፣ ከእሳቸው የዘር ሃረግ የተገኙት አንድሪያን ግሬቭስ የተባሉ ግለሰብ ፕሮጀክቱን በተመለከተ ከትናንት በስቲያ መግለጫ መስጠታቸውን ገልጿል፡፡
አንድሪያን ግሬቭስን ጠቅሶ ቢቢሲ እንዳለው፣ የተለያዩ ዝግጅቶችን ባካተተው በዚህ ፕሮጀክት፣ በአለማቀፍ ደረጃ ታዋቂነትን ያተረፉ አራት የተለያዩ አገራት ዝነኛ አርቲስቶች ጦርነቱን የሚያስታውሱ የስዕል፣ የፊልምና የሙዚቃ ስራዎቻቸውን በስኮትላንድ፣ በዌልስ፣ በሰሜን አየርላንድና በእንግሊዝ በሚገኙ የስነጥበብ ጋለሪዎችና ሲኒማ ቤቶች ለእይታ ያቀርባሉ፡፡የእንግሊዝን ፓርላማ ጨምሮ ታላላቅ የእንግሊዝ ተቋማት በዕለቱ ለአንድ ሰዓት ያህል መብራቶቻቸውን እንደሚያጠፉ የገለጸው ዘገባው፣ ቢቢሲን ጨምሮ ታዋቂ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ደግሞ የስቱዲዮዋቸውን ብርሃን እንደሚያደበዝዙ ይጠበቃል ብሏል፡፡

ባለፈው መጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ 239 ሰዎችን አሳፍሮ ከኳላላምፑር በመነሳት ወደ ቤጂንግ በመብረር ላይ እያለ ድንገት የገባበት የጠፋውን የማሌዢያ አየር መንገድ አውሮፕላን ለማግኘት የተጀመረውና ይህ ነው የሚባል የተጨበጠ ውጤት ያልተገኘበት ፍለጋ አስርት አመታትን ሊፈጅ እንደሚችል የኩባንያው አንድ የስራ ሃላፊ መናገራቸውን ዘ ቴሌግራፍ ዘገበ፡፡
የአየር መንገዱ የንግድ እንቅስቃሴ ዳይሬክተር ሃግ ዳንሌቪ ከሳምንታት በፊት ከኢቭኒንግ ስታንዳርድ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ ድንገት በተሰወረው ኤም ኤች 370 ቦይንግ 777 አውሮፕላን ላይ፣ የሆነ የማይገባ ድርጊት ተፈጽሞበታል ብለው እንደሚያስቡና ወደመነሻው ለመመለስ በሚሞክርበት ጊዜም ፈታኝ የሆኑ ነገሮች ተጋርጠውበት ሳይሳካለት እንደቀረ መናገራቸውን ዘገባው አስረድቷል፡፡
አውሮፕላኑ በደቡባዊ የህንድ ውቅያኖስ አካባቢ ሳይወድቅ እንዳልቀረ የገለጹት ዳንሌቪ፣ አወዳደቁ የከፋ ሊሆን እንደሚችልና ውቅያኖሱ ውስጥ ከሚገኙ ተራሮች ጋር ከተጋጨም ስብርባሪው ርቆ ሊሄድና ሊበታተን እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
ከዚህ አንጻርም የአውሮፕላኑን ስብርባሪ ለማግኘት የሚደረገው ጥረት እጅግ ፈታኝ ሆኖ ሊቀጥልና ምናልባትም አስርት አመታትን ሊፈጅ እንደሚችል ገልጸዋል፡፡
አውሮፕላኑ ከጠፋ ከቀናት በኋላ፣ ፍለጋውን በተመለከተ ከአንድ የአገሪቱ ከፍተኛ ሚንስትር ጋር ቃለ መጠይቅ እንዳደረገ ያስታወሰው ዘ ቴሌግራፍ፤ ሚንስትሩ በወቅቱ በሰጡት ምላሽ፤ ፍለጋው ሳምንታትን ግፋ ቢልም ወራትን ብቻ ሊፈጅ እንደሚችል ነግረውኝ ነበር ብሏል፡፡

የጐንደር ዩኒቨርስቲን የ60 አመት ጉዞ የሚዘክር “የስልሳ ገፆች ወግ” የተሰኘ መጽሐፍ ታትሞ ለንባብ በቃ፡፡ በጋዜጠኛ አብርሃም ዘሪሁን የተዘጋጀው መጽሐፉ፤ በሁለት ምዕራፎች የተቀናበረ ሲሆን የመጀመሪያው ምዕራፍ ስለ ጐንደር ዩኒቨርስቲ አመሠራረትና ዛሬ የደረሰበትን ደረጃ ሲተነትን ሁለተኛው ምዕራፍ ለዩኒቨርስቲው እድገት አስተዋጽኦ ያበረከቱ ምሁራንን ይዘክራል፡፡
የመጽሐፉ ዋጋ 100 ብር ሲሆን ገቢው ለዩኒቨርስቲው ይውላል ተብሏል፡፡
በሌላ በኩል፤ በአሸናፊ ውዱ የተፃፈው “ሚስት መሆን” የተሰኘ የወግ መጽሐፍ ከትናንት በስቲያ ሀሙስ ምሽት ሰዓት በራስ ሆቴል ተመርቋል፡፡ በ196 ገፆች የተቀነበበው መጽሐፉ፤ በአንድ ሚስቱን በሞት ያጣ ባልና ከሴት ልጁ ጋር አጉል ድርጊት ውስጥ በገባ አባት ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን ሲሆን በ50 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነትና በፆረና ተጋድሎ እውነተኛ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥነው “የኢትዮ - ኤርትራ ጦርነትና የፆረና ተጋድሎ” የተሰኘ መፅሀፍ በትላንትናው እለት በሂልተን ሆቴል ተመርቋል፡፡ በምክትል አስር አለቃ የማታወርቅ ተገኝ ተፅፎ በዳዕሮ አድቨርታይዚንግ የተዘጋጀው ይህ መፅሀፍ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት የተከሰቱ ተጋድላችን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል ተብሏል፡፡
በምረቃ ሥነስርአቱ ላይ የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት፣ የጦር መኮንኖች፣ የታሪክ ምሁራንና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተው ነበር፡፡  

         በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደተሳለ የተነገረለትና ፓሪስ ውስጥ ከሚገኘው ‘ሚዩዜ ዲ ኢሆሜ’ ሙዚየም እኤአ በ1989 የተሰረቀው የቅዱስ ዮሃንስን ምስል የሚያሳይ ጥንታዊ የኢትዮጵያ ስዕል፣ ከሰሞኑ ዱሮውት በተባለ አጫራች ድርጅት አማካይነት ማይሰን ፒያሳ ውስጥ በተዘጋጀ ጨረታ ለሽያጭ ቀርቦ መገኘቱን ዘ ፊጋሮ የተባለው የአገሪቱ ጋዜጣ ባለፈው ሰኞ ዘግቧል፡፡
እኤአ በ1932 ማርሴል ግሪአውሌ የተባሉ የኢትኖግራፊ ባለሙያ ከዳካር እስከ ጅቡቲ ባደረጉት የጥናት ጉዞ በእጃቸው እንዳስገቡትና አባ አንጦንዮስ በተባለ ደብር ውስጥ እንደነበረ የተነገረለት ይህ ጥንታዊ የኢትዮጵያ ስዕል፣ ወደ ሙዚየሙ ከመግባቱ በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ ለተመልካች የቀረበው ፈረንሳይ ውስጥ በሚገኝ ቤተክርስቲያን ነበር ተብሏል፡፡
ባለሙያው ቤተክርስቲያኑ መሰል ጥንታዊና ውድ ስዕሎችን ለማሰቀመጥ ምቹ አለመሆኑን በመግለጽ ስዕሎቹን በዘይት ቀለም አስመስለው በማሰራት ለመተካትና ዋናውን ቅጂ ለማውጣት እንዲችሉ ያቀረቡት ጥያቄ በአካባቢው የቤተክህነት አስተዳዳሪዎች ፈቃድ ማግኘቱ የተገለጸ ሲሆን፣ በወቅቱ የኢትዮጵያ መንግስት የውጭ ጉዳይ ሚንስትር የስዕሉን ከቤተክርስቲያኑ መውጣት ቢቃወሙም የስልጣን ላይ የነበሩት የፈረንሳይ ንጉስ ግን ድጋፋቸውን ለባለሙያው መስጠታቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
በግለሰቡ እጅ ላይ ለተወሰነ ጊዜ ቆይቶ፣ ፓሪስ ውስጥ ወደሚገኘው ‘ሚዩዜ ዲ ኢሆሜ’ ሙዚየም እንዲገባ የተደረገው  ይህ ስዕል፣ እኤአ በ1989 ከሙዚየሙ የስዕል ስብስቦች መካከል ድንገት እንደተሰወረና ማን እንደሰረቀው ሳይታወቅ ደብዛው ጠፍቶ እንደኖረ ተነግሯል፡፡
ከ25 አመታት በኋላ ታዲያ፣ ጃክ ሜርሲየር የተባሉ በኢትዮጵያ ዙሪያ የተለያዩ ጥናቶችን በመስራት የሚታወቁ ምሁር ናቸው፣ ደብዛው ጠፍቶ የኖረውን ይህን ጥንታዊ ስዕል በጨረታ ሊሸጥ ቀርቦ ባለበት ሁኔታ ሰሞኑን ድንገት ያገኙት፡፡ የእኒህን ምሁር ጥቆማ የተቀበለው ሙዚየሙ አጫራቹን ድርጅት በማግኘት ስለጉዳዩ ያነጋገረ ሲሆን፣ ስዕሉን ለጨረታ ያቀረበችው ነዋሪነቱ በፈረንሳይ የሆነው የታዋቂው ኩባዊ ሰዓሊ ጃኪን ፌረር ባለቤት መሆኗ ታውቋል፡፡
 ሴትዮዋ ስዕሉ ከሙዚየሙ ከጠፋ ከጥቂት አመታት በኋላ ከአንድ ገበያ እንደገዛችው ተናግራለች፡፡ በወቅቱ ስዕሉን ከሙዚየሙ ማን እንደሰረቀውም ሆነ ለእሷ እንደሸጠላት አሁንም ድረስ የተጨበጠ ነገር አልተገኘም፡፡
ስዕሉ ግን ሙዚየሙ ከሴትዮዋ ጋር ባደረገው ስምምነት ሊሸጥ ከቀረበበት ጨረታ እንዲወጣ የተደረገ ሲሆን፣ በቀጣይም ኳይ ብራንሊ ውስጥ በሚገኘው የስዕል ማዕከል ውስጥ ከሚገኙት የሌሎች 11 ቅዱሳን ስዕሎች ጋር እንዲቀላቀል የሚደረግ መሆኑ ተገልጧል፡፡



የጣሊያኗ ቬነስ በአንደኛ ደረጃ ተቀምጣለች


ዩኔስኮ በአለም ቅርስነት ከመዘገባቸው የኢትዮጵያ ቅርሶችና የቱሪስት መስህቦች መካከል የሚጠቀሱት ጥንታዊ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙባት የላሊበላ ከተማ፣ ‘አንድ ሰው በህይወት ዘመኑ ሊያያቸው የሚገባቸው 50 ምርጥ የአለማችን ከተሞች’ በማለት ታዋቂው ሃፊንግተን ፖስት ጋዜጣ ከጠቀሳቸው ከተሞች ተርታ ተመደበች፡፡
ጋዜጣው በቅርቡ ሚኑቢ ዶት ኔት በተባለ ድረገጽ አማካይነት የአለማችን ጎብኝዎች የሚያደንቋቸውን ታላላቅ የቱሪስት መዳረሻዎች እንዲጠቁሙ በማድረግ ባሰባሰበው መረጃ፣ በጎብኝዎቹ ከተመረጡ 50 የአለማችን ከተሞች ዝርዝር ውስጥ ላሊበላ 17ኛ ቦታ ላይ መቀመጧን ታዲያስ መጽሄት በሳምንቱ መጀመሪያ ዘግቧል፡፡
ላሊበላ ከኢትዮጵያ ታላላቅ ቅዱስ ከተሞች አንዷ ናት ያለው ሃፊንግተን ፖስት፣ በውስጧ የያዘቻቸው ጥንታዊ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትም በመላው አለም የሚታወቁ ድንቅ መስህቦች መሆናቸውን ገልጧል፡፡
ከጥንታዊ የአገራት ርዕሰ መዲናዎች፣ እስከ እስያ ዘመናዊ ከተሞች በመላው አለም የተለያዩ ክፍሎች የሚገኙ ከተሞችን ባካተተው በዚህ ዝርዝር ውስጥ ቀዳሚነትን ያገኘችው የጣሊያኗ ቬነስ ናት፡፡ የሚያማምሩ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች፣ ገራሚ አብያተ ክርስቲያናት፣ ማራኪ ቤቶች፣ ምቾት የሚለግሱ መጠጥ ቤቶች ብዙ ብዙ ማራኪ ነገሮች የሞሉባት ቬነስ፣ ከአለም ከተሞች አምሳያ የሌላት ምርጥ ከተማ ናት ብሏታል ጋዜጣው፡፡
የስፔን ነገስታት መናገሻ ውብ ከተማ፣ ጎብኝዎች በብርቱካናማ አበቦች የተዋቡ ጠባብ መንገዶቿን ተከትለው በመጓዝ ማራኪ ጥንታዊ ህንጻዎችን አሻግረው እየቃኙ መንፈሳቸውን የሚያድሱባት አይነግቡና ቀልብ አማላይ ከተማ በማለት ሁለተኛ ደረጃ የሰጣት ደግሞ የስፔኗን ሲቪሊ ነው፡፡
 ኒዮርክ ሲቱን ሶስተኛዋ መታየት ያለባት የአለማችን ቀልብ ገዢ ከተማ ያላት ሃፊንግተን ፖስት፤ የትም ዙሩ የትም፣ እንደ ኒዮርክ ሲቲ መንፈስን ገዝቶ በአድናቆት የሚያፈዝ የኪነጥበብ፣ የባህል፣ የምግብ አሰራርና የንግድ እንቅስቃሴ በአንድ ላይ ተዋህደው የሚገኙባት ከተማ በየትኛውም የአለም ጥግ አታገኙም ብሏል፡፡
የህንዷን ላህሳ በመንፈሳዊ ማዕከልነቷና በማራኪ የተፈጥሮ ገጽታዋ፣ የብራዚሏን ሪዮ ዲ ጄኔሮ በውበቷ፣ የእንግሊዟን ለንደን በምርጥ ሙዚየሞቿና በጎብኝዎች ተመራጭ ከሆኑ የአለማችን ቀዳሚ ከተሞች አንዷ በመሆኗ በተከታታይ እስከ ስድስተኛ ያለውን ቦታ ሰጥቷቸዋል፡፡ የሞሮኮዋ ማራኬች፣ የዮርዳኖሷ ፔትራ፣ የጣሊያኗ ሮምና የህንዷ ቫራናሲም አንድ ሰው በህይወት ዘመኑ ሳለ ሳያያቸው ማለፍ የሌለባቸው ከተሞች ናቸው ተብለዋል፡፡

Saturday, 12 July 2014 12:30

የግጥም ጥግ

ላለ - መጨቆን
ሞት ይቅር ይላሉ…
    ሞት ቢቀር አልወድም
ከድንጋይ ---ቋጥኙ---
    ከሰው ፊት አይከብድም፡፡
ማጣት ክፉ ክፉ፤
ችግር ክፉ ክፉ፤
ተብሎ ይወራል
ከባርነት ቀንበር
ከሬት መች ይመራል፡፡
***
ለ- ጅገና
ተው! ተመለስ በሉት
ተው! ተመለስ በሉት!
ያንን መጥፎ በሬ
ከጠመደ አይፈታም ያገሬ ገበሬ
* * *
ያባቴ ነው ብሎ፤
የናቴ ነው ብሎ፤
ይፋጃል በርበሬ
አባት የሌለው ልጅ፤
እናት የሌለው ልጅ፤
አይሆንም ወይ አውሬ
ለወንድ - አደር
ዓይንሽ የብር ዋጋ
ጥርስሽ የብር ዋጋ
    ወዳጆችሽ በዙ ከስንቱ ልዋጋ?
(ከክፍሌ አቦቸር (ሻምበል)
“አንድ ቀን” የግጥም መድበል፤ 1982፣ የተወሰዱ)

ከወንድወሰን ተሾመ የማህበራዊ ሳይንስና የስነ ልቦና ባለሙያ
 (ከአልታ ምርምር ሥልጠናና ካውንስሊንግ)
ጭንቀት ምንድን ነው?
ጭንቀት የሰውነትን ተፈጥሯዊ ሚዛን የሚያዛባ የአካል፣የአዕምሮና የስሜት ትንኮሳ(stimulus) የሚፈጥረው  ምላሽ፣ ወይም የአንድ ሰው  ፍላጎት (demand) ሊያንቀሳቅሰው ከሚችለው የግልና የማህበራዊ ሃብቶች አቅም በላይ ሆኖ ሲታየው የሚፈጠር ስሜት፣  ወይም ነገሮች ና ሁኔታዎች ከቁጥጥራችን  እንደወጡ ስናስብ የሚፈጠር ስሜት ነው፡፡
መጠኑና ጊዜው ይለያይ እንጂ ጭንቀት የማይነካው ሰው እንደሌላ ይታወቃል፡፡ በአንድ ወቀት በአንድ ኮሌጅ ውስጥ የሳይኮሎጂ ኮርስ ሳስተምር አንድ ተማሪ አንድ ከፍተኛ ባለስልጣንን ጠቅሶ “እንዴት እሳቸው ይጨነቃሉ?” በማለት ሰውየው ከማንኛውም ጭንቀት በየትኛውም ሁኔታና  ጊዜ ነፃ ናቸው ብሎ እንደሚያምን ገልጾ እንደተሟገተ ትዝ ይለኛል፡፡ ሆኖም በየትኛውም የስልጣን እርከን ወይም የሥራ ሃላፊነት ላይ ብንሆን በጥቂቱም ቢሆን በተለያየ ጊዜና ሁኔታ ጭንቀት ወደ እኛ ሊመጣ ይችላል፡፡ የሚወጡ ሳይንሳዊ መረጃዎች ደግሞ ሃላፊነትና ውሳኔ ሰጪነት ሲጨምር ጭንቀት እንደሚጨምር ይጠቁማሉ፡፡ ለዚህም ነው ባለስልጣናት፣ ስራ አሰኪያጆች፣ ዲሬክተሮች፣ ሥራ ሃላፊዎች በጭንቀት መቆጣጠሪያ (stress management strategies) ስልቶች እንዲሰለጥኑ መደረግ ያለበት፡፡ በማንኛውም ደረጃ የሚሰራና ከስራ ውጪም የሆነ ሰው የጭንቀት መቆጣጠሪያ  ስልቶችን መሰልጠኑ፤ማወቁና መተግበሩ የተረጋጋ ህይወት እንዲመራ ይረዳዋል፡፡ ጭንቀት ውሳኔን የማዛባትና ትኩረትን የመቀነስ ሃይል ስላለው የጭንቀት መቆጣጠሪያ ስልቶችን ማወቅና መሰልጠን ይገባቸዋል፡፡
የጭንቀት ምንጮች ምንድን ናቸው?
የጭንቀት ምክኒያቶች በርካታ ናቸው፡፡  ሆኖም  በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች ለይቶ ማየት ይቻላል፡- አካላዊና ስነ ልቦናዊ  ምንጮች፡፡ እነዚህም የሚከተሉትን ሊያጠቃልል ይችላል፡-
በስራ ቦታ በሚፈጠር የሥራ ጫና
የሥራ አሰራር ግልፅነት ማጣት
ከሚወዱት ሰው ጋር የሚፈጠር ችግር
መሰረታዊ የኢኮኖሚ ግዴታዎችን መወጣት አለመቻል፡- ለምሳሌ የቤት ኪራይ፣ አስቤዛ፣ ወርሃዊ የመብራት ክፍያ ወዘተ…
ለአዳዲስ ነገሮች መዘጋጀት፡- ለምሳሌ ልጅ መወለድ፣ አዲስን ስራ መያዝ
የትራፊክ መጨናነቅ
ከፍተኛ ድምፅ
ህመም
ክፍተኛ የአየር ሁኔታ፡- ለምሳሌ ከባድ ሙቀት ወይም ከባድ ቅዝቃዜ
አካላዊ ህመም፣እንቅልፍ ማጣት፣ከመጠን ያለፈ አልኮል መጠጣትና ሲጋራ ማጨስ በሰውነት ላይ የሚፈጥሩት ጫና ወዘተ ናቸው
ቲምና ፔተርሰን (Timm and Peterson) የተባሉ ምሁራን  በተለይ በሥራ አካባቢ የጭንቀት ምንጮች የሚላቸውን  እንደሚከተለው ይዘረዝራሉ።
ውጤታማ ያልሆነ ተግባቦት (Communications)
አግባብነት የጎደለው የመስሪያ ቤት አሰራር
ከመጠን በላይ የሆነ የመረጃ ብዛት
ወጥ ያልሆነ የሥራ አስኪያጆች ወይም የመሪዎች ባህሪ
ከመጠን ያለፈ የስራ ብዛት ወይም ጫና
አዲስ ሥራ መግባት
የግል ችግሮች
ጭንቀትን የሚዘሩ ግለሰቦች- በንግግራቸው ሁሉ ጭንቀት የሚፈጥር ወሬን የሚያወሩ (Stress carriers ይባላሉ)
የ ድርጅቶች ደሞዝ፣ፖሊሲ እና የስራ አካባቢ(working conditions)
የሥራ ቦታዎች ከፍተኛ ሙቀት ወይም ቅዝቃዜ፣ ከፍተኛ ብርሃን ወይም ድንግዝታ ለጭንቀት መነሻዎች እንደሆኑ በፃፉት መፅሃፍ ላይ ይገልፃሉ፡፡
የጭንቀት ውጤቶች ምንድናቸው?
የሰውነት ድካም
ከፍተኛ የራስ ምታት
ብስጭት
የምግብ ፍላጎት መዛባት
የማስታወስ ችሎታ መቀነስ
ለራስ የሚሰጥ ዋጋ ወይም ክብር መቀነስ(low self-esteem)
ከማህበራዊ ህይወት መገለል
የ ደም ግፊት መጨመር
ትንፋሽ ማጠር
የወሲብ ፍላጎት መቀነስ
የእንቅልፍ መዛባት
የጨጓራና አንጀት ስርዓት መዛባት  ወዘተ
ከእነዚህም በተጨማሪ ጭንቀት  የልብ ህመምን፣ የቆዳ ችግርን(skin disorders) እና ሜታቦሊዝምን (በሰውነታችን ውስጥ የሚካሄዱ ኡደቶችን)የማዛባት አቅም አለው ተብሎ ይታመናል፡፡ በተጨማሪም ለስነልቦናዊ ቀውሶች ለምሳሌ፡- ለፍርሃትና ለድብርት ይዳርጋል፡፡ ጭንቀት ስነልቦናዊ ችግር ነው ቢባልም አካላዊ ተፅእኖን ይፈጥራል፡፡
ጭንቀትን ለመቀነስ ምን ማድረግ አለብን ?
ከላይ የተጠቀሱት  ምሁራን ለጭንቀት መላ ይሆናሉ ያሉትን መፍትሄዎች እንደሚከተለው ዘርዝረዋል፡-
ለአፍታ ዞር ይበሉ፡- ጭንቀት ከፈጠረብዎ ሁኔታ ወይም ሌላ ምንጭ ዞር ይበሉና የማሰቢያና የማሰላሰሊያ ጊዜ ይውሰዱ፡፡
ያውሩት፣ይናገሩት፡-ለቅርብና ለሚያምኑት ሰው የጭንቀትዎን ስሜት  ይናገሩ፡፡ ባወሩ ቁጥር ይቀልልዎታል፡፡
ወጣ ብለው የሚወዱትን ይጫወቱ፡- የእግር ጉዞ ያድርጉ፣ ደረጃዎችን ወደ ላይና ወደ ታች ይውጡ፡፡
አንዳንዴ እጅ ይስጡ፡- ለምሳሌ እርስዎና ባለቤትዎ ወይም አለቃዎ “ይሄ ነው ትክክል ያኛው ነው ትክክል ” እያሉ ሙግት ከገቡና ጉዳዩ ብዙ ለወጥና ተፅዕኖ የማያመጣ ከሆነ ችላ ይበሉት፤ አንዳንዴ እያወቁ ይተውት፡፡
ለሌሎች መልካም ነገር ያድርጉ፡-በከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ ሲገቡና ሃዘን ውስጥ ሲሆኑ ችግረኞችን በመርዳትና ልገሳ በማድረግ ይሳተፉ፤ ቀለል ይልልዎታል፡፡
በአንድ ጊዜ አንድን ነገር ይስሩ፡- ሁሉንም ነገር በአንድ ጊዜ ለመስራት መሞከር ጭንቀትን ስለሚያባብስ እንደ ስራዎቹ ጠቃሚነትና አስቸኳይነት ቅደም ተከተል  በማሲያዝ  በአንድ ጊዜ አንድን ነገር ይስሩ፡፡
የታላቁን ሰው ፍላጎት አድብ ግዛ ይበሉት፡-አንዳንዴ የራስዎንም ሆነ የሌሎች ሰዎችን ችግር በሙሉ ራስዎ መፍታት እንደሚችሉ ማሰብዎ “በውስጥዎ ያለው የሃሰተኛው ትልቅ ሰው urge of superman” ምክር ነውና አድብ ግዛ ይበሉት፡፡ እርስዎ የሁሉንም ሰው ችግር ፈቺ አይደሉም፡፡
ትችትን መቋቋም ይለማመዱ፡- አንዳንድ ሰው ትንሽ ትችት እንቅልፍ ትነሳዋለች፡፡ በተጨማሪም ሌሎችንም ከመተቸት ይቆጠቡ። ቶማስ ፍሬድማን የ “ The world is flat” ፀሃፊ በዚህ አለም አንድ መንደር በሆነችበት ግሎባላይዜሽን ዘመን ለትችት ቆዳህን አወፍር (Make your skin thick) ብሎ ይመክራል፡፡
ለሌሎች ራስህን አስገኝ፡- ሰዎች ሲፈልጉህ ተገኝላቸው፡፡ ብቸኝነት የጭንቀት ምክኒያትም ሊሆን ስለሚችል፡፡
ራስህን ለማዝናናት ጊዜ ውሰድ፡-ዘና ማለት፣መጫወት፣ አዳዲስ ነገሮችን መጎብኘት መንፈስን ያድሳል፣ ጭንቀትንም ይቀንሳል፡፡
ቆፍጣና ሁን፡- በቀን ወስጥ የምትሰራውን፣ የምትሄድበትን ሥፍራ፣ የምታገኘውን ሰው በትክክል ለይተህ በማወቅ ዝርክርክነትን አስወግድ።
ስብዕናህን ፈትሽ፡- ጭንቀት ውስጥ የሚከትህንና የማይከትህን ነገሮች ለይተህ በመረዳት ራስህን ጠብቅ፡፡
ከላይ ከተጠቀሱት በተጨማሪ ጭንቀትን ለመቀነስ ቴክኒኮችን ማወቅና አስተሳሰብን መለወጥ አስፈላጊ ነው፡፡ ይህም በሥልጠናና በባለሙያ የካውንሰሊንግ አገልግሎት  ሊገኝ ይችላል፡፡
ለዛሬ ሁለት ቴክኒኮችን ብቻ  እንመልከት(በርካታ ቴክኒኮች እንዳሉ መገንዘብ ያስፈልጋል)፡-
አንደኛው በእንግሊዝኛው ምህፃረ ቃል ABCDE ተብሎ የሚጠቀሰው ነው፡፡ ይህ ቴክኒክ አልበርት ኤሊስ (Albert Ellis) በተባሉ የስነልቦና ባለሙያ የተገኘ ዘዴ ነው፡፡ አልበርት ኤሊስ ሰዎች ወደ ጭንቀት የሚገቡት አግባብ ያልሆነ አስተሳሰቦችና እምነቶች  (Irrational beliefs and thoughts) ሲጠናወቷቸው ነው ብለው ያምናል:: ለምሳሌ ሰው ሁሉ ይጠላኛል፣ ሰው ሁሉ ይወደኛል፣ ከሰው ሁሉ ተቀባይነትን ማግኘት አለብኝ፤ በምሰራው ስራ ሁሉ መሳሳት የለብኝም ወዘተ የሚሉ እምነቶችና አስተሳሰቦች ለጭንቀት እንደሚዳርጉ ያሰምሩበታል። እኚህ ሰው እንደሚሉት አሉታዊ ነገሮችን አጋኖ ማየት(Awfulising)፤ ጥቁርና ነጭ እሳቤ(Black and White thinking) (ይህ እንግዲህ አንድን ነገር ጥሩ ወይም መጥፎ ብሎ መመደብና በውስጡ ሊኖር የሚችለውን የተወሰነውን ጥሩ ነገር አለማየት ነው)፣ጠቅላይ እሳቤ (Over generalizing)-ሁልጊዜ፣ሁሉም ሰው፣ በፍፁም ወዘተ የሚሉ ቃላትንና ሃሳቦችን መጠቀም፤ የማይመለከተንን ነገር ከራሳችን ጋር አቆራኝቶ ማየት (Personalizing)፤ በሁኔታዎች ውስጥ አሉታዊን ነገር ብቻ መርጦ ማየት(Filtering)፣ ይህንን አስቦ ነው ብሎ ያለምንም ማስረጃ ድምዳሜ ላይ መድረስ (Mind reading)፣ሰዎችን መተቸትና መውቀስ (Blaming)፣ለራስ ስያሜ መስጠት ለምሳሌ ደካማ ነኝ፤ዋጋ ቢስ ነኝ ወዘተ ማለት (Labeling) አግባብ ላልሆኑ አስተሳሰቦች ምክኒያት ናቸው ይሉናል፡፡
የ ABCDE ቴክኒክን ተንትነን ለማየት እንሞክር
Antecedent(Activating event, Stimulus)፡ ይህ ማለት ጭንቀትን የሚቀሰቅሰው ሁኔታ ወይም ነገር ነው(ተንኳሽ እንበለው)፡፡ ይህ ተንኳሽ  የኛን ምላሽ (Response) ይጠይቃል። ለምሳሌ ከስንት አንድ ቀን ቀጠሮ ብናረፍድ ጭንቀት ሊፈጠርብን ይችላል፡፡ በዚህ ምሳሌ መሰረት ጭንቀትን የሚፈጥርብን ጉዳይ ማርፈዳችን ነው ማለት ነው፡፡
Belief-our cognition about the situation፡- ይህ እንግዲህ ስለ ተንኳሹ ያለን ሃሳብና እምነት ነው፡፡ ለምሳሌ ማርፈዴ ያለኝን ተቀባይነት ያሳጣዋል፣ በምንም አይነት ምክኒያት ቢሆን ማርፈድ አሳማኝ አይደለም ወዘተ የሚል እምነት ማለት ነው፡፡
Consequences-the way that we feel and behave፡ ይህ ውጤት ነው - ጭንቀታችን፡፡ ይህ ምን  ባህሪ ይፈጥራል? ቶሎ ለመድረስ አላግባብ ጣልቃ እየገባን መኪናችንን መንዳትን፣ በእጃችንም በአንደበታችንም የተንቀረፈፈ የመሰለንን ሾፌር መስደብ፣መቆጣት፤ ከአስፋልት ወጥቶ በእግረኛ መንገድ መንዳት  ወዘተ ማለት ነው፡፡ እዚህ ላይ አልበረት ኤሊስ ይሞግታሉ “ያስጨነቀን ማርፈዳችን ነው ወይስ ስለ ማረፈድ ያለን አስተሳሰብና እምነት ነው?” አሳቸው እንደሚሉት፤ ውጤቱን የፈጠረው ማርፈዳችን(stimuls ) ሳይሆን ስለ ማርፈድ ያለን አስተሳሰብና እምነት ነው ባይ ናቸው፡፡
Dispute is the process of challenging the way we think about situations: ይኸኛው አስተሳሰባችንን የምንሞግትበት ዘዴ ነው። እሳቸው አግባብነት የሌለውን አስተሳሰብና እምነት መሞገት ያስፈልጋል ይላሉ፡፡ ለምሳሌ ከላይ የጠቀስነውን ማርፈድ ብንወስድ እምነታችንን ስንሞግተው እንደሚከተለው ይሆናል፡፡ “ ብዙ ጊዜ በሰዓቱ የምገኝና ቀጠሮ አክባሪ የሆንኩ ሰው ነኝ፡፡ አንድ ዛሬን ባረፍድ ተቀባይነቴን አያሳጣም”፣ “ለማርፈዴ ምክኒያት የሆነኝ የትራፊክ መጨናነቅና ያልጠበቅሁት የመንገዶች መዘጋጋት ነው፡፡ ስለዚህ በቂ ምክኒያት ሊሆን ይችላል፡፡” እነዚህን ምክኒያቶች በማሰብ ነባሩን ሃሳብ መሞገት እንደሚገባ ይጠቁማሉ፤ አልበርት ኤሊስ፡፡
Effect: ይሄ አዲሱ ውጤት ነው። አስተሳሰባችንን ከሞገትነውና በአዲስ አስተሳሰብ ከተካነው በኋላ የሚፈጠር ባህሪ ነው፡፡ የላይኛውን ምሳሌ ብንከተል ተረጋግቶ መንዳት፤ ተራ መጠበቅ፤ በተፈቀደው አስፋልት መንዳት ወዘተ ማለት ነው፡፡ በነገራችን ላይ ሃሳብ ስሜታችን እና ባህሪያችን ላይ ተፅእኖ ይፈጥራል፡፡
በሁለተኛ ደረጃ የሶቅራጠስን ቴክኒክ እንመልከት፡- የጥንቱ የግሪክ ፈላስፋ ሶቅራጠስ አስጨናቂ ሁኔታዎች ሲፈጠሩ የሚጠይቃቸውን  የሚከተሉትን አምስት ጥያቄዎች መጠየቅ ይጠቅማል፡፡
ተጨባጩ ነገር ምንድነው?  ስለዚህ ነገር ያለኝ የኔስ  የግል እሳቤ?
የግል እሳቤዬን  የሚደግፍ ማስረጃ አለ?
የግል እሳቤዬን የሚቃረን ማስረጃስ?
የአስተሳሰብ ስህተት ፈፅሜያለሁ?
ስለ ተፈጠረው (ስለ ተጨባጩ) ሁኔታ ምን ማሰብ አለብኝ?
ነገሩ የግል እሳቤን የሚያጠናክር ማስረጃ ካለው(ተ.ቁ 2.2) ለችግሩ መላ መፈለግ ያስፈልጋል። ከእምነቴ ተቃራኒ  ከሆነ(ተ.ቁ 2.3) መጨነቅ ለማያስፈልገው ነገር ጊዜዬን እያባከንኩ ወይም ለጭንቀት ውጤቶች ራሴን እየዳረግሁ ነው ማለት ነው፡፡ የሶቅራጠስ ቴክኒክ የነገሮችን ወይም የሁኔታዎችን ተፅእኖ የምንፈትሽበትና የእርግጠኝነት ምላሽን የምንፈልግበት ነው፡፡ በነገራችን ላይ ዴል ካርኒጊ፤ አብዛኛው ሰው የሚጨነቀው ገና ባልደረሰብት ችግር ነው የሚል አስተሳሰብ ነበረው።
በመጨረሻም እንድ ማወቅ የሚገባን ነገር አለ፡- እንዳንድ ነገሮችንና ሁኔታዎችን መቆጣጠር እንችላለን። ይህንን ፅሁፍ ማዘጋጀትና አለማዘጋጀት በኔ ቁጥጥር ስር ነው፡፡ ከፈለግሁኝ አዘጋጀዋለሁ ካልፈለግሁኝ አላዘጋጀውም፡፡
ስለ ፈለግሁኝ አዘጋጀሁት፡፡ በአንዳንድ ነገሮች ወይም ሁኔታዎች  ደግሞ ተፅእኖ መፍጠር እንችላለን ነገር ግን ልንቆጣጠራቸው አንችልም፡፡ ለምሳሌ በቡድን በሚሰሩ ስራዎች እርስዎ የሚያምኑበትን ነገር ተግባራዊ እንዲሆን የስራ አመራሩን ተፅኖ ሊፈጥሩበት ይችላሉ  እንጂ ውሳኔውን  በግልዎ ሊቆጣጠሩት አይችሉም። አንዳንድ ነገሮችን ደግሞ መቆጣጠርም ሆነ ተፅእኖ መፍጠር አይቻልም። ስለዚህ ሁኔታውን መቀበል ወይም በሁኔታው ውስጥ ውጤታማ ሆኖ ለመኖር መወሰን ነው የሚጠበቅብዎ፡፡ ለምሳሌ የእርስዎ የቅርብ ሰው በሞት ቢለይ ወይም ፈፅሞ እርስዎን ላለማግኘት ወስኖ ከእርስዎ መለየት  ቢቆርጥ የሚቀይሩት ጉዳይ ስላልሆነ መቀበል እንዲሁም በተፈጠረው ሁኔታ ውስጥ ራስን አዘጋጅቶ መኖር ያስፈልጋል።
 አብዛኛው ሰው መቆጣጠር የሚገባውን ነገር ለሌሎች ተፅእኖ አሳልፎ ሲሰጥ ወይም ተቀብሎ ሲኖር፣ ወይም ተፅእኖ ማሳደር የሚገባውን ነገር ለመቆጣጠር ወይም በቸልተኛነት ሲቀበለው እና ራስን አዘጋጅቶ መኖር የሚገባውን ወይም መቀበል ያለበትን ሁኔታና ነገር ለመቆጣጠር ወይም ተፅእኖ ለማሳደር ሲሞክር የጭንቀት ሰለባ የመሆኑ ዕድል የሰፋ ነው። ይህንን በአጭሩ ለማስታወስ በእንግሊዝኛው ምህፃረ ቃል CIA-Control-Influence-Accept/Adapt to ብሎ መያዝ ይጠቅማል፡፡
አንዳንዱን ነገር Control እናደርጋልን፤ አንዳንዱን influence  ነው የምናደርገውን አንዳንዱን ደግሞ Accept/Adapt to ነው ማድረግ የሚገባን፡፡
ቸር እንሰንብት
(ፀሐፊውን በሚከተለው የኢ-ሜይል አድራሻው ሊያኙት ይችላሉ This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. )

Saturday, 12 July 2014 12:21

የፖለቲካ ጥግ

አመፅን የመከላከያ አስተማማኙ መንገድ ጉዳዩን ከእጃቸው ላይ መቀማት ነው፡፡
ፍራንሲስ ቤከን
(እንግሊዛዊ ፈላስፋ፣ ፖለቲከኛና የህግ ባለሙያ)
እኔና ህዝቦቼ ሁለታችንንም የሚያረካ ስምምነት ላይ ደርሰናል፡፡ እነሱም ደስ ያላቸውን ይናገራሉ፤ እኔም ደስ ያለኝን አደርጋለሁ፡፡
ዳግማዊ ፍሬድሪክ
(የፕረሽያ ንጉስ)
ማንኛውም ምግብ አብሳይ አገሪቱን መምራት መቻል አለበት፡፡
ቭላድሚር ኢሊች ሌኒን
 (የሩሲያ አብዮታዊ መሪ)
በምርጫ ለተሸነፉት ሁሉ አዝናለሁ፡፡ ፈፅሞ አይቼው የማላውቀው ተመክሮ ነው፡፡
ማርጋሬት ታቸር
(የቀድሞ የእንግሊዝ ጠ/ሚኒስትር ስለ 1997 እ.ኤ.አ አጠቃላይ ምርጫ የተናገሩት)
ዲሞክራቶቹ እዚህ የሚመጡት ድምፃችንን ሲፈልጉ ብቻ ነው፡፡ እኛን ለመደለል ጣፋጭ አምጥተውልናል፡፡ ኮሙኒስቶቹ ቮድካ ያመጡልን ነበር፡፡ እነሱ የበለጠ ስኬታማ ናቸው፡፡
ጋሊና ዴኒሶቫ
(ሩሲያዎት የሱቅ ነጋዴ ለጎረቤቷ የተናገረችው)
የኮሚኒስት ፓርቲ አመራርን ለመቃወም የሚሞክር አዲስ ፓርቲ ከተቀረፀ እንዲኖር አይፈቀድለትም፡፡
ሊ ፔንግ
(የቻይና የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር)
ኮሚቴ አራት የኋላ እግሮች ያሉት እንስሳ ማለት ነው፡፡
ጆን ሊ ካሬ
(እንግሊዛዊ ደራሲ)
ሂትለርና ሙሶሎኒ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ገብተው ቢሆን ኖሮ ዓለምን መምራት እንዴት ይቀል እንደነበር ብዙ ጊዜ አስባለሁ።
ሎርድ ሃሊፋክስ
(እንግሊዛዊ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣን)
የትኛውም አገዛዝ ታላላቅ ፀሃፍትን ወድዶ አያውቅም፤ አነስ አነስ ያሉት እንጅ፡፡
አሌክሳንዳር ሶልዝሄኒትሽን
(ሩሲያዊ ደራሲ)
ሞራላዊም ሆነ መንፈሳዊ አፈጣጠሬ አምባገነን እንድንሆን አይፈቅድልኝም፡፡ አምባገነን ብሆን ኖሮ ብዙ ነገሮች ይከሰቱ እንደነበር አትጠራጠሩ፡፡
አውግስቶ ፒኖቼት
(የቺሊ ወታደራዊ አምባገነን የነበሩ)