Administrator

Administrator

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በባሕር ዳር፣ በጅግጅጋ እና በሃዋሳ ከተሞች ያካሄደውን ግልጽ የምርመራ መድረክ (National Inquiry/Public Inquiry) ተከትሎ፣ በአዳማ ከተማ ከሚያዝያ 17 እስከ 20 ቀን 2015 ዓ.ም. ድረስ አራተኛውን ግልጽ የምርመራ መድረክ ማካሄዱን አስታውቋል፡፡
በመድረኩም በተለይ የዘፈቀደ እስርን፣ የተራዘመ የቅድመ ክስ እስርና በእስር ወቅት ተከስተዋል ስለተባሉ የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ተጎጂዎችና ምስክሮች ያቀረቧቸውን አቤቱታዎች እንዲሁም ጉዳዩ በሚመለከታቸው አካላት የተሰጡ ምላሾችን ማዳመጡ ተጠቁሟል፡፡
 ለአብነት ተመርጠው ከቀረቡት 18 አቤቱታዎች መካከል:- ያለ ፍርድ ቤት ትእዛዝ መያዝና መደበኛ ባልሆኑና በማይታወቁ ቦታዎች በእስር ማቆየት፣ በሕግ በተቀመጠው ጊዜ መሠረት የታሰረን ሰው ፍርድ ቤት ያለማቅረብ፣ የፍርድ ቤት የዋስትና መብት ትእዛዝ አለማክበር ይገኙበታል ተብሏል።
በተጨማሪም የተፋጠነ ፍትሕ የማግኘት መብትን፣ በእስር ወቅት በቤተሰብ የመጎብኘት መብትን፣ በቂ ምግብ፣ ውሃ፣ መጸዳጃና ሕክምና የማግኘት መብትን አለማክበርና ጭካኔ የተሞላበትና የማሰቃየት ድርጊት መፈጸም በቀረቡት አቤቱታዎች በተደጋጋሚ ከተጠቀሱት የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች መካከል እንደሚገኙበት ኮሚሽኑ አመልክቷል፡
የግልጽ ምርመራ መድረክ፤ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ደርሶብናል የሚሉ ሰዎች፣ ምስክሮች፣ ሌሎች ባለድርሻ አካላት እንዲሁም የሚመለከታቸው የመንግሥት ተወካዮች በአንድ መድረክ በተገኙበት በሕዝብ ፊት የሚከናወን የምርመራ ስልት መሆኑን ኢሰመኮ ጠቁሟል፡፡
“አቤቱታ አቅራቢዎች ደርሶብናል የሚሏቸውን የሰብአዊ መብቶች ጥሰት በግልጽ መድረክ ምስክርነት መስጠትና ማስረጃ ማቅረብ የሚችሉ ሲሆን፤ የሚሰጡት ቃል ሚስጥራዊ ባሕርይ ወይም የደኅንነት ሥጋት ያለባቸው ሰዎች ደግሞ በልዩ ሁኔታ በሚስጥር ቃላቸውን የሚሰጡበትን ዕድልንም ያካትታል፡፡” ብሏል፡፡
 ለግልጽ ምርመራው በኦሮሚያ ክልል ነጻነታቸውን ከሕግ አግባብ ውጪ እና በዘፈቀደ የተነፈጉ ሰዎች መብቶች ላይ ያተኮረ ጥናትና ምርምር ወይም የምርመራና ክትትል ግኝቶች ያሏቸው አካላት ይህንኑ እንዲያቀርቡ ኮሚሽኑ ያደረገውን ጥሪ ተከትሎ፣ መቀመጫውን በውጭ ሀገር ያደረገ Oromo Legacy Leadership & Advocacy Association/OLLAA የተባለ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅትን ጨምሮ ሌሎችም የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የየበኩላቸውን መረጃዎችና ትንተናዎች በጽሑፍ ለኮሚሽኑ ማስገባታቸው የታወቀ ሲሆን፤ በግልጽ ምርመራ መድረኩም ላይ በበይነ መረብ ቴክኖሎጂ በመታገዝ ዋና ዋና ሐሳቦቻቸውን አቅርበዋል ተብሏል፡፡
ሌሎች የሲቪል ማኅበራት ተወካዮችም ከሕግ ውጪ የሆኑና የዘፈቀደ እስራትን በተመለከተ አጣርተን ደርሰንበታል ያሉትን መረጃዎች በመድረኩ አቅርበው የመንግሥት አካላት ምክረ ሐሳቦቻቸውን በመቀበል ተግባር ላይ እንዲያውሉና ለሰብአዊ መብቶች መከበር አብረዋቸው እንዲሠሩ ጥሪ ማቅረባቸው ተመልክቷል፡፡
 “በኦሮሚያ ክልልና በተለያዩ ዞኖች በየደረጃው ያሉ የፍርድ ቤት፣ የፍትሕ ቢሮ፣ የፖሊስ ኮሚሽንና የሰላምና ጸጥታ ጽሕፈት ቤት ተወካዮች ለቀረቡት አቤቱታዎችና ተፈጽመዋል ለተባሉት የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል፤ በተጨማሪም የፍትሕና  የጸጥታ ተቋማቱ ያሉባቸውን ተግዳሮቶች እንዲሁም ለመብት ጥሰቶቹ መነሻ ምክንያት የሆኑ የክልሉን ነባራዊ ሁኔታም አስረድተዋል::” ብሏል ኮሚሽኑ በመግለጫው፡፡በአዳማ ከተማ የተካሄደውን ግልጽ ምርመራ መድረክ የኢሰመኮ የሲቪል፣ የፖለቲካ፣ የማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መብቶች ኮሚሽነር ዶ/ር አብዲ ጅብሪል፣ የሴቶችና የሕፃናት መብቶች ኮሚሽነር መስከረም ገስጥ እና የሰብአዊ መብቶች ክትትልና ምርመራ ሥራ ክፍል የሪጅን ዳይሬክተር ኢማድ አብዱልፈታህ መርተውታል፡፡
የዝግጅቱን መጠናቀቅ ተከትሎ የመርማሪ ኮሚሽነሮች ሰብሳቢ ኮሚሽነር ዶ/ር አብዲ ጅብሪል ባደረጉት ንግግር፤ “በግልጽ የምርመራ መድረኩ ተጎጂዎች፣ ባለግዴታዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ዙሪያ በግልጽ መነጋገር መቻላቸው እንዲሁም ለወደፊት ሊወሰዱ ስለሚገባቸው እርምጃዎች በሁሉም አካላት በኩል ለመደጋገፍ የመፍትሔ ሐሳቦች መቅረባቸው የሚያበረታታ ነው፡፡” ብለዋል፡፡


ግሪን ቴክ ፤ላለፉት ሦስት ወራት በኤሌክትሪክ መኪኖች ቴክኒሽያንነት  ያሰለጠናቸውን 25 ተማሪዎች ባለፈው ማክሰኞ ፣ ቃሊቲ ቶታል በሚገኘው የድርጅቱ ዋና መ/ቤት አስመረቀ፡፡
25ቱ ተመራቂዎች  በዘርፉ የመጀመሪያዎቹ ሰልጣኞች ሲሆኑ ፤ሥልጠናው የተሰጠው ከኤስኦኤስ የህጻናት መንደር ጋር በመተባበር  ነው  ተብሏል፡፡
ለተመራቂዎቹ የእንኳን ደስ ያላችሁ መልዕክት ያስተላለፉት የግሪን ቴክ አፍሪካ ዋና ሥራ አስፈጻሚ  ኢንጂነር ቅደም ተስፋዬ፤” በዘርፉ ተቀጣሪዎች ሳይሆን ሥራ ፈጣሪዎች እንድትሆኑ ነው የምንፈልገው” ብለዋል፡፡ሰልጣኞቹ ወደ ሥራ ከመግባታቸው በፊት የአምስት ቀናት የሥራ ፈጣሪነት (entrepreneurship) ሥልጠና እንደሚሰጣቸውም ተነግሯል፡፡
በአገራችን  በኤሌክትሪክ መኪኖች ቴክኒሽያንነት ሥልጠና የሚሰጥ ተቋም እንደሌለ የተናገሩት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ ያሁኖቹ ተመራቂዎች የመጀመሪያዎቹ ሰልጣኞች ናቸው ብለዋል፡፡በዕለቱ የተመረቁት ተማሪዎች በኤሌክትሪካልና መካኒካል ኢንጂነሪንግ በድግሪና በማስተርስ ድግሪ ደረጃ ትምህርት የወሰዱ መሆናቸው ታውቋል፡፡ግሪን ቴክ በአጠቃላይ 300 ወጣቶችን በኤሌክትሪክ መኪና ቴክኒሽያንነት  ለማሰልጠን ያቀደ ሲሆን፤ 27 ወጣቶች በሥልጠና ሂደት ላይ መሆናቸው ተጠቁሟል፡፡
ግሪን ቴክ ኢትዮጵያ፤ በአገራችን የመንገድ ትራንስፖርት ዘርፍ ፈር ቀዳጅ የሆኑና ለማህበረሰቡ የተቀላጠፈ አገልግሎት የሚሰጡ ሙሉ በሙሉ በኤሌክትሪክና በሶላር ቻርጅ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን ለተጠቃሚው ህብረተሰብ እያቀረበ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡

ይህ መጽሐፍ አማርኛ ምን ያህል ባለጸጋ እንደሆነ ፣ በአንጻሩ ሥነ-አመክንዮ አንገብጋቢ ርዕሰ ጉዳይ መሆኑን በግልጽ ያሳየ ሥራ ነው :: በአማርኛ ቋንቋ ከተጻፉ ፣ ትውልድን ብዙ ከጠቀሙ አንጋፋ መጻሕፍት መካከል ይህ አንዱ ነው የሚል እምነት አለኝ :: "
ዓለሙ ፊጤ ( ዶክተር )
University Of Michigan America
ስለመጽሐፉ አስተያየት የሰጡ

 ሸበተ መሰለኝ!
               (በድሉ ዋቅጅራ)


        ሸበተ መሰለኝ፣ እውቀትም አረጀ፤
ጡት ተጣባውና፤
አበልጅ ሆኑና፤
ከድንቁርና ጋር፣ በወግ ተወዳጀ፡፡
ብርሃኑ ጠፋ፣ አይኑ ደነገዘ፤
መቅኒው በረዶ ሆነ፣ በቁሙ ፈዘዘ፡፡
ይኽው እውቀት ጃጅቶ፤
ከድንቁርና ላይ፣ በሊዝ ቦታ ገዝቶ፤
ጎጆ ቀለሰና፣ መስሎ ጎረቤቱን፤
ፀሐዩን ይሞቃል፣ እያሻሸ ሪዙን፡፡
መጥኔ ለዚች ሀገር!
‹‹የት ይደርሳል›› ስንል በወጣትነቱ፤
እዚህ እቅርባችን፣ ይኽው ተመልከቱ፤
እውቀት ተመፃድቆ፤
ማወቁን አድምቆ፤
ህፀፁን ደብቆ፤
ከድንቁርና ጋር፣ ከጠላቱ ታርቆ፡፡
ደባልነት ገባ፣ አብሮ ቤት ቀለሰ፤
አንዱ ሲገነባ፣ አንዱ እያፈረሰ፡፡
ውሃ እያፈሱ፤
ጤፍ እየቆጠሩ፤
ውሃ እየወቀጡ፤
ባንድ ተቀመጡ፡፡
ይብላኝ ለዚች ሀገር!
የሀገር ጥሪት ነጥፎ፤
የሕዝብ ሀብት ባክኖ፤
የእድሜ ሻማ ነዶ፤
ስልጣኔ ብሎ፤ ፈረንጅ ሀገር ሄዶ፤
ሩቅ… ባህር ማዶ፤
የተገኘን እውቀት፤
ወይም
እዚሁ ሀገር ውስጥ፣ ኮሌጅ ተኮልጆ፤
የተገኘው እውቀት፤
ይኽው ተመልከቱ…
ከውጭ ሲመለስ፣ ከኮሌጅ ሲወጣ፤
ቦቃ በግ ሰውቶ፤
ዛፍ ቂቤ ቀብቶ፤
ንፍሮውን በትኖ፣ እጣኑን አጢሶ፤
ይኽው ተመልሶ፣
ተንበርክኮ ሽቅብ፣ ቱፍታ ይቀበላል፤
መርፌውን ሰክቶ፤
ከድንቁርና ጋር እውቀት ይማማላል፡፡
መጥኔ ለዚች ሀገር!
እውቀትም እንደ ሰው፣
ያለ እድሜው አረጀ፤
ከጠላቱ ጋራ፣ በወግ ተወዳጀ፡፡
አያት ድንቁርና፣ ለምለም አስጨብጠው፤
ለጋ የጊደር ቂቤ፣ ግንባሩን ቀብተው፤
በአምሳላቸው ቀርጸው፣
አውራ ጣት አጠቡት፡፡
ልጃቸውም ሆነ፣ አባት አያት ሆኑት፡፡
ከዚያማ ጋለቡት፣
ሉጋም አበጅተው፣ ለህሊናው መግቻ፤
ለራዕዩ መቀጨት፣ ለህልማቸው መፍቻ፡፡
ለእኩይ እጣ ብሎት፣
 እውቀትም አርጅቶ፤
ይኸው ተመልከቱ፤ ደጅ ተጎልቶ፤
ከድንቁርና ጋር፣ እሳት እየሞቀ፣
እውቀት ተጃጅሎ፡፡
ለአድባር ይሰዋል፤
ለአውልያ ይሰግዳል፤
ያማል፣ ያማል፣ ያማል፣
እውቀት ተጃጅሎ፤
የኦክስፎርድ ዲግሪ፤
ያለማያን ካባ፣ ግርግዳው ላይ ሰቅሎ፡፡
ይብላኝ ለዚች ሀገር!
ይብላኝ ለኢትዮጵያ!
እውቀት ድንቁርና ለተወዳጁባት፣
አንዱ ሲገነባ፣ ሌላው ለሚንዳት፡፡
መጥኔ ለዚች ሀገር፡፡
(1989- ፍካት ናፋቂዎች)




 ቢዝነስ አዋቂው ዊሊያም ሪግሊ

                  ለ8.5 ሚ. አሜሪካውያን መስቲካ በነጻ አስቀምሷል
                     ዋሲሁን ተስፋዬ


       ዊሊየም ሪግሊ፤ በአሜሪካን ፔንስልቫንያ የተወለደና ፡  እስካሁንም በአለም ላይ ቁጥር አንድ ተሻጭ ማስቲካዎች መሀከል አንዱ የሆነው የሪግሊ  ባለቤት ነው ።
በልጅነቱ በአባቱ የሳሙና ፋብሪካ ውስጥ በትርፍ ጊዜው ይሰራ ነበር ፡ እድሜው 13 አመት ሲሞላ ደግሞ ፡ በአባቱ ኩባንያ የሚመረተውን ሳሙና እየተረከበ መሸጥ ጀመረ ። በዚህ ሁኔታ የተወሰኑ አመታት እንደሰራ   በወቅቱ የነበሩትን የሳሙና ፋብሪካዎች በልጦ ለመገኘት አንድ ዘዴ ማሰብ ጀመረ ።
ይህ ዘዴ አነስ ያለ የቤኪንግ ፓውደር መስሪያ ማሽን በመግዛትና በማምረት ፡ የሱን ሳሙና ለሚገዙ ሰዎች ፡ አንድ ቤኪንግ ፓውደር በነጻ መስጠት ነው ።
 በዚህ መልኩ ሳሙናውን መሸጥ ሲጀምር፣ የሳሙናው ገበያ በሚገርም ሁኔታ ጨመረ ። ሆኖም  ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ፣ ሰዎች ሳሙናውን የሚገዙት በስጦታ መልክ፣ በነፃ ለሚያገኙት ቤኪንግ ፓውደር ሲሉ እንደሆነ አወቀ ።
ልክ ይህን እንደተረዳ፣ ወዲያውኑ ግዙፍ ማሽን ገዝቶ ፡ በሰው ዘንድ ተወዳጅ መሆን የጀመረውን የቤኪንግ ፓውደር ምርት በሰፊው ማቅረብ ጀመረ ።
በወቅቱ ቤኪንግ ፓውደር የሚያመርቱ ብዛት ያላቸው ካምፓኒዎች ስለነበሩም፣ የገበያ ፉክክሩን ለማሸነፍ ፡ ማስቲካ የሚያመርት ማሽን ገዝቶ፣ ቤኪንግ ፓውደር ለሚገዛ ሰው  አንድ ማስቲካ  መስጠት ሲጀምር. ..በነጻ ለሚሰጠው ሪግሊ ማስቲካ ሲባል፣ ቤኪንግ ፓውደሩ እንደ ጉድ መሸጥ ጀመረ ። ቢዝነስ አዋቂው ዊሊያም ሪግሊ ይህን እንደተረዳ። የቤኪንግ ፓውደር ማምረቱን በመተው፣ ሙሉ ለሙሉ ማስቲካ በማምረት ስራ ውስጥ ገባ። ምርቱ ተወዳጅ ሆኖ በመላው አሜሪካ ቆይቶም ፡ በመላው አለም ታዋቂ ብራንድ ሆነ።
እንግዲህ፤ ከላይ ባየነው አጋጣሚ ምክንያት የተፈጠረው ሪግሊ፣ ከአመታት በኋላ ዛሬ ላይ አመታዊ ሽያጩ ከሁለት ቢሊየን ዶላር በላይ አልፏል።
 ቢዝነስህን ወይም  ሥራህን አሻሽለህ ለመስራት ባሰብክ ቁጥር፣ ሥራህ  ወይም ቢዝነስህ  ያሻሽልሀል፡፡ .እዚህ ላይ ሳንጠቅስ የማናልፈው፣ ዊሊየም ሪግሊ፣ ይህን የማስቲካ ካምፓኒ ሲጀምር ፡ ማስቲካውን ለማስተዋወቅ የተጠቀመበት ዘዴ እስካሁንም ይወራለታል ።
 ይህ ሰው ማስቲካ ማምረቱን በሰፊው እንደጀመረ ሰሞን  ....ለ8.5 ሚሊዮን አሜሪካውያን ሪግሊ ማስቲካን እንዲቀምሱ በነጻ ልኮላቸው ነበር ። ይህ የማስተዋወቅ ዘዴውም  ውጤታማ የሆነው ወዲያውኑ ነበር ።

____________________________________________

                      እያረሩ መሳቅ--?

 
         “… በነዳጅ ማደያ ዙሪያ ያለው የመኪና ሰልፍ ያስደነግጣል። ወደ አንዱ ባለ መኪና ጠጋ አልኩና ጠየቅኩት...
“ምነው ነዳጅ የለም እንዴ?”
“ኧረ አለ”
“ታዲያ ይኼ ሁሉ ሰልፍ ምንድነው?”
“የነዳጅ  ቀጂው ስልክ ዘጋበት”
“ምን ዘጋበት?”
“የስልኩ ቻርጅ አለቀበት” ሳቄ ደርሶ ድቅን አለ።
ይኸውልህ እንግዲህ፣ ያልተጠና አሰራር እንዲህ ያለ ችግር ይፈጥራል። የነዳጅ ቀጂ ስልክ ቻርጅ ማለቅም እንቅስቃሴ ይገድባል?
(Jony Zewde በገፃቸው ካሰፈሩት)




        ሰዓሊ ዳዊት ሙሉነሕ በመደመር አፍሪካ የስነ ጥበብ ስፍራ ታላቅ አውደ ርዕይ “Reflections on the I Ching በሚል  ርዕስ አዘጋጅቷል። ከ70 በላይ ስዕሎች ለህዝብ እይታ ይቀርባሉ ። ለስነጥበብ ስራዎቹ  “The Complete I Ching : The Definitive Translation by Taoist Master Alfred Huang” የተባለው መፅሐፍ  መነሻ ሆኗል።
ሰዓሊ ዳዊት መፅሐፉን በመጥቀስ እንደገለፀዉ፤ ኤግዚብሽኑ “የገነት፤ የመሬትና የሰው ልጅ ትልቅነት...ገነት፤ መሬትና የሰው ልጅ የሚግባቡበት አስተሳሰብ “ ይንፀባረቅበታል። ብሏል፡የሰዓሊ ዳዊት ሙሉነህ Reflections on the I Ching ታላቅ  አውደርዕይ፣  በመደመር አፍሪካ የስነጥበብ ስፍራ ሰኞ ሚያዝያ 23 ላይ በይፋ ተመርቆ በመከፈት፣ በቋሚነት ጎብኝዎችን የሚያስተናግድ ይሆናል። በስነጥበብ ስፍራው በሚገኘው የከተማችን ግዙፍ የስዕል አዳራሽ Yellow hall እና በአስደናቂው የስነጥበብ ዱንካን ubntu dome ከ70 በላይ ስዕሎች ይቀርባሉ ።ሰዓሊ ዳዊት ሙሉነህ በስነጥበብ ሙያው ከ28 ዓመታት በላይ ሰርቷል።  አፈርን ቀለም ባደረገ ምርምርና ጥናትም ተሳክቶለታል። ለስዕል ስራዎቹ ከኢትዮጵያ የተሰበሰቡ አፈርና ድንጋይ ተፈጭተው ቀለማት ሆነዋል። ሰዓሊ ዳዊት ሙሉነህ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ‹‹አለ የስነጥበብ እና ዲዛይን ትምህርት ቤት›› በግራፊክ አርት በ1987 ዓ.ም በዲግሪ የክብር ተመራቂ ነው፡፡
 በአዲስ አበባ ከተማ  የስዕል ስቱድዮዎችን በግል እና በቡድን መስርቶ በመንቀሳቀስ ይታወቃል፡፡  ከ25 በላይ ኤግዚብሽኖችን  ለዕይታ አብቅቷል።



Saturday, 29 April 2023 18:23

የብልህነት መንገድ

  ምንም ነገር ጥሩም  ሁን መጥፎ እስከ ጽንፍ ድረስ አትውሰደው አንድ ብልህ ይሄን ጉዳይ በአንዲት አባባል ቀንብቦ አስቀምጧታል። ጽንፍ የወጣ ፍትህ ኢ-ፍትሐዊነት ይሆናል። ብርቱካንን አለአግባብ ብትጨምቀው ጭማቂው መራራ ይሆናል። ደስታም እንኳ ቢሆን መረኑን እስኪለቅ ድረስ መሆን የለበትም። ላምን አለቅጥ ማለብ ደም ያሳዣታል።
ለራስህ ትንሽ ስህተት ፍቀድለት እንደዚህ አይነት ግድየለሽነት በአብዛኛው ችሎታን ደግፎ ይገኛል። ቅናት የራሱ አይነት የተለየ ውግዘት አለው። መታወቅህ በጨመረ መጠን ወንጀልህ ይጨምራል። አንድ ነገር በሃጥያት አለመውደቅ መልሶ ራሱን በሀጥያተኛነት ይስከሰስዋል። ጽሩሕ በመሆኑ ብቻ ይወነጀላል። አርጎስ ይሆናል። ሂስ እንደ በረድ በነጻው ውስጥ ነቁጥን በመፈለግ፤ እንደ መብረቅ የተራራውን ጫፍ ትመታለች። የሆሜርን የጭንቅላት ውዝወዛ፣ ለጠላት መርዝ ማርከሻ እንዲሆን ፍቀድለት። ስለዚህ የማስተዋል ሳይሆን ያለማወቅ ትንሽ ዝንጉነትን ለጥላቻ ማብረጃ ፍቀድ።
ጠላቶችህን ተጠቀምባቸው ነገሮችን በሚቆርጠው  ስለታቸው አትያዝ፤ በአፎታቸው እንጂ። በተለይ ከጠላቶችህ ጋር ባለህ ግንኙነት ይህ ህግ ከጉዳት ታደግሃል። አዋቂ ከጠላቶቹ ሚጠቀመውን ህል ነፍላላ ከወዳጆቹ አይጠቀምም። የጠላቶችህ  ክፋት የማትወጣውን የችግር ተራራን ወደ ሜዳ የመዳመጥ ሃይል አለው። ብዙዎች በገዛ ጠላቶቻቸው ታላቅነት እንደ ስጦታ ተበርክቶላቸዋል። ቁልምጫ ቆሻሻን ስለሚደብቅ ከጥላቻ የባሰ መጥፎ ነገር  ነው። ብልህ ክፋትን ወደ ጥሩ መስታወት ይቀይራል።
የረጅም ህይወት ምስጢር ጥሩ ህይወት መምራ ነው። ሁለት ነገሮች ህይወትን ወደ ፍጻሜዋ ያዳፏታል። ከንቱነት እና ሞራለ-ቢስነት።  አንዳንድ ብልሃቱ ስለሌላቸው ብቻ ህይወትን ያጧታል፤ሌሎች ደግሙ ፈቃዱ ስለሌላቸው። ሰናይነት ለህይወት ሽልማት እንደሆነ ሁሉ ሃኬትም ቅጣቷ ነው። ወደ ሃኬት ፊቱን ለማዞር የቸኮለ ሁሉ ሁለት ሞትን ይሞታል። የመንፈስ ሐቀኝነት ወደ ስጋ ይሰርጻል። ህይወት በቆይታዋ ድምቀት  ብቻም አይደል ጥሩ እምትባለው፤ በቆይታዋ ርዝመት ጭምር እንጂ።
እያመነታኽ አትስራ ጠርጣራ  ህሊና ለሁሉም ግልጽ ነው። በተለይ ለባላንጣ። በተጋጋለው ግርግር መሃል ብያኔኸ የሚመስለውን ፍርድ ካላቀበለህ፣ ኋላ ነገሮች ሲረጋጉ ይክስሃል። ጥንቃቄ የሚያሻው አጠራጣሪ ነገር ሲያጋጥም ምንም አለመስራቱ ይሻላል። ጥሩ የማመዛዘን ችሎታ ይሁንታን አይቀበልም። ሁሌም  በምክንያታዊነት የቀትር ብርሃን ነው የሚጓዘው። ጅማሮህ ላይ ችግር ካለ አፈጻጸሙ እንዴት ሊያምር ይችላል? በመጀመሪያ ጥሩ የመሰለህ ውሳኔ ውዳኤው ካላማረ፣ ተጠራጥረህበት የነበረውስ እንዴት ይከፋ ይሆን?
 እነሆ በሁሉም ዘርፍ የላቀ ጥበብ የባህርይ እና የንግግር ቀዳሚውና ዋነኛው ህግ ነው እላለሁ። በተለይ በስልጣን መሰላል ከፍ እያልህ በሄድህ ቁጥር ደግሞ አስፈላጊነቱ እየጨመረ ይመጣል። የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል ጥበብ ከጆንያ ሙሉ ብርታት ትልቃለች። ይሄ ብዙም ባይመሰገንም፣ በተፈጥሮ የተረጋገጠ ምንገድ ነው። የጥበበኛነት ክብር የዝናዎች ሁሉ የመጨረሻ ድል ነው። ብልሆችን ማርካት ከቻልክ በቂ ነው። ብያኔያቸው የስሜት ናሙና ስለሆነ።
ሁለገብ ሰው የፈርጀ ብዙ ብቃቶች ባለቤት  የሆነ ሰው፤ ብቻውን ከብዙ ሰዎች እኩል ነው። ይህን ፍስሃ ለባልንጀሮቹ በማጋራት ህይወታቸውን አበልጽጎ አስደሳች ያደርጋታል። ማለቂያ ባላቸው ጉዳዮች ያለ ልዩነት፣ የህይወት  ትፍስሕት ነው። ተፈጥሮ ሰውን በራሷ ረቂቅ አምሳያ እስካበጀችው ድረስ ጥበብ የሰው ልጅን ምርጫና ብልሃት በማሰልጠን፣ በውስጡ ደቂቅ ህዋን  እንድትፈጥር ፍቀድላት።
የችሎታህን መጠን አታሳይ ብልህ በሁሉ ዘንድ መከበርን ከመረጠ የእውቀቱንና  የችሎታውን ትግል አያሳይም። እንድታውቀው እንጂ እንድትረዳው አይፈቅድልህም።
ማንም የችሎታውን መጠን ማወቅ የለበትም። ካወቀ ይከፋል። ማንም ጥልቀቱን ለክቶት አያውቅም።
ምክንያቱም  ስለሱ ችሎታ የሚሰነዘሩ ግምቶችና ጥርጣሬዎች ካለው ከትክክለኛው ችሎታ በላይ ክብርን ያቀዳጁታልና።
ተስፋ አንብረው፤ እያነሳሳህ አቆየው። ቃል በመግባትና በድርጊት ተስጥኦህን አለምልም። ያለህን ሁሉ አንጠፍጥፈኽ በአንድ ጉዳይ ላይ ማዋል የለብህም። ትልቁ ታክቲክ የጥንካሬና የእውቀት አጠቃቀምህን እየመጠንክ ወደ ስኬት ማምራት ነው።
አስተውሎት የምክንያታዊነት አክሊል ነው። የጥንቃቄ መሰረት። በዚህች ዘዴ ብቻ ስኬት በትንሽ ወጪ ይገኛል። የመጀመሪያው እና ጥሩው ችሎታ እስከሆነ ድረስ በጸሎትም ቢሆን መገኘት አለበት። የሰማያት ስጦታ የሆነው አስተውሎት፤ እጅግ በጣም ጠቃሚው ጋሻ ሲሆን፤ ማመዛዘንህን ማጣት ትልቁ ሽንፈት ሊባል ይችላል። ጉድለቱ ከርቀት ይታያል። የህይወት ሁሉም ትግበራዎች በሱ ተጽዕኖ ስለ የወደቁ  የሱንም ይሁንታ የሚሹ እስከሆኑ ድረስ ሁሉም ነገር አስተውሎት ጋር  ተጓድኖ መሄድ አለበት። አስተውሎት በተፈጥሮው ምክንያታዊነት ጋር ተቀላቅሎ ለሚገኝ እርግጠኛ አቅጣጫ የማላት ባህርይ አለው። ዝናን አግኛት አኑራትም… ታዋቂነትን ማግኘት ውድ ነው። ከታላቅነት ስለሚገኝ።
 ተራ የሆኑ ነገሮች በብዛት የሚገኙትን ያህል ዝና ደግሞ ብርቅ ናት። አንዴ ከተገኘች ለመጠበቅ ትቀላለች።
ብዙ ግዴታዎችን  ትፈጥራለች። ውጤትንም ታገኛለች። ዝና በፍጽምነትዋ ዋና በተገኘችበት የስራ ዘርፍ የተነሳ ወደ ክብር ሰለምትቀየር ዘውዳዊነትን ትቀዳጃለች። ነገር ግን በጽኑ መሰረት ላይ የተገነባ ዝና ብቻ ነው ዘላቂ የሚሆነው።
ምኞትህን ደብቅ፤ ጥልቅ ስሜቶች የነፍስ መግቢያ በሮች ናቸው። ተግባራዊው እውቀት እነሱን መደበቅ ያጠቃልላል። የያዘውን ካርታ  ለእይታ አጋልጦ የሚጫወት የመበላት እድል አለው። ለተጠያቂዎች የማወቅ ፍላጎት ጥንቃቄ መደረግ አለበት። እንደ ዱር ድመት ካተኮሩ አይጦች፤ ከኩትል አሳ ቀለም ሁሉ መከለል አለበት። ፍላጎቶችህን በቅድሚያ በፍጥጫም ይሁን በቁልምጫ እንዳይገመቱ ደብቃቸው።
እውነታና ገጽታ ነገሮች በምንነታቸው ብቻ ተቀባይትን አያገኙም ፤በገጽታቸውም ጭምር  እንጂ። ጥቂቶች ናቸው ወደ ውስጥ የሚያጮልቁት። አብዛኞች በገጽታ ብቻ ይደሰታሉ። ገጽታህ የተሳሳተ ከመሰለ ትክክል መሆን ብቻውን በቂ አይደለም።  
***
(“ከየግሬሽያን ባልታሳር የብልህነት መንገድ” የተቀነጨበ)


  ‹‹ሁሉንም ሞክሩ፤የተሻለውን ያዙ›› የሚለውን አባባል፣ ቢያንስ እስከ 1966 ዓ.ም ድረስ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ዩኒቨርስቲ (የዛሬው አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ) ገብቶ የተማረ ተማሪ ያውቀዋል፡፡ በየድግሪው ላይ የተፃፈ መሪ ቃል እና ጥቅስ ነው፡፡ በህይወታችን ውስጥ በርካታ ውጣ ውረዶች ይገጥሙናል፤ እና በየፈርጅ በየፈርጃቸው እየሞከርን፣ እየወደቅን እየተነሳን፤ በጎና ሰናይ የሆኑትን እየለየን እና እያጠናከርን፤ የሚበጀንን መያዝ አለብን፤ ለማለት ነው፡፡ በእርግጥም በየአንዳንዱ ሙከራ ወቅት፤ እንቅፋት፣ ችግርና መከራ መኖሩ አይቀሬ ነው ለማለት ነው፡፡ ለዚህ አብነት ይሆነን ዘንድ የሚከተለውን የአበው ወግ እንይ፡፡
ሁለት ደገኛ ገበሬዎች ኑሮ አልገፋ ብሎ ቁም ስቅላቸውን ያሳያቸዋል፡፡ አንዴ ዝናቡ እንቢ ይላል፡፡ አንዴ በሬዎቹ ይለግማሉ፡፡ አንዴ ደቦ ወጪዎች አይመቻቸውም፡፡ አንዴ ደግሞ ሰብሉን ተባይ ይፈጀዋል፡፡ በእጅጉ ይቸገራሉ፡፡ አዝመራውም አልሰምር ይላል፡፡
አንደኛው ገበሬ አንድ ቀን መላ ዘየደ፡፡ ንግድ መጀመር አለብኝ ብሎ ወሰነና፣ አዲስ ሙከራ ጀመረ፡፡ በሬዎቹን ሁሉ ሸጠ፡፡ የዘር እህሉንም ከሰቀለበት አውርዶ፣ ለቤት የሚፈልገውን ያህል አስቀረና አውጥቶ ሸጠ፡፡ ከዚያም ባገኘው ገንዘብ ወደ ቆላ ወርዶ ለማረሻ ለዶማና ለማጭድ ወዘተ--መስሪያ የሚሆን ብረታ ብረት ገዛ፡፡ የገዛውንም ብረታ ብረት ወስዶ ለቸገረው ደገኛ ህዝብ ቸበቸበው፡፡ ቀስ በቀስ ኑሮው ተለወጠ፡፡ አዱኛም አገኘ፡፡ ለውጡ በቀዬውም በአገሩም ተወራ፤ ተሰማ፡፡ ሃብቱ ጣራ ነካ፡፡ ይጭነው አጋስስ ይለጉመው ፈረስ በደጅ በግቢው ሞላለት፡፡
‹‹አያ፤ እንዲህ በአንዴ ዲታ የሆንከው ምን ዘዴ ከውነህ ነው ጃል?›› ብሎ ይጠይቀዋል፡፡
ያም የድሮ ገበሬ፣ የዛሬ ነጋዴ፤ የተሰማራበትን ሙያ ያስረዳዋል፡፡ ወደህ ስራ ቢገባም በቀላሉ ካብታም እንደሚሆን ይገልፅለታል፡፡
ሁለተኛው ገበሬ፤ ሳይውል ሳያድር ምክሩን ተቀብሎ፣ በስራ ላይ አዋለና፣ ያለ የሌለ ንብረቱን ወደ ገንዘብ ለወጠ፡፡ ንግድ ጀመረ፡፡
ቆላ ወረደ፡፡ ያገሩን ብረታ ብረት ገዛ፡፡ ተሸከመና ሽቅብ ወደ ደጋ መንገድ ጀመረ፡፡ ሆኖም፤ ገና ዳገቱን አጋምሶ ሳያበቃ በተሸከመው ብረታ ብረት ክብደት ሳቢያ ወገቡም ጉልበቱም ከዳውና ተዝለፍልፎ ወደቀ፡፡ አወዳደቁም አጉል ነበረና አረፋ አስደፈቀው ፡፡
አንድ መንገደኛ የሰፈር ሰው ድንገት ሲያልፍ አይቶት ኖሮ ወደሱ ቀርቦ፤
‹‹አያ እገሌ፤ምን ሆነህ ነው?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
ገበሬውም፤ ‹‹አይ ወዳጄ፤ ያ ጎረቤቴ አያ እገሌ የሰራኝን ስራ ለጠላት አይስጥ!›› አለና መለሰለት፡፡
‹‹ምን አደረገህ? የልብ ወዳጁ እማይደለህ እንዴ? በሞቴ ንገረኝ፤ ምን አደረገህ?››
‹‹ትርፉን ነግሮ መከራውን ሳነግረኝ፤ ይሄው ለዚህ ዳረገኝ!!›› አለው፡፡
***
ሁሉም ስራ ችግሩ የሚታወቀው ሲሞከር ብቻ ነው፡፡ ንግዱ፣ትምህርቱ፣ ልማቱ፣አስተዳደሩ፣ ፓርላማዊ ስነስርዓቱ፣ ምርጫው፣ ፍትሃዊ ባህሉ ወዘተ ሁሉም ተሞክሮ፣ ተሰርቶ ታይቶ ነው፡፡ ካላዋጣ ደግሞ ካፈርኩ አይመልሰኝ ሳይሉ፣ የማይሰራውን ፈጥኖ ጥሎ ሌላ መንገድ መፈለግ ግድ ነው፡፡ ስህተትንም በወቅቱ አርሞ፣ ሰናዩን አለምልሞ፣ ጠንካራውን አጎልብቶ፣ መያዝ ደግ ነው፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ከአምናው ምን ተምረናል? ለነገስ ምን ጨብጠናል? የማለት ድፍረትና ግልፅነት እንዲኖረን ያሻል፡፡
አዲስ ፈር ለመቅደድ መስዋዕትን መክፈል፣ ያልተሞከረውን መሞከር ያልታየውን ማየት ያስፈልጋል፡፡ ትላንት በሄድንበት መንገድ ዛሬም ብንመላለስበት ኮቴአችንን ከመጨረስ በቀር፣ ወደላቀ ግብ መድረስ እርም ነው፡፡ ትላንት በተሟገትንበት፣ በተዛለፍንበት፣ ላንደማመጥ በተጯጯህንበት ሸንጎ፣ ዛሬም ያንኑ እሪታና ጩኸት፣ ያንኑ ችኮላና ድንፋታ፣ ያንኑ እርግማንና ውግዘት ብናላዝን ብናስተጋባበት፤ ድምፃችን ከመዛሉ፤ ጉዟችን ከመሰናከሉ በቀር ብዙ አንራመድም፡፡ ከመበቃቀል መተራረም፣ ቂም ከማርገዝ የቂምን ሥነ-ነገር መርምሮ ለመንቀል መጣጣር ዋና ጉዳይ የሚሆነውም ለዚህ ነው፡፡
ከቶውንም ትላንት እጅግ ጨለማ የመሰለንን ንፍቀ ክበብ፣ ዛሬ በመጠኑ እንኳን ደብዛዛ ውጋጋን ካየንበት ውጋጋኑን ለማስፋት እንጂ ‹‹ይሄውላችሁ፣ ዛሬም በደምብ አላነጉትም!›› እያልን ቡራ-ከረዩ ብንል አንድም የለውጥን አዝጋሚ ሂደት መካድ፣ አንድም ያ ውጋጋን ብሩህ ፀዳል እንዳያገኝ የእኛን አስተዋፅዖ መንፈግ ይሆናል፡፡ ባለፈው፣ ባልሞከርነው ነገር ሳቢያ ባጠፋነው ጊዜ ስንፀፀት አዲስ ሙከራ የምናደርግበትን ሌላ ውድ ጊዜአችንን እንዳናጨልም መጠንቀቅ ይበጃል፡፡ ሀገራችን አሁን ላለችበት ቦታ የበቃችውኮ በደጉም በክፉውም ሂደት ሳቢያ ነው፡፡ ማህበረሰባችንም እንደዚያው፡፡ ክፉውን አስወግዶ አንድ እርምጃ ለመራመድ ግን አዲስ ሙከራ እንደሚስፈልግ በመገንዘብ መንቀሳቀስ ይጠይቃል፡፡ የሌሎችን ድምፅ በትዕግስት መስማት፣ መንገዳቸውን በጥሞና ማየት፣ እኛ ያደረግንላቸውን ያህል እነሱም ያደርጉ ዘንድ ሁኔታዎችን ማመቻቸት፡፡ ለዚህ ደግሞ ትርፉን ብቻ አውቀን መከራውን ሳናውቅ ከተጓዝን ህልማችን ሁሉ ከላይ እንደተጠቀሰው ገበሬ ጉልበት አጥቶ ይወድቃል፡፡ የራእያችንም ክንፉ ከወዲሁ ይሰባበራል፡፡ ተስፋችን ሳይጫር ይከስማል፡፡ በዚህ መንገድ የሄዱ ቄሱም፣ ሼኪውም፣ ሹሙም ዜጋውም፣ የፖለቲካ ቡድኖቹም፣ መንግስታዊ የሆኑና ያልሆኑ ድርጅቶቹም አበክረው ማስተዋል ያለባቸው ቁምነገር ይሄ ይመስለናል፡፡
‹‹ያለፈ ጥረታችንን ሳስታምመው ትዝ ሲለኝ፣ ከሞከርነው ነገር ይልቅ ያልሞከርነው ነው እሚቆጨኝ››
ለማለት መቻል አለብን፤ እንደ ‹‹ቴዎድሮስ››፡፡ ያልሞከርነውን ለመሞከር ዝግጁነት ወሳኝ ነው!! የመንፈስም የአካልም፡፡
ከዚያ በኋላ፤ ‹‹ሁሉንም ሞክሩ፣ የተሻለውን ያዙ››! ለመባባል እንችላለን፡፡



 • ከፍተኛ የጨው አጠቃቀም ለደም ግፊት በማጋለጥ፣ የልብና ደም ቧንቧ እንዲሁም ስትሮክ አደጋን ይጨምራል
     • በኢትዮጵያ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች የሞት ምጣኔ 43 በመቶ ደርሷል
     • እ.ኤ.አ በ2017 ከ2.8 ሚ. በላይ ሰዎች በልብና ደም ቧንቧ በሽታ ተጠቅተዋል


      ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች፣ ሥር የሰደዱ በሽታዎች በመባል የሚታወቁ ሲሆን፤ ከአንድ ሰው ወደ ሌላ ሰው የማይተላለፉና ለረዥም ጊዜ የሚቆዩ የጀነቲክ፣ የፊዚዮሎጂ፣ የአካባቢና የባህርይ ሁኔታ ውጤቶች ናቸው፡፡ እነዚህም የልብና የደም ቧንቧ በሽታዎች፣ የልብ ድካምና ስትሮክ፣ ካንሠር፣ ሥር የሰደዱ የመተንፈሻ አካላት ህመሞች፣ ሥር የሰደደ የሳምባ ምችና አስም እንዲሁም የስኳር በሽታዎች ናቸው፡፡
ለእነዚህ በሽታዎች ዋና ዋና አጋላጮች ከሚባሉት መካከል ጤናማ ያልሆነ አመጋገብ፣ ትምባሆ ማጨስ፣ ጎጂ የአልኮል አጠቃቀም፣ ጫት መቃምና  የሰውነት እንቅስቃሴ አለማድረግ ይጠቀሳሉ፡፡
“ጤና፣ ልማት እና ጸረ- ወባ ማህበር” ባሰራጨው ጥናታዊ መረጃ መሠረት፤ ጤናማ ያልሆኑ ምግቦች የሚባሉት የስኳር፣ የጨውና በመደበኛ የቤት ውስጥ ሙቀት የሚረጋ ዘይትና የአትክልቅ ቅቤ (Transfat and Saturatedfat) መጠናቸው የበዛባቸው ፈጣንና በፋብሪካ የተቀነባበሩ ምግቦችና መጠጦች ሲሆኑ፤ እነዚህን አብዝቶ መመገብ ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎችና ለሌሎች የጤና እክሎች እንደሚያጋልጥ ተረጋግጧል፡፡
የከተሞች መስፋፋትና የአኗኗር ዘይቤ መለወጥ የአመጋገብ ሥርዓትን እየቀየሩና ከዚህ ጋር ተያይዞ በፋብሪካ የተቀነባበሩ ምግቦች አቅርቦት በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ መምጣቱን የጠቆመው ጥናታዊ መረጃው፤ ሰዎች እነዚህን የረጋ ስብ (Transfat and Saturatedfat)፤ የስኳርና የጨው ይዘት ያላቸው ምግቦችና መጠጦች አዘወትረው በመመገብ ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎች እንደሚጋለጡ አመልክቷል፡፡
በጤናማ አመጋገብ ላይ የማህበረሰቡ  የግንዛቤ ማሳደጊያ ሥራዎች ባለመሰራታቸው፣ ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ምክንያት በርካታ ዜጎች ለህመምና ለሞት እየተዳረጉ ነው ያለው “ጤና፣ ልማት እና ጸረ- ወባ ማህበር”፤ የመገናኛ ብዙኃንና የማህበራዊ ሚዲያ ጋዜጠኞች ይህን ክፈተት በመሙላት የበኩላቸውን ሚና እንዲጫወቱ በዛሬው ዕለት በርዕሰ ጉዳዩ ዙሪያ  የግማሽ ቀን የአቅም ግንባታ ሥልጠና በኢንተር ሌግዠሪ ሆቴል ሰጥቷል፡፡   
በርካታ የሚዲያ ባለሙያዎች በተሳተፉበት በዛሬው ዎርክሾፕ ላይ፤ ከጤና ሚኒስቴር እንዲሁም ከኢትዮጵያ ምግብ እና መድሃኒት ባለሥልጣን የመጡ ባለሙያዎች ጥናታዊ ጽሁፍና ማብራሪያ አቅርበዋል፡፡  
በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ከፍተኛ ኤክስፐርት የሆኑት ዶ/ር ሙሴ ገ/ሚካኤል፣ “ጤናማ ያልሆኑ አመጋገቦች በጤና ላይ የሚፈጥሩት አሉታዊ ተጽዕኖና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች የሚያሳድሩት ኢኮኖሚያዊ ጫና” በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጥናት፤ ጤናማ ያልሆኑ አመጋገቦች ለስኳር በሽታ፣ ለካንሰርና ስትሮክ እንደሚዳርጉ አስረድተዋል፡፡ በቂ አትክልትና ፍራፍሬ አለመመገብ ለልብ ህመምና ለካንሰር የመጠቃት ዕድልን ይጨምራልም ብለዋል፡፡ በየሁለት ሰከንዱ አንድ ሰው ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች አማካኝነት ያለዕድሜው እንደሚሞትም ነው የጠቆሙት፡፡ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች በኢትዮጵያ ጤና እና ኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ከፍተኛ ስጋት መሆናቸው የተገለጸ ሲሆን ያለጊዜ ሞትና ህመም እንዲከሰት በማድረግ፣ የሃገሪቱን ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት በማዘግየት ትልቅ ጫና ማሳደራቸው ተመልክቷል፡፡ እ.ኤ.አ በ2017 ዓ.ም፣ 313 ቢሊዮን ብር  (ቀጥተኛና ቀጥተኛ ባልሆነ ወጪ) የኢኮኖሚ ኪሳራ መድረሱ ታውቋል፡፡ በልብና የደም ቧንቧ በሽታ 1.97 ቢ. ብር፣ በካንሰር 0.98 ቢ. ብር፣ በስኳር በሽታ 0.58 ቢ.ብር እንዲሁም ሥር በሰደዱ የመተንፈሻ አካላት በሽታዎች 0.85 ቢ.ብር እና በሥራ ላይ አቅም መቀነስና ሞት 26.9 ሚ. ብር ኪሳራ ደርሷል  ተብሏል፡፡ የዓለም ጤና ድርጅት፣ አገራት ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ለመቆጣጠር እንዲያስችላቸው “ቤስት ባይ” በሚል ካስቀመጣቸው የፖሊሲ ምክረ ሃሳቦች መካከል፡- ጤናማ ያልሆኑ ምግቦችን ለመቆጣጠር የሚያስችል አስገዳጅ ህግ ማውጣት አንዱ ሲሆን፤ ይህም በፋብሪካ የተቀነባበሩ ምርቶች የፊት ለፊት ማሸጊያዎች ላይ የሚቀመጡ የማስጠንቀቂያ ምልክቶች እንዲኖር ማስገደድ፤ የገበያ ቁጥጥር ማድረግ፣ የማስታወቂያ ገደብና ከፍተኛ ታክስ መጣል በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡
ከፍተኛ የጨው፣ ስኳርና ስብ መጠን ያላቸው የታሸጉ ምግቦች ላይ የሚቀመጥ የፊት ለፊት የማስጠንቀቂያ ምልክት ከሚጠቀሙ አገራት መካከል ቺሊ፣ አርጀንቲና፣ ብራዚልና ሜክሲኮ የሚገኙበት ሲሆን፤ ይህም መደረጉ ጤናማ ያልሆኑ ምግቦች ግዢ እንዲቀንስና ሸማቾች ጤናማ ምግቦችን መለየት እንዲችሉ አድርጓቸዋል ተብሏል፡፡
ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ሥርጭት መጠን በኢትዮጵያ  
•  በ2016 በተደረገ ጥናት፣ አንድ ኢትዮጵያዊ  ዋና ዋና በሚባሉት ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ያለዕድሜው ወይም ከ70 ዓመት በፊት የመሞት ዕድሉ 18.3 በመቶ ነው፡፡
•  እ.ኤ.አ በ2018 የዓለም ጤና ድርጅት እንዳስታወቀው፤ በኢትዮጵያ በልብና ደም ቧንቧ በሽታ፣ የሟች ቁጥር 47ሺ712 ደርሷል፡፡
•  እንደ “ግሎባል በርደን ኦፍ ዲዚስስ” ጥናት፤ ስትሮክ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ፣ 44 በመቶ ለልብና የደም ቧንቧ በሽታ ያጋልጣል፡፡
•  እ.ኤ.አ በ2019 ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች የተከሰተው ሞት 34.2 በመቶ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ 14 በመቶ በልብና የደም ቧንቧ፣ 12 በመቶ ሥር በሰደዱ የመተንፈሻ አካላት፣ 4 በመቶ ደግሞ በስኳርና ኩላሊት በሽታዎች ነው፡፡
(ምንጭ፡- “ጤና፣ ልማት እና ጸረ- ወባ ማህበር”)


 “ማር ሲሰፍሩ፤ማር ይናገሩ”

       ከ2010  ጀምሮ ኦርጋኒክ ማርና ሰም በከፍተኛ የጥራት ደረጃ  ለአሜሪካ፣ አውሮፓና ጃፓን ገበያዎች ሲያቀርብ የቆየው  ግሪን ፌስ ትሬዲንግ ኃ.የተ.ግ.ማህበር፤አሁን ደግሞ ኦርጋኒክ ማርና ሰም ለአገር ውስጥ ገበያ ማቅረብ መጀመሩን አስታወቀ፡፡
ድርጅቱ ሀሙስ ሚያዚያ 19 ቀን 2015 ዓ.ም ከ8፡30 ጀምሮ በኢሊሊ ሆቴል ባዘጋጀው የማብሰሪያ ሥነስርዓት ላይ “ማርደን” በሚል ሥያሜ ኦርጋኒክ ማርና ሰም፣ በፋብሪካው እያቀነባበረ፣ ለአገር ውስጥ ገበያ ማቅረብ መጀመሩን በይፋ አስተዋውቋል፡፡
ኢትዮጵያ ከዓለም  የመጀመሪያዎቹ አሥር የማር አምራቾች አንዷ ስትሆን፤ከአፍሪካ ቀዳሚዊ የማር አምራች እንደሆነች  ይታወቃል፡፡ ሆኖም የአምራችነቷን ያህል ማርን የመመገብ ባህል በአገሪቱ  አላደገም ተብሏል፡፡
በአገሪቱ ማር የመመገብ ባህል ያልዳበረበት አንዱ ምክንያት ተብሎ የተጠቀሰው፣ በከተማዋ ለሽያጭ የሚዘዋወረው ማር፣ ባዕድ ነገሮች ያልተቀላቀሉበት ንጹህ መሆኑን ማረጋገጥ ከባድ በመሆኑ ነው ተብሏል፡፡
በመርሃግብሩ ላይ የአገር ውስጥ የማር አቅርቦት ጥራትን በተመለከተ ጥናታዊ ጽሁፍ ያቀረቡት አቶ ተረፈ ዳምጠውም፣ በጥናታቸው ያረጋገጡት  ይህንኑ ነው፡፡
ይህንን ችግር በሚገባ የተገነዘበው ግሪን ፌስ ትሬዲንግ፤በአውሮፓ ስታንዳርድተመርምሮ ተቀባይነት ያገኘውን ንጹህ ኦርጋኒክ ማር በማምረት፣ የህብረተሰቡን ፍላጎት ለማሟላት፣ ለአገር ውስጥ ገበያ ማቅረብ መጀመሩ  ተነግሯል፡፡
 የግሪን ፌስ ትሬዲንግ ኃ.የተ.ግ.ማህበር መሥራችና ባለቤት አቶ ጆኒ ግርማ፤ በመርሃ ግብሩ መክፈቻ ላይ ድርጅታቸው፣ “ማርደን” በሚል ስያሜ፣ ኦርጋኒክ ማርና ሰም ለአገር ውስጥ ገበያ ማቅረብ መጀመሩን አብስረዋል፡፡
***
በነገራችን ላይ የመድረኩ አጋፋሪ፣ በየመድረኩ ከሚያጋጥሙንና የሚናገሩበትን ርዕሰ ጉዳይ ከማያውቁ ወይም ተዘጋጅተው ከማይመጡ ብዙዎች በእጅጉ ይለያል፡፡   ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ፣ በቅጡ ተዘጋጅቶና ተለማምዶ (Rehearse አድርጎ) መምጣቱን አለመመስከርና አለማድነቅ ንፉግነት ነው፡፡ የመድረክ አጋፋሪነቱን ማር ማር በሚሉ ተረቶችና ቀልዶች አሽሞንሙኑ ነው ያቀረበው፡፡ ሳቅ ብርቅ በሆነበት በዚህ ዘመን፤ ታዳሚውን ሁለት ሦስቴ ማሳቅ ድንቅ ችሎታ ይጠይቃል፡፡



Page 6 of 646