Administrator

Administrator

ተቃዋሚዎቹ ሙጋቤ ስልጣን እንዲለቁ ጠይቀዋል

   የዚምባቡዌ መንግስት ለሰራተኞቹ ደመወዝ መክፈል አልቻለም፤ የአገሪቱን ኢኮኖሚም ወደ ከፋ ቀውስ እየከተተው ነው በሚል የተቀሰቀሰው ተቃውሞ እየተባባሰ መምጣቱንና በመዲናዋ አብዛኞቹ አካባቢዎች የንግድ፣ የትራንስፖርት፣ የጤና፣ የትምህርት አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ መቋረጡን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
የአገሪቱ መንግስት የዶላር እጥረት በማጋጠሙ ከደቡብ አፍሪካ ይገዙ የነበሩ የመሰረታዊ ሸቀጦችን ግዢ መከልከሉን ተከትሎ ባለፈው አርብ ቢትብሪጅ በተባለቺው የአገሪቱ የድንበር ከተማ የሚገኙ ነዋሪዎች ተቃውሞ ማሰማታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው ማክሰኞም በርዕሰ መዲናዋ ሃራሬ የታክሲ አሽከርካሪዎች አደባባይ ወጥተው ተቃውሞ ማሰማታቸውንና ይሄን ተክትሎ ፖሊስ 113 አሽከርካሪዎችንና የተቃውሞው ተሳታፊዎችን ማሰሩ ብዙዎችን ማስቆጣቱንና ተቃውሞውን ማባባሱን ገልጧል፡፡ባለፈው ረቡዕም ደመወዛችን አልተከፈለንም ያሉ የአገሪቱ መምህራንና የጤና ባለሙያዎች የስራ ማቆም አድማ በማድረግ ተቃውሞውን መቀላቀላቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በሃራሬ ሆስፒታሎችና ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸውንና በመዲናዋ ከፍተኛ ውጥረት መንገሱን አስረድቷል፡፡አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ በበኩሉ፤የሮበርት ሙጋቤ መንግስት ባጋጠመው የኢኮኖሚ ድቀትና የገንዘብ እጥረት ሳቢያ ለመንግስት ሰራተኞች መክፈል የሚገባውን ደመወዝ ከሚገባው ጊዜ ማዘግየቱን በመጥቀስ፣ በመንግስት ላይ ይደረጉ የነበሩ ተደጋጋሚ ተቃውሞዎች ሰሞኑን ተባብሰው መቀጠላቸውንና ፕሬዚዳንት ሙጋቤ ስልጣን እንዲለቁ እስከመጠየቅ መድረሱን ዘግቧል፡፡የአገሪቱ መንግስት የገንዘብ እጥረት በማጋጠሙ ሳቢያ ያልከፈለውን ደመወዝ በስራ መስኮች ከፋፍሎ በቀናት እድሜ ውስጥ ለመክፈል ቃል በመግባት ዜጎቹ ተቃውሞውን አቋርጠው በትዕግስት እንዲጠባበቁ ጥሪ ቢያደርግም፣ ተቃውሞው ከቀን ወደ ቀን እየተባባሰ መቀጠሉን ያመለከተው ዘገባው፤ተቃዋሚዎች ጎዳናዎችን በመዝጋትና ጎማ በማቃጠል ድርጊቶች ላይ መሰማራታቸውንና የአገሪቱ ፖሊስም አስለቃሽ ጭስ መጠቀሙንና በርካቶችን ማሰሩን ገልጧል፡፡


ቻይና በዓለማችን የቴሌስኮፕ ኢንዱስትሪ ታሪክ በትልቅነቱ ቀዳሚውን ስፍራ እንደያዘ
የተነገረለትንና 180 ሚሊዮን ዶላር ወጪ የተደረገበትን እጅግ ግዙፍ ቴሌስኮፕ ግንባታ
ሙሉ ለሙሉ ማጠናቀቋን ሮይተርስ ዘገበ፡፡ ለምድራችን ባዕድ የሆኑ ፍጡራንን በተመለከተ በሚደረጉ ሳይንሳዊ ምርምሮች ላይ መረጃዎችን ለማሰባሰብ ታስቦ በቻይና ብሄራዊ አስትሮኖሚካል ኦብዘርቬሽን ተቋም የተሰራው ይህ ቴሌስኮፕ፣ስፋቱ የ30 የእግር ኳስ ሜዳዎችን ስፋት  ንደሚያክል የተነገረ ሲሆን ግንባታውን ለማጠናቀቅ አምስት አመታት ያህል መፍጀቱ ተዘግቧል፡፡ ይህ ሬዲዮ ቴሌስኮፕ የሬዲዮ ሞገዶችን ከህዋ እያሰባሰበ ወደ አንድ የምርምር ማዕከል የሚያስተላልፍ ሲሆን መጠኑ ትልቅ መሆኑም ከዚህ ቀደም ከተሰሩ ቴሌስኮፖች በበለጠ ሁኔታ፣ እጅግ ያነሱ ሞገዶችን ሳይቀር  መለየት እንደሚያስችለው ተነግሯል፡፡ ከዚህ ቀደም በአለማችን ትልቁ ቴሌስኮፕ የነበረው
በፖርተሪኮ የሚገኘው አርሴቦ ኦብዘርቫቶሪ የተባለ ቴሌስኮፕ እንደነበር ያስታወሰው
የሮይተርስ ዘገባ፣ አዲሱ የቻይና ቴሌስኮፕ ግን ከቀድሞው በአምስት እጥፍ ያህል ግዙፍ
እንደሆነ አስረድቷል፡፡ በደቡብ ምዕራባዊ ቻይና በምትገኘው ጉዚሁ አውራጃ ውስጥ የተተከለው ይህ እጅግ ግዙፍ ቴሌስኮፕ፤በመጪው መስከረም ወር በይፋ ስራ ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

(በተለይ ለአዲስ አድማስ )

* የደርግ አባሎችና ርእሰ ብሔር የነበሩ    ፍርዳቸውን ፈጽመዋል  
* መኢሶንና ወዝሊግን ከተከሳሾች መዝገብ    ውስጥ እናስወጣ
* መንግስቱ ኃይለማርያምን ለፍርድ ማቅረብ  ይኖርብናል  
* ኢሕአፓ ደርግን መክሰስ ሙሉ ስራው   አድርጎታል
ለሁለት አስርት ዓመታት ነዋሪነታቸውን በአሜሪካ ያደረጉት የህግ ባለሙያውና ፖለቲከኛው አቶ አሰፋ ጫቦ በቅርቡ ለንባብ ያበቁት ፖለቲካ - ቀመስ መፅሃፋቸው “የትዝታ ፈለግ” ተወዳጅነትን አግኝቶላቸዋል፡፡ አቶ አሰፋ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ በኢ-ሜይል ለቀረበላቸው የተለያዩ ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
መፅሐፍ ለማሳተም እስከ ዛሬ ለምን ዘገየህ?
ዘገየህ የሚባል ነገር ያለ አይመስለኝም። በየጋዜጦችና መጽሔቶች በየዘመናቱ የወጣው ተሰባስቦ መጽሐፍ ይሆናል ብዬ አስቤም አላውቅም። ስብስቡም አልነበረኝም። የነበረኝም አንዴ ሎስ አንጀለስ የምኖርባት አፓርትመንት ጣራው ላይ ቧንቧው ፈንድቶ፣ እንደ ጽሕፈት ቤት የምጠቀምበት ክፍል ኮምፒዩተሬንም ጭምር ጨርሶ በላው። የዚህ መጽሐፍ የማድረጉን ሐሳብ ያመነጩት “ያንተን ጽሁፍ እያነበብን ነው ያደግነው!” የሚሉ ወጣቶች ናቸው። አሁን በFacebook ጭምር እንደዚያ የሚሉ ቁጥራቸው ብዙ መሆኑን ተረዳሁ። እንዳለጌታ ከበደና ወሰንሰገድ ገብረኪዳን እዚያው ውስጥ ቅድሚያ ያላቸው ናቸው።
 መቼ፤ ምን ብዬ ጽፌም እንደነበር ያው ከናንተው ጋር ወይም ትንሽ ቀደም ብዬ ነው ያነበብኩት። ሳነበው “እፎይ!” አልኩኝ። “ምነው ባላልኩት!” የምለው ነገር አላገኘሁበትም። ሊጠራ፤ሊሰፋ፤የበለጠ ሊብራራ የሚገባው ሞልቷል፡፡
ቀደም ሲል በተለያዩ የፕሬስ ውጤቶች ላይ ትጽፍ ነበር፡፡ አሁን ግን ከሚዲያ ተሳትፎ እየራቅህ መጥተሃል?
Self-Evident Truth የሚባል አለ። ”የታወቀ ፤የተረጋጋጠ፤ተጨማሪ ማስረጃ አቅርብበት የማይባል!” ለማለት ነው። ለምሳሌ፤አሰፋ ጫቦ ለመሆኔ ማስረጃ ያስፈልጋል። ማስረጃው መታወቂያዬ ነው። ሰፈራችን ውስጥ ሁሉም ሰው ሊያውቀኝ ይችላል። ያ ሌላ የሰፈር፣የመንደር ነገር መሆኑ ነው። አዲስ አበባ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ለመሆኑ ግን ማስረጃ አቅርብ አልባልም። “ምነው?; ቢሉ “አገር ያወቀው ፀሐይ የሞቀው ዕውነት!” ነዋ። “ከሚድያ ተሳትፎ እየራቅህ የመጣኸው ለሚለው ጥያቄ፣ ርቄ ከሆነ ተጠያቂው እኔ ሳልሆን ሜዲያው ነው። ሚዲያው ነው የራቀኝ። ግልጽ ለማድረግ ማራራቅ የሚችሉ ኃይሎች ሚዲያውን ከኔም፤ከሁላችንም አራራቁትና ቦታው ኦና ወይም ወደ ኦናነት ተጠጋ። ጦቢያ፣ኢትኦጵ፣ምንሊክ …ወዘተርፈ የሚባሉት መጽሔቶች፣ መተንፈሻ የነበሩ መድረኮች ተዘጉ። አዘጋጆቹም፤ከርቸሌ ተቀረቀረባቸው። የተረፉትና እድለኞቹ ተሰደዱ። ድረ-ገጹ ሚዲያ ነው ከተባለ ደግሞ ለራሴ ገና ጠርቶ ያልወጡ የውስጥ ማእቀቦች ያሉብኝ ይመስለኛል። የመጀመሪያው፣“ለመሆኑ ስንቱ ኢትዮጵያዊ ነው ከድረገጽ ላይ የሚያነበው?” የሚለው ነው። አብዛኛው፣ ማንበብ የሚችለው ማንበብ ካልቻለ የተመጋቢው ቁጥር በጣም የተመጠነና አብዛኛው የኔቢጤዎች አካባቢ የሚንገዋለል ነው የሚመስለኝ። የሚመስለኝ ማለቴ የተጠና ነገር ስለሌለኝ ነው። ሌላው በአብዛኛው ድረገጽ ላይ፤በተለይም በእንግሊዝኛው የማነበው ብዙም ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ አይሸትም የሚለው ፍርሐቴም ሊሆን ይችላል። በኢትዮጵያ ስም የሌሎች አገሮች፤ ህግ፣ ባሕል፤ ስነ-መንግስት፤ታሪክ ሲያመጡ ስለማይ፣ እዚያ ውስጥ የገባሁ እንደሆነ፣ “ውሃ ሲወስድ እያሳሳቀ ነው!” እንደሚባለው እኔንም እዚያ ከቶ ተመሳሳይ ዕጣ ፈንታ እንዳይደርሰኝ  የሚልም ፍርሐት አላጣም። ሌላው፣በሌላ ጊዜ፣በሌላ ቦታ (መድረክ) አንስቼው የነበረ ነው። ሱባዔ ገብቼ ስለነበር ነው። ራስን ፍለጋ (Introspection) ሊባል የሚችል ይመስለኛል። ከዚያ ስመለስ (ስወጣ) ብዙም የተናገርኩ፣ብዙም የጻፍኩ ስለሚመስለኝ ተመልሻለሁ ብዬ አስባለሁ።
በጽሑፎችህ ብዙ ጊዜ ስለ ትውልድ አካባቢህና የተወለድክበት ማህበረሰብ  ዙሪያ ታተኩራለህ የሚሉ አስተያየቶች ይሰነዘራሉ። አንተ ምን ትላለህ?
“የትውልድ አካባቢህ ላይ ታተኩራለህ?” ይህ ብዙ የሚያነጋግር ይመስለኛል። በተለይም በአሁኑ፣“ሁልህም ወደ ክልልህ!” በተባለበት ዘመን። “አንተም ክልልህ ውስጥ ነህ ለካ!” የሚል አንድምታም የሚያጣ አይመስለኝም። ያም ሆነ ይህ እኔ በዚህ ጉዳይ ላይ የትዝታ ፈለግ ላይ ያልኩት አለኝ። “እኔ ጋሞ ነኝ! እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ! እነዚህ ሁለቱ ተጣልተውብኝ ሳስታርቃቸው አልኖርኩም!” የሚል ነው። እኔ እንደማስበው ቁምነገሩ ትውልድ አካባቢ ተተኮረ አልተተኮረ አይመስለኝም። መሆን ያለበት፤ “አተኳኮሩ ጤነኛ ነው ወይ?” የሚለው ይመስለኛል። ጤነኛ ያልሆነ አመለካከት ሕገመንግሥት ደረጃ የደረሰበት ዘመን ውስጥ ነው ያለነውና ከጥያቄው በስተጀርባ ያለው “ጠርጥር!” ይገባኛል። ይህን በዚህ እንዝጋው።
SBS በሚባል ካሳሁን ሶቦቃ በሚያዘጋጀው አውስትራሊያ ባለ ራዲዮ ጣቢያ፤ስለ የትዝታ ፈለግ ስንወያይ፣ “አንተ እንደኔ እንደኔ ሁሉም ኢትዮጵያ እንደ ጋሞ በሆነ ትላለህ!” ብሎኝ፣ ያንን ምን እንዳሰኘኝ አስረድቼ ነበር። SBS ስብስብ (Archive) ስለአለው ቢቻል ያንን ማዳመጡ ጥሩ ይመስለኛል።
ይህ ጥያቄ ሌላም፤ስብሐት ኃይለማርያምንና ማእከላዊንም፤አስታወሰኝ። ስብሐት የባኮ ልጅ ነው። ባኮ ከጅንካ በፊት የገለብና የሐመር ባኮ አውራጃ ይባል የነበረው ዋና ከተማ ነበር። ስብሐት ከብላታ ኃይለማርያም ልጆች ውስጥ አንዱ ነው። ብላታ ኃይለማርያም ደግሞ የመጀመሪያው ወያኔ መስራችና መሪ የነበሩ ናቸው። በዚያ ተከሰው የኃይለ ሥላሴ መንግስት አግዟቸው የኖሩትም፣ልጆቻቸውንም የወለዱትም ባኮ ነው። ደርግ በምህረት ሲለቃቸው፣ አገር አስተዳደር ነበርኩና ብላታ ኃይለማርያን ለአፍታ አነጋግሬአቸው ነበር። ስብሐት የታሰረው በወያኔነት ተጠርጥሮ ነበር። ስብሐት በወያኔነት ታስሮ ግን “የአገሩ ልጅ፤የጋሞ ጎፋ ልጅ!” ብሎ የሚቀርበኝ እኔን ነበር።
አንድ ቀን በረንዳው ላይ ቆመን፣ ያለ የሌለን ስናወራ፣ የጢስ አባይ ፏፏቴ ተነሳ፣ እኔም ጢስ አባይን አውቀው ነበርና፤ሌሎችም ጨምረውበት በማድንቀ፣ስብሐት ቱግ ብሎ፤ “የኛ ይበልጣል! ስላላያችሁት፤ስለማታውቁት ነው እንጅ ባኮ ያለውን ፏፏቴ የሚያስንቅ የትም የለም!” አለ። ”የኛ ይበልጣል!” ነው ያለው። ስብሐት ኃይለማርያም አገሩ፤ተቆርቋሪነቱ ለባኮ፤ብሎም ለጋሞ ጎፋ መሆኑ ነው። ከባኮ፤ከጋሞ ጎፋ ጋር መንፈሱ፣ነፍሱና ስጋው ተዋህደዋል ልንል እንችላለን።
ከስብሐት ሌላ ብዙ ምሳሌዎች ልጠቅስ እችላለሁ። አንድ የሚደንቅ የአማራን ነገር ማንሳት እፈልጋለሁ። በግራኝ ወረራ ጊዜ ታቦታቸውን ይዘው የሸሹ አማሮች ከየትም በላይ ወደ ጋሞ ጎፋ በብዛት የመጡ ይመስለኛል። ለዚህ ማስረጃው የአባ ባህርይ የብርበር ማርያም፤የዶርዜ ጊዮርጊስ፤የኤሌ ገብርኤል አሉ። ጋሞ “ቆሞ” የሚለው ራሱን የሚለይበት መጠሪያ አለው። ክላን (clan) የሚሉትን የእንግሊዝኛው ቃል ይገልጸው እንደሁ እንጃ። ወደ 10 ቆሞ አለ። ከነዚህ 10 ቆሞዎች አንዱ አማራ ነው። አሁን ዶርዜ ሄደው አማራ የት ነው ቢሉ ማንም ያሳያል። የዶርዜ ጊዮርጊስ አጥቢያው ዶርዜ አማራ ነው የሚባለው። የኤሌ ገብርኤል አጥቢያውም ኤሌ አማራ ነው የሚባለው። የጋሞ አማራ የሚለው ቃል አጠራሩ በመሠረቱ እንደሚባለው ሳይሆን ቅላጼው ለየት ይላል። ”ማ’ እና “ራ” ላይ ላላ፤ለቀቅ ይላል። ይህ እንግዲህ ወደ 400 አመት የሚደርስ ታሪክ መሆኑ ነው።
በኔ ግምት ምናልባትም ከየትኛውም አለም በላይ፤በኢትዮጵያም አንጻር ሲታይ፣ ብዙ ብሔረሰብ ያለበት አካባቢ ቢኖር ጋሞ ጎፋ ነው። አሜሪካኖቹ አሜሪካንን Melting Pot ይሉታል። ማቅለጫ ድስት (ሰታቴ) እንደማለት ነው እንበለው። እዚህ የመጣው ህዝብ ሁሉ ቀልጦ አንድ አሜሪካዊ ሆኗል ለማለት ነው። ወረቀት ላይ አንድ ሆኖ እንደሁ እንጅ በድርጊት አሁንም ፈንጠር ፈንጠር ብሎ እንደቆመ ነው። ሰው ቀልጦ ወደ አንድ ሸማ መልበስ የደረሰበት አካባቢ ቢኖር ጋሞ ጎፋ ነው ማለት የምችል ይመስለኛል። “አሻም!” የሚል ሕዝብ ነው። አሻም ከአማርኛው “እንኳን ደህና መጡ!”፤ከእንግሊዝኛው “Welcome” ከፈረንሳይኛም “Beinvenue” ለየት የሚል የማቀፍ ቃና ያለው አቀባበል ነው። ዛሬ በመላው ኢትዮጵያ ባለ- በሌለ፤ከፋብሪካ በወጣ ክስ-ውቅስ ጭምር ያ ሁሉ ንትርክ ሲታይ፣ በአንጻራዊ አነጋገር እጅግ ሰላማዊ አካባቢ ደቡቡ፤በተለይም ጋሞ ጎፋ ነው። ታዲያ ያንን ታሪክ፤ያንን ባህል፣ ይህንን ተመክሮ ለመላው ኢትዮጵያ ለማሳወቅ፤ቢቻልም ለመላው አለም ለማዳረስ የኔ ሙከራ ቅንጭብ (The Tip of the Iceberg) ነች ማለት ነው።
ሌላ ስለ ጋሞ ደጋ የውጭ አጥኝዎችም ብዙ ያሉት አለ። “A Thousand Suns: The View From Ethiopia’s Gamo ...” የሚለውን ፊልም መመልከቱ/ማየት ጋሞ ለስንት ዘመናት፤የመሬት ጥበቃን ስርዐት የያዘ እርሻ ሲያርስ የኖረ ሕዝብ መሆኑን እናያለን። የቋንቋ አጥኝዎች፤የውጭም የኢትዮጵያም የአፍሪቃና የአዚያ ህዝቦች ቋንቋ (Afroasiatic Languages) የሚሉት አለ። ይህ ቋንቋ ቤተሰብ ከሲዳማ እስከ ወለጋ እስከ ባምባሲ የሚዘረጋ ነው። ዝነኛውን የከፋን ንጉሳዊ ግዛትም የሚጨምር ነው። ምናልባትም የዚህ ህዝብ ዋና ቤቱ ጋሞ ሊሆን ይችላል የሚል አዝማሚያ አለ። በቅርቡ ክ4,500 አመት በላይ የሆነ የሰው አፅም ቅሪት ከጋሞ ደጋዎች ተገኝቷል። ”ባይራ!”ብለዉታል። ባይራ ማለት ታላቅ ማለት ነዉ። ይህ ጥንታዊ፣ የሰለጠነና ዘመናዊ የእርሻ ዘይቤ ነበራቸው/አላቸው ከሚባለው ጋር ተደምሮ፣ ጋሞ ጎፋን እንደ ጋና አትኩረን ለማየት የሚጋብዝ ይመስለኛል።
አብዛኛው የናንተ ዘመን ፀሐፊዎች ያለፈ ስርአትን ወቃሽ ናቸው። በየዘመናቱ በነበሩ መንግስታት የተሠሩ በጐ ነገሮችን ለማንሳት ለምን አይሞከርም?
በክስ-በውቅስመልክ መቅረቡ ንጅ ታሪክ የሚባለው’ኮ ያለፈን፣ማብጠልጠል፤ማበራያት፤ፍሬውን ከገለባው፣እውነቱን ከፖለቲካውና ከተረቱ ለይቶ አብጠልጥሎ ማውጣት ይመስለኛል።
 መውቀስ ካልነውም መላ ያለው፤ማስረጃ ያለው ወቀሳም ጥሩ ይመስለኛል። ጅምላ ወቀሳ ከሆነ ደግሞ ወቀሳውንም ወቃሹንም ከፍቶ ማየቱ ጥሩ ይመስለኛል።
ማለትም፣ “ለመሆኑ አንተ ማነህ?”፣ “ከነማን ጋር ነበርክ?”፣ ”ያኔስ የት ነበርክ?”፣ “ምን ምን ሰራህ?”፣ “ምን ምንስ መስራት ሲገባህ ሳትሰራ ቀረህ?”፣ ”በምን ምክንያት?”፣ “ሌላው አይን ውስጥ ያለውን ትቢያ ማሳየት ብቻ ሳይሆን አንተስ አይን ውስጥ የተጋደመውን ግንድ ምን እናደርገው?” ማለቱ ጥሩ ይመስለኛል።
“የእናንተ ዘመን ጸሐፊዎች” ሲባል እኔ እንደሚገባኝ ይህንን፤በ1950ዎቹ አጋማሽ ጀምሮ ያለውን፤የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ተብሎ የሚታወቀውን፤በአሜሪካና በአውሮጳም ቅርንጫፎች የነበሩትን፤ዘውዱ ወርዶ ከደርግም ጋር ጎራ ለይተው የተፋለሙትንና የተላለቁትን፣አሁንም በርዝራዥ መልክም ቢሆን መንግስት የሆኑትና ተገፍተው ወጥተው ዳር ቆመው “እኔ/ እኛ አይደለንም፤ እነሱ ናቸው!” የሚለውን የምናስተጋባውን ይመስለኛል።
ተከሳሹ ሁሌም ደርግ ነው። ሻዕቢያ፤በወያኔ አማካኝነት “ኤርትራ የኢትዮጵያ ቅኝ ግዛት ነበረችና አሁን ነጻ ብትወጣ እደግፋለሁ!” የሚል ደብዳቤ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጽፈው ነጻ ወጥተዋል። ስለዚህ ሻዕቢያ ዛሬ፣በአሁን የክሱ ችሎት ውስጥ የለም። የቀሩት ከሳሾች በጋራም ሆነ በተናጠል የሚከሱት ደርግን ነው።
ይህንን የደርግን ተከሳሽነት በሕግ አንጻር እንየው። አንድ ተከሳሽ ፍርድ ቤት ቀርቦ፤ ጉዳዩ ተሰምቶ፣ ፍርድ ከተሰጠበትና በፍርዱ መሠረት ቅጣቱን ተቀብሎ ከፈጸመ የድርጊቱን ከፍሏል ማለት ነው። የደርግ አባሎችና ርእሰ ብሔር የነበሩ ብቻ ሳይሆን ከደርግ ጋር ነበሩ የሚባሉ፤በወያኔ ቋንቋ ንክኪ የሆኑ ሁሉ ታስረው፣ ማቀው፣ ፍርዳቸውን ፈጽመው ተለቀዋል። መሪዎቹ የሚባሉት የተለቀቁት ከ20 አመት በኋላ ነበር። ብዙዎቹ ከርቸሌ ነበር የሞቱት። ይህም ማለት በክስ መልክ የደርግ ፋይል እስከ ወዲያኛው ተዘግቷል ማለት ነው። ደርግን አሁን መክሰስ፣ እዚህ እኔ ያለሁበት አገር Double Jeopordy ይሉታል። ለዚያው ወንጀል ሁለቴ መክሰስ እንደ ማለት ነዉ። ሕግ አይፈቅድም! ከአሁን በኋላ የደርግ ነገርና ዘመን የሚያገለግለን ለሰከነ የታሪክ ጥናትና ምርምር ብቻ ነው። የደርግ ከሳሾች፤ ይህንን ልብ ሊሉ ይገባል፡፡ ”እስከ ሰባት ትውልድ እበቀልሀለሁ!” ኦሪት ነው። ሐዲስ ተክቶታል! ይልቁንም ለዚህ ሁሉ ክስና- ውቅስ በአብዛኛው የዳረገንን ፤መንግስቱ ኃይለማርያምን እንዴት አድርገን ፍርድ አደባባይ እናድርስ የሚለውን ብንመክርበት የተሻለ ይመስለኛል።
መኢሶንና ወዝሊግን ከተከሳሾች መዝገብ ውስጥ ማስወጣት ያለብን ይመስለኛል። ቀይ ሽብር ነጭ ሽብር ተብሎ የኢትዮጵያን ቀጣይ ትውልድ በፈጀውና የደርግ አባላትንም እርስ በርስ በማባላት የተጫወቱትን ሚና ሌሎች የጻፉት እንደተጠበቀ ሆኖ፤ ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስና ፍስሀ ደስታ ደህና አድርገው ገልጠዉታል። ያም ሆኖ፣ መኢሶኖች በተለየ አይቀጡ ቅጣት ተቀጥተዋል። መንግስቱ ኃይለ ማርያም፤የመኢሶንን መሪዎች አርዷቸዋል። ከዚህ በላይ የሚከፈል ዋጋ ሊኖር ስለማይችል፣ ከደርግ ጋር በማበር የፈጸሙትን ወንጀል መዝገብ ዘግተን፣ ወደ መዝገብ ቤት በቋሚነት መመለስ ያለብን ይመስለኛል። አሁን ያለው ትንሹ ችግር በሕይወት የተረፉት ይህንን የክስ መዝገብ ያልዘጉ መሆናቸው ነው። ስለ ኢትዮጵያ ፖለቲካ ለምን ተናገሩ? ለምንስ ይናገራሉ? አይደለም። ንስሀ መግባት ግን አማራጭ ያለው አይመስለኝም።
አሁን የሚቀሩን ሁለት ፤ሙሉ ሥራቸውና ከፊል ሥራቸው ወቃሽ የሆኑ ናቸው። እነሱም ኢሕአፓና ወያኔ ናቸው። ኢሕአፓ ደርግን መክሰስ ሙሉ ስራው ማድረጉ ብቻ ሳይሆን አዲስ፣ ደርግንም ኢሕአፓንም የማያውቁትን አሰልጥኖ፣ በከሳሽነትና-ወቃሽነት አሰማርቷል። እዚህ አሜሪካ፤ “እገሌ በደርግ ጊዜ ቀበሌም….እዚህም… እዚያም ነበር” እንዲሉ ስራ የተሰጣቸው እድሜያቸው 30ው ውስጥ የሆኑ አሉ። ለመጭው ትውልድ ውርስ መሆኑ ነው። ስለ ደርግ መጥፎነት፤ስለ ኢሕአፓ መስዋእትነት እንጅ የነገሯቸው ሙሉ እውነት የለም። ቢያንስ ከነዚህ አንዱን “ለመሆኑ ስለ ኢሕአፓ ምን ምን ታውቃለህ?” ብዬው ነበር። “ለኢትዮጵያ የቆመ ብቸኛው ድርጅት; መሆኑን ብቻ እንጅ ሌላ ምንም የሚያውቀው አልነበረም። “ጌታቸው ማሩን ታውቀዋለህ?” አያውቀውም።
ያ እንዳለ ይሁን እንበል። ከሁሉም በላይ ግን የኢሕአፓ ሙሉ ለሙሉ ያልተወራረደ ሂሳብም አለ’ኮ። በዚያ ይባስ ብሎ ደግሞ ሂሳቡን ሊያወራርዱ የሚችሉ ከመሪዎች ውስጥ የተረፉ፣ በሕይወት ያሉት ሁለቱ፤ክፍሉ ታደሰና እያሱ አለማየሁ ብቻ ይመስሉኛል። እንደምገምተው፤ሁለቱም እድሜያቸው እንደኔው 70ው ውስጥ ይመስለኛል። “ለንስሀ ሞት አብቃኝ!” የሚባልበት እድሜ መሆኑ ነው።
እንደሚታወቀው የኢሕአፓ አስኳሉ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ማህበር (አአዩተማ) ነበር። እኔም እዚያው ነበርኩ። ማሕበሩ የተሰባሰበው በሁለት ሰንደቆች ዙሪያ ነበር። እነዚህም ፡-1. የዘውድ አገዛዝ ይብቃው (ይውደም) 2. መሬት ላራሹ ነበሩ።
መስከረም 2,1967 የዘውድ አገዛዝ በኢትዮጵያ ለአንዴም ለዘለዓለምም አከተመ። የካቲቲ 25,1967 የገጠር መሬት አዋጅ ታውጆ፣ መሬት ላራሹ ሆነ። የአአዩማ ጥያቄ መልስ አገኘ ማለት ነው። የቀረ የሚሟላ የለም ማለት አይደለም። የትግላችን እምብርት ጥያቄ የነበረው መልስ አግኝቷል ማለት ነው።እስቲ አሁን ደግሞ ኢሕአፓ ያደረጋቸውን፤በግልጽ በራሳቸው በተለይም በመሪዎች በክፍሉ ታደሰና በብርሐነ መስቀል ረዳ ከተነገሩን ብቻ ልጥቀስ።በኋላ የኢሕአፓ መሪ የሆኑት ብርሐነ መሰቀል ረዳና እያሱ አለማየሁ፤ ፈር ቀዳጅ ሁነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን ጠላፊዎች ነበሩ። ከዚያ በኋላ ሌላ 4 ጊዜ ተጠለፈ። አምስቱንም ጠላፊዎች ያቀነባበረው ጀበሀና ሻአቢያ ነበረ። ይህንን የሚነግረን ክፍሉ ታደሰ “ያ ትውልድ” በሚለው መጽሐፉነው።
ኢሕአፓ ትግራይ ውስጥ፣ አሲምባ የሚባል ቦታ ምሽግ የከፈቱት የካቲት 25 ቀን 1967 ነበር። ይህንን የሚነግረን ብርሐነ መስቀል ነው። መሬት ላራሹ ያሉት፣ መሬት ላራሹን ያወጀን መንግስት ለመውጋት ጫካ የገቡበትን ቀን ልብ ይሏል። (መሬት ለአራሹ) የታወጀ ለት ነበር!) ለሁለት አመት ያክል አስልጥኖ፤መሳሪያ አስታጥቆ፤ስንቅ ሰንቆ አሲምባ ያስገባቸው ሻቢያ ነበር።
ክፍሉ እንደሚነግረን፤ ሶማሌያ ከሲአድ ባሬም ጋር ነበሩ። ሶማሌ ኢትዮጵያን ስትወር፣ የኢትዮጵያን ወታደር ከውስጥ በ5ኛ ረድፈኝነት ወግተዋል። የገጠር መሬት አዋጅን ስራ ላይ ለመተርጎም የዘመተውን በትነዋል። በመላው ኢትዮጵያ ከተማ ከሕጻን እስከ አካለ ስንኩል (የምኒልክ ትምህርት ቤት ዲሬክተር) በየመንገዱና በየቢሮው ገድለው ጥለዋል። የመድኃኔአለም ትምህርት ቤት ተማሪ ሰቅለዋል። ቀበና ወንዝ ውስጥ ፈጥፍጠው ገድለዋል። ጌታቸው ማሩን መግደል ብቻ ሳይሆን በአሲድም አቃጥለዋል። ጫካ ለውጊያ ያሰማሯቸውን፤ይርጋ ተሰማን ጨምሮ በመቶ የሚቆጠሩ፣መጀመሪያ እስኪቀምሉ ጉድጓድ ውስጥ አስረው አማቀው፣በመጨረሻም ረሽነዋቸዋል። የገደሉትን ሰው ቁጥር በከፊልም ቢሆን ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስ በመጽሐፉ ገልጾታል። ኢሕአፓ ከሻቢያም ብቻ ሳይሆን የወያኔ ተባባሪ፣ዛሬም የኢህዴግ አባል ነው። የመጀመሪያው የኢህአዴግ ጠቅላይ ሚንስቴር ፤ታምራት ላይኔ፤ምክትል ጠቅላይ ሚንስትሩ አዲሱ ለገሰ ኢሕአፓ የነበሩ ናቸው። አሁን ብአዴን ሆነናል የሚሉት አክሮባቲክስ አንደተጠበቀ ሆኖ።ይህ ያልተዘጋ ቁስል ነው። መልስ የሚፈልግ ነው። ኢሕአፓ ደርግም ላይ ሆነ ወያኔ ላይ ጣቱን ከመቀሰሩ በፊት ለዚህ ክፍት ለተቀመጠ ቁስላችን መዝጊያ መስጠት ያለበት ይመስለኛል። (እናም ኢሕአፓ ውስጥ ያለችው “ኢ” ኢትዮጵያ መሆንዋ ነው።) በዚህ ድርጊታቸው ውስጥ ለመሆኑ ኢትዮጵያ አለችበት የሚለውም ጥያቄ መልስ የሚሻ ይመስለኛል።የወያኔ ጉዳይ በመሠረቱ ህግ ውስጥ Mutatis mutandis የሚሉትን አይነት ይመስለኛል። በግዕዙ ዚኒ ከማሁ የሚባለው ነው። አነሰም በዛ ከላይ እንደተገለጸው እንደ ማለት ነው። ይህም ማለት ቀደም ሲል ስለ ኢሕአፓ ያልኩት ለወያኔም ያገልግላል። ለምሳሌ፣ ወያኔ የተነሳው፣የተመሠረተው ከደርግ መጥፎ አገዛዝ ነጻ ለመውጣት አይደለም። ደርግ አልነበረምና አይተዋወቁምና ነው። ደርግ ንጉሱን በማውረዱ በተፈጠረው ክፍተት ትግራይን ነጻ ለማውጣትና የትግርይን ሬፑብሊክ ለመመስረት ነው። የመጀመሪያው የእነብላታ ኃይለ ማርያም ቀጣይ መሆኑ ነው። ይህ ሰነዳቸው የሚመስከረው ነው።
ንፁህ ህዝብም ሆነ ወይም ተቃዋሚ ነው ተብሎ የተፈረጀ በመፍጀት ከኢሕአፓ ቢበልጡ እንጅ አይተናነሱም። ልዩነቱ (እስከ 1983 ግንቦት መሆኑ ነው) የወያኔ አባሎቻቸው በነበሩትም ሆነ በሕዝብ ላይ የተፈጸመው ግፍ ከኢሕአፓ የሚለየው ትግራይ ውስጥ ብቻ በመሆኑ ነበር። ----- አንድ ነገር ልብ ብንል የሚሻል ይመስለኛል። ባለፈው ወር የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን፣ በኤርትራ ጉዳይ ያቋቋመው ቡድን፣ስለ ኤርትራ መንግስት የሰጠውን ሰፊ ሪፖርት ልብ ይሏል። ያ ሠነድ ሲታይ፣ስለ ኢትዮጵያ ጭምር ይሆን? የኢትዮጵያ መንግስትን ከዚያ ውስጥ የሚመለከተው ክፍል ስንት እጁ (%) ነው? የሚል ጥያቄ መነሳት ያለበት ይመስለኛል፡፡

    ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት አሮጊት ከእንቅልፋቸው ሲነቁ የማይታመን ነገር አዩ፡፡ ግቢያቸው በጎርፍ ተጥለቅልቋል፡፡ ውሃው የምድር ቤቱን አጥለቅልቆ ጨርሶ የመጀመሪያውን ፎቅ ሞልቶታል፡፡ አሰቃቂው ነገር ደግሞ ከደቂቃ ደቂቃ፣ ከሰዓት ሰዓት ገና ማጥለቅለቁን እየቀጠለ፣ እያደገ ነው፡፡
አሮጊቷ ከመኝታ ቤታቸው ወደ ውጪ ሲያስተውሉ፣ ጎርፉ ገና ካፋፍ ወደ ታች እየተንደረደረ ነው፡፡ ከፍታውም አፍታ በአፍታ እያደገ ነው፡፡ ሁለት ሰዎች በእጅ በምትቀዘፍ ጀልባ ሆነው በአሮጊቷ ቤት አጠገብ ሲያልፉ፤
“እማማ፣ እማማ፣ ኧረ እማማ!” ብለው ጮኸው ይጣራሉ!
“እመት፤ ምን ፈልጋችሁ ነው?”
“ይውረዱ፡፡ አብረን እንድናለን፡፡ እባክዎ ይምጡ!” አበክረው አሮጊቷን ለመኗቸው፡፡
“አመሰግናለሁ ሂዱ” አሉ አሮጊቷ፡፡ “ለእኔ እሱ የላይኛው ያውቅልኛል” ብለው ወደ ሰማይ አመለከቱ፡፡ አምላካቸው እንደሚያድናቸው በመተማመን መናገራቸው ነው፡፡
ባለ ጀልባዎቹ ትከሻቸውን ከፍ ዝቅ አድርገው፤ እኛ ምንቸገረን በሚል ስሜት በጀልባቸው እየቀዘፉ መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡ ማታ ገደማ ውሃው አድጎ አድጎ የመኝታ ክፍላቸውን ወደ ማጥለቅለቅ እየመጣ በመሄዱ፤ አሮጊቷ ያላቸው አማራጭ ጣራው ላይ መውጣት ሆነ፡፡ አሮጊቷ ጣራው ላይ ወጡ፡፡ አንድ ባለሞተር ጀልባ እንዳጋጣሚ ብቅ አለና አያቸው፡፡ ከዚያም፤
“እማማ” ሲል ጮኾ ተጣራ፡፡
“አቤት የእኔ ልጅ” አሉ የሞት ሞታቸውን፡፡
“አይጨነቁ፤ መጥቼ አወርድዎትና በሞተር ጀልባ እንሄዳለን!”
አሮጊቷም፤
“ግዴለህም ልጄ በምንም አትቸገር! ለእኔ እሱ የላይኛው ያውቅልኛል፡፡ አንተ ሂድ በሰላም ግባ” ይሉታል፡፡ ጀርባቸውን ያዞሩበታል፡፡ ሞተሩን ቀስቅሶ እሱም መጭ ይላል!
አሮጊቷ ምንም ሳይቆዩ ጎርፍ ጣራውን ማጥለቅለቅ ስለጀመረ፤ ከጣራው በላይ ወዳለው ወደ ብቸኛው፣ እስካሁን ጎርፍ ወዳልነካው፣ ቦታ፤ ወደ ጭስ ማውጫው አናት ወጡ! እንደ ዕድል ሆኖ የቀይ መስቀል ጎርፍ መከላከያ ቡድን ወደ አሮጊቷ ቤት አጠገብ ይመጣል፡፡
“ወደ ትልቁ ጀልባ ይዝለሉ እማማ!” አለ ከመከላከያ ቡድን አባላት አንዱ፡፡
አሮጊቷ ራሳቸውን ነቀነቁና ኮስተር ብለው፤
“እሱ የላይኛው ያውቃል፡፡ እሱ የትም አይጥለኝም!” ይላሉ፡፡ ትልቁ ጀልባም፤ እየተምዘገዘገ የአሮጊቷን ቤት አልፎ ሄደ፡፡ ውሃው ማደጉን አላቋረጠም፡፡ እስከ ጭስ ማውጫው አናት ደረሰና አሮጊቷን ዋጣቸው፡፡ አሮጊቷ ውሃው እየዋጣቸው ሳሉ ፀሎታቸውን ለአምላካቸው አሰሙ፡፡
“ምነው አምላኬ! አንተን አምኜ ጉድ ታረገኝ?” ሲሉ አማረሩ፡፡
አምላክም እንዲህ ሲል መለሰላቸው፤
“አንቺ ሴት! ችግርሽን አይቼ ሶስት ጀልባ ላክሁልሽ፡፡ ያውም በመጀመሪያ በእጅ የሚዘቀፍ ትንሽ ጀልባ፡፡ ምናልባት ጥሩ ኑሮ ትኖሪ ስለነበር ትንሹን ጀልባ አልቀበልም ያልሺው ያንሰኛል ብለሽ ይሆናል ብዬ! ቀጥዬ በሞተር የሚነዳ መካከለኛ ጀልባ ላኩልሽ፡፡ እሱንም አሻፈረኝ አልሽ፡፡ በሶስተኛው ትልቁን ጀልባ፣ ከነትልቅ ሞተሩ፤ ሊያውም ከነሰራተኞቹ ላኩልሽ፡፡ በጭራሽ አልቀበልም አልሽ! ከዚህ በላይ ምን ላድርግሽ?! ከእንግዲህ የራስሽን መንገድ ፈልጊ!” አላቸው፡፡
*       *       *
ጎርፉንም ድርቅንም ካልተቆጣጠሩት ለከፍተኛ አደጋ እንደሚያጋልጥ እንገንዘብ፡፡ ሲረዷቸው የማይረዱ አያሌ ናቸው፡፡ በዓመታትና በወራት ጊዜ ውስጥ ሳይሆን በቀን ውስጥ ከተከሰተው የማይማሩ ብዙ ናቸው፡፡ ጎርፍ መምጣቱን፣ ክረምት መግባቱን እዩ፤ አጥራቸውን ማጠርን፣ እርከናቸውን መስራትን፣ ጣራቸውን ማጠንከርን የማይሹ በርካታ ናቸው፡፡ ኑሮ መቼም ሞልቶ አያውቅም፡፡ ውጣ ውረድ አለው፡፡ በሁሉም መልክ ጥረትና ትግልን ይጠይቃል፡፡ የአንዳንዱ ኑሮ ውሃ ወቀጣ ነው፡፡ የአንዳንዱ የዘነጋ ተወጋ ነው፡፡ የአንዳንዱ ከድጡ ወደ ማጡ ነው፡፡ አንዳንዱ ወፍራም ውሻ፣ አለ ሲሉት ይሞታል ነው፡፡ ወረቀት ላይ ያስቀመጥነው ዕድገት የሰውየውን መሶብ እንዴት አድርጎት ይሆን ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ አለበለዚያ ድህነት ላይ የምናሰግረው መፈክር የወረቀት ላይ ነበር (Paper tiger እንዲሉ) ያደርገናል፡፡
ነጋ ጠባ የሚወራለት የመልካም አስተዳደር ችግር ዛሬ ቁስሉ ዳነ ሲባል፣ ነገ እያመረቀዘ የቆላ ቁስል ይሆንብናል፡፡ ጨርሶ ወደ ማይድን በሽታ፣ ወደ ጋንግሪንነት፤ እንዳይሄድ መጠንቀቅ ተገቢ ነው፡፡ የከፋው ችግር ደግሞ ለሙስናውም፣ ለዲሞክራሲዓዊና ለመብት ጥያቄውም፣ ለፍትሕ መጓደልም ወዘተ “ተጠያቂው መልካም አስተዳደር ነው” ማለቱ ሲሆን ዕውነቱን ከማደብዘዝም አልፎ ፈር ያስተዋል፡፡ የሀገራችን ሌላው ቁልፍ ችግር፣ ቤተ-ሰሪ ለፍቶ ለፍቶ “ደም - የለውም” እስኪባል ድረስ ቅርሱን ጨርሶ፣ ቤት ሰርቶ “ፊኒሺንጉ” ያስቸግራል እንደሚባለው፤ በጣም ያስቸግራል ይላሉ፡፡ ይሄንን በቀላሉ ለመረዳት የኳስ ቡድናችንን ማጤን ነው፡፡ ሁሌ እግብ ጋ ሲደርሱ አይሳካላቸውም እንደሚባለው ነው - “የአፈፃፀም ችግር” አለባቸው የተለመደች አባባል ናት፡፡ ስንት ዘመን የዚህ ችግር ቁራኛ እንሆናለን? ነው ወይስ እየደጋገምነው አዋቂው እንዳለው፤ “ትለምጂዋለሽ” ሆኖ አረፈው፡፡ የበጀት መዝጊያ ሲደርስ “ምንጣፍ መግዛት” የአፈፃፀም ችግርን መቅረፍ ነውን? ወይስ በዘመኑ ቋንቋ “የአፈፃፀም ችግር “ውስጤ ነው” በሚል “ቃና” የምናልፈው ጣጣ ይሆን? የችግሮቻችን ብዛትና የመፍትሔ አሰጣጣችን አቅም ሲታይ፣
“በነጠላ ጫማ፣ ባንቺ አረማመድ
እንዴት ያልቅልሻል ያ ሁሉ መንገድ!” የሚባለው ህዝባዊ ዘፈን ግጥም ዓይነት ነው፡፡ ስለዚህ ጉዳይ ብዙ የወተወትነው በሥራ እንለወጥ ዘንድ እንጂ እንደው የማንጓጠጥ ወግ ለማምጠቅ አይደለም፤ በቀና መንፈስ ነው፡፡
“ለትምክህት አይደለም፣ ይህን መናገሬ
ለማስቀናት እንጂ ሰነፉን ገበሬ፡፡
ሃዋርያው ሲናገር ወደ ምዕመናኑ
ለምትበልጥ ፀጋ ይላል ቅኑ አስቀኑ!”
እንዳለው ነው፡፡
በህዝብ ተዓማኒነትን ለማፍራት የመሞከር ጉዳይ በመንግስት ልዩ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ነገር ነው፡፡ በኦሮሚያ ግጭት ነበር፡፡ በአማራ ክልል ግጭት ነበር፡፡ በአዲስ አበባም ግጭት ነበር፡፡ በወለጋም ግጭት ነበር፡፡ ግጭትን በእልህ ሳይሆን በዘዴ፣ በብልህነት ለመፍታት መሞከር፣ ካለፈው ትምሀርት መውሰድ፣ ዋና መንገድ ነው፡፡ ሌላው ቁልፍ መንገድ ከጎረቤቶቻችን ጋር ያለን ዲፕሎማሲያዊ አካሄድ ነው፡፡ አንዱን በዱላ አንዱን በመላ፤ የሚለው አያያዝ መፈተሽ አለበት፡፡ ዲፕሎማሲያችን፤ “የሀፍረተ-ስጋህን ፀጉር የምታሳየው አለ፡፡ የብብትህን ፀጉር የምትከለክለው አለ፡፡” የሚለውን ልብ ይበል፡፡

   ጅማ ዩኒቨርሲቲ ከኤቢኤች ሰርቪስ ጋር በመተባበር በሁለት የድህረ ምረቃ ፕሮግራሞች ያስተማራቸውን 136 ተማሪዎች ነገ በሸራተን አዲስ ያስመርቃል፡፡
በማስተርስ ኦፍ ቢዝነስ አድሚኒስትሬሽንና በማስተርስ ኦፍ ፐብሊክ ኸልዝ የሚመረቁት እነዚሁ የድህረ ምርቃ ተማሪዎች፤ ላለፉት ሁለት ዓመታት በአዲስ አበባ ኤቢኤች ካምፓስ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የቆዩ ናቸው፡፡
ዩኒቨርሲቲው የረጅም ዓመታት ሙያዊ እውቀትና ልምድ ያላቸውን መምህራን በመመደብ ተማሪዎቹን በማስተማር ላይ እንደሚገኝ የገለፁት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ፍቅሬ ለሜሳ፤ አሁንም አዳዲስ ፕሮግራሞችን በመክፈት የመንግስትና የግል ዘርፉን አጋርነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ እንደሚሰራ ገልፀዋል፡፡
 የኤቢኤች ሰርቪስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዶ/ር ማርቆስ ፈለቀ በበኩላቸው፤ የጅማ ዩኒቨርሲቲን ወደ አዲስ አበባ መምጣት ተከትሎ የድህረ ምረቃ ተማሪዎች ፍላጎት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሄዱን ጠቁመው፤ በቀጣዩ በሁለት የድህረ ምርቃ ፕሮግራሞ በፐብሊክ ሪሌሽንና ኮርፖሬት ኮሚዩኒኬሽን እንዲሁም በኸልዝ ሞኒተሪንግና ኢቫሉዬሽን አዳዲስ ተማሪዎን እንደሚቀበል ተናግረዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በነገው ዕለት ከሚያስመርቃቸው የድህረ ምረቃ ተማሪዎች መካከል 42ቱ ሴቶች ሲሆኑ ባለፈው ዓመት ለመጀመሪያ ጊዜ 97 ተማሪዎችን በሁለተኛ ዲግሪ አስተምሮ ማስመረቁ አይዘነጋም፡፡ 

የከተማዋ ስራ አጦች ሁለት ወጣቶች ብቻ ናቸው

   ኬታንጋታ የተባለቺውና 800 ነዋሪዎች ብቻ ያሏት የኒውዚላንድ ከተማ “እጅግ ብዙ ክፍት የስራ ቦታና አነስተኛ ዋጋ ያላቸው የመኖሪያ ቤቶች ቢኖሩኝም፣ ይህን ዕድል የሚጠቀምበት ሰው አጥቼ ተቸግሬያለሁ፣ እባካችሁ ኑ ወደ እኔ” ማለቷን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ የሰው ሃይል እጥረት ያጋጠመው የከተማዋ አስተዳደር ችግሩን ለመቅረፍ፣ የሌሎች የኒውዚላንድ ከተሞች ነዋሪዎችን እባካችሁ ኑልን ሲል ጥሪ ያሰተላለፈ ሲሆን፣ የከተማዋ የስራ አጦች ቁጥር 2 ብቻ ነው ሲሉ ከንቲባው ማስታወቃቸውንም ገልጧል፡፡ ከንቲባው ወደ ከተማዋ ለሚመጡ አዳዲስ ነዋሪዎች፣ የመኖሪያ ቤት በእጅግ አነስተኛ ዋጋ ከማቅረብ ባለፈ፣ሌሎች በርካታ ማበረታቻዎችን ለማድረግ ማቀዳቸውንም አስታውቀዋል፡፡ በከተማዋ ካሉ ክፍት የስራ ቦታዎች መካከል የመነሻ ደመወዛቸው እስከ 26ሺህ 500 ፓውንድ የሚደርሱ እንደሚገኙበት የጠቆመው ዘገባው፤ አስተዳደሩ በህክምና፣ በህንጻ ግንባታ፣ በወታደራዊ ሃይልና በሌሎች በርካታ ዘርፎች ያሉትን ክፍት የስራ ቦታዎች ዝርዝር ይፋ ማድረጉንም ገልጧል፡፡

ኢትዮጵያ ከ178 የዓለም አገራት ባለመረጋጋት 24ኛ ደረጃን ይዛለች

የዓለማችንን አገራት ያለመረጋጋት አደጋ ደረጃ በየአመቱ ይፋ የሚያደርገውና ፈንድ ፎር ፒስ የተባለው ተቀማጭነቱ በአሜሪካ የሆነው የምርምር ተቋም ባለፈው ረቡዕ ባወጣው የ2016 አመታዊ ሪፖርት፤ ሶማሊያ ከፍተኛ ያለመረጋጋት ችግር የታየባት ቀዳሚዋ የአለማችን አገር መሆኗን አስታውቋል፡፡
የአገራትን አጠቃላይ ሁኔታ የሚያመለክቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ሪፖርቶችንና ጽሁፎችን በመተንተን እንዲሁም ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ሁኔታዎችን የሚያመላክቱ 10 ቁልፍ መስፈርቶችን መሰረት በማድረግ ደረጃ የሚሰጠው ተቋሙ፤ ለ12ኛ ጊዜ ባወጣውና 178 የአለማችን አገራትን ባካተተው ሪፖርቱ፣ ሶማሊያን በቀዳሚነት አስቀምጧታል፡፡ከሶማሊያ በመቀጠል ከፍተኛ ያለመረጋጋት ችግር ያለባት አገር ደቡብ ሱዳን እንደሆነች የጠቆመው ሪፖርቱ፤ መካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ ሱዳን፣ የመን፣ ሶርያ፣ ቻድ፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ አፍጋኒስታንና ሃይቲ እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ እንደያዙ ገልጧል፡፡ኢትዮጵያን በ24ኛ ደረጃ ላይ ያስቀመጠው የዘንድሮው ፈንድ ፎር ፒስ ሪፖርት፤ አገሪቱ ባለፉት አራት አመታት የመረጋጋት ሁኔታዋ እየተሻሻለ  ቢመጣም፣ በአገሪቱ የቡድን ግጭቶችና የተማረ የሰው ሃይል ፍልሰት ከአምናው ጋር ሲነጻጸር ጭማሪ አሳይቷል ብሏል፡፡
ከአለማችን አገራት መካከል እጅግ ዘላቂ የሆነ መረጋጋት ያለባት አገር ፊንላንድ ናት ብሏል የተቋሙ ሪፖርት፡፡

የአየር ሃይል አዛዡና ሌሎች ባለስልጣናትም በ74 ሚ. ዶላር ሙስና ተከስሰዋል

   የናይጀሪያው ፕሬዚዳንት ሙሃመድ ቡሃሪ ልዩ ጠባቂ የሆነው ሃሰን አሚኑ የተባለ የአገሪቱ የደህንነት አባልና ሌሎች ለፕሬዚዳንቱ ቅርበት ያላቸው የደህንነትና የጦር ሃይል አባላት አገሪቱን በሽብር ከሚያምሰው ጽንፈኛው ቡድን ቦኮ ሃራም ጋር ንክኪ አላቸው በሚል ተጠርጥረው ባለፈው ረቡዕ አቡጃ ውስጥ በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋላቸው ተዘገበ፡፡
የአገሪቱ መንግስት የደህንነት ልዩ ግብረ ሃይል ለፕሬዚዳንቱ ቅርበት ያላቸውን ግለሰቦች የጀርባ ማንነትና ድብቅ አጀንዳ በመመርመር ላይ እንደሚገኝ የዘገበው ናሽናል አኮርድ ኒውስ ድረገጽ፤ይሄው የፕሬዚዳንቱ ጠባቂና የደህንነት አባላትም ከአሸባሪው ቡድን ጋር የድብቅ ግንኙነት እንዳላቸው በመረጋገጡ መታሰራቸውን ገልጧል፡፡ግለሰቡና ግብረ አበሮቹ ከቦኮ ሃራም ጋር ግንኙነት እንዳላቸው መረጋገጡንና በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ተከትሎ፣ ሽብርተኞች በፕሬዚዳንቱ ጠባቂዎችና ለቤተመንግስቱ ቅርበት ባላቸው ግለሰቦችና ሰራተኞች አማካይነት ጥቃት እንዳይፈጽሙ ለመከላከል የተጠናከረ ክትትል እየተደረገ መሆኑም ተነግሯል፡፡ የፕሬዚዳንቱ ጠባቂና የደህንነት አባላቱ ከቦኮ ሃራም ጋር ግንኙነት እንዳላቸው መረጋገጡ፣ አሸባሪ ቡድኑ ከሽምቅ ውጊያ ባለፈ ምን ያህል እስከ ቤተ መንግስቱ የሚደርስ የጥቃት ሰንሰለት እንደዘረጋ ያመላክታል ተብሏል፡፡በተያያዘ ዜናም፣ የቀድሞው የናይጀሪያ አየር ሃይል አዛዥና ሌሎች ሁለት የጦር ሃይል ባለስልጣናት በሚሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር  የህዝብ ገንዘብ ለግል ጥቅማቸው አውለዋል በሚል ተከስሰው ፍርድ ቤት መቅረባቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ የቀድሞው የአገሪቱ የአየር ሃይል ላይ አዛዥ ማርሻል ጃኮብ ቦላ አዲጉን እና ሌሎች በቁጥጥር ስር የዋሉት ባለስልጣናት በድምሩ 74 ሚሊዮን ዶላር የህዝብ ገንዘብ መዝብረዋል በሚል ነው የተከሰሱት፡፡

   ለታሪክና ለባህላዊ ጥናቶች ትልቅ ዋጋ ያለው ሥራ፤ የተባለለት ‹‹እጨጌ ዕንባቆም - ከየመን እስከ ደብረ ሊባኖስ›› በሚል ርእስ በዲያቆን ዳንኤል ክብረት የተዘጋጀው አዲስ መጽሐፍ ታትሞ በያዝነው ሳምንት ለንባብ በቅቷል፡፡ ብዙ ምስቅልቅል፣ ጦርነቶች፣ ከፍተኛ የሕዝቦች እንቅስቃሴና መፈናቀል የተከሠተበትን የኢትዮጵያን የ16 ኛውን ክፍለ ዘመን ታሪክና አስተዳደራዊ መልክዓ ምድር (ጂኦግራፊ) ለመረዳት ያስችላል የተባለው ይኸው መጽሐፍ፤
ዋጋው ብር 60.00 ሲሆን፤ በመጪው ሳምንት ቅዳሜ (ሐምሌ 9) ከሰዓት በኋላ ከ 8፡30 እስከ 12፡00 ሰዓት፤ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል አዳራሽ የታሪክ ምሁራንና ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት እንደሚመረቅ ተገልጿል፡፡ አዲሱ ጽሐፍ የዲያቆን ዳንኤል ክብረት 23ኛ ሥራ መሆኑ ታውቋል፡፡ ዲያቆን ዳንኤል የአዲስ አድማስ ቋሚ አምደኛ መሆናቸው ይታወቃል፡፡

Saturday, 02 July 2016 12:37

‘Fikru’….‘ፍቅሩ’

የሥዕል ትርዒት ዳሰሳ (Exhibition Review)
የትርዒቱ ርዕስ፡ ፍቅሩ
ሠዓሊ፡ ፍቅሩ ገ/ማርያም
የትርዒቱ አይነት፡ የግል፤ የቀለም ቅብ ስራዎች
ብዛት፡ 25 የቀለም ቅብ፤ ስራዎች
የቀረበበት ቦታ፡ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም ጊዜያዊ የስዕል ማሳያ አዳራሽ አዲስ አበባ
ጊዜ፡ ሰኔ 06 - ሐምሌ 7: 2008 ዓ.ም
ዳሰሳ አቅራቢ፡ ሚፍታ ዘለቀ(የሥነ-ጥበብ አጋፋሪ)

“ፍቅሩ”
ለግል የሥዕል ትርዒት ስያሜነት ከሚውሉ አሰያየሞች መካከል መጠሪያ ስምን ለትርዒት ስያሜ ማድረግ ከተለመዱት መሃል አንደኛው ነው፡፡
ይህን ማድረግ ራሱን የቻለ መደንግግ ነው፡፡ ሠዓሊ ፍቅሩ ገብረማርያም ለዚህኛው ብቻ ሳይሆን በላጮቹንና አብዛኛዎቹን የግል የሥዕል ትርዒቶቹን መጠሪያ በስሙ ‘ፍቅሩ’ በሚል ነው ለህዝብ እይታ የሚያበቃው፡፡ ይህ ደግሞ መደንግግነቱን እንድናስተነትንና ‘ፍቅሩ’ የሚለውን ስያሜ በድግምግሞሽ እንዲጠቀም ያስቻለውን አመክንዮ ለመረዳት ቆፈር ቆፈር እያደረግን እንድንፈትሽው በር ከፋች ነው ባይ ነኝ፡፡ አሃዱ፡ ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም ‘ፍቅሩ’ ነቱ ላይ ችክ ያለ ሠዓሊ መሆኑን መረዳት እንድንችል እየነገረን ሊሆን ይችላል፡፡ ክልኤቱ፡ ሠዓሊው ገና የ’ፍቅሩ’ነቱን ፍቅር አጣጥሞ አለመጨረሱን እንድንጠረጥር በገቢርም ሆነ በነቢብ የማርያም መንገድ እየሰጠን ይሆናል፡፡ ሰልስቱ፡ ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም ራሱ ፍቅሩን ወይም የፍቅሩንነቱን ጥግ፣ልክ፣ጥልቀትና ርቅቀት ገና ዳሰሶ ወይም ፈልጎ አለመጨረሱንና አለማግኘቱን ለመጠቆም፤ ይልቅስ በፍለጋው ሂደት ያገኘውን ወይም የደረሰበትን ፍቅሩን እንካችሁ ማለቱ ሊሆን ይችላል፡፡ አርባዒቱ፡ ሠዓሊው በደረሰበት ወይም ባገኘው ፍቅሩነት እርግጠኛ ሆኖ፣ እነሆ ፍቅሩ መጥቷልና ከበረከቱ ትካፈሉ ዘንድ ትርዒቱን እንካችሁ እያለም ይሆናል፡፡ ሐምስቱ፡ መ ሁሉም መልስ ነው፣ አልተሰጠም ወይም መ መልስ የለውም የሚል መደምደሚያ ላይ ልንደርስ እንችላለን፡፡ ወደ ትርዒቱ፡-
በትርዒቱ ከቀረቡት ስራዎች ሰባ በመቶ የሚሆኑት በአውታረ መጠናቸው ብቻ የሚናገሩት ሃቅ አለ፡፡ የሥራዎቹ የጎን ስፋትና ቁመት ተቀራራቢነት ያላቸው፤ ወደ ስኩዌር ካሬነት የሚያዘነብሉና መሃከለኛና በብዛት ትልቅ መጠን ያላቸው የሥዕል ሰሌዳዎችን ነው የሚጠቀመው፡፡ እንዲህ አይነቱ አውታረ መጠን በተለምዶ ግዘፍ የሚነሳ፤ ዓይን የሚሞላና ደርፈጭ ያለ ወይም (bald) እንደሆነ ይነገራል፡፡ አንድ ሠዓሊ ይህን አይነት አውታረ መጠን ሲጠቀም ግዘፍ የሚነሱና ስለ ራሳቸው በልበ ሙሉነት የሚናገሩ ሀሳቦችን በማንሸራሸር እንዲያግዘው ሆን ብሎ የሚመርጠው እንደሆነ ይታመናል፡፡ በዚህ ትርዒት የቀረቡ አብላጫዎቹ ስራዎች በዚህ አቀራረብ የተቃኙ እንደሆኑ ይስተዋላል፡፡ ሆኖም እንዲህ አይነት ዝንባሌ ያላቸው ስራዎች በአንድ ላይ ለዕይታ ሲቀርቡ፣ ሲደረደሩና ሲሰቀሉ ሰዓሊውም ሆነ የትርዒቱ አጋፋሪ (curator) በጥንቃቄ ማሰብና መከወን የሚገባውን ወሳኝ ነጥብ የሳተ አቀራረብ በዚህ ትርዒት ይስተዋላል፡፡ ይኸውም ትርዒቱ ከሚታይበት ህንፃ ውስጥ ፎቅ ላይ ባለው የመጨረሻውና ሰፊው የሥዕል ማሳያ አዳራሽ ውስጥ የተሰቀሉት ሳይሆን የተገጠገጡት ሊባል በሚያስችል ደረጃ እንደ ሱቅ በደረቴ በአንድነት ተቸምችመው ያሉት አምስት ስድስት ሰራዎች የግዙፍነታቸውን ብቻ ሳይሆን ያመቁትን የሃሳብና የስሜት  ጥቅጥቅነት (density) ከግምት ያላስገቡ ናቸው፡፡ ሠዓሊው ፍቅሩ ገ/ማርያም፤ በፍቅር የወደቀላቸውን ስራዎች ለማሳየት በጉጉት ሲጣደፍ አሰቃቀሉ ለዕይታ እንደሚጎረብጥ እንኳ ማስተዋል እንደነሳው ማየት እንችላለን፡፡ ለአንድ ነገር ፍቅር ብቻ ሲቸረው የሚያስከትለው ችግር ይኖራል፡፡ ምናልባትም በ’ፍቅሩ’ነቱ ጥግና ልክ እርግጠኛ የሆነ ቢሆን ኖሮ እንዲህ ከመገጥገጥ ይልቅ አንድ ወይ ሁለት ስራዎቹን ብቻ “ገጭ” አድርጎ ሰቅሎ ሙሉ “ፍቅሩ”ነቱን በልበ-ሙሉነት መንፈስ ጀባ ሊለን ይቻለው ነበር የሚል ሙግት አመክንዮ እንዳነሳ የሚጋብዝ ፍንጭ በተለይ ከተጠቀሰው የሥራዎቹ አውታረ መጠናቸውን መሰረት በማድረግ፣ሥራዎቹ ከተሸከሙት የሀሳብና የስሜት ጥቅጥቅነት በመነሳት ለተመልካች እይታ ብሎም መረዳት ትግዳሮት (problem) የሚፈጥረውን የትርዒቱን ባህሪ ማየት ይቻላል፡፡ በመሰረቱ እንዲህ አይነት ጥቃቅን የሚመስሉ ነገር ግን ለአንድ የሥዕል ትርዒት ምሉዕነት ጉልህ ሚና ያላቸውን የአቀራረብ ባህሪያት ከግምት ውስጥ አስገብቶ የሚሰራ የሥነ-ጥበብ አጋፋሪ ከሌላው ትርዒት የሚጠበቅ ህፀፅ ቢሆንም እንደ ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም በዓለም አቀፍ መድረኮች፣ በታላላቅ ሙዚየሞችና ጋለሪዎች ዓለማችን ካፈራቻቸው ምርጥ ሠዓሊያን ጎንና በአንድነት ስራውን ካቀረበ ሠዓሊ የማይጠበቅ በመሆኑም ነው ይህን ያህል ትኩረት ሰጥቼው የነካካሁት፡፡ በአንፃሩም የትርዒት ማሳያው አዳራሽ አስተዳደርም ቢሆን ለአዳራሹ ኪራይ አይሉት አበል ለፅዳትና ጥበቃ አንዳንዴም የአዳራሹን በርና መስኮት ከፍቶ ለሚዘጋው ሰው አበል በሚል ሰበብ ለሚሰበሰበው ገንዘብ ትኩረት ከመስጠት ውጪ ለእንዲህ አይነት ሙያዊ እገዛዎችም ሆነ የአዳራሹን ግድግዳዎች ለማደስ፣ የሥዕል አስቃቀልንና ዕይታን ለሚረብሹት እንዲያው እንደዘበት አቡጂዲ ጨርቅ በመስኮቶቹ ላይ ጣል ከማድረግ ውጪና አንድ የሥዕል የተሳካ ለሚያደርጉት የብርሃን አምፑሎች “በዕድላቸው” እንዲበሩ ከመተው የዘለለ መፍትሔ ከማቅረብ ሌላ ዳተኝነቱን በተከታታይ እየተዘጋጁ ካሉ ትርዒቶች ለመረዳት ችለናል፡፡ እናም ከዚህ ዓይነት የአዳራሹ አስተዳደር የሥነ-ጥበብ አጋፋሪ (curator) መጠበቅ “እዬዬም ሲደላ ነው” ሊሆንብን ይችላል፡፡ ሆኖም የኢትዮጵያ ብሔራዊ … የሚል ሁለት ከባባድ መጠሪያዎችን ከተሸከመ የሥዕል ማሳያ አዳራሽ እንዴት “እዬዬም ሲዳላ” ይሆናል የሚል ሀሳብ ዘወትር ወደ አዳራሹ ጎራ ባልኩ ቁጥር የሚነዘንዘኝ ሃሳብ በመሆኑና መተቸት የሚገባው እንደሆነ ስለማምንበት ነው ያነሳሁት፡፡ አስተዳደሩ አዳራሹን ለተከታታይ ትርዒት ክፍት ከማድረጉ ባሻገር በዚህ በ “ፍቅሩ” ትርዒት ሙዚየሙና የአዳራሹ አስተዳደር ካሳየው አበረታች ጅምሮች መሃከል የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን አቶ ዮናስ ደስታ በትርዒቱ መክፈቻ ተገኝተው ስለ ትርዒቱና ስለ ሥነ-ጥበብ እንዲሁም ባለስልጣን መ/ቤቱ ለሥነ-ጥበብ ስለሚያደርገው ድጋፍ የሰጡት ጠንካራ የመክፈቻ ንግግር ነው፡፡ በተለይ ባለስልጣን መ/ቤቱና የአዳራሽ አስተዳደር ከላይ የተጠቀሱት አይነት ችግሮችን በጊዜ ሂደት እየቀረፈ ቢሄድ ይበል የሚያስብል ማለፊያ ማበረታቻ ነው፡፡ ወደ “ፍቅሩ” እንመለስ፡-
ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም በ1987 ዓ.ም ነው ከአሁኑ የአዲስ አበባ ዮኒቨርስቲ  አለ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት  በቀለም ቅብ በዲፕሎማ የተመረቀው፡፡ ለዲፕሎማው አራት ዓመታትን፣ ከዚያ በፊት ት/ቤቱ ይሰጥ በነበረው የማታ ትምህርት ክፍለ ጊዜ ለሁለት ዓመታት፣ እንደገና ከእነዚህ ሁለት ዓመታት በፊት ለአራት ዓመታት በተከታታይ የክረምት ትምህርት ክፍለ ጊዜ በት/ቤቱ ተከታትሏል- አስር ዓመታትን በድምሩ የሥዕል ትምህርት ሲማር ቆይቷል ማለት ነው፡፡ ተመርቆ ከወጣ በኋላ እስካሁን ባሉት ሀያ አንድ ዓመታት ውስጥ ደግሞ  በስቱዲዮ ሠዓሊነት ቆይቷል፡፡ ሥዕል የተማረበትና የሰራበት ዓመታት ሲደመሩ የአንድ ትውልድ እድሜ ይተካከላሉ ማለት ነው፡፡ የሥዕል ትምህርት መማር ሠዓሊ አያደርግም፤ምናልባት ሥዕል ለመስራት ያግዝ ይሆናል እንጂ፡፡ የሥዕል ትምህርት አለመማምርም ከሠዓሊነት አያግድም፡፡ በሀገራችን ብቸኛው የሥነ-ጥበብ ተቋም ሆኖ ከግማሽ ምዕተ ዓመታት በላይ የዘለቀው የአለ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት፣ ሲያስተምርበት የቆየውንና አሁንም ከሞላ ጎደል እያስተማረበት የሚገኘውን የትምህርት አሰጣጥ ዘዬና ፍልስፍና እጅጉን ክሊሎት (skill) ላይ መሰረት ያደረገና ቆይታው ያዳበረው ልምድ ብቻቸውን ወደ አንድ ከዚህ ቀደም ሲሰራ ከቆየበት ወደ ተለየ የአሰራር አቅጣጫ እያመጡት እንደሆነ በዚህ ትርዒት ላይ መመልከት እንችላለን፡፡
 ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም አበድ፣ሰከር፣ቆፍጠንና ፈጠን ያለ ድፍረት በዚህ ትርዒት አሳይቶናል፡፡ እብደቱ ስካሩ ነፃነቱን፤ፍጥነቱና ቆፍጣናነቱ ደግሞ ሩቅ አላሚነቱን ያመለክታሉ፡፡ ጭልጥ አድርጎ ከመጠጣት ሳይሆን ቀስ በቀስ፣ ያውም የአስር ዓመታት ትምህርትንና ሃያ የሚሆኑ የሠዓሊነት ዓመታት ልምዶችን በዝግታ በማጣጣምና በማሰላሰል ከሚመነጭ ድፍረት ነው እብደቱና ስካሩ የተወለዱት፡፡ ቀጥ ብሎ ለመቆም፣አሻራውን ለመተው፣ምናልባትም ለመዝናናት፣ ፈታ ብሎ በስራዎቹ ሙከራ ለማድረግና እንደውም (ቀጣዩን ዓረፍተ ነገር ቡፍ ብሎ ከሚያመልጥ ሳቅ ጋር ነው ያሰብኩት)… እንደውም “ሥዕል ምናባቱ-የታባቱ አፈር ድሜ ማብላት ነው እንጂ” እያለ መስራ ከሚያስችል ድፍረት ውሰጥ የሚገኝ ሩቅ አላሚነት የከሰቱት ፍጥነትና ቆፍጣናነትም በስራው ማየት ይቻላል፡፡ በዚህ ትርዒት የቀረቡት ሥራዎች በሥነ-ጥበብና በሚሰራው ሥዕል ለመፈላሰፍና ለመዝናናት የሸሚዞቹን እጀታ ከክንዱ ከፍ አድርጎ የሰበሰበ ሰው የሚሰራቸው አይነት ስራዎቸ ይታዮኛል፡፡ ሥራዎቹ ቆፍጣናነትና ፍጥነት ካልተሞላባቸውም ለዘዝ ብለው ለዘመናት ሲመላለስበት ወደ ኖረበት ድግምግሞሽ ለመመለስ የፈራ የሚደፍረው ዓይነት ድፍረት ይስተዋላል፡፡ ይልቅስ ቆፍጠን ብሎ ፍጥነት በመጨመር ቢነጉድ አንድ ከፍታ ላይ ለመድረስ የሚያልም፣ነፍሱን የሳተ እብድና ሰካራም ጋላቢ ከሚደፍረው ድፍረት የመነጩ ስራዎች በትርዒቱ ይታያሉ፡፡
በትርዒቱ የቀረቡ አብዛኛዎቹ ሥራዎች ሙከራዊ (experimental) ቢሆኑም የአካዳሚክ (የሥዕል ትምህርት) ህግጋትን ለመጣስ የሚፍጨረጨሩ ናቸው፡፡ ከመማርም አልፎ በሥራ ያዳበረውን የአሳሳል መንገዶች ካላፈረስኩ ብሎ መታገል፣ እብደትና ስካር ካልታከለበት በቀር መድፈር አስቸጋሪ ነው፡፡ ብዙ ሠዓሊያን ይህን ድፍረት አጥተው ለተማሩት ትምህርት ብቻ እስረኛ ሆነው ቀርተዋል፡፡ በሥነ-ጥበቡም ሆነ በፍልስፍናው እመርታ ለማሳየት ሙከራ ወሳኝ ነው፡፡ ሠዓሊ ፍቅሩ ይህንኑ ነው እያደረገ ያለው፡፡ እየሞከረ፡፡ ሙከራውም አያሌ የዓለማችን ሠዓሊያን ከሞከሩት የተለየ አይደለም፡፡ አሜሪካዊው ሠዓሊ ዊሊያም ደኩኒንግን ማንሳት እንችላለን፡፡
የፍቅሩ ሙከራ ማፍረስ ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ የሚሰራቸውን ምስሎች እያጠፋ አንዳች ሥነ-ጥበባዊ ፋይዳ ለማግኘት ነው እየተጋ ያለ የሚመስለው፡፡ በዚህ ከቀጠለም ያለፈባቸውንና በስራዎቹ ይስተዋሉ ከነበሩ ተፅዕኖዎች ከመላቀቅና ነፃ ከማውጣትም ባሻገር እንደ ድግምት ከሚደጋግመው “ፍቅሩ”ነቱ ሲጎነጩት እሚያረካ ጣዕም ሊቸረን ይችላል፡፡ ይህን ትጋት ወደ አንድ ጥበባዊና ሰብዓዊ አላማ የማዞር ኃላፊነት እንዳለበትም የሚዘነጋው አይመስለኝም፡፡ ጥበብ ሃቀኝነትን ትሻለች፡፡ በሃቀኝነት የሚከወን ጥበብ፣ከሠዓሊው ባሻገር ሃገርን፣ዓለምንና ሰብዓዊነትን ያገለግላል፡፡ በዚህ ትርዒት የቀረቡ ሥራዎች ይህን ታላቅ ኃላፊነትና ዓላማ ለማሳኪያ በር ከፋች አድርጌ ብወስዳቸው እመርጣለሁ፡፡ ሠዓሊው ጊዜውን፣አትኩሮቱንና እድሜውን ሙሉ ሲለፋለት በኖረለት ሥነ-ጥበብ ውስጥም አንዳች ፋይዳ ከመፈለጉና … ይህን ፍላጎት ክብር መስጠት አስፈላጊ ሆኑ በማግኘቴ ይበል ከማለት ውጪ መጨረሻውን ለመተንበይ እንኳንስ እኔ ሠዓሊውም የሚያውቀው አይመስለኝም፡፡
 ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም ተማሪ በነበረበት ጊዜና ተመርቆ ከወጣም በኋላ የት/ቤቱ አስተማሪዎችም ሆኑ የሀገራችን ግንባር ቀደም ሠዓልያን ክሂሎት ላይ የተመረኮዘ የአሳሳል መንገድን ሲያቀነቅኑ ነው የኖሩት፡፡ ሠዓሊ ፍቅሩና በዚህ ትውልድ ውስጥ ያለፉ አብዛኞቹ ሠዓልያኖቻችን፣ይህን ዘፈን ሲያዜሙም ነው የኖሩት፡፡ በእርግጥ የዜማው ጥዑምነት ያማልላል ነፍስንም ይገዛል፡፡ ብዙ አቅም ያላቸው ነገር ግን የዜማውን ጥዑምነት ብቻ እያጣጣሙና እየነሆለሉ በዚያውም የዓለምና የዘመኑ የሥነ-ጥበብ ኮቴ እያሰማና እየፈጠረ ያለውን ንቅናቄ ማዳመጥ ተስኖአቸው በዚያው የጠፉና የቀሰሙ እንዲሁም በዚሁ አዘቅጥ ውስጥ ያሉ ሠዓሊያኖቻችንም አያሌ ናቸው፡፡ አዲሱን፣ዘመንኛውን፣ የዘመኑንና የአለምን የቅርብ ጊዜ ወይም ለእኛ አውድ “መጤ” የሆነውን የሥነ-ጥበብ ኮቴ ለመስማት ብለውም ለቀደመው ጥዑሙ ዜማ ጆሮና ሁለመናቸውን ደፍነው ያሉበት እስኪጠፋቸው እየተደናበሩ ያሉትንም  የስዕል ስቱዲዮ  ይቁጠራቸው፡፡ የወቅቱ የሀገራችን ሥነ-ጥበብ መመለስ ከሚገባው ጥያቄዎች አንዱም ይሄኛው ይመስለኛል፡፡ ሚዛን መጠበቅ አልያም ሚዛን መድፋት የሚችለውንም በጊዜ ሂደት የምናየው ይሆናል፡፡
ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም በሥነ-ጥበብ ት/ቤት ቆይታው ክሂሎቱን ሲያዳብር ለመቆየቱና በስቱዲዮ ሠዓሊነት ባሳለፋቸው ዓመታት የተማረውን ክሂሎት ሥዕል ለመስራት ሲጠቀምበት ለመቆየቱም አንዳች ጥርጣሬ የለኝም፡፡ የዳበረ ክሂሎቱን ብቻም ሳይሆን በት/ቤት ቆይታው በእሳት የተጠመቀባቸው እስኪመስል የተጣቡት የእነ ፒካሶና ጉጌይን ተፅዕኖዎች፤ በፍቅር ያንበረከከውና እንደ ድርሳን ለዓመታት ሲደጋግመው የኖረው የመምህሩና የሃገራችን ታላቁ ሠዓሊ የታደሰ መስፍን ተፅዕኖ በስራዎቹ ለዓመታት መታየታቸው የእርግጠኝነቴ መሰረቶች ናቸው፡፡ ተፅዕኖቹ በአካዳሚክ ህይወቱና በመስራት ልምዱ የተፈጠሩ ናቸው፡፡ ከመስራትም ደጋግሞ በመስራት፡፡ እነዚህ ሁለት ተፅዕኖዎች መልካም ጎኖች እንዳሏቸውም ልብ ማለት ይኖርብናል፡፡ የመጀመሪያው ገንዘብና እውቅና፡፡ የሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም የሥነ-ጥበብ ልምምድ (practice) በትጋት የተሞላ ነው፡፡ ያለማቋረጥ ይሰራል፤ከዚህም ባሻገር ልፋቱ ተገቢው ቦታ ክብርና ዋጋ እንዲያገኝም ይለፋል፡፡ መሳል ብቻ ሳይሆን ሥራውን ለማስተዋወቅ ይጥራል፡፡ በዚህም የሀገራችን የሥነ-ጥበብ እንቅስቃሴ “ሙት” እንደሆነ ገና ድሮ ገብቶት የሚያገኛቸውን እድሎች ሁሉ እንደ መሰላል እየተጠቀመ፣ ሥራዎቹን ሞቅ ያለ የሥነ-ጥበብ እንቅስቃሴ ባላቸው የዓለማችን ሀገራት ጋለሪዎች ሙዚየሞችና አጋፋሪዎች ዘንድ ለማድረስ ቀና ደፋ ሲል ብዙ ተንከራቶ ተሳክቶለትማል፡፡  ገንዘብንና እውቅናንም በዓለም አቀፍ ደረጃ አግኝቷል፡፡ ተፅዕኖዎቹ ጠንካራ መሰረት ባይኖራቸው ማንኛውም ጋለሪ ሙዚየምና ኪዩሬተር ፊት እንደነሱት ነበር የሚኖረው፡፡ ዛሬ ለደረሰበት ደረጃም ላይበቃ ይችል ነበር፡፡ እነ ፒካሶና ጎጌይን የሰሩት ለዓለምና ለሃገራቸው አሁንም ድረስ ቤዛ እየሆነ ነው፡፡ ታደሰ መስፍንም ለሠዓሊ ፍቅሩ በቀጥተኛ መልኩ፣ ከሰላሳ ሶስት ዓመታት በላይ ለአስተማረበት ት/ቤትና ተማሪዎቹ በተለያየ መልኩ፣ለሀገራችን ሥነ-ጥበብ ደግሞ በጥቅሉ ቤዛ ነው፡፡
ሠዓሊ ታደሰ መስፍን እንደ “እድር አህያ” አንዴ በማስተማር፣ በሌላ ጊዜያት የስብሰባዎች ናዳ ሀገሪቱን ያሻሽሏት ይመስል እዚህም እዚያም በሚካሄዱት ስብሰባዎች ሲዶል በስቱዲዮው ጊዜ ለማሳለፍና ለመስራት መላ መምታት ተስኖት፣ በዘመናት ያዳበረውን ሥነ-ጥበባዊ እርምጃ አንድ ቦታ ማድረስ ቢሳነውም፤ ተማሪው የነበረው ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም ተፅዕኖው አርፎበት የተጀመረውን ለማስቀጠል እንኳን ባይሆን እንደ መሻገሪያ ተጠቅሞት ሊያተርፍበት ችሏል፡፡  ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም የተጠመቀባቸውና የተንበረከከባቸው እነዚህ ሁለት ተፅዕኖዎች፣ገንዘብና እውቅናን እንዲሸምትባቸው ከማስቻላቸውም በላይ አብዛኛው ሠዓሊ ስራውን ለመቀጠል ተግዳሮት ከሚሆንበት የገንዘብ  ጥያቄ ነፃነት አግኝቶ ስራውን በረጋና በነፃነት መንፈስ እንዲሰራ አስችሎታል ወይም ሊሰራ እንዲችል ምቹ ሁኔታ እየፈጠረለት ነው ባይ ነኝ፡፡
የተፅዕኖዎቹ ዳና በድግግሞሽ፤ አሊያም በመስልቸት፤ “አዲስ” ነገር ለመፈለግ እንዲነሳሳ፣ የተፅዕኖዎቹን ዳና ለማጥፋት የራሱ ብቻ ወደሆነ ዳና እንዲመጣ በማድረግ አቀጣጣይ፣ አነሳሽ ወይም ደግሞ አናዳጅ ሀይል መሆን ሁለተኛው ተፅዕኖቹ የተፈጠሩለት መልካም ጎን ይመስለኛል፡፡ ከላይ ስለዘረዘርኩት የአንደኛው ተፅዕኖ ምክንያታዊነት ሰዓሊው ፍቅሩ ገ/ማርያም ራሱ፣ሌሎች ሠዓሊያንና የሥነ-ጥበብ ባለሙያዎች እንዲሁም አንባቢ ሊስማማበትም ሆነ ላይስማማበትም ይችላል፡፡ እንደው የቀደሙ ሥራዎቹ ከማንኛውም ተፅዕኖ የፀዱ ናቸው ተብሎ ቢካድ እንኳን ለዓመታት የተማረው ትምህርት በሠዓሊነቱ ላይ ተጽዕኖ ከማሳደሩም በላይ አሁንም ከተጽዕኖው ለመላቀቅ የሚያደርገው ጥረት ላይ ማነቆ እየሆነበት እንደሆነ ማየት ይቻላል፡፡
ትርዒቱን ታድሜ ከገጠሙኝና ልጠቅሳቸው ከምፈልጋቸው ሁነቶች መሃል እንካችሁ፡-
“እንትን ያለው ልጅ”፤ ትርዒቱን ታድመው የነበሩ አንድ ትልቅ ሰው ናቸው አሉ “ከእስክንድር በኋላ እንትን ያለው ሰዓሊ ተገኘ” ሲሉ የተደመጡት፡፡
አባባሉ “እንትን” ያላቸው ሠዓሊያንና እንትናቸው የሚያዝና ዘር የሚዘራ፤ እየዘራም ያለ ሠዓሊያን በሞሉባት ሀገር፣ ሠዓሊ ፍቅሩ ገ/ማርያም እኔ ብቻ ነኝ “እንትናም” ብሎ እንዲያስብ በር ከፋች ሊሆን ይችላል፡፡ ይሁን ሠዓሊው ፍቅሩ፤እኔ ብቻ ነኝ “እንትናም” ብሎ ያስብ… ግን እሳቸው የሌሎችን ሠዓሊያኖቻችንን እንትን ማየት አልቻሉምና ባለ እንትናም እሱ ብቻ ነው?
የተመልካች አስተያየቶች፡- የብሔራዊ ሙዝየም ታዳሚያን ብዙዎቹ ትርዒቱን ዘልፈውታል፣ ሰድበውታል፣ አነፃፅረውም ዋጋ ቢስ አድርገውታል፡፡ ሥዕል መመልከት፣ ልምምድ ዕውቀት ቢጠይቅም ከሚታየው ሥራ ጋር ስሜታዊና ሃሳባዊ ቁርኝት ይፈልጋል፡፡ የዕይታ ባህሉ ያልዳበረ የማህበረሰብ ክፍል ትርዒቱን ሲመለከት ምንም ስሜት ባይሰጠው፣ ሃሳብ ባይገለጥለትና የሆነ ዘባተሎ ነገር ቢሆንበት ሊገረም ወይም በሰዓሊው ሊናደድ አይገባም፡፡
ጎበዝ የሆነ ተመልካች ራሱን ይጠይቃል-፤ካልሆነም እርዳታ ይጠይቃል- ይህም ካልተሳካ አይተወውም? ምን አስጨነቀው? በእርግጥ አጥብቆ ጠያቂ፣ የእናቱን ሞት ሊረዳ ቢችልም መዳኗንም ሊበሰር ይችላል፡፡