Administrator

Administrator

ኢትዮጵያ የሁለት ቅርሶችን ሕጋዊ የምዝገባ ምስክር ወረቀት ከዩኔስኮ ተረከበች
ኢትዮጵያ የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክና የጌዴኦ ባህላዊ መልክዓ ምድር ሕጋዊ የምዝገባ ምስክር ወረቀት ከተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) ተረክባለች፡፡
የቅርሶቹን የምዝገባ ምስክር ወረቀት ኢትዮጵያ ከዩኔስኮ የዓለም ቅርስ ማዕከል የአፍሪካ ቢሮ ሃላፊ ሙሃመድ ጁማ (ዶ/ር) መረከቧን በፈረንሳይ የኢትዮጵያ ኤምባሲ መረጃ ያመላክታል፡፡
በሳዑዲ ዓረቢያ ሪያድ በተካሄደው 45ኛው የዩኔስኮ የዓለም ቅርስ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ ኢትዮጵያ የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክና የጌዴኦ ባህላዊ መልክዓ-ምድርን በዓለም ቅርስነት ማስመዝገቧ ይታወሳል፡፡

የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas

Wednesday, 01 November 2023 00:00

>

1, በስኳር በሽታ መያዝን ይከላከላል።
2, የካንሰር ስርጭትን ይከላከላልደ።
3, የሆድ ውስጥ አለሰርን ይከላከላል።
4, በልብ በሽታ መያዝን ይከላከላል።
5, ጉንፍን የጉሮሮ ህመም እና ትኩሳት የመሳሰሉትን ህመሞች የመፈወስ ሀይል አለው።
6, ሰውነታችን በቀላሉ በበሽታዎች እንዳይጠቃ ያግዛል።
7, ለጥርስ ህመም እና ለብሮንካይት ችግር እንደ መፍተሄ ይወሰዳል።
8, የደም ዝውውርን ማስተካከል ይችላል።
9, የኮልሌስትሮል መጠንን ማመጣጠን ይችላል።
10, የሰውነትን ክብደት። የተመጣጠነ እንዲሆን ያደርጋል።

ኢትዮ ቴሌኮም የአምስተኛው ትውልድ (5ጂ) የሞባይል
አገልግሎትን በጅግጅጋ ከተማ በይፋ ገበያ ላይ አዋለ


ኢትዮ ቴሌኮም በዛሬው ዕለት፣ ከዚህ በፊት በአዲስ አበባና አዳማ በይፋ ለአገልግሎት ያበቃውን የዘመናችንን የመጨረሻ የ5ኛ ትውልድ የሞባይል አገልግሎት፤ በምስራቅ ምስራቅ ሪጂን፣ በጅግጅጋ ከተማ በመዘርጋት በይፋ ገበያ ላይ ማዋሉን አስታውቋል፡፡


በዚህም መሰረት በሶማሌ ክልላዊ መንግሥት አስተዳደር ቢሮ፣ ሆደሌይ (ቤተ-መንግስትና አየር መንገድ)፣ በሸህ አብዱሰላም ት/ቤት፣ በክልሉ ም/ቤት (ፓርላማ) አዳራሽ፣ በክልሉ ገቢዎች ቢሮ፣ በአሮጌው ታይዋንና በኢትዮ ቴሌኮም የምስራቅ ምስራቅ ሪጂን ጽ/ቤት አካባቢዎች አገልግሎቱን ማስጀመሩን ጠቁሞ፤ በጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ፣ በጅግጅጋ ሸህ ሐሰን ያባሬ ሪፈራል ሆስፒታል፣ በአዲሱ ታይዋን፣ ቀበሌ 06 (አህመድ ጉሬይ ት/ቤት) እና ጀላባ አካባቢዎች ደግሞ በቅርቡ አገልግሎቱን እንደሚያስጀምር አስታውቋል፡፡


”የ5ጂ የሞባይል ኔትወርክ አገልግሎት እስከ 10 ጊ.ባ በሰከንድ (Gbs) የሚደርስ ከፍተኛ ፍጥነት ያለው፣ ዳታ የማስተላለፍ መዘግየትን እጅግ በላቀ ሁኔታ በመቀነስ (Ultra-low latency) ወደ 1 ሚሊ ሰከንድ የሚያደርስ ሲሆን፤ በተጨማሪም በአንድ ካሬ ኪሎሜትር ውስጥ እስከ 1 ሚሊዮን የሚደርሱ በርካታ የቴክኖሎጂ መሳሪያዎችን እርስ በርሳቸው ለማገናኘት የሚያስችል ዓለማችን የደረሰበት ዘመናዊ የገመድ አልባ ኔትወርክ ቴክኖሎጂ ነው፡፡“ ብሏል፤ኩባንያው በመግለጫው፡፡


ኩባንያው በማከልም፤ “5ጂ አገልግሎት በተለይም ወሳኝ ተልዕኮ ላላቸው (Mission Critical) እና በተመሳሳይ ወቅት (real time) መከናወን የሚፈልጉ አገልግሎቶችን ለአብነትም የማምረቻ ፋብሪካዎች፣ ግብርና፣ ህክምና ለመሳሰሉ ኢንዱስትሪዎች እጅግ የላቀ ፋይዳ ያለው ሲሆን፤ እንደ ሹፌር-አልባ ተሽከርካሪዎች (self-driving vehicles) ፣ Internet of Things የመሳሰሉ ቴክኖሎጂዎች በተግባር እውን እንዲሆኑ የሚያስችል አስተማማኝ የዘመኑ ቴክኖሎጂ ነው፡፡” ሲል አብራርቷል፡፡

የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas

*ማህበሩ የቱሪዝም ሚዲያ ለማቋቋም የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርሟል


የኢትዮጵያ ቱሪዝምና ሆቴሎች ማርኬት ማህበር፣ አርቲስት ምህረት ታደሰን የቱሪዝም አምባሳደር አድርጎ የሾመ ሲሆን፤ ማህበሩ በዛሬው ዕለት ረፋዱ ላይ በስካይ ላይት ሆቴል  ከአርቲስቷ  ጋር የስምምነት ሰነድ ተፈራርሟል፡፡

 የማህበሩ ፕሬዚዳንት አቶ  ጌታሁን አለሙ በፊርማ ሥነስርዓቱ ላይ  እንደገለጹት፣ ማህበራቸው አርቲስት ምህረት ታደሰን የቱሪዝም አምባሳደር አድርጎ የመረጣት የተለያዩ  መስፈርቶችን አሟልታ በመገኘቷ ሲሆን፤ በቀጣይ አንድ ዓመት ኢትዮጵያን ለአለም በማስተዋወቅ ትሰራለች ብለዋል።

በሞዴሊንግና ትወና ዘርፍ እየሰራች እንደምትገኝ የገለጸችው አርቲስት ምህረት ታደሰ በበኩሏ፤ “ማህበሩ እኔን ለዚህ ትልቅ አገራዊ ሃላፊነት በመምረጡ የተሰማኝን ታላቅ ደስታ እገልጻለሁ“ ብላለች፡፡

እንደ አገር ቱሪዝምን ለማስተዋወቅ በሚደረጉ ጥረቶች ላይ የድርሻዋን እንደምትወጣም አርቲስቷ በፊርማ ሥነስርዓቱ ላይ ተናግራለች፡፡  

 በተጨማሪም፣ የኢትዮጵያ ቱሪዝምና ሆቴሎች ማርኬት ማህበር፣ ኒዮ ሶሳይቲ ከተባለ መንግስታዊ ያልሆነ አገር በቀል ድርጅት ጋር የቱሪዝም ሚዲያ ለማቋቋም የመግባቢያ ሰነድ የተፈራረመ ሲሆን፤ የሚቋቋመው የቴሌቪዥን ጣቢያ 24 ሰዓት ስለ ኢትዮጵያ ቱሪዝም በተለያዩ ቋንቋዎች የሚያስተዋውቅ እንደሚሆን ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ቱሪዝምና ሆቴሎች ማርኬት ማህበር ፕሬዚዳንት አቶ  ጌታሁን አለሙ፤ ማህበሩ የቱሪዝሙን ዘርፍ በማነቃቃት የሆቴሎችን የአገልግሎት ደረጃ ለማሳደግ በትጋት እንደሚሰራ ተናግረዋል፡፡

በቅርቡ በ3 የአፍሪካ አገራት የዳታ ማዕከሎቹን ይከፍታል

በሰባት የአፍሪካ አገራት የሚንቀሳቀሰው  ራክሲዮ የዳታ ማዕከል ኩባንያ፣ በአዲስ አበባ አይሲቲ ፓርክ ውስጥ የገነባው ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የዳታ ማዕከል  በይፋ ሥራ መጀመሩን አብስሯል፡፡
በዓይነቱ ልዩ መሆኑ የተነገረለት ራክሲዮ ኢትዮጵያ የዳታ ማዕከል፣ በይፋ ሥራ መጀመሩን የማብሰሪያ ሥነስርዓት ባለፈው ማክሰኞ ህዳር 11 ቀን 2016 ዓ.ም፣ በአይሲቲ ፓርክ የተከናወነ ሲሆን፤ በሥነሥርዓቱ ላይ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ አምባሳደሮች፣ የፋይናንስ ተቋማት ሃላፊዎች፣ የቴክኖሎጂ ዘርፉ መሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡


ራክሲዮ ኢትዮጵያ  ባሰራጨው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ “በኢትዮጵያ ዋና ከተማና የአገሪቱ የኢኮኖሚ ማዕከል በሆነችው አዲስ አበባ የሚገኘው አዲሱ የራክሲዮ ደረጃ III ዕውቅና የተሰጠው ዘመናዊ የዳታ ማዕከል፣ ከምንጊዜውም በላይ እያደገ ለመጣው የመንግሥትና የግል ተቋማት የዳታ ማዕከል አገልግሎት ጥያቄዎች፣ አስተማማኝና የማይቆራረጥ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መፍትሄ በማቅረብ መልስ የሚሰጥ ይሆናል፡፡” ብሏል፡፡ ማዕከሉ፤ 800 ራኮችና እስከ 3 MW የአይቲ ሃይል፣ ደህንነቱ በተጠበቀ የዳታ ማዕከል አገልግሎት ለመስጠት፣ ሙሉ በሙሉ ምትክ ያለው ያለማቋረጥ የሚሰራ የአይቲ መሰረተ ልማቶች  ዝግጁ አድርጓል ተብሏል፡፡

በኢትዮጵያ የራክሲዮ ዳታ ማዕከል ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ በዕውቀቱ ታፈረ ባደረጉት ንግግር፤ “ይህ አገልግሎት በአዲስ አበባ መጀመሩ ለራክሲዮና ለአገራችን በዲጂታል መሰረተ ልማት ረገድ መሰረት የሚጥል ነው፡፡ አገልግሎቱ በኢትዮጵያ የምጣኔ ሃብት ዕድገት ውስጥ ከፍተኛ ሚና የሚጫወት ሲሆን፤ በተለያዩ አካባቢዎች የሚከናወኑ የንግድ ሥራዎችንና የመንግሥት ኤጀንሲዎች የሥራ እንቅስቃሴን ከማፋጠንም ባሻገር፣ አህጉራዊና ዓለማቀፍ አገልግሎትና የይዘት አቅራቢዎችን ወደ ኢትዮጵያ ለመሳብ አጋዥ እንደሚሆን እናምናለን፡፡” ብለዋል፡፡ ዋና ሥራ አስኪያጁ በማከልም፤ “የማዕከላችን ደረጃ III ዓለማቀፍ የምስክር ወረቀት፣ እኛ  እየሰጠን ያለው የአገልግሎት ጥራት መጠን ማሳያ ሲሆን፤ ለደንበኞቻችን ደግሞ ለማናቸውም ንብረቶቻቸው ከፍተኛ ደህንነት አስተማማኝ ማረጋገጫ የሚሰጥ ነው፡፡” ሲሉ አስረግጠው ተናግረዋል፡፡


የዳታ ማዕከሉ በይፋ ሥራ መጀመሩን ያበሰሩት የራክሲዮ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሮበርት ሙሊንስ በበኩላቸው፤ “ይህንን በዓይነቱ ልዩና የመጀመሪያ የሆነ ወሳኝ መሠረተ ልማት በኢትዮጵያ ተግባራዊ በማድረጋችን እጅግ ኩራት ይሰማናል፡፡ የኢትዮጵያን ቀጣይ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽንና የዲጂታል አካችነት ጅምር ግቦችን የሚደግፍ እንደሆነ ሙሉ እምነታችን ነው፡፡ ብለዋል፡፡ ሮበርት ሙሊንስ አክለውም ሲናገሩ፤ “ይህ ጊዜ ለእኛ እንደ ኩባንያ እጅግ በጣም ደስተኛ የሆንበት ነው፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት በኡጋንዳ እንደዚሁ ተመሳሳይ ማዕከላችንን ከጀመርን በኋላ፣ ራክሲዮ ኢትዮጵያ በአህጉሪቱ ሁለተኛው ማዕከላችን  መሆኑ ነው፡፡ እ.ኤ.አ. እስከ 2024 የመጀመሪያ አጋማሽ ድረስ ተመሳሳይ ማዕከሎችን  በሞዛምቢክ፣ በአይቮሪኮስትና በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የምንከፍት ይሆናል፡፡” ብለዋል፡፡ በዕለቱ  ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና ባለድርሻ አካላት እንዲሁም የሚዲያ ባለሙያዎች የራክሲዮ ኢትዮጵያ  የዳታ ማዕከልን  ጎብኝተዋል፡፡

አንድ የአይሁዶች አፈ-ታሪክ አለ።
ገና ዓለም ስትፈጠርና በውስጧ ያለው ነገር ሁሉ አዲስ በነበረ ጊዜ ፀሐይና ጨረቃ እኩል ነበሩ አሉ። ፀሐይ ግዙፍና ወርቃማ ነበረች። ሁለቱም ብሩህ ሁለቱም ቆንጆዎች ነበሩ።
ያኔ ጨረቃና ፀሐይ እየተፈራረቁ ነበር የሚያበሩት። ሰማይ ላይ የሚቆዩበት ጊዜም እኩል ነበረ። አቅማቸውም እኩል ነበረ።
እያደር ጨረቃ የበለጠ ጥቅም መፈለግ፣ የበለጠም ኃይል መመኘት አመጣች።
“ለምንድነው ሰማይን ከፀሐይ ጋር የምንጋራው?” አለች ለራሷ። “ጊዜንስ ለምን ግማሽ ግማሽ አካፍላለሁ።  ለምንስ ግማሽ ቀን ተሸሽጌ እቆያለሁ። ሁልጊዜ ማብራት አለብኝ። ከፀሐይ የበለጠ ማብራት መቻል አለብኝ። የበለጠ ግዙፍና የበለጠ ኃይለኛም መሆን አለብኝ። እኔ ከፀሐይ የበለጠ ቆንጆ መሆኔን እንደሆነ ማንም የሚያየው ነገር ነው።”
ስለዚህም ወደ አምላክ ዘንድ ሄደችና፤ “ ከፀሐይ የበለጠ ብርሃን፣ የበለጠ ጊዜ እና የበለጠ ሰማይ ሊኖረኝ ይገባል” አለችው።
አምላክም፤ “ለምን የበለጠ ይኖርሻል?” ሲል ጠየቃት፡፡
ጨረቃም፤ “ለእኔ የበለጠ ስለሚገባኝ ነዋ- የበለጠ ሊኖረኝ ስለሚገባ። ከፀሐይ የተሻልኩና የበለጠም ቆንጆ ስለሆንኩ።” አለችና መለሰች።
“ምን ላድርግልሽ ታዲያ?” አለ ፈጣሪ።
“ከፀሐይ የበለጠ ግዙፍ፣ የበለጠ ብሩህና በሰማይ ላይ የምቆይበት ጊዜም የእኔ ብዙ እንዲሆን አድርግልኝ።”
“አንቺ በጣም ስስታም ነሽ። ከአቅምሽ በላይ ትመኛለሽ። ስለራሽም ያለሽ ግምት ከልኩ በላይ ነው። ያም ሆኖ አንዳንድ ለውጥ አደርግልሻለሁ”
ፈጣሪ ልክ ይሄን ከተናገረ በኋላ ጨረቃ መለወጥ ጀመረች።  ፈቷ በደስታ በፈገግታ ተሞላ።
የበለጠ ግዙፍና ብሩህ ለመሆን ትጠብቅ ጀመር። “ባንድ ጊዜ በልጫት ስገኝ ፀሐይ ምን ይሰማት ይሆን?” አለች በሆዷ።
ነገሩ ግን እንዳሰበችውና እንደተመኘችው አልሆነም። “በጣም ስስታም ነሽ!!” አላት አምላክ በቁጣ። “ስለዚህም ከእንግዲህ ከፀሐይ ያነስሽ ትሆኛለሽ። ስለራስሽ ያለሽ ግምት ከልክ በላይ ስለሆነም ብርሃንሽ ይደበዝዛል። ለስስትሽና ያለአቅምሽ ለመንጠራራትሽ ቀሪውን ዕድሜሽን ትቀጭበታለሽ” አላት።
ጨረቃ አለቀሰች። “ከድርሻዬ በላይ ስጠኝ ማለት አልነበረብኝም። መታበይ አልነበረብኝም። አምላክ ሆይ ይቅርታ አድርግልኝ” አለችው።
ፈጣሪም፤ “አሁንማ ረፈደ። ዕድል አንዴ አመለጠሽ” አላት በለሆሳስ። በእርግጥ ከልቧ እንዳዘነች ግን ገብቶታል። ከዚህ በላይ ሊቀጣት አልፈለገም።
“ከእንግዲህ ከዋክብት እንዲያጅቡሽ ፈቅጀልሻለሁ።” አለና ጥቁሩ ሰማይ ላይ ከዋክብትን ዘራቸው። “ጊዜን ለመለካት አስተዋጽዖ ታደርጊያለሽ። ከዛሬ ጀምሮም እያንዳንዱ ቀን ነጋ የሚባለው ፀሐይ ስትወጣ ሳይሆን ሶስቱ የምሽት ኮከቦች ሲታዩ ይሆናል። ከዚህ ቀን በኋላ አይሁዶች ቀኑ ነጋ ብለው የሚያስቡት የመጀመሪያዎቹ ሶስት የምሽት ከዋክብት ሲወጡ ሆነ። ቀናትን፣ ወራትንና ዓመታትን የሚቆጥሩትም በፀሐይ ሳይሆን በጨረቃ ሆነ። በሰማይ ላይ አዲስ ጨረቃ በየጊዜው ስትወጣ ለፈጣሪ ፀሎት ያደርሳሉ።
**            *
ያለአቅም መመኘት ያለአቅም መንጠራራት፣ ሁሉን ለእኔ ካላጋበስኩ ማለት ውጤቱ ሀዘንና ፀፀት ነው። የእኩል ሰማይን በእኩል ለመጠቀም ሲቻል፤ እኔ የተለየሁ ነኝ፣ እኔ የበኩር ልጅ ነኝ፣ እኔ የተሻልኩ ነኝ በሚል አስተሳሰብ፣ የአንበሳውን ድርሻ እኔ ካልወሰድኩ ብሎ ለራስ የተሳሳተ ግምት መስጠት፣ ውሎ አድሮ ማቀርቀር፣ ውሎ አድሮ ማፈርና ማነስ፣ ቀጥሎም ዝቅ ብሎ መገኘትን ያስከትላል።
ሀገራት የጋራ ናት። ሁሉም በእኩል የሚኖርባት፣ ሁሉም በእኩል የሚጠቀምባት፣ የጋራ እናት፣ የጋራ ሀብት መሆን አለባት። አንዱ ዘመድ፣ አንዱ ባዕድ፣ አንዱ አቻ ጋብቻ፣ ሌላው የሩቅ ሰው ተደርጎ የሚታይባት አይደለችም። አንዱ በወገንነት ተፈርጆ፣ ከስባቱም ከሹመቱም የሚቋደሱባት፣ ሌላው ለገበታም ለሰላምታም አይበቃም የሚባልባት አይደለችም። ይህን ከግንዛቤ ሳንጨብጥና በተግባር ሳናውል እኩልነት የሰፈነባት፣ ፍትሕ ያረበበባት፣ እናት አገር ብንል የለበጣ ይሆናል። ስለራሳችን የምንሰጠው ማናቸውም ግምት ትክክል፣ ሌሎች እንዴት እንደሚያዩን የሚነግሩን ሁሉ ሀሰትና የተሳሳተ፤ እኛን የደገፈ ሀቀኛ፣ እኛን የተቃወመ የሃገር  ጠላት  ተደርጎ የሚታይባት አገር፣ የሁሉ እናት ለመባል ከቶም አትችልም። ለአንዱ ሰፊና እንደልብ መንቧቻ፣ ለሌላው ጠባብና መላወሻ የሌላት ከሆነች የእኩል ቤት ለመሆን አትችልም። “ተጠንቀቅ የሚልህ ወዳጅህ፤ አይዞህ የሚልህ ጠላትህ” ይሏልና፤ ከምሥራች ጭብጨባ ይልቅ የማስጠንቀቂያ ደወልን ማዳመጥ፣ አገርን በአግባብና በሚዛን ለመምራት ይበጃል።
ያለ ዕድሜ- ስስት ለነገ ትውልድ ማሰብ፣ የትላንትናን ድርጊት በጥሞና መርምሮ ለነገ መዘጋጀት፣ ራስ-ተኮር አካሄድን በጊዜ መቅጨት የአስተዋይ መሪዎች፣ የበሳል ፖለቲካ ፓርቲዎችና ቡድኖች መለያ ምልክት ነው። “ያለ የማያልፍ ይመስለዋል፣ ያለፈ ያልነበረ ይመስለዋል” እንዲል መጽሐፍ፣ ዘመን ሲጠባ ለውጥ መምጣቱ እንደማይቀር አለመገንዘብ ሁለቴ መጎዳት ነው። ያኔ፣ የተደረገው ሁሌ ትዝታና ታሪክ ሳይሆን በለውጡ ሰዓት የሚፈተሽ፣ በደጉ የሚወሳው መወደሻ፣ በክፉ የሚወሳው መወቀሻ መሆኑ አሌ አይሉት ሃቅ ነው። ስለዚህም የትናንቱ ለዛሬ ትልቅ ፋይዳ አለው ማለት ነው። “ታሪክ የትላንት ፖለቲካ ነው። ፖለቲካ ደግሞ የዛሬ ታሪክ ነው” ይለናል  ጆን ሲሌይ። ታሪክ ተያያዥነት ያለው መስተጋብር እንጂ ይህ ድንበር እዚህ ጋ ይቁም፣ ይሄኛው ከዚህ ወዲያ ይቀጥል የሚባል የጊዜ ደሴት አይደለም። ታሪክ ፈሳሽ ወንዝ ነው- ለዋጭ-ተለዋጭ (Dynamic) ማህረሰብ ይዞ የሚጓዝ። ለለውጥ መዘጋጀት የሚያድግ ማህበረሰብ ተስፋ ነው። የሚለወጥ ህብረተሰብ አገር ያሳድጋል። የተስፋ ነብሰ-ጡር ነው።
“ካፈርኩ አይመልሰኝ” ማለት የግትርነትና የግብዝነት ቀኝ እጁ ነው። “ካፈርኩ አይመልሰኝ” የዲሞክራሲም፣ የመልካም አስተዳደርም፣ የፕሬስ ነጻነትም ጠር ነው። ያለአቅማችን አቅም ያለንና የተረፈን በመሰለን ቁጥር ለብዙ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ህልውናችንና እንቅስቃሴያችን የምንሰጠው ግምት የተዛባ ይሆናል። የተዛባ እሳቤ ደግሞ የተዛባ መደምደሚያ ላይ ያደርሳል። ይህ እየተነገረን “ካፈርኩ አይመልሰኝ” አሻፈረኝ ማለት፤ “ዳን ሲሉት ልኮነን አለ” እንደተባለው መሆን ነው። የተራመድን እየመሰለን መዳከር፣ የሮጥን እየመሰለን መንሸራተት ይሆናል ጉዟችን። ለየጉዳዩ ሁሉ ያልተስተካከለ ስእል እንድንሰጥ፣ ኮሳሳውን አቅማችንን አጋንነን፣ ግዙፉን ስህተታችንን ጠብታ ጉድፍ ብለን እንድናይ ያደርገናል።
አቅም ለመገንባትም የአስተሳሰብ ብስለት፣ የእምነት ፅናት፣ ከመጠራጠር የመውጣት፣ የሰብዓዊነት፣ የሴራ-አልባነት፣ የአንድ-ወገን ተጠቃሚነትን መዋጋት፣ የግል ወይም የፓርቲ ተልዕኮን ከአገር ተልዕኮ ለይቶ የማየት፣ አድማሰ-ሰፊ ራዕይን ከቅርብ የፖለቲካ ግብ አለማምታታትን - አብሮ መገንባት ይጠይቃል። የአቅም ግንባታ ከሁሉም  በፊት የቀናነትን መንፈስ በየልቡ ውስጥ መገንባትን ይጠይቃል።
ብዙ ዕቅዶችን መዘርጋትን በራሱ እንደ ግብ ከመቁጠር፣ አንድን አጠንክሮ ካለመያዝና እዚህም እዚያም ከመዋዠቅ የተነሳ አገር ትላላለች። በየእለቱ የኢኮኖሚ አቅሟም ይላላል። በመቶና በሺህ የሚቆጠሩትን እቅዶች ተግባር ካልዳሰሳቸው፣ በሁለት እግር ለመቆም አይቻልም። እንዲያውም ከነአካቴው አቅም ገንቢው የራስን አቅም አፍራሽ ሆኖ ቁጭ ይላል። ፖለቲካዊ ጥላቻ ኢኮኖሚያዊ የሥራ መንፈስን መግደሉን እስከዛሬ ስናይ ኖረናል። የኢኮኖሚ ውድቀት ደግሞ የየጓዳችን መሶብ ባዶ መሆን ብቻ ሳይሆን፣ እጃችንን ተጠምዝዘን የሃያላን መንግሥታት ፈቃደ-ልቡና ፈፃሚ እንድንሆን ያደርገናል። ያኔ እንግዲህ አለን አይባልም።
የፖለቲካው ጫና የሥራ መንፈስን እንዳያቀጭጭ ብርቱ ጥንቃቄ ይሻል። “በየትም አይደርሱም” እና “መንገዱን ጨርቅ ያድርግልህ” ወንዝ አያሻግርም። የሥራ መንፈስ የጎደለው ህዝብ፤ ለውጥ አብሪ አይሆንም። ይልቁንም የባሰ መንገዱን ያጨልማል። ማንኛውንም የፓርቲ አሰራር ከሀገር ጉዳይና ጥቅም አኳያ ካላየን አደገኛ ነው። “ከሁለት የወለደ አይደሰት፣ ሳይወልድ የሞተ አስተዛዛኝ የለው” መሆኑ ነውና። ሁለተዜ ጉዳት ብቻ ሳይሆን ነገ ያስጠይቃል። ታሪክ ጠያቂ፣ እኛ ተጠያቂዎች ነንና። የነገ ታሪካችን መጣጥፎች የዛሬዎቹ እኛ ነን። ለዛሬ ብቻ እየኖርን የአንበሳውን ድርሻ እያሰብን ከተጓዝን፣ ነገ የአበሳውም ድርሻ የእኛው ይሆናል። ማኘክ ከምንችለው በላይ መጉረስ፣ መተግበር ከምንችለው በላይ ማቀድ፣ ተሽመድምዶ መውደቅን፤ ራስን በራስ መብላትን ያስከትላል። “ለሁልጊዜ የሚሆን ምከር፣ ለጥርስ የሚሆን ንከስ” የሚባለውም ለዚህ ነው። ፀሐይ እንጂ ጨረቃ አንሁን።

* ቢል ጌትስን ጨምሮ በርካታ ባለጸጎች ሰፋፊ የእርሻ መሬቶችን እየገዙ ነው
* የአሜሪካ ቢሊየነሮች ከቻይና ጋር በፍቅር መውደቃቸው ተረጋግጧል
* የዜጎችን ህይወት ለመቆጣጠር አርቴፊሻል ኢንተለጀንስን እየተጠቀሙ ነው

ባለፈው ማክሰኞ በአሜሪካ  ለንባብ የበቃው “Controligarchs: Exposing the Billionaire Class, their Secret Deals, and the Globalist Plot to Dominate Your Life” የተሰኘው የአሜሪካ ቢሊየነሮችን ድብቅ አጀንዳ የሚያጋልጠው አዲስ መጽሐፍ፣ የመገናኛ ብዙኃን የሰሞኑ መነጋገርያ ሆኗል፡፡
እኔና የጥናት ቡድኔ የገንዘቡን ዱካ ተከትለን በአሜሪካ ቢሊየነሮች ላይ ጥልቅ ጥናትና ምርምር አድርገናል የሚለው የመጽሐፉ ደራሲ ሼመስ ብሩነር፤ በጥናቱም ያልተጠበቀና አስደንጋጭ ውጤት ላይ መድረሳቸውን ይገልፃል፡፡  Controligarchs በሚል የሚገልጻቸው ቢሊየነሮች፣ ከአሜሪካ ጠቅላላ ህዝብ 1 ፐርሰንቱን ብቻ የሚወከሉ ባለጠጎች መሆናቸውንም  ይናገራል።  
መጽሐፉ፤ እንደ ቢል ጌትስ፣ ማርክ ዙከርበርግና ጆርጅ ሶሮስ ያሉ ልሂቃን  ቢሊየነሮች  እንዴት  የአሜሪካውያንን የዕለት ተዕለት ህይወት  ለመቆጣጠር እንደሚታትሩ ይጠቁማል፡፡  እኒህ  ቢሊየነሮች ህይወታችንን ለመቆጣጠር “ጨቋኝ አምባገነናዊ  ሥርዓት” በንቃት እየገነቡ ነው የሚለው ብሩነር፤ እንደ ፌስቡክ ባሉ ግዙፍ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች የሚስተዋለው ሃሳብን ሳንሱር የማድረግ ተግባር፣ ገና የእንቅስቃሴያቸው  “መጀመሪያ” ነው ይላል፡፡
እንደ ማርክ ዙከርበርግ፣ ጄፍ ቤዞስና ቢል ጌትስ ያሉ ባለጸጎች፣ በኮቪድ ወረርሽኝ ወቅት  ሌሎቻችን  ሁሉ  ከእንቅስቃሴ ተገድበን ሳለ፣ እነሱ  የሃብታቸውን መጠን፣ በቢሊዮን ዶላሮች በማሳደግ ራሳቸውን ማበልጸጋቸውን ደራሲው ይነግረናል፡፡
እነዚህ ሰዎች  ግሎባሊስቶች ናቸው የሚለው ደራሲው፤ ታማኝነታቸውም ከአሜሪካ ይልቅ ለዓለም ኢኮኖሚክ ፎረም ነው፤ ባይ ነው፡፡ ”ለአሜሪካ ታማኝ አይደሉም፤ ተግባራቸውና የገንዘብ ድጋፋቸውም ሌላ የሚታመኑለት  አካል መኖሩን ያሳያል“ ብሏል፡፡     
ቻይናንና የቻይና ሥርዓትን እንዴት በፍቅር እንደሚወዱ በጥልቀትና በዝርዝር አሳይቻለሁ የሚለው ደራሲው፤ ሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI)፣ በህብረተሰቡ ውስጥ የበለጠ ሃይልና ቁጥጥር ለማግኘት የሚጠቀሙበት ሌላ መሳሪያቸው  መሆኑን ያስረዳል፡፡
“Red-Handed,” “Clinton Cash” እና “Profiles in Corruption” የተሰኙት መጻሕፍት ደራሲው ፒተር ሽዊትዘር፣  በ“Controligarchs” መቅድም ላይ ባሰፈረው ሃሳብ፤ “መፅሐፉ፤ መጪውን ዘመን በጥንቃቄ አሻግሮ የሚመለከትና  አስደንጋጩን የግራ ዘመም ልሂቃን፣ የ5 ዓመት ፍኖተ ካርታ የሚያጋልጥ ነው፡፡” ብሏል፡፡
በዚህ መጽሐፍ ውስጥ መረጃን መቆጣጠር ሌላው “ትልቁ ጭብጥ” ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ለግዙፍ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ሴንሰርሺፕ እንግዳ አለመሆናቸውን የሚያነሳው  ደራሲው፤ ይሄ ግን “ገና ጅምሩ ነው” ሲል ያስጠነቅቃል፡፡   “የግል መረጃችሁን  እየመነተፏችሁ   ነው፡፡ ሰው ሰራሽ አስተውሎትን (AI) እያሳደጉ ነው፤ እናም አሁን ያሉትን ብዙዎቹን የሥራ ዕድሎች  ለማስወገድ ይጠቀሙበታል፡፡ ከአምስት እስከ አሥር ዓመት ባሉት ጊዜያት ውስጥ  እስከ 40 በመቶ፣ ምናልባትም ከዚያ በላይ የሚሆነውን ሥራ ይወስዱታል፡፡” የሚለው ብሩነር፤ ይህም  የዕቅዳቸው አካል መሆኑን ይጠቁማል፡፡ የአየር ንብረት ለውጥን መዋጋት ወይም የህዝብ ብዛትን መቀነስ የሚሏቸውን  ጉዳዮች ለእውነተኛ አጀንዳቸው እንደ መሳሪያ  የሚጠቀሙበት መሆኑን   የሚገልጸው ደራሲው፤ እውነተኛ አጀንዳቸው ግን ሌላ ነው - “ቁጥጥር!”  ሁሉንም ነገር የመቆጣጠር አባዜ የተጠናወታቸው ይመስላል፡፡     እነዚህ ጥቂት  ቢሊየነሮች እያንዳንዱን ዕለታዊ  የህይወት ገጽታ  - ከምግብና ኢነርጂ እስከ ሥነ ተዋልዶና የግለሰቦች መረጃ ድረስ ለመቆጣጠር አቅደው እንደሚሰሩ  ደራሲው ባደረገው ጥናት መገንዘቡን ይገልጻል፡፡    
ቢል ጌትስ፣ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በሚል ሽፋን፣ የአሜሪካን የእርሻ መሬቶች  ለመግዛትና በሰው ሰራሽ የወተት ተዋጽኦዎችና በቤተ ሙከራ  ስጋዎች ላይ መዋዕለ-ንዋዩን ለማፍሰስ  የሚያደርገውን  ጥረት በጥናቱ መፈተሹን የሚገልጸው  ስመ-ጥር  የምርመራ ጋዜጠኛው  ብሩነር፤ በዚህ ሂደትም፣ ቢሊየነሩ የካርቦን ልቀትን ከማስወገድ በበለጠ ሀብቱን ለማሳደግ በእጅጉ እየሰራ መሆኑን ጠቁሟል፡፡
“መጀመሪያ ላይ የፈጠራ ባለቤትነት የተሰጣቸው ዘሮችና ማዳበሪያዎች ነበሩ፣ አሁን ደግሞ የስጋ አማራጮችን የፈጠራ ባለቤትነት  እየሰጡ ነው። ከብቶች ላይ  እገዳ መጣል ለአማራጭ የፕሮቲን ኩባንያዎች ውጤታማ የበላይነት ቁጥጥርን የሚያጎናጽፍ  ሲሆን፤ ይህም  እንደ ቢል ጌትስ፣ ጄፍ ቤዞስ፣ ማርክ ዙከርበርግና ብላክሮክን የመሳሰሉ ባለሀብቶችን ጠቃሚ ነው፡፡ ሰው ሰራሽ ሥጋ፣ ፕላኔቷን የመታደግ ጉዳይ ሳይሆን፣ የምግብ ገበያውን የመቆጣጠር ጉዳይ ነው፡፡” ብሏል፤ብሩነር ከፎክስ ኒውስ ዲጂታል ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ።
የመጽሐፉ አንድ ምዕራፍ የሚያተኩረው “በገበሬዎች ላይ በሚደረገው ጦርነት” ላይ ሲሆን፤ እንደ ቢል ጌትስ ያሉ ግዙፍ የቴክኖሎጂ ኩባንያ ባለቤቶች፣ የሀገሪቱን የምግብ አቅርቦት በብቸኝነት ለመቆጣጠር የሚያደርጉትንም ጥረት   ያሳያል።
“የምግብ ስርዓቱን መቆጣጠር ልክ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ እንዳሉት ሌሎች በርካታ የቁጥጥር መርሃ ግብሮች በሮክፌለርስ የተጀመረ ቢሆንም፣ በቢል ጌትስ የላቀ ደረጃ ላይ መድረስ ችሏል፡፡ ልክ እንደ አብዛኛዎቹ ሞኖፖሊዎቻቸው (- ከዘይት ወደ ሶፍትዌርና በመጨረሻም ባዮቴክኖሎጂ -) የምግብ ቁጥጥሩ፣ የምግብ ምርት የአዕምሯዊ ንብረትን  በንግድ ምልክቶች፣ በቅጂ መብቶችና በባለቤትነት መብቶች አማካይነት መቆጣጠር ነው፡፡” ይላል መጽሐፉ። ቢል ጌትስ ከአስር ዓመታት በላይ የማዳበሪያ ኢንዱስትሪው ላይ አነጣጥሮ መዝለቁን የሚጠቁመው መጽሐፉ፤ በእነዚህ ጊዜያት ታዲያ  ድምጹን አጥፍቶ ሰፋፊ  የእርሻ መሬቶችን ሲገዛ መቆየቱንም ይገልጻል፡፡
ብሩነር እንደሚለው፣ ቢል ጌትስ፣ ለእርሻ መሬት ግዥዎችና አሁን ለሚተገብሩት የአጀንዳ 2030 ተስማሚ ቴክኖሎጂዎች ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ወጪ አድርጓል፡፡
 አጀንዳ 2030፤ “የከፋ ድህነትን ለማስወገድ፣ የእኩልነት መዛባትን  ለመቀነስና ፕላኔቷን ከጥፋት ለመታደግ” ያለመ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት መርሃግብር ነው፡፡ “ቢል ጌትስ በአስር ሺዎች የሚሰላ ሄክታር መሬት ሲገዛ መሬቱን ብቻ አይደለም የሚገዛው - ከመሬት በታች ያለውን የውሃ መብትም ጭምር  እየገዛ ነው፡፡ ጌትስ  ከእርሻዎች (እና መስኖው) እንዲሁም ማዳበሪያ በተጨማሪ - የግብርና ኢንዱስትሪን ለመቆጣጠር ሲፈለግ ወሳኝ አካል በሆነው - በውሃና የውሃ አያያዝ ላይም ከፍተኛ ድርሻ  ለማግኘት ሲታትር ከርሟል፡፡” ብሏል ብሩነር፡፡
ሌላው የመፅሐፉ ክፍል፣ የቢል ጌትስ  ቀጣይ ኢላማ፣ እንደ Beyond Meat እና  Impossible Foods ያሉ ሰው ሰራሽ የስጋ ማምረቻ ኩባንያዎች ላይ ያነጣጠረ መሆኑን ያስጠነቅቃል፡፡ ኩባንያዎቹ  ለአርቴፊሻል  ስጋ (እና ሰው ሰራሽ የወተት ተዋጽኦ) ምርቶቻቸው ከሁለት ደርዘን በላይ የፈጠራ ባለቤትነት የተቀበሉ ሲሆን፤ ገና የሚጠባበቁት ከ100 በላይ የፈጠራ ባለቤትነት ያላቸው ናቸው።
 ቢል ጌትስ በነዚህ ኩባንያዎች ውስጥ ብዙ ሚሊዮን ዶላሮችን  ኢንቨስት አድርጓል፤ ምንም እንኳን በአጠቃላይ ሸማቾች በምርቶቹ  ላይ እምብዛም  ፍላጎት ባያሳዩም፡፡   ብሩነር እንደሚለው፣ ቢል ጌትስ ወደ ሰው ሰራሽ  የስጋ ገበያ የመግባቱ ነገር የመጣው፣ ከብቶች  ለአየር ንብረት ለውጥ ከፍተኛ  አስተዋፅዖ እንደሚያደርጉ ማስጠንቀቁን ተከትሎ ነው፡፡  “ገበሬዎች፤ አርቴፊሻል የዕጽዋት ስጋና በላቦራቶሪ የተመረተ ስጋ እንዲመገቡ ሲጠበቅባቸው ፣ እንደ ቢል ጌት ያሉ ቢሊየነሮች  ከግል ሼፎቻቸው ጋር - ተመሳሳይ ምግብ ለመመገብ  ምንም ዓይነት ፍላጎት የላቸውም።”
ሲል ይተቻል፤ብሩነር።“ቢል ጌትስ በኦማሃ አማካሪውን ዋረን ቡፌትን  ሲጎበኝ፣ ሁለቱም  ከበሬ ሥጋ የተዘጋጀ  በርገርና ስቴክ መብላት ይወዳሉ። ዙከርበርግ በጭስ የተሰናዳ የበሬ ሥጋና የተጠበሰ የአሳማ ጎድን (የእውነተኛ በሬና አሳማ) እንደሚወድና “ስጋ የበለጠ ጣዕም የሚኖረው እንስሳቱን ራስህ ስታድን ነው” ሲል መናገሩን  ብሩነር በመጽሐፉ አስፍሯል፡፡ **
የመጽሐፉን ቅኝት ከመቋጨታችን በፊት ለውይይት መነሻ የሚሆኑ ጥቂት ጥያቄዎችን እነሆ፡-
* ለመሆኑ  ደራሲው “Controligarchs” ሲል የሚጠራቸው  ቢሊየነሮች፣ ለምንድነው ከአሜሪካውያን የፖለቲካ ባህልና ወግ ባፈነገጠ መልኩ፣ ጨቋኝ የቁጥጥር ሥርዓት ለመገንባት የሚታትሩት?
*ለምንስ ይሆን ከአገሪቱ የሰለጠነ የፖለቲካ ልምምድ በተለየ፣ የሃሳብ ነፃነትን ለመገደብና ተቃዋሚዎችን ለማፈን በትጋት የሚሰሩት?
 * ለምንድን ነው የዜጎችን ህይወትና እያንዳንዱን እንቅስቃሴያቸውን ለመቆጣጠር አልመው የሚንቀሳቀሱት?
ለእኒህ ጥያቄዎች ትክክለኛውን መልስ የምትፈልጉ ከሆነ፣ ብቸኛው አማራጫችሁ  መፅሐፉን ፈላልጎ  ማንበብ ብቻ ነው። አንብቡት፡፡  ሠናይ ጊዜ!

Saturday, 25 November 2023 20:17

“ሲበቃ በቃ ነው…”

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ስሙኝማ… መቼም ያቺ “..ድሮ ቀረ” የሚሏት ነገር በሰበብ አስባብ ብቅ ማለቷ ባይቀርም …አለ አይደል… አንዳንዴ ‘ፍሬሽ’ ነገር አይጠፋም፡፡
 የምር’ኮ… አንዳንዴ የሆነ ነገር ትሰሙና…በቃ “ጆሮዬ ነው!” ትላላችሁ፡፡
አንዳንዴ ”ሲበቃ በቃ ነው“ እንዴት አንጀት ያርሳል መሰላችሁ፡፡ ግን ደግሞ ድፍረት ይጠይቃል፤ወኔ፡፡ በተለይማ ‘ራስ’ ላይ “ሲበቃ በቃ ነው” ማለት… አለ አይደል… “ሊታረቀን ይሆን እንዴ?” ያሰኛችኋል፡፡ አሀ… የምር’ኮ እንዲህ ሲባል ምን ትዝ ይላችኋል መሰላችሁ..”ወተት ይሸፍታል እንኳን ሰው ሲበደል…” የሚሉት ነገር፡፡
እኔ የምለው… መቼም ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…በቃ ‘ቤስት ፍሬንድ’ ምናምን የሚባል ነገር ቀረ ማለት ነው? የምር … ከግብፅ አውሮፕላንና መድፍ ይልቅ… የሚያሰጋው ይሄ! በቅርብ የምናውቀው ወዳጃችን… ‘ሲያበላው ሲያጠጣው’ በነበረ የልብ ጓደኛው፣ ሀምሳ ምናምን ሺህ ብር ሲጭበረበር … ተስፋ ያላስቆረጠ ምን ያስቆርጥ!
አሀ… ጭራሽ እኮ አሁን አሁንማ ‘የልብ ጓደኝነት’ የሚባለው ቀረላችሁና… አለ አይደል… ‘ፍሬንድሺፕ’ የሆነ ኢንቬስትመንት ነገር ሆነላችሁ፡፡ ዘንድሮ… የጓደኝነት መስፈርት ‘ባህርይ’ ሳይሆን… የባንክ ደብተር ሆኖላችኋል፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ… ለስድሳ አምስት ሳንቲም አረቄም… ለስድስት ብር ‘ወርቅ ውሃም’ መፈነጋገል! ይህንን ነበር “ሲበቃ በቃ ነው!” ማለት፡፡
“እኔን ካንተ በፊት…” “ካንቺ ያስቀድመኝ…” ምናምን እንኳን በእውን ሊታይ ቀርቶ… በልብ ወለድም ቢፃፍ “አቤት ውሸት!” የሚያሰኝ እየሆነ ነው፡፡
ስሙኝማ.. እዚህ አገር እኮ… በቃ፣ አንዳንዱ ‘እንደልቡ’ እንዲሆን ‘ልዩ ፍቃድ’ የተሰጠው ይመስላችኋል፡፡ አንዳንዱ ባለሥልጣን የአዳራሽ ውስጥ የቦርድ ስብሰባም ይሁን… የዛፍ ስር የቤተ ዘመድ ጉባኤ… ለመፎከር ‘ፍቃድ የተሰጠው’ ይመስላል፡፡ ከጥቂት ወራት በፊት አንድ ወዳጄ… የሆነ ‘እንጎቻ ቦስ’ [ቂ…ቂ…] “ሁልሽም የመዋቅር ጊዜ ታገኛታለሽ…” ብሎ ሲፎክርባቸው ውሎ… ምን አለፋችሁ… እንደተንጨረጨረ ነው የዋለው፡፡
አሀ… ከፈለገ ‘የቀረው ይቀራል’ እንጂ ገና ለገና… ‘አብዮት ማስነሳት ቀርቷል’ ተብሎ መሰደብ አለብን! [አንተ ወዳጄ… እንዴት ነው፣ የማኦን ጥቅስ ‘ቀዩዋን መጽሐፍ ልስጥህ እንዴ!] እናላችሁ… በዚህ ለ’እነ እንትናም ባልሆነ ዘመን…ለምን ይፎከርብናል!
የምር ግን… እዚህ አገር ምን ግርም ይለኛል መሰላችሁ… ይሄ ‘ሹም ሽረት’ የሚሉት ነገር፡፡ ከሆነ ቦታ “እፎይ ተነሳልኝ…” ያላችሁት ‘ቦስ’ ዞሮ ሌላ ቦታ ‘ገጭ’! እና… በ‘ቀሺምነት’ ከአንድ ቦታ ተነስቶ… ሌላ ላይ ቁጭ… እንዴት ነው ነገሩ! ‘ሥልጣን’ አካባቢም “የሰፈር ልጅ ተደጋገፍ” ምናምን የሚባል ነገር አለ እንዴ! ሂሱን ጠጥቶ ጠጥቶ ከሆነ ቦታ የተነሳ ‘ቱባ…’ በአስራ አምስተኛው ቀን የሆነ አዳራሽ ውስጥ “አገራችን በተያያዘችው የግንባታ ጥረት…” ምናምን ሲል… በቃ፣ ተስፋ ነው የምትቆርጡት! ልጄ… እንኳን አዲስ ሊገነባ የተሰነጠቀውን መለሰኛ ሲሚንቶ የሚያቀርብ ጠፍቷል፡፡
እናላችሁ… ይልቅ “ሲበቃ በቃ ነው” ማለት እንዲህ ዓይነቱን ነው፡፡ “ከሌለህ፣ የለህም፣” እንደሚለው… እዛ ‘ላይም’ “ካልቻልክ አልቻልክም” መባል አለበት፡፡ አሀ…‘የላቦራቶሪ አይጥነት’ ሰለቸና! ‘አንገታችን የሚደርሰው’ ነገር በዛብን’ኮ!
እናላችሁ… መዓት ነገር “ሲበቃ በቃ ነው” የሚል እየጠፋ… ከአንገታችንም እያለፈብን ነው፡፡ አሁን ለምሳሌ... ይሄ  የ‘መፈክር’ ነገር ልባችንን እንዳቆሰለው! የምር! በቃ በጨርቅ መፈክር ካልተደረደረ “የምናምን ቀን” ማክበር አይቻልም ማለት ነው!
ኮሚኩ ነገር ደግሞ ምን መሰላችሁ…‘እውነት’ የሚሆን መፈክር የለም፡፡ አሀ…ልክ ነዋ! ይኸው ዓለም የወዛደር አልሆነች… ኢምፔርያሊዝም አልወደመ… ተፈጥሮ በቁጥጥር ሥር አልዋለች! አሀ… ለጨርቁም ይታዘንለታ! እኛ ይኸው… የአሜሪካን ገበያ ሰብረን እንገባለን እያልን… ጨርቁን ሁሉ ‘ላንለብሰው’ ሰቅለን ጨረስነው!
 እናላችሁ…. ጨርቅና ቀለም የሚጨርስ የመፈክር ጋጋታ “ሲበቃ በቃ ነው፣” ካላልን… ነገርዬው ሁሉ…. አለ አይደል… “ሆድ ሲያውቅ፣ ዶሮ ማታ፣” ይሆናል፡፡ የምር መፈክርን “ሲበቃ በቃ ነው፣” የተባለ እለት… ብቻዬንም ቢሆን ‘የተለመደው ቦታ’ ሰልፍ እወጣለሁ - መፈክር ይዤ! ቂ…ቂ…
እንደውም… ሀሳብ አለን፡፡ በዘንድሮ የዚህ አገር ፖለቲካ ‘ማን ምን እንደሚፈልግ’ ግራ ስለገባን… ሁሉ ነገር ‘አንገታችን ላይ የደረሰ ዜጎችን’ የሚወክል “ሲበቃ በቃ ነው፣” የሚባል ፓርቲ ይቋቋምልን፡፡ [እኔ የምለው… መቼም ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ.. ‘ምልመላ’ ቀረ እንዴ! አሀ… አሁን ትንሽ “እፎይ” እንደማለት ብለናላ! አንድ ሰሞን’ኮ ቢራ እንኳን ስንጎነጭ… “ይሄን ቢራ’ኮ ውስኪ ማድረግ ይቻላል…” ዓይነት ‘ምልመላ፣’ መከራችንን አብልቶን ነበር፡፡ እና… ‘እንዲመዘገብልን’ የምንፈልገው… እኛ ‘ሲመለመል’ ደስ የሚለን ሰው ሳይሆን… የባህር ዛፍ ቅጠል ነው፡፡ ቂ….ቂ…!
እኔ የምለው… እግረ መንገዴን ሳልነግራችሁ ብቀር ያቃዠኛል ብዬ ነው፡፡ የቮልስን ነገር ሰማችሁልኝ! ቮልስ ሆዬ የቸርችል ጎዳናን ዳገት “እኔስ ከእግረኛ ምን ተለየሁ፣” እያለች እያቃሰተች ትወጣለች፡፡ ሊሞዚን ሆዬ ደግሞ በሆዷ፤ “ጠቁሞ እዚህ አገር ያመጣኝ የእጁን አይጣ…” እያለች ቮልስን አልፋት ሽው ማለት፡፡ እናላችሁ… የ’አበሻ ልብ አውቃ’ የሆነችው ቮልስ ምን አለች መሰላችሁ… “ሊሞ፣ ተይ እንዲህ አያድርግሽ.. መልክ እኮ አላፊ ጠፊ ነው” አለችላችኋ! አሀ…’ከማን ዋለችና!
እናችሁ… ዘንድሮ መዓት ነገር የተበላሸው… አለ አይደል…”ሲበቃ በቃ ነው” የሚል እየጠፋ ነው፡፡ “ከእንግዲህማ እንዲህ መቀጠል አትችልም!” የሚል ነገር በተደጋጋሚ መስማት እየናፈቀን ነው፡፡ ነገርዬው ሁሉ፣ “አንድ እርምጃ ወደፊት፣ ስድስት ወደ ኋላ…” የሆነው፣ መዓት ነገር ከዓመት ዓመት ያው ‘ውሃ ቢወቅጡት ቦጭ’ የሆነው… እንትና ያበላሸውን፣ እንትና ‘የሚያብሰው’.. “ሲበቃ በቃ ነው፣” የሚል ጠፍቶ ነው፡፡
‘ሲበቃ በቃ ነው’ ለጽሁፍም ይሰራል፡፡
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Saturday, 25 November 2023 20:04

በቡና ፍቅር የወደቀው ራስታ

ብሬዳ ኒል ከኪንግ ሻይሎህ ሳውንድ ሲስተም

ብሬዳ ኒል ይባላል፡፡ በትውልዱ እንግሊዛዊ ቢሆንም ቋሚ መኖርያው ግን በሆላንድ አምስተርዳም ነው፡፡  የሳውንድ ሲስተም ኦፕሬተር፤ የሬጌ ሙዚቃ ባለሙያና ዲጄ ሆኖ በመስራት ከ35 ዓመታት በላይ አስቆጥሯል፡፡ ከሬድ ላየንና ማጀስቲክ ቢ ጋር በመሆን የኪንግ ሻይሎህ ሳውንድ ሲስተምን King Shiloh Sound system መስርቷል፡፡ ሳውንድ ሲስተሙ በአውሮፓ፤ በሰሜን አሜሪካ፤ በደቡብ አሜሪካና በሌሎች የዓለም ክፍሎች በሚካሄዱ የሙዚቃ ዝግጅቶችና የሬጌ  ፌስቲቫሎች ቋሚ ተሳታፊነት ይታወቃል፡፡ብሬዳ ኒል ሰሞኑን ወደ ኢትዮጵያ  የመጣው ለሰባተኛ ጊዜ ነው፡፡ ከታዋቂ የሬጌ ሙዚቀኞች መካከል በተደጋጋሚ በመምጣት የልዩ ክብረወሰን ባለቤት ያደርገዋል፡፡ለሙዚቃ ስራና ለጉብኝት ከሰባት ጊዜ በላይ ወደ ኢትዮጵያ በመምጣቱ ነው፡፡    ራስተፈርያኖችና የሬጌ ሙዚቀኞች ወደ አፍሪካ ወደ ኢትዮጵያ ስለመምጣት በብዛት እንደሚዘፍኑ ይታወቃል፡፡ ግን ለብዙዎቹ አይሆንላቸውም፡፡ ታዋቂው የሬጌ  ድምፃዊ ሉችያኖ ወደ ኢትዮጵያ ከ5 ጊዜ በላይ በመምጣት ይታወቅ ነበር፡፡   
ብሬዳ ኒልና የኪንግ ሻይሎህ ሳውንድ ሲስተም ቡድን ዘንድሮ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ ትልቅ ራእይ ሰንቀው ነው፡፡  ኢትዮጵያን በሳውንድ ሲስተም ዝግጅቶችና የሬጌ  ፌስቲቫሎች የቱሪዝም መስህብና መናሐርያ በምትሆንበት አቅጣጫ ላይ ለመስራት ነው፡፡ ከአገር ውስጥና ከዓለም አቀፍ የሬጌ ድምፃውያን፤ ባለሙያዎችና ባለድርሻ አካላት በመተባበር ተከታታይ የሙዚቃ ዝግጅቶችን በአዲስ አበባ እና በተለያዩ የኢትዮጵያ ከተሞች ተዟዙሮ ለማዘጋጀትም አቅደዋል፡፡
የኪንግ ሻይሎህ ሳውንድ ሲስተም ቡድን ከሆላንድ አምስተርዳም በመነሳት ከሳምንት  በፊት አዲስ አበባ ገብተዋል፡፡ በመጀመርያ 7ኛውን አዲስ ደብ ክለብ የሬጌ ሙዚቃ ዝግጅት ከታዋቂዎቹ የሬጌ ሙዚቀኞች ራስ ጃኒ ፤ ቴዲ ዳን፤ ከአፍሪካ ወንድምና ሌሎች ሙዚቀኞች ጋር በመሆን አካሂደዋል፡፡ በማግስቱ ደግሞ በ23ኛው ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ  ላይ  ሳውንድ ሲስተሙን በመትከል በሙዚቃ ጨዋታቸው አስደናቂ ትኩረት አግኝተዋል፡፡ የሳውንድ ሲስተም ቡድኑ በታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ላይ የተሳተፈው ለ3ኛ ጊዜ ነበር፡፡ ባለፈው ሳምንት 5ኛ ፖሊስ ጣቢያ አካባቢ በሚገኝ አደባባይ ላይ ግዙፉ ሳውንድ ሲስተም ተተክሎ በብሬዳ ኒልና ሌሎች አጋሮቹ የቀረበው ጨዋታ የጎዳና ላይ ሩጫው ተሳታፊዎችን በከፍተኛ ደረጃ አዝናንቷል፡፡ የታላቁ ሩጫ ተሳትፎ የሳውንድ ሲስተሙን የጎላ ሚና  ያረጋገጠ ሲሆን ኪንግ ሻይሎህ ሳውንድ ሲስተምን ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ማስተዋወቅ የተቻለበት ነው፡፡  በተለይ ብሬዳ ኒል የኢትዮጵያ ቡና የስፖርት ክለብ ማልያ ለብሶ  ሙዚቃዎቹን ማጫወቱ በርካቶችን ያስደሰተ ነበር፡፡ በጎዳና ላይ ሩጫው የተሳተፉ የቡና ደጋፊዎች፤ የእግር ኳስ አድናቂዎች፤ የሬጌ አፍቃሪዎች በሳውንድ ሲስተሙ ዙርያ በነበረው ማራኪ ድባብ እጅግ ተደስተዋል፡፡ከታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ስለነበራቸው  ለስፖርት አድማስ አስተያየት ሲሰጥ ‹‹ በሳውንድ ሲስተም ቡድናችን እኔን ጨምሮ ሁለትና ሶስት አባላት በአትሌቲክስ ውስጥ ያለፉ ናቸው፡፡ በታዳጊነት እድሜዬ  እግር ኳስና ውሃ ዋና ባዘወትርም ፕሮፌሽናል  አትሌት ለመሆን ነበር የሞከርኩት ፡፡ በረጅም ርቀት አትሌቲክስ  ወጣትነቴን ካሳለፍኩ በኋላ ነው ስፖርቱን በመተው ወደ ሙዚቃ የገባሁት፡፡ አትሌት ሆኜ  በማሳለፌ እጅግ ደስተኛ ነኝ፡፡ ፅናትን ተምሬበታለሁ፡፡ ዛሬ በሳውንድ ሲስተም ባለሙያነት ለምሰራቸው ተግባራት ሙሉ የአካል ብቃት ያዳበረኩበት ነው፡፡  አንዳንድ ግዜ በምናዘጋጀው የሳውንድ ሲስተም ሙዚቃ 6፤ 8  እና  10 ሰዓታትን ተወጥረን የምንሰራበት ሁኔታ አለ፡፡ በአጠቃላይ ሳውንድሲስተምን እንደ ማራቶን ውድድር መመልከት ይቻላል፡፡ አትሌቲክስ የአዕምሮና የአካልን ዲስፒሊን የሚጠይቅ ነው፡፡ ሳውንድ ሲስተምም እንደዚያው ነው፡፡ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ላይ በነበረን ተሳትፎ በአትሌቲክስ እና በሳውንድ ሲስተም መካከል ያለውን መተሳሰርና መመሳሰል ያስተዋልኩበት ነው፡፡›› በማለት ተናግሯል፡፡ በ23ኛው ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ላይ የኪንግ ሻይሎህ ሳውንድ ሲስተም መስራት ከፍተኛ ድምቀት መፍጠሩን በስፍራው ተገኝተን ለመታዘብ ችለናል፡፡ ከሳውንድ ሲስተሙ ጋር የነበሩ ባለሙያዎች የጎዳና ላይ ሩጫውን ተሳታፊዎች በሬጌ ሙዚቃ ከማነቃቃታቸውም በላይ ከሩጫው ባሻገር በዳንስ የሚፈለገውን እንቅስቃሴ እንዲሰሩ በማድረግ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ነበረው፡፡
ከታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በኋላ ብሬዳ ኒልና የኪንግ ሻይሎህ ሳውንድ ሲስተም አባላት ለመገናኘት የበቁት ከኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ ጋር ነው፡፡ በሳምንቱ አጋማሽ ላይ  በአበበ ቢቂላ ስታድዬም የተካሄደው የአዲስ አበባ ሲ ካፕ የዋንጫ ጨዋታ ምክንያት ሆኗል፡፡ ብሬዳ ኒል በታላቁ  ሩጫ ላይ የቡናን ማልያ ለብሶ ሙዚቃ ማጫወቱ ብዙዎቹ የክለቡ ደጋፊዎች በማህበራዊ ሚዲያው በተለይ በቲክ ቶክ በአድናቆት ተከታትለውታል፡፡ ስለዚህም ከሲቲ ካፑ የፍፃሜ ጨዋታ በፊት ማለዳ ላይ ከቀንደኛ የቡና ደጋፊዎች ጋር የኪንግ ሻይሎህ ሳውንድ ሲስተም ቡድን አባላት ተገናኝተዋል፡፡ ብሬዳ ኒልን ያረፈበት ሆቴል ድረስ መጥተው አድናቆት የገለፁለትና በክለቡ ደጋፊነት እንዲመዘገብ የጠየቁት አንጋፋው የክለቡ ደጋፊ አዳነ ሽጉጤ እና  ከወቅቱ የክለቡ ደጋፊዎች አስተባባሪ ሆነው  አብርሐም ናቸው፡፡
ብሬዳ ኒል  በወጣትነት ዘመኑ በአትሌቲክስ ፕሮፌሽናል ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ በክለብ ደረጃ ለረጅም ጊዜያት የተወዳደረ ሲሆን እንግሊዝን በኦሎምፒክና በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮን የመወከል ፍላጎት የነበረው ቢሆንም ሩጫውን ብዙም አልገፋበትም፡፡ ከአትሌቲክሱ ባሻገር ለእግር ኳስም ልዩ ፍቅር ነበረው፡፡ በተለይ በታዋቂው የእንግሊዝ ክለብ ሊድ ዩናይትድ ደጋፊነቱ ይታወቅ ነበር፡፡ የሳውንድ ሲስተም ባለሙያ ሆኖ ለመስራት ወደ ሆላንድ አምስተርዳም ገብቶ ከከተመ በኋላ ደግሞ ለአያክስ ክለብ ድጋፉን በመስጠት እግር ኳስን ሲከታተል ቆይቷል፡፡‹‹ ከስፖርት ጋር የተዋወቅኩት ገና በታዳጊነቴ ነው፡፡ ያደግኩት ከእግር ኳስ ጋር ነው፡፡ አባቴ ስፖርት በጣም ይወዳል፡፡ ስለዚህም በሳምንቱ መጨረሻ ላይ ወደ ስታድየም ተያይዘን እንሄዳለን፡፡ የምደግፈው ክለብ ሊድ ዩናይትድን ነው፡፡ በተጨማሪም የበርንሌይና የሌችስተር ሲቲ ክለቦች የሚያደርጓቸውን  ጨዋታዎች በየስታድየማቸው እየተገኘን እንመለከታለን፡፡ እድገቴ በሙሉ ከስታድዬም ጋር የተገናኘ ነው፡፡ የስፖርቱ ባህልና ስሜቱ ዛሬም ውስጤ    አለ፡፡›› ሲል ይናገራል፡፡
ከሰባት ዓመት በፊት ለመጀመርያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ፤ በሬጌ ሙዚቃ ውስጥ የተስፋፋውን የሳውንድ ሲስተም ባህል ለማስተዋወቅ ነበር፡፡ ከዚህ ስራው ባሻገር ለስፖርቱ ባለው ፍቅር ስለ አገሪቱ የእግር ኳስ ክለቦች መጠየቅ ነበረበት፡፡ አብረውት ከሚሰሩ ባለሙያዎች መካከል ሽሜ የሚባለው በተለይ ስለ ኢትዮጵያ ቡና ክለብ አብራራለት፡፡ የህዝብ ክለብ መሆኑና ደጋፊዎቹ በዝማሬያቸው፤ በቀለማቸውና በስታድዬም ውስጥ በሚፈጥሩት ድምቀት የሚስተካከላቸው አለመኖሩን  በደንብ ገለፀለት፡፡ ብሬዳ ኒል ስለ ቡና ክለብ የመጀመርያውን ማብራርያ ከሰማ በኋላ ስታድዬም ገብቶ የክለቡን ጨዋታ መመልከት የፈለገው፡፡ ከኢትዮጵያዊው ሽሜ  የቡናን ጨዋታ ስታድዬም ገብተው ለመመልከት በቁ፡፡ ከዚያ በኋላ ብሬዳ ኒል ከኪንግ ሻይሎህ የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ ደጋፊ ሆኖ ቀረ፡፡ወደ ኢትዮጵያ ቡና የስፖርት ክለብ ስለተሳበበት አጋጣሚ ሲገልፅ  ‹‹እግር ኳስ ያደግኩበት ስፖርት ብቻ አይደለም ፤ በተለያየ የዓለም ክፍል እየተዘዋወርኩ ባህሉን የተማርኩት ነው፡፡  ወደ አዲስ አበባ ስመጣ የአፍሪካን እግር ኳስ  የማወቅና የመረዳተ ፍላጎት ነበረኝ፡፡ ከመላው ዓለም ጋር ለማነፃፀር ነው፡፡ ሽሜ የተባለው ወዳጄ ይህን ፍላጎት ተረድቶ እሽ እንሂድ አለኝ፡፡ የተ ስለው እኔ የምደግፈው ቡድን ቡና ነው በማለት እንባ እየተናነቀው ስለክለቡ ብዙ ነገረኝ፡፡  የቡና ደጋፊዎች መደበኛ የከተማ ነዋሪዎች መሆናቸውን፤ ደሃው የህብረተሰብ ክፍል ለክለቡ ቅርብ መሆኑን፤ ጠንካራ ሰራተኞችና በላባቸው ለፍተው የሚያድሩ ህዝቦች ክለብ መሆኑን በተለያየ መንገድ አስረዳኝ፡፡ በመጨረሻም ስታድየም ገብተን የቡናን ጨዋታ እንድንመለከት ሃሳብ አቀረብኩለት፡፡ ተያይዘን ወደ ስታድዬም ጉዞ ቀጠልን መንገድ ላይ የቡና ደጋፊዎች የክለባቸውን ማልያ ለብሰው በህብረ ዝማሬ ታጅበው ወደ ስታድዬም ሲጓዙ ተመለከትኩ፡፡ ስታድዬም ስገባ የደጋፊዎቹ ማራኪ ዝማሬዎችና እንቅስቃሴዎችን በአይኔ በብረቱ ስመለከት በቡና ክለብ በእጅጉ ተማረኩኝ፡፡ ደጋፊዎቹ ክለባቸውን የሚያበረታቱበት የጠለቀ ስሜት የሚገርም ነው፡፡ እግር ኳስ የህይወት ነፀብራቅ መሆኑን የምትመለከትበት ድንቅ ክለብ ነው፡፡›› በማለት  ለስፖርት አድማስ  አብራርቷል፡፡
ብሬዳ ኒል ለኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ ያለው ፍቅር እየጨመረ የሄደው የክለቡን ማሊያዎች በቡኒና ቢጫ ቀለማት ከገዛ በኋላ ነበር፡፡ በአውሮፓ፤ በሰሜን አሜሪካ፤ በኤሽያና በአፍሪካ በሚሰራቸው ትልልቅ ኮንሰርቶች ላይ ለብሶት ታይቷል፡፡ የሳውንድ ሲስተም ጨዋታውን ሲያቀርብ ከሚለይባቸው አለባበሶች  xንዱ ሆኖለታል፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት በዓለም ዙርያ ባቀረባቸው ኮንሰርቶች የቡናን ማልያ በመልበስ በከፍተኛ ደረጃ ክለቡን ሊያስተዋውቀው በቅቷል፡፡ በተለይ ከ2019 እኤአ ወዲህ በመላው ዓለም በሰራቸው ኮንሰርቶች ነው፡፡ በቡና ማሊያ ዝግጅቶቹን ማቅረቡን የተመለከቱ የሳውንድ ሲስተም ቡድኑ አባላት ማልያውን በመልበስ ስሜቱን መጋራታቸው ክለቡን በመደገፍ እንዲቀጥል መነቃቃት ስለፈጠሩለት እጅግ አስደስቶታል፡፡ በፈረንሳይ ፓሪስ በሚካሄደውና በቀን ውስጥ ከ45ሺ በላይ ተሳታፊ በሚያገኘው ደብ ካምፕ  የሳውንድ ሲስተም ፌስቲቫል ላይ የቡናን ማልያ ለብሶ ነበር፡፡ በሳምንት ውስጥ ከ250ሺ በላይ ጎብኝዎችና ታዳሚዎችን በሚያሳትፈው የስፔኑ ሮተተቶም ሰንስፕላሽ የሬጌ ፌስቲቫል ላይም የቡና ማሊያውን ለብሶ ለመጫወት በቅቷል፡፡ ዘንድሮ ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣቱ በሰሜን አሜሪካ በነበረው ቆይታም ጋር በተያያዘ የቡናን ማሊያ ታጥቆ ነበር፡፡ በሜክሲኮ ከተማ በሚካሄድ የሬጌ ፌስቲቫል ላይ የሰራው የሚወደውን ክለብ ቡኒ ማልያ በመልበስ ሲሆን ከወር በፊት ሎስአንጀለስ ውስጥ በግዙፍ ክለብ ባቀረበው ዝግጅትም የሰራው በተመሳሳይ አለባበስ ነበር፡፡ በሎስ አንጀለስ ዝግጅት ላይ ሁለት ኢትዮጲያውያን ታዳሚ እንደነበሩ ለስፖርት አድማስ ያስታወሰው ብሬዳ ኒል የቡና ክለብ ደጋፊዎች እንደሆኑና የክለባቸውን ማልያ ለብሶ መጫወቱ እንዳኮራቸው ገልፀውልኛል ብሏል፡፡
ብሬዳ ኒል በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በአበበ ቢቂላ ስታድዬም የተካሄደውን የቡና እና የሃድያ ሆሳዕና የሲቲ ካፕ ጨዋታ ከመመልከቱ በፊት  ከአንጋፋው የቡና ክለብ ደጋፊ አዳነ ሽጉጤ እና ከደጋፊዎች አስተባባሪው አብርሃም ጋር በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ውይይት አድርገዋል፡፡ የቡና ደጋፊዎች አውሮፓዊው ክለባቸውን በዓለም ዙርያ ስላስተዋወቀላቸው አመስግነውታል፡፡ እሱም ለክለቡ ያለው ፍቅር የገለፀላቸው ሲሆን ወደ ኢትዮጵያ በመጣ ቁጥር የሚያስደስተው የቡናን ጨዋታ ስታድዬም ገብቶ መመልከት መሆኑንም ነግሯቸዋል፡፡ ከዚህ ቆይታው በኋላ ብሬዳ ኒል አራት ኪሎ አምባሳደር የሚገኘውን የክለቡን የስፖርት ትጥቆች መሸጫ መደብር ጎብኝቶም ነበር፡፡ በስፖርት ትጥቅ መሸጫው መደብር የክለቡን የተለያዩ የስፖርት ትጥቆችና ምርቶች በመጎብኘት ከመደሰቱም በላይ ከሳውንድ ሲስተም አጋር ባለሙያዎች ጋር በርካታ የማስታወሻ ማልያዎች፤ የስፖርት ትጥቆችና ቁሶችን ለመሸመት በቅተዋል፡፡
 ብሬዳ ኒል፤ ማጀስቲክ ቢ እና  አይታል ዩዝ ከኪንግ ሻይሎህ ሳውንድ ሲስተም ዛሬ ቅዳሜ ላይ የመጀመርያውን አርባምንጭ ሬጌ ፌስቲቫል ያቀርባሉ፡፡ ከአዲስ አበባ ከተማ ወጣ ብሎ  በተዘጋጀ ፌስቲቫል ላይ ዲጄ ሀርቲካል ከኬንያ፤ ራስ ጃኒ፤ ቴዲ ዳንና ራስ ኪውንተሰብ ከኢትዮጵያ ተሳታፊ ይሆናሉ፡፡
የኪንግ ሻይሎህ ሳውንድ ሲስተም አባላት ወደ አውሮፓ ሲመለሱ የኢትዮጵያ ቡና ክለብ ኦፊሴላዊ ደጋፊ የሚሆኑበትን እቅድ ይዘው ነው፡፡ የሳውንድ ሲስተሙን ሌሎች አባላት ወደ ክለቡ ድጋፍ ለማምጣት ቃል ገብተዋል፡፡ በቀጣይ በመላው ዓለም በሚያቀርቧቸው የሙዚቃ ዝግጅቶች የክለባቸውን ማልያዎችን እየለበሱ ማስተዋወቅ እንደሚቀጥሉም ተናግረዋል፡፡ ብሬዳ ኒል ለስፖርት አድማስ እንደገለፀው ወደፊት ከቡና ክለብ አስተዳደር እና ከደጋፊዎች ጋር በመተባበር የሳውንድ ሲስተም ዝግጅቱን ክለቡን በሚጠቅም ፕሮጀክት ለማቅረብ ይፈልጋል፡፡ በተለይ  ኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኝ ስታድዬም የሳውንድ ሲስተም  ጨዋታውን ለማቅረብ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳለው የገለፀ ሲሆን የቡና ክለብ ስታድዬም ለመገንባት በሚያደርጋቸወ እንቅቃሴዎች የበኩሉን ድጋፍ ለመስጠት፤ ክለቡን ለማጠናከር በሚዘጋጀው የጎዳና ላይ ሩጫ ልዩ ተሳትፎ ማድረግ እንደሚፈልግም ተናግሯል፡፡