Administrator

Administrator

በቁጥር አንድ መፅሐፉ የህወሐትን የትጥቅ ትግል ታጋዮችን ታሪክ በትግርኛ ያሳተመው ጋዜጠኛና ደራሲ ኃይላይ ሃድጉ፤ “ጽንአት ቁጥር 2” መፅሐፉን ከትናንት ወዲያ ከሰአት በኋላ በአዲስ አበባ ሂልተን አስመረቀ፡፡ በትግል ስሙ “ቃል (አል) አሚን” ተብሎ በሚጠራው ታጋይ የኋላእሸት ገብረመድህን ላይ ያተኮረውና በፎቶግራፎች የተደገፈው ባለ 320 ገፅ መፅሐፍ ሲመረቅ የህወሓት ነባር ታጋይ አቶ አባይ ፀሐዬ በክብር እንግድነት ተገኝተዋል፡፡ መፅሐፉን አንብበው አስተያየት ከሰጡት መካከል፤ የኢሠፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ ፖሊት ቢሮ ተለዋጭ አባል እና የቀድሞ መንግሥት ከፍተኛ ባለስልጣን አቶ ፋሲካ ሲደልል እንዲሁም የኢህአፓ እና የኢዲዩ አባላት ይገኙበታል፡፡ መፅሐፉ በ70 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

“በህዝብ ጥያቄ የተደገመ…” የሚሉት ነገር ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ ማንበብ፡፡ ሁልጊዜ ግርም የሚለው ነገር ምን መሰላችሁ… እኛ በቅርበትም በርቀትም የምናውቃቸው ሰዎች አንዳቸውም “ጥያቄ አቅራቢዎች ውስጥ አለሁበት…” ሲሉ አለመስማታችን፡፡ እኔ ይሄኔ…በቃ…“የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ እየተነበበ ነው” እንላለን፡፡ (ጥያቄ አለን…“አህዛብ እንጂ ህዝብ አይደላችሁም” ካልተባልን በስተቀር እንዴት ነው “እንዲደገም…” የሚጠይቁት ውስጥ የማንገባሳ! ቂ…ቂ…ቂ…)

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

ሰውየው… የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አስተማሪ ነው፡፡ እናላችሁ… ተማሪዎቹን ስለ ውሸት ሊያስተምራቸው ይፈልጋል፡፡ ትምህርቱን ለመጀመርም እንዲያነቡ የሰጣቸውን መጽሐፍ ከፍ ያደርግና “እዚህ መጽሐፍ ላይ ሀያ አምስተኛውን ምዕራፍ ያነበባችሁ ስንት ናችሁ?” ሲል ይጠይቃቸዋል፡፡ ክፍሉ ውስጥ ያሉ ሁሉ እጃቸውን ያነሳሉ፡፡
አስተማሪውም ምን ቢላቸው ጥሩ ነው…“ሥራዬ ከባድ ይሆናል ማለት ነው፡ መጽሐፉ ውስጥ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ የለም፡፡”
እናላችሁ…እንዲሀ አይነት የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ነው፡፡ ሰዎች ብቻ ሳንሆን ‘የሰማይ ስባሪ’ የሚያካክሉ ተቋማት፣ ‘የሰማይ ስባሪ’ የሚያካክሉ ‘ፐርሰናሊቲስ’…ምን አለፋችሁ…ከዳር ዳር የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አነበብኩ…” ማለት በጋራ የተሰጠን ባህሪይ እየመሰለብን ነው፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ፣ “ለምንድነው ህብረተሰባችን ውስጥ እንዲህ መተማመን የጠፋው?” ብላችሁ ጠይቃችሁ አታውቁም፡፡ እንደዚህ አይነት ህብረተሰብን ከስረ መሰረቱ ሊነቅሉ የሚችሉ ነገሮችን ጥናት አካሂዶ መፍትሄ የሚጠቁመን ይጥፋ! የምር አስቸጋሪ ነገር ነው፡፡ ያለመተማመን የግለሰቦች፣ የቡድኖች ምናምን ጉዳይ ብቻ መሆኑ ቀርቶ ወደ አገር ደረጃ ከፍ ሲል አሪፍ አይደለም፡፡ በብዙ ነገር “በእነሱ ቤት እኮ እኛን ማታለላቸው ነው!” እየተባባልን ነው፡፡
እንዲህ የሆንነው ለምን መሰላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ስለሄድን፡፡
ለምሳሌ መግለጫዎች ምናምን ስንሰማ ወይም ስናነብ “እሱን እንኳን ተዉት፣ ምን ያላልንበት ዳገት የለም አለች እንስሳዋ…” ምናምን ማለት ከጀመርን ውለን አደርን፡፡ አሀ..ልክ ነዋ…ብዙ ነገሮች ከቃላተ ጋጋታና ከ‘ዘመኑ አማርኛ’ ባለፈ ከመግለጫው አዳራሽ እንደተዋጣ ሁሉም ነገር ‘የሀላፊ ጊዜ ግስ’ ሆኖ ይቀራላ!
በተበለጨለጨ አዳራሽ ‘የተብለጨለጩ መገለጫዎች’ ሲሰጡን ለማመን እየተቸገርን ያለነው የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ነው፡፡
(በዚህ መሀል የሚያሳዝነው ምን መሰላችሁ… ‘እውነት ሊሆኑ የሚችሉ’ ነገሮች ሜዳ ላይ እየቀሩ መሆናቸው፡፡)
ለምሳሌ…ይሄ “በህዝብ ጥያቄ የተደገመ…” የሚሉት ነገር ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ ማንበብ፡፡ ሁልጊዜ ግርም የሚለው ነገር ምን መሰላችሁ… እኛ በቅርበትም በርቀትም የምናውቃቸው ሰዎች አንዳቸውም “ጥያቄ አቅራቢዎች ውስጥ አለሁበት…” ሲሉ አለመስማታችን፡፡ እኔ ይሄኔ…በቃ…“የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ እየተነበበ ነው” እንላለን፡፡ (ጥያቄ አለን…“አህዛብ እንጂ ህዝብ አይደላችሁም” ካልተባልን በስተቀር እንዴት ነው “እንዲደገም…” የሚጠይቁት ውስጥ የማንገባሳ! ቂ…ቂ…ቂ…)
እናላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ነው፡፡
አንዳንዴ ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…ይሄ “በህዝብ ጥያቄ የተደገመ…” ዝም ብሎ ምክንያት መፍጠሪያ አይነት ነገር ይመስለኛል፡፡ “ይህ ፕሮግራም ጠቃሚ ነገሮች ስላሉበት ያዩት እንዲደግሙት፣ ያላዩት እንዲያዩት ተደግሟል…” ማለት ይቻላል፡፡ ለዚህ እኮ ‘ዋር ኤንድ ፒስ’ ‘ክራይም ኤንድ ፐኒሽመንት’ ምናምን መዘርዘር አያስፈልግም፡፡
እናላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ነው፡፡
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል… እዚህ አገር አዲስ አሠራር ሁሉ ሳይሳካ በሌላ አዲስ አሠራር ለምን የሚተካ ይመስለኛል መሰላችሁ…ገና የወጡ ‘ናሙና’ ሳይቀመስ እምቢልታና መለከቱ ስለሚበዛ!
ለምሳሌ አንዳንድ ሰው በአጭር ጊዜ መልኩ ምናምን ተለዋውጦ ስናየው “የእግዚአብሔር ሥራ ነው…” ምናምን ቢለን ምንም አናምነውም፡፡ እዚህ አገር አፍንጫ፣ ‘ብሬስት ምናምን’ አይነት ‘ፕላስቲክ ሰርጀሪ’ ተለምዷላ!
መልክን የመለወጥ ነገርን ካነሳን አይቀር…ይቺን የሆነ ቦታ ያነበብኳትን ነገር ስሙኝማ…የሆነች መካከለኛ ዕድሜ ላይ የደረሰች ሰው የልብ ድካም ይገጥማትና ሆስፒታል ትሄዳለች፡፡ እናላችሁ… እየታከመች ሳለች በመንፈሷ እግዚአብሔር ይታያታል፡፡ ይሄኔ እያስተዛዘነች “አምላኬ፣ በቃ አለቀልኝ ማለት ነው?” ትለዋለች፡፡ እሱም፣ “አይ ያንቺ ጊዜ ገና ነው፡ ምድር ላይ ገና 43 ዓመት፣ ከ2 ወር ከ8 ቀን ይቀርሻል” ይላታል፡፡ሲሻላትም ራሷን ለመለወጥ ‘ፕላስቲክ ሰርጀሪ’ ለማድረግ ሀኪም ቤት ትሄዳለች፡፡ አፍንጫዋ ሰልካካ ተደረገ፣ ሾል ያለ አገጯ ተስተካከለ፣ ‘ብሬስቶቿ’ ሞላ እንዲሉ ተደረጉ፣ የጸጉሯ ቀለም ተለወጠ…ብቻ ሙሉ ለሙሉ ሌላ ሰው ሆነች፡፡ ህክምናው አልቆ ልክ ከሆስፒታሉ ስትወጣ ግን መኪና ይገጫትና ትሞታለች፡፡
ከዛም እግዜሐር ፊት ስትቀርብ ምን ትላለች…“ገና አርባ ሦስት ዓመት አለሽ አላልከኝም ነበር እንዴ! ለምንድነው ከመኪናው ፊት ስበህ ያላወጣኸኝ?” ትለዋለች፡፡ እግዜሐር ምን ብሎ ቢመልስላት ጥሩ ነው… “ሙሉ ለሙሉ ተለውጠሻል፣ አንቺ መሆንሽን አላወቅሁማ!” አላት፡፡
እናማ… ይሄ ሙሉ ለሙሉ ለመለወጥ የሚደረገው ጥረት አበሳም አለው ለማለት ነው፡፡ ነገራችን ሁሉ ድንብርብሩ እየወጣ እንደገና የውሸት አፍንጫና አገጭ እየበዛ ሲሄድ “የእግዚአብሔር ሥራ…” የሆነውን ሁሉ እየተጠራጠርን ነው፡፡እናላችሁ…የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ያለመተማመን የባህሪያችን ዋና መገለጫ እየሆነ ነው፡፡
እኔ የምለው…መቼም የዘንድሮ ነገራችን ቢወራ፣ ቢወራ ፈቀቅ የማይል ሆኗል፡፡ በብዙ ነገሮች በአለባባስ በሉት፣ ከሰዎች ጋር ሰላምታ በመለዋወጥ በሉት፣ በምግብ ‘አመራራጥ’ በሉት…እዚቹ እኛዋ ሀበሻ አገር ሆኖ የፈረንጅነት የክብር ዜግነት አለኝ ሊል ምንም የማይቀረው የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የሚል መአት አለላችሁ፡፡
ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…የዜግነት ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ስሙኝማ፡፡ ሩሲያዊው፣ ፈረንሣዊውና እንግሊዛዊው አዳም የምን አገር ዜጋ እንደሆነ ይከራከሩ ነበር፡፡ፈረንሣዊው፣ “ያለምንም ጥርጥር አዳም ፈረንሣዊ ነው፡፡ ከኢቭ ጋር እንዴት በስሜት ፍቅር እንደሚሠራ አታዩትም!” አለ፡፡እንግሊዛዊው ደግሞ፣ “የነበረቻቸውን ብቸኛ አፕል ለሴቷ ሰጣት፡ በእርግጥም እንግሊዛዊ እንጂ የሌላ አገር ዜጋ ሊሆን አይችልም፣” ይላል፡፡
ሩስያዊው ይህን ሁሉ ከሰማ በኋላ ምን ቢል ጥሩ ነው…“አዳም የሌላ አገር ዜጋ ሳይሆን ሩስያዊ ብቻ ነው ሊሆን የሚችለው፡፡ ከአንዲት አፕል ሌላ ምንም ሳይኖራቸውና ራቁቱን ወዲህ ወዲያ እያለ ብርድ እየቀፈቀፈው መንግሥተ ሰማያት ነኝ ብሎ የሚያስብ ሩስያዊ ብቻ ነው፡፡” አሪፍ አይደለች!
“አንድ ቁራሽ ዳቦ እንክት ያደርግና
አንድ ጣሳ ውሀ ግጥም ያደርግና
ተመስገን ይለዋል ኑሮ ተባለና…” የምንለው አይነት የእኛ አገር ጉድ እንደ ማለት ነው፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…የሩስያን ነገር ካነሳን ይቺን የተስማማችኝን ቀልድ ስሙኝማ…ስታሊን ይሞትና ገሀነም ይወርዳል፡፡ እሱ እዛ በወረደ በጥቂት ቀናት ውስጥ አንድ ሌሊት መንግሥተ ሰማያት በር ላይ ቅልጥ ያለ ጩኸት ይሰማል፡፡ ለሽ ያለ እንቅልፍ ላይ የነበሩት መላዕክት ተደናግጠው ይነቃሉ፡፡ ቅዱስ ዼጥሮስ በሩን ሲከፍት ደጅ የሰይጣን መአት ሜዳውን ጥምቀተ ባህር አስመስሎታል፡፡ “ምን ሆናችሁ! ደግሞ እዚሀ ምን ልትሠሩ መጣችሁ?” ይላቸዋል፡ እነሱም “እኛን ከገሀነም እንደመጣን የመጀመሪያዎቹ ስደተኞች ቁጠረን፣ የፖለቲካ ጥገኝነት ይሰጠን፣” ይሉታል፡፡ እሱም ምክንያታቸውን ሲጠይቃቸው ምን ቢሉት ጥሩ ነው… “ስታሊን የሚባል ሰው መጥቶ ገሀነምን በአንድ እግሯ አቁሟታል፣ የእሱን ጭቆና መቋቋም ስላልቻልን በመንግሥተ ሰማያት ጥግኝነት ይሰጠን” አሉ ይባላል፡፡እናላችሁ…የግብረ ገብ ጉዳይ ያገባናል ማለት የሚገባቸው አንዳንድ ተቋማት… እንኳን እኛን ወደ ትክክለኛ አቅጣጫ መመለስ ቀርቶ…አለ አይደል… ለራሳቸውም ‘ራዳሩ ሲጠፋባቸው/ሲያገኙ፣ ሲጠፋባቸው/ሲያገኙ’…አንዳንዴ ራሳቸው አቅጣጫ የሚያሳይ ያጡ ይመስላል፡፡ ረናማ…አሌ የሚለን እየጠፋ የሌለ ሀያ አምስተኛ ምዕራፍ “አንብቤያለሁ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ነው፡፡
መልካሙን ያምጣልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

“እግዚአብሔር የፈቀደውን
ነው የምንሰራው”ብፁዕ አቡነ ማትያስ

“ከኔ ይበልጥ ወንድሞቼ
እንዲመረጡልኝ ነው የምመኘው”
(ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ፤ የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ)

“ፓትርያሪክም ብሆን ሊቀጳጳስ እርቁ ይቀጥላል
(ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ፤ የሰሜን ጐንደር ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ)
ለስድስተኛ ፓትርያርክነት እጩ መሆንዎን የሰሙት ከማን ነው?
ሰው ዝም ብሎ ያወራል፡፡ እገሌ ይሆናል ይባላል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት እጩ ነህና እንድትመጣ አሉኝ፡፡ አሁን ባለፈው የካቲት 13 ነው አዲስ አበባ የገባሁት፡፡ እኔ ምንም የማውቀው ነገር የለም፤ ከኢየሩሳሌም ተነስቼ ስገባ የፓትርያሪክ ምርጫ ሕግ ተረቋል ተባለ፡፡ ያ ሕግ ታህሳስ 30 ለሲኖዶስ ይቀርባልና በሲኖዶስ አባልነትህ ና ተባልኩ፤ ሥራ ይበዛ ስለነበር አልተመቸኝም፡፡ ጥር 6 ቀንም ለሌላ ስብሰባ ና ተብዬ አልቻልኩም፡፡
ቀደም ሲል የአሜሪካ ዜግነት እንደነበርዎ ሰምቻለሁ…አሁንስ?
በፈረንጅ አቆጣጠር ከ1994-1995 ዓም ችግር ስለነበረብኝ የአሜሪካ ፓስፖርት ይዤ ነበር፡፡ አሁን ግን ተለውጧል፡፡ ይኼ ከአሁኑ ምርጫ ጋር አይያያዝም፡፡ ለምርጫው ብዬ ፓስፖርት አልቀየርኩም፡፡ በመሰረቱ የኢየሩሳሌም ሊቀጳጳስ ሆኜ ከተመደብኩ በኋላ ሃሳቤ ወደ ኢትዮጵያዊነቱ ለመለወጥ ነበረ ተጓቶ ነው እንጂ፡፡ እንደዚህ አይነት እጬ እሆናለሁ ብዬ አላሰብኩም፡፡
ግን እንዴት የአሜሪካ ዜግነት ወሰዱ?
አይ እሱማ ---- የኢየሩሳሌም ሊቀጳጳስ በነበርኩበት ጊዜ የደርግ ወታደራዊ መንግሥት ተፅእኖ ነበረብኝ፡፡ መንግስት ደህንነቶች ከተሳላሚዎች ጋር እየላከ ብዙ ችግር አስከትሎብኛል፡፡ በዚያ ምክንያት ወደአሜሪካ ተሰደድኩ፡፡ እዚያ የነበሩትን ምዕመናንም ሳገለግል ቆየሁ፡፡ በኋላ ሲኖዶሱ ጠርቶ የአሜሪካ ሊቀጳጳስነቱን አፀደቀልኝ፡፡
በወቅቱ ፓትርያሪክ ተወግዘው ነበር-----
መወገዙማ የመጣው እኔ ደርግን ስላወገዝኩ ነበር፡፡ ደርግን ሳወግዝ የነበሩት ሰዎች እንዴት መንግሥትን ያወግዛል ብለው ፓትርያሪኩን አሳሳቱና አውግዘውኝ ነበረ፡፡
በኋላ ስመጣ በስህተት ነው ተብሎ አነሱት፡፡ የተወገዝኩት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለኃይማኖት ጊዜ ነው፡፡ የተነሳው ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሪዎስም ለቀው አቡነ ያዕቆብ አቃቤ መንበር በነበሩ ጊዜ ነው፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከመሾማቸው ጥቂት ጊዜ በፊት ነው ይሄ፡፡
ከአቡነ ጳውሎስ ጋርም ለፓትርያሪክነት ተወዳድረው ነበር ይባላል…
እኔ አወዳድሩኝ ብዬ አላውቅም፤ አሁንም ድሮም፡፡ ብቻ ከየክልሉ ሁለት ሁለት ተወዳዳሪዎች ሲባል ከአቡነ ጳውሎስ ጋር እኔ ሳላውቅ ተወዳድሬ እሳቸው ከአምስቶቹ እጩ ፓትርያሪኮች አንዱ ሆኑ፤እኔ ቀረሁ፡፡
ጠርተውኝ የመጣሁት ግን የመርቆሪዎስ ምክትል በነበሩት በብፁዕ አቡነ ዜና ማርቆስ ጊዜ ነበር፡፡ መወገዜን እኔም አላውቅም ነበር፡፡ ምን ሆኜ? ስል እንዲህ ተላልፎብህ ተባልኩኝ፡፡
ብፁዕነትዎ ሲወገዙ ሌላ አቡነ ማትያስ መሾማቸው ትክክል ነበር?
በቤተክርስትያን ባህላችን ሁለት ጳጳሳት በአንድ ስም አይጠሩም፡፡ ግን ያን ጊዜ ተደረገ፡፡ በአቡነ ተክለኃይማኖት ላይ ግፊት አድርገው ነው፡፡ ሆነ ብለው የእኔን ስም ለመውሰድ ያደረጉት ነው፡፡ ስመለስ ግን ፀፀት ውስጥ ገቡ፡፡
ብፁዕነትዎ ፓትርያሪክ ቢሆኑ እርቀ ሰላሙ በምን መልክ ይቀጥላል?
እርቀሰላሙ እንደሚቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ተናግሯል በዚያው መሰረት ይቀጥላል፡፡ ከሲኖዶስ የተለየ ሃሳብ ሊኖረኝ አይችልም፡፡
በፓትርያሪክነት ቢሾሙ በኢየሩሳሌም የቤተክርስትያኒቱን ይዞታ ለማስመለስ ምን ለመስራት አቅደዋል?
ፓትርያሪክ የመሆን ጉዳይ ሳይሆን እኔም ሆንኩ ሌሎቹ እንዲገፉበት ቅዱስ ሲኖዶሱን እገፋፋለሁ ከሆንኩ አለሁ ማለት ነው፡፡ ካልሆንኩ ደግሞ ቅዱስ ሲኖዶሱ ሥራዬ ብሎ ከግብፅ ኦርቶዶክስ ጋር ተነጋግሮ አንድ መፍትሄ እንዲገኝ ጥረት ይደረጋል፡፡ ወደ ሌላ ሀገረ ስብከት ብቀየርም ይሄ ይቀጥላል፡፡
ፓትርያርክ ቢሆኑ ከአምስተኛ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ምን የተለየ ነገር ይሰራሉ?
መቼም እግዚአብሔር የፈቀደውን ነው የምንሰራው፡፡ ቤተክርስትያኒቱ ትክክለኛውንና ቀጥተኛውን መንገድ አንድትይዝ፣ በውስጧ ያለው ሁሉ መንፈሳዊነትን የተጐናፀፈ እውነተኛነትን የተከተለ መሆን አለበት ባይ ነኝ፡፡ በተቻለ መጠን ይህንን ወደ እውነተኛው መንገድ ለመመለስ ነው ተስፋ የማደርገው፡፡
ከአቡነ ጳውሎስ ስራዎች በጣም የሚያደንቁት ምንድነው?
ቅዱስነታቸው ዓለም አቀፍ ሰው ነበሩ፡፡ በዚህም ቤተክርስትያኒቱን አስተዋውቀዋል፡፡ በመንበረ ፓትርያርክ ግቢ ለጳጳሳት ማረፊያ አሰርተዋል፡፡
ቤት አልነበረም፡፡ መሰብሰቢያ አዳራሽ አልነበረም፣ ቤተመፃህፍት አልነበረም፡፡ እነዚህ ሁለቱን አደንቅላቸዋለሁ፡፡
መሻሻል ይገባቸዋል በሚሏቸው ጉዳዮች ላይ ለአቡነ ጳውሎስ አስተያየት አቅርበው ያውቃሉ?
አንዳንድ ስህተቶች ሳይ እነግራቸው ነበር፡፡ ለምሳሌ በስብከተ ወንጌል፣ በኃይማኖት አጠባበቅ በኩል የኃይማኖቱን ሥርዓት ያልጠበቁ ሰባኪዎች… በዘፈቀደ ሲሆን እናገራለሁ፡፡
ይቀበሉዎት ነበር?
ይቀበሉኛል ግን ነገሩ ከባድ ይሆንና የተባለው መቶ በመቶ ላይሰራ ይችላል፡፡ መቻቻል ጥሩ ነገር ይመስለኛል መቻቻል ከሌለ ሁከት ነው ያለው፣ የሕዝቡንና የሀገር አንድነት ለማስጠበቅ ተቻችሎ መስራት ያስፈልጋል፡ሌላ ምርጫ የለም፡፡ አንዱ ሌላውን ሳይቀማ መኖር መቻል አለበት፡፡


===============
በፓትርያርክነት ቢመረጡ ምን ለመሥራት አቅደዋል?
እግዚአብሔር አምላክ ለዚያ ካደረሰኝ ከዚያ በኋላ ነው የምናገረው፡፡
ነገር ግን እኔ የምመኘው ከአራቶቹ እጩዎች መካከል ለሀገር ለወገን ለቤተክርስትያን የሚያስብ አባት እግዚአብሔር እንዲሰጠን ነው፡፡ ለዚህም እግዚአብሔርን በፀሎት እጠይቃለሁ፡፡ ቅድሚያ ከኔ ይበልጥ ወንድሞቼ እንዲመረጡልኝ ነው የምመኘው፡፡ ነገር ግን ይሄን ጥቆማ ላደረጉት ወገኖቼ በእግዚአብሔር ስም ምስጋናዬን አቀርባለሁ፡፡
ለእጩነት በመጠቆምዎ ምን ተሰማዎት? እንደሚመረጡ ጠብቀው ነበር?
እዚህ ደረጃ እደርሳለሁ፣ ጨርሶ እጠቆማለሁ የሚል ሀሳብ አልነበረኝም፡፡
በመጠቆሜም ደስተኛ አይደለሁም፡፡ ለምን ትለኝ እንደሆነ ከባድ ኃላፊነት ነው፡፡ ከአርባ ሚሊዮን በላይ የሆነውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ተዋህዶ ሕዝብ ማገልገል ከባድ ነው፡፡ እግዚአብሔር ከወደደ ደግሞ ይኼን ሕዝብ ለማገልገል አንተ እንደፈቀድክ ይሁን ብዬ ነው የተውኩት፡፡
ብዙ ቋንቋዎች እንደሚናገሩ ሰምቻለሁ----- ምን ያህል ይችላሉ?
አፌን የፈታሁት በኦሮምኛ ነው፡፡ አማርኛ፣ ግዕዝ፣ እንግሊዝኛ፣ ጀርመንኛና በመጠኑ ጣሊያንኛ እናገራለሁ፡፡ አማርኛን፣ ግእዝንና እንግሊዝኛን በትምህርት ቤት ነው የተማርኩት፡፡ ጀርመንኛን ቅድስት ቤተክርስትያን አሁን በህይወት ከሌሉት ከእነ ብፁዕ አቡነ ይስሀቅ ጋር ወደ ምዕራብ ጀርመን ልካኝ ነው የተማርኩት፡፡
በእነዚህ ቋንቋዎች በመግባባቴ ደስታ ይሰማኛል፡፡ ጣልያንኛውን ደግሞ ስድስት አመት ተኩል እዚያ በመቆየቴ ነው የቻልኩት፡፡ ኦሮምኛ በመናገሬ ደስታ ይሰማኛል፡፡ በኦሮሚያ ክልል ኦሮሚኛ ተናጋሪ ካህናት ጥቂት ናቸው፡፡
ከብሔረሰቡ ተመርጬ ጳጳስ በመሆኔ ይደንቀኛል፤ የእግዚአብሔር ምርጫ ነው፡፡ ተልእኮውን ያፋጥናል፡፡ ህብረተሰቡ በአስተዳደርም ሆነ በወንጌል ስብከት ይበልጥ በሚረዳው ቋንቋ ማስተማር እንዲሁም ከአካባቢው ህብረተሰብ ጋር ለመግባባት ቋንቋ መቻል ጥሩ ነው፡፡ ኦሮምኛ ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር ከፈቀደ በርካታ ቋንቋዎችን ብችል እወዳለሁ፡፡ በቋንቋ አላመልክም፣ የማመልከው በኢትዮጵያዊነቴ ነው፡፡ በእምነቴ አማራ፣ ኦሮም በሚል አልከፋፍልም፡፡
ፓትርያርክ ቢሆኑ ለእርቀሰላሙ ምን ያህል ዝግጁ ነዎት?
ለእርቀሰላሙ እኔ ሳልሆን ቅዱስ ሲኖዶስ በወሰነው መሰረት መቀጠሉ ያስደስተኛል፡፡ ሊቃነጳጳሳቱ ሳይሆኑ ከጀርባቸው ያሉት ብሶት ያለባቸው ሁሉ ወደ እናት ሀገራችን ገብተው ሰላማዊ ኑሮ ቢኖሩ ደስተኛ ነኝ፡፡ ለእርቀሰላም ደግሞ ቅዱስ ሲኖዶስ በሩን ከፍቷል፡፡ በተከፈተው በር ገብተው ብፁአን ሊቃነ ጳጳሳት ሀገራቸውን እንደእኛ ቢያገለግሉ በጣም ደስተኛ ነኝ፡፡

=======================

ለፓትርያርክነት እጬ ሆነው መጠቆምዎን የሰሙት ከማነው?
ሲወራ ነው የሰማሁት፡፡ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ በፊት ወሬ ይሰማል፤እውነትና ውሸትነቱ አይታወቅም እንጂ፡፡ በሲኖዶስ ጉባዔ በይፋ ተነገረኝ፡፡
የምረጡኝ ዘመቻ መሰል ነገር በሀገረስብከትዎ እንደነበር ሰምቻለሁ…
ኧረ እንዲህ አይነት እንቅስቃሴ መኖሩን አላውቅም፡፡ እንደውም ጐንደር ከአምስቶቻችን እጩዎች ውጪ የሆኑ ሊቀጳጳስ መርጠው ማስተላለፋቸውን ነው የማውቀው፡፡
ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ጋር ለፓትርያሪክነት ተወዳድረው ነበር፡፡ አሁን በእጩነት እንደሚመረጡ ጠብቀው ነበር?
አሁንም ሆነ ያን ጊዜ እጩ መሆኔን ተቃውሜ ነበር፡፡ ለቅዱስ ሲኖዶስም ይህንኑ ተናግሬአለሁ፡፡ የሲኖዶሱ አባላት ዝም ቢሉም አራታችን ተናግረናል፤ ሁላችንም ተናግረናል፡፡ ለማሟያ ነው ሊያሰኝም ይችላል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ሲመረጡ የአስመራጭ ኮሜቴ ሊ/መንበር ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ ብትተውኝ ግን ብዬ ማመልከቴ አልቀረም፡፡
ስድስተኛው ቅዱስ ፓትርያሪክ ቢሆኑ ቅድሚያ የሚሰጧቸው ተግባራት ምንድን ናቸው?
በዚያን ጊዜ ይገልፅልኝ ይሆናል፤አሁን ያሰብኩበት አይደለም፡፡
ለእርቀሰላሙ መቀጠል ትልቅ አስተዋፅኦ እንዳበረከቱ ይነገራል፡፡ እስቲ የሰሩትን ይንገሩኝ---
ከፍተኛ ጥረት ያደረግሁበት ነው፤አባታችን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስም እያሉ እኔ ሃያ አመት ደብረታቦር ተቀምጫለሁ፡፡ ሃያ አመት ሙሉ የፋርጣ እና የእስቴ የደቡብ ጐንደር ካህናት፤“አባታችን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያሪክ ሲሉ እንጂ አንድ ቀን እንኳ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ሲሉ አልተሰሙም፤እንዲህ ማለት ቅዱስነትዎን የቤተክርስትያንንም ስርዓት በመቀበል ነው እንጂ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስን ጠልተው አይደለም፡፡ አሁንም ይህ ሀገር ለቅዱስነትዎ ባለውለታዎ ነው፡፡ ስለዚህ ውለታዎን ለመክፈል ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ እንዲመጡ አሳስባለሁ” ብዬ ሁለት ሦስት ጊዜ ተናግሬአለሁ፡፡
መጥተው ሀገራቸው እንዲገቡ እንጂ በአቡነ ጳውሎስ ላይ ፓትርያሪክ እንዲሆኑ አይደለም፡፡ አቡነ መርቆሬዎስ አሁን መንበሩ ላይ እንዲቀመጡ የሚሉ አሉ፤ እንዲህ ያለ ሀሳብ የለኝም፡፡ ምኞታቸው ሀገራቸው መግባት ነውና ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አሁን ሀገራቸው እንዲገቡ ነው እንጂ ፓትርያርክ እንዲሆኑ አይደለም፡፡
ይህ አቋሜ በአቡነ ጳውሎስም ጊዜ አሁንም ተመሳሳይ ነው፡፡ ሰላሙ እንዳይንጠለጠል ነበር ምኞቴ፡፡ ሰላሙ እየተወለካከፈ እዚህም እዚያም ያሉት እያስቸገሩ ስለሆነ በተረጋጋ ጊዜ ይሻላል፤ አሁን ቤተክርስትያኒቱን የሚመራ አባት ይመረጥ ብለናል፡፡
ብፁዕነትዎ ፓትርያሪክ ቢሆኑ እርቀሰላሙ ከምን ይደርሳል? በምን ያህል ጊዜስ ይጠናቀቃል?
የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው እንጂ ትንቢት አልተናገርንም፡፡ ፓትርያሪክም ብሆን ሊቀጳጳስም ብሆን እርቁ ይቀጥላል፡፡ እዚህም ያሉት እዚያም ያሉት ቤተክርስትያን እንድትከፈል አይፈልጉም፡፡ ቤተክርስትያን እንዳትከፈል እርቁም እንዲጠናቀቅ ነው ምኞቴ፡፡
በስደት ካሉ ብፁአን አባቶች ጋር ጥብቅ ግንኙነት አለዎት ይባላል፤እውነት ነው?
በስደት ካሉት ብፁአን አባቶች ጋር ተገናኝተንም አናውቀም፡፡ ሆኖም ስዊድን ያሉት አቡነ ኤልያስ ደብረታቦር ሳለሁ ይደውሉልኝ ነበር፡፡
ብዙ ጊዜ በቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ አይገኙም ---- ለምንድነው?
ብዙ ጊዜ አልመጣም፡፡ ሀገሩም ሩቅ ስራውም ከባድ ነው፡፡ በዚያ ላይ ስራው ይበዛል፡፡ ደብረታቦርም ሳለሁ በዓመት አንድ ጊዜ ነው የምመጣው፡፡ ይህ በሌላ ምክንያት ወይም ከፓትርያሪኩ ክፍተት ኖሮን አይደለም፡፡ አቡነ ጳውሎስ እንደውም ወዳጄ ናቸው
አቡነ ጳውሎስ ሰሩት ከሚባሉ በጎ ሥራዎች የሚያደንቁት አለ?
ብዙ በጐ ተግባራት ነበሯቸው፡፡ ይህን የጳጳሳት መኖርያና መንበረ ፓትርያርክ አሰርተዋል፡፡ እንግዳ ተቀባይም ነበሩ፡፡ የመጣውን እንግዳ ማብላት ማጠጣት ይወዳሉ፡፡ ቤተክርስትያን ማገልገል ይወዳሉ፡፡አቡነ ጳውሎስን “ይኼ ስህተት ነው” ብለው የተናገሩበት ጊዜ አለ?
ሰው አብሮ ከኖረ እንዲህ ቢሆን ይሻላል መባባል አይቀርም፡፡ ለምሳሌ ደብረታቦር አይሄዱም ነበር በስደተኞቹ ይሁን በሌላ ከበድ ይላቸው ነበር፡፡ ብዙዎቹ ውጭ ያሉት ብፁአን አባቶች ከዚያ አካባቢ ናቸው፡፡
አንድ ጊዜ ስለ ኤችአይቪ ለማስተማር፤ቡራኬም ለመስጠት፤ የሠራናቸውን ትምህርት ቤትና ቤተክርስትያን እንዲባርኩልን በሃያ አመቱ ውስጥ አንዴ ለመሄድ ፈቃዳቸው ሆኖ ነበር፡፡
እናም “ደብረታቦር ልንመጣ ነው፤ ጐብኝተን ምዕዳን ሰጥተን እንመለሳለን፤ አናድርም ባህርዳር ነው የምናድረው” አሉኝ፡፡ “ለአንድ ቀን መጥቶ የሚመለስ ሰው ወይ ለለቅሶ ወይ ዘመድ ለመጠየቅ ይመስላል እንጂ የፓትርያርክ ጉብኝት አይመስልም----” ብዬ ተከራክሬአቸው፤ የአውሮፕላን ትኬት አስቀይረው አርብ ሄደው እስከ እሁድ ቆይተዋል፡፡

በስደት ላይ የሚገኘው ሲኖዶስ ሢመት ፕትርክናውን አውግዟል
‹‹ዕርቀ ሰላሙ ቅዱስ ሲኖዶስ በተናገረው መሠረት ይቀጥላል››
/ተመራጩ ፓትርያርክ/
አምስት ዕጩ ፓትርያርኮች ለውድድር በቀረቡበት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የስድስተኛው ፓትርያርክ ምርጫ÷ ብፁዕ አቡነ ማትያስ 500 ድምፅ በማግኘት ሌሎች ዕጩዎችን በሰፊ ልዩነት ያሸነፉበት ውጤት የምርጫውን ተሳታፊዎችና ተከታታዮች እያነጋገረ ነው፡፡
አዲስ አድማስ ያነጋገራቸው የምርጫው ተሳታፊዎችና በተለያዩ መንገዶች የምርጫውን ሂደት የተከታተሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዮችና ምእመናን÷ የምርጫው አሸናፊ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ሊኾኑ እንደሚችሉ ከወራት በፊት በሰፊው ሲነገር የቆየ ነበር፡፡ ይኹንና በምርጫው ድምፅ ከሰጡ 806 መራጮች መካከል ከ60 በመቶ በላይ ድምፅ በማግኘት ያሸነፉበት ውጤት÷ በዕጩነት ከተካተቱትና ለፓትርያርክነት ይበቃሉ የተባሉት ሌሎች ዕጩ ፓትርያሪኮች በተናጠል ካገኟቸው አነስተኛ ድምፆች አንጻር የምርጫውን ሂደት መለስ ብለው ለማጤን እንዳስገደዳቸው ይገልጻሉ፡፡
ስማቸውና የተወከሉበት አህጉረ ስብከት እንዳይገለጽ የጠየቁ ሁለት መራጮች፣ ከትላንት በስቲያ በመንበረ ፓትርያሪክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ የተከናወነውን የስድስተኛው ፓትርያርክ ምርጫ ከጅምሩ እስከ ፍጻሜው በቅርበት መከታተላቸውን፣ በአፈጻጸሙ ግልጽና ቀልጣፋ ከመኾኑም ባሻገር ለትችት የሚዳርግ የጎላ ችግር እንዳላዩበት አስረድተዋል፡፡ ይኹንና ከምርጫው ቀን በፊትና ምርጫው ከተካሄደበት አዳራሽ ውጭ ተፈጽመዋል የሚሏቸው ተግባራት ለተጠቀሰው የውጤት መራራቅ በምክንያትነት አስቀምጠዋል፡፡
አስተያየት ሰጭዎቹ በቅድመ ምርጫው ተፈጽመዋል ከሚሏቸው ተግባራት መካከል÷ መንግሥት አሸናፊው ዕጩ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ‹‹ቀጣዩ ፓትርያርክ እንዲኾኑ ይደግፋል›› በሚል በሰፊው መወራቱና ይህንንም ተከትሎ በመራጮች ውሳኔ ላይ ተጽዕኖ ለማሳደር ተፈጽሟል የሚሉት መጠነ ሰፊ ቅስቀሳ ነው፡፡ ቅስቀሳው በተወሰነ መልኩ ‹‹ብፁዕነታቸውን ባትመርጡ…›› የሚል ማስፈራሪያም የተቀላቀለበት እንደነበር መራጮቹ የራሳቸውንና የሌሎች ጓደኞቻቸውን ተሞክሮ በመጥቀስ ይናገራሉ፡፡
በርካታ የካህናትና ምእመናን ጥቆማ ካገኙና በዕጩ ፓትርያሪክነት ለመወዳደር ይበቃሉ ያሏቸው ሊቃነ ጳጳሳት በዕጩነት አለመካተታቸው ቅር እንዳሰኛቸው የገለጹት እኒህ አስተያየት ሰጭዎች÷ በምርጫው ለቀረቡት ዕጩዎች በአስመራጭ ኮሚቴው የተሰጠው ትኩረትም ምክንያታዊና ሚዛናዊ አለመኾኑንም ለውጤቱ መራራቅ በመንሥኤነት ጠቅሰዋል፡፡ በድምፅ መስጫው ወረቀት ላይ አሸናፊው ዕጩ ብፁዕ ማትያስ በመጀመሪያ ደረጃ መቀመጣቸው በሢመተ ጵጵስና ዘመነኛቸው ከኾኑት፣ በዕድሜ ከሚበልጧቸውና በሁለተኛ ደረጃ ከተቀመጡት ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ አንጻር የራሱ ተጽዕኖ አሳርፏል ብለው እንደሚያምኑ ገልጸዋል፡፡
የሁለቱን አስተያየት ሰጭዎች አስተያየት የሚተቹትና ድምፃቸውን ለአሸናፊው ዕጩ መስጠታቸውን ገልጠው የተናገሩ ሌሎች መራጮች በበኩላቸው÷ ብፁዕ አቡነ ማትያስ በአባታዊ ሞገሳቸው፣ በአገልግሎት ልምዳቸውና በዓለም አቀፍ ተሞክሯቸው ያገኙት ድምፅ ውጤት የሚያንሳቸው እንጂ የሚበዛባቸው እንዳልኾነ ይከራከራሉ፡፡ በቅድመ ምርጫው በየአቅጣጫው በብፁዕነታቸው ላይ ሲሰጡ የቆዩ ትችቶችን መከታተላቸውን የገለጹት መራጮቹ÷ በመጨረሻ ለውጤቱ ወሳኝ የሚኾነው መራጩ የሚወስደው አቋም ነውና በዕጩነት ከቀረቡት ሊቃነ ጳጳሳት ብፁዕነታቸው በሰፊ ድምፅ መርተው የተመረጡበት ውጤት ተቺዎቻቸውን ጭምር ያስደነቀ መኾኑን በምርጫው ስፍራ ማረጋገጣቸውን መስክረዋል፡፡
በምርጫው በዕጩ ፓትርያሪክነት የተወዳደሩት ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ 98 ድምፅ፣ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ 98 ድምፅ፣ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል 70 ድምፅ እና ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ 39 ድምፅ ማግኘታቸው አስመራጭ ኮሚቴው ይፋ ባደረገው የምርጫ ውጤት ተገልጧል፡፡
ከምርጫው አንድ ቀን በፊት ከአዲስ አድማስ ዘጋቢ ጋር አጭር ቆይታ ያደረጉት ተመራጩ ፓትርያሪክ ብፁዕ አቡነ ማትያስ በዕጩነት መካተታቸውን ያወቁት በሀ/ስብከታቸው ኢየሩሳሌም ሳሉ ከኢትዮጵያ በተደረገላቸው ጥሪ መኾኑን ገልፀዋል፡፡ “መንግሥት እርሳቸው ስድስተኛው ፓትርያሪክ እንዲኾኑ ይፈልጋል ስለመባሉ ተጠይቀው÷ ‹‹ስለዚህ ጉዳይ ምንም የማውቀው ነገር የለም፤›› ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
በሌላ በኩል በሰሜን አሜሪካ በስደት ላይ የሚገኘው ‹‹ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ›› የካቲት 24 ቀን 2005 ዓ.ም የሚካሄደው ሢመተ ፓትርያሪክ÷ ‹‹ኢ-ቀኖናዊና የቤተ ክርስቲያንን ክብር ዝቅ የሚያደርግ፣ ሥርዐተ አልበኝነትን የሚሰብክ፣ ቤተ ክርስቲያንን የሚከፋፍል ነው፤›› በሚል ቀደም ሲል ያስተላለፈውን ውግዘት ማጽናቱን ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ በመላው ዓለም የሚገኙ ካህናትና ምእመናን ለቤተ ክርስቲያን ክብርና አንድነት፣ ሰላምና ሐዋርያዊ ተልእኮ መሳካት አብረውት እንዲቆሙና እንዲሠሩም ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
በውጭ በስደት ከሚገኙት የቤተ ክርስቲያኒቱ አባቶች ጋር የተጀመረውን የዕርቀ ሰላም ንግግር ለፍጻሜ ከማብቃት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን ተቋማዊ መሻሻል በማፋጠን አስተዳደራዊ ለውጥ እንዲመጣ ከመንቀሳቀስ አኳያ በርካታ ተግባራት የሚጠብቋቸው አሸናፊው ተመራጭ ፓትርያሪክ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ለአዲስ አድማስ እንደገለጹት÷ ‹‹ቤተ ክርስቲያኒቱ ቀጥተኛውንና ትክክለኛውን መንገድ እንድትይዝና መንፈሳዊነትን እንድትጎናጸፍ ነው ተስፋ የማደርገው፡፡ ዕርቀ ሰላሙ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ተናግሯል፡፡ በዚያው መሠረት ይቀጥላል፡፡ ከሲኖዶስ የተለየ ሐሳብ ሊኖረኝ አይችልም፤›› ብለዋል፡፡
በአስመራጭ ኮሚቴው በወጣው መርሐ ግብር መሠረት የስድስተኛው ፓትርያሪክ በዓለ ሢመት በነገው ዕለት የአኀት አብያተ ክርስቲያን ተወካዮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም መገለጹ ይታወሳል፡፡

 

በተቅማጥ በሽታ ህይወታቸው የሚያልፈውን በ10ሺዎች የሚቆጠሩ ህፃናትን ከሞት ለመታደግ የሚያስችለውን ዚንክ የተባለ ንጥረ ነገር ለቀጣዮቹ አራት ዓመታት ለማቅረብ የሚያስችለውን ስምምነት ማይክሮ ኒውትሬንት የተባለውና በካናዳ መንግስት የሚደገፈው ድርጅት ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ጋር ሰሞኑን ተፈራረመ፡፡
ባለፈው ሣምንት በሒልተን ሆቴል በተካሄደው በዚሁ የስምምነት ፊርማ ላይ እንደተገለፀው ድርጅቱ ለቀጣዮቹ 4 አመታት የ Zinc ንጥረ ነገሮችን በመድሃኒት መልክ የተቅማጥ በሽታ በስፋት በሚታይባቸው አካባቢዎችና በአገሪቱ የተለያዩ ክልሎች ያሰራጫል፡፡
ዚንክ በተቅማጥ ህመም ሣቢያ ህይወታቸው የሚያልፈውን ሰዎች በተለይም ህፃናትን ሞት በእጅጉ ለመቀነስ ከማስቻሉም በላይ የአዕምሮና የሰውነት ቅልጥፍና በመጨመር ጤናማ ማህበረሰብ እንዲኖር ትልቅ አስተዋፅኦ ያደርጋል፡፡
ማይክሮ ኒውትሬንት ኢንሼትቭ የተባለውና በእናቶችና ህፃናት ሥነ ምግብና ጤና ላይ አተኩሮ የሚሰራው ድርጅት ከጤና ጥበቃ ሚኒስትር መ/ቤት ጋር ባደረገው ስምምነት መሠረት ዚንክን ወደ አገር ውስጥ በማስገባት በአገሪቱ የተለያዩ ክልሎች እንዲሰራጭ ያደርጋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ በየዓመቱ ከ27ሺ በላይ ህፃናት በተቅማጥ በሽታ ይሞታሉ፡፡

ውሃና ፍሳሽ በ6 ወራት 187 ሚሊዮን ብር ገቢ ሰብስቧል
የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን 40 የፍሳሽ ቆሻሻ ማንሻ መኪናዎችን ግዥ ሊፈጽም ነው፡፡ ይህም በባለስልጣን መ/ቤቱ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ እንደሆነና ከዚህ ቀደም አነስተኛ ቁጥር ያላቸው መኪኖችን ብቻ ይገዛ እንደነበር ተገልጿል፡፡ በፍሳሽ ቆሻሻ ማንሳት ሥራ ላይ የሚሰማሩ በቂ መኪኖች ባለመኖራቸውና የህብረተሰቡ ፍላጐት ከፍተኛ እየሆነ በመምጣቱ የአርባ መኪኖች ግዥ ለመፈፀም መታሰቡን የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ተስፋዓለም ባዬ ገልፀዋል፡፡
የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ከትናንት በስቲያ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደገለፀው፤ በስድስት ወራት ውስጥ 187.15 ሚሊዮን ብር ገቢ ሰብስቧል፡፡ ባለስልጣን መ/ቤቱ በአሁኑ ወቅት በከተማው ውስጥ ተስፋፍቶ የሚገኘውን የውሃ እጥረት ለመቅረፍ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ መሆኑን የገለፁት የባለስልጣኑ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ አሰግድ ጌታቸው፤ ይህንን ችግር ለመቅረፍና ለህብረተሰቡ በቂ የውሃ አቅርቦት እንዲኖር ለማድረግ ቀን ከሌት እንሠራለን ብለዋል፡፡
በባቡር መሥመር ዝርጋታው ሰበብ የሚነሳውንና በ1947 ዓ.ም የተሰራውን 8.5 ኪ. ሜትር ርዝመት ያለውን የውሃ መስመርና ትልቅ የውሃ ማከፋፈያ ቱቦ በማንሳት በአፋጣኝ ቀይሮ ለአገልግሎት ለማዋል ጥረት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ የውሃ ቱቦዎቹና ልዩ ልዩ መሣሪያዎች በቻይና አገር እንዲመረቱ ተደርጐ ጅቡቲ ወደብ መድረሳቸውን ተናግረዋል፡፡ የውሃ መስመር ዝርጋታው እስከሚጠናቀቅም በጊዜያዊ መስመር ህብረተሰቡ ውሃ ለማግኘት እንዲችል ለማድረግም እየሰራን ነው ሲሉ ሥራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ውስጥ ንብረትነታቸው የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ የሆኑ ቤቶችን ለንግድ ሱቅ አገልግሎት ተከራይተው ሲጠቀሙ የነበሩ ነጋዴዎች ከኤጀንሲው ጋር የነበራቸው ውል ሣይቋረጥ የክፍለ ከተማው የመሬት አስተዳደር ቦታው ለቤተ አምልኮ እና ሁለገብ ህንፃ ግንባታ ስለሚፈለግ በአስቸኳይ ልቀቁ ማለቱ ውዝግብ አስነሣ፡፡
የክፍለ ከተማው የመሬት አስተዳደር አካላት በተደጋጋሚ የፖሊስ ግብረ ሃይል ይዘው በመመላለስ ንብረታችሁን አንሡና ቤቶቹን ልቀቁ የሚል ትዕዛዝ እንደሚያስተላልፉ የተናገሩት ባለ ንግድ ሱቆች፤ እኛ በውላችን የምናውቀው ያከራየንን አካል ስለሆነ እሡ ውላችሁን አቋርጫለሁ የሚል ትዕዛዝ ካላስተላለፈ አንለቅም ማለታቸውን ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል። ስለ ጉዳዩ ያከራያቸውን የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲን ሲጠይቁ፤ “እኛ ከእናንተ ጋር ያለንን ውል እስካላቋረጥን ዝም ብላችሁ ስሩ” ማለቱን ቅሬታ አቅራቢዎቹ ይናገራሉ። በቅርቡ ባደረጉት የውል ስምምነት እድሣትም፣ ከጥር 1 እስከ መጋቢት 30 የሚቆይ ስምምነት ከመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ ጋር መፈራረማቸውን የሚናገሩት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ሁለቱ የመንግስት አካላት ችግራቸውን ተነጋግረው መፍታት ሲገባቸው የክፍለ ከተማው አመራሮች በፖሊስ ግብረ ሃይል በመታገዝ ውክቢያ መፍጠራቸው ተገቢ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡
ቀደም ሲል በቀበሌ ቤትነት ተመዝግበው የነበሩ አምስት ቤቶች ከአንድ አመት በፊት በተመሣሣይ አላማ እንዲፈርሡ ተደርጐ በቦታው ላይ ምንም ሣይሠራበት መቆየቱን የሚናገሩት ግለሠቦቹ፤ አካባቢው ሠፊ የንግድ እንቅስቃሴ ያለበት በመሆኑ የገቢ ምንጭ ፈጥረን ቤተሠቦቻችንን እያስተዳደርን ባለበት ወቅት አሣማኝ ባልሆነ ምክንያት እንድንለቅ መደረጉ አግባብ አይደለም ብለዋል፡፡ በአካባቢው መሪ ፕላን ላይ ቦታው ለልዩ ልዩ አገልግሎት የሚውል መሆኑ የተመለከተ ቢሆንም ከሊዝ ነፃ ተደርጐ ለኢትዮጵያ ህይወት ብርሃን ቤተክርስቲያን የቤተ አምልኮ ግንባታ መፈቀዱም የከተማው አስተዳደር መሪ ፕላኑን በማስፈፀም ረገድ ጉድለቶች እንዳሉበት አመላካች መሆኑን ቅሬታ አቅራቢዎቹ ገልፀዋል፡፡
በጉዳዩ ዙሪያ ያነጋገርናቸው የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ የህዝብ ግንኙነት እና ኮሚኒኬሽን የስራ ሂደት ባለቤት አቶ አዲስ እጅጉ በበኩላቸው፤ ክፍለ ከተማው ጉዳዩን ከኤጀንሲው ጋር በመሆን መፈፀም ሲገባው ተከራዮቹን ማስጨነቁ አግባብ አለመሆኑን አመልክተው፣ የውዝግቡ መነሻ ቤተ ክርስቲያኗ ለግምት ካሣ ክፍያ የተተመነላትን 1.8 ሚሊዮን ብር ለኤጀንሲው ከፍላ በጊዜው ባለማጠናቀቋ መሆኑን ለዝግጅት ክፍላችን ገልፀዋል፡፡ አሁን ግን ቤተክርስቲያኗ የሚፈለግባትን ገንዘብ ከፍላ ባሣለፍነው ሣምንት በማጠናቀቋ፣ ለተከራዮቹ የውል ማቋረጫ ደብዳቤ ተፅፎላቸው በቀናት ውስጥ እንዲደርሣቸው ይደረጋል፤ ይህንንም ቅርንጫፍ መስሪያ ቤቱ እንዲያስፈፅም ትዕዛዝ ተላልፎለታል ብለዋል፡፡
ከተከራዮቹ ጋር የተዋዋላችሁት ስምምነት ግለሠቦቹ እስከ መጋቢት 30/2005 ዓ.ም ቤቱን እንዲገለገሉበት ይፈቅዳል፤ ይሄን እንዴት ልታስታርቁት ነው ብለናቸውም፤ መንግስት ቦታውን ለልማት ሲፈልገው በማንኛውም ጊዜ ውሉ ሊቋረጥ ይችላል የሚል ስምምነት በአከራይ ተከራይ ውላቸው ላይ መስፈሩን አቶ አዲስ አስታውቀዋል፡፡
በተመሣሣይ በአካባቢው በባለቤታቸው ስም የተመዘገበ የግል ይዞታ እንደነበራቸው የገለፁልን አቶ ወንድማገኝ መኮንን ካሣ፤ ተሠጥቷችሁ ትነሣላችሁ ሲሉን ቦታው ላይ ሠፍሮ የሚገኘው ግለሠብ አቅሙ ካለው ቅድሚያ የማልማት እድል ይሠጠዋል የሚለውን የህግ ድንጋጌ ዋቢ በማድረግ አቅሙ ስላለን ማልማት እንችላለን ብለናቸው፣ ብር በባንክ ዝግ የሂሣብ መዝገብ አስገቡ ካሉን በኋላ፣ ቦታው ለእናንተ አይፈቀድም ተሸጧል፣ ካሣችሁን ውሠዱ ብለውናል፡፡ እኛ ግን ካሣውን ለመውሠድ ፈቃደኛ ስላልሆን የሚመለከተው አካል ጉዳያችን በአንክሮ እንዲመለከት እንጠይቃለን ብለዋል፡፡
በቂርቆስ ክፍለ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማት ማናጅመንት ፅ/ቤት ሃላፊ አቶ ተገኝ ጦፎ፤ ጉዳዩ ለሠባት አመታት የዘለቀ መሆኑን፣ ለቤተክርስቲያኗ የሊዝ ቦርዱ ቀደም ብሎ በ2003 ያስተላለፈውን ውሣኔ እስከ ዛሬ ባለማስፈፀማቸው ቅሬታ እንደቀረበባቸው፣ ለዚህም ሲባል ክፍለ ከተማው የማስፈፀም ሃላፊነቱን ለመወጣት ግለሠቦቹን ማንሣት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ እርምጃውን ሊወሠድ መቻሉን ገልፀዋል፡፡ “እኛ ከተከራዮቹ ጋር ምንም ግንኙነት የለንም፤ የተላለፈውን ትዕዛዝ በአግባቡ ማስፈፀም ነው ሃላፊነታችን፤ በዚህ ሂደት ነው ችግሩ የተፈጠረው” ያሉት አቶ ተገኝ፤ በቦታው ላይ ቤት ያላቸው ግለሠቦች እና የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ ካሣ ተከፍሏቸው፣ የቀበሌ ቤቶቹ ደግሞ ምትክ ቤት ተሠጥቷቸው እንዲነሡ ይደረጋል ብለዋል፡፡ በዚህ ሂደት አግባብነት የሌለው እርምጃ ተወስዷል የሚል አካል ካለ በህግ መጠየቅ እንደሚችል የሚናገሩት ሃላፊው፤ “እኛ በደንቡ መሠረት ከቤተክርስቲያኗ ካሣውን ተቀብለን በመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ አካውንት እናስገባለን፣ ሂሣቡ መግባቱን ስናረጋግጥ አካባቢውን ወደ ማፅዳት እርምጃ እንገባለን፤ በዚህ አግባብ ነው ቦታው እንዲፀዳ እየተደረገ ያለው ብለዋል፡፡

Monday, 04 March 2013 00:00

እናት ባንክ ሥራ ጀመረ

የሴቶችን ኢኮኖሚያዊና ሁለንተናዊ አቅም የሚያሻሽሉና ከዚህ ቀደም በኢንዱስትሪው ትኩረት ያልተሰጣቸውን አገልግሎቶች ይዞ ሥራ መጀመሩን እናት ባንክ አስታወቀ፡፡ 

ባንኩ አገልግሎት የሚጀምርባቸው የመጀመሪያዎቹ ቅርንጫፎች ባንቢስ አካባቢ ከዮርዳኖስ ሆቴል ፊት ለፊት በሚገኘው ዋና መ/ቤቱና ቦሌ መድኃኒዓለም ቤተክርስቲያን አካባቢ መሆኑ ታውቋል፡፡ የባንቢስ አካባቢው ዓቢይ ቅርንጫፍ በእቴጌ ጣይቱ ስም የተሰየመ ሲሆን የቦሌ መድኃኒዓለሙ በንግሥተ ሳባ እንዲሁም የሰንጋ ተራው በወ/ሮ አበበች ጎበና ስም መሰየማቸውን ገልጸዋል፡፡ 

እናት ባንክ የሴቶችን አቅም በማጐልበትና በመጠቀም በኢንዱስትሪው ፈጣን ዕድገት ለማምጣትና የአገሪቱን ዕድገት ቀጣይ ለማድረግ የበኩሉን ሚና እንደሚወጣ አስታውቋል፡፡

የዱር አራዊት ተሰብስበው ግብረ - ገብነታችንንና ሥነ-ምግባራችንን የሚያርቅ፣ መሠረታችንን የሚያበጅ፣ ደህና ጠባይ ያለው እንስሳ እንምረጥ ይባባላሉ፡፡
አንበሳ፤ የአራዊቱ ሁሉ ንጉሥ ነውና “ምርጫው ይሳካ ዘንድ ጦጣን፣ አህያንና ነብርን ስጡኝና የአመራረጡን ሥነ ስርዓት አስቀድመን እናበጃጀው!” ይላል፡፡
አራዊቱ፤ “መልካም ሀሳብ ነው፡፡ እነዚህን ሶስቱን ወስደህ ምከሩበት፡፡ አስቀድመህ ግን፤ ለምን እነሱን እንደመረጥክ ምክንያቱን አስረዳ” አሉት፡፡
አንበሳም፤
“መልካም፡፡ በአዘጋጅ ኮሚቴነት ሶስቱን ስመርጥ ሶስት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉኝ፡፡ እጅግ አስፈላጊ የሆነው የሥራ ሀላፊነት፡-
አንደኛ - ብልሃተኛ መሆን ነው፡፡ ለዚህ ጦጣን መረጥኩ፡፡
ሁለተኛ - ሸክም የሚችል ትከሻ ያስፈልጋል፡፡ እንደምታውቁት ለዚህ ከአህያ የተሻለ መሸከም የሚችል አይገኝም፡፡
ሦስተኛ - ፈጣን መሆን ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ እንደነብር ጥይት የለም፡፡
ምክንያቴ ይሄ ነው፤ አለ፡፡ ጭብጨባው ቀለጠ፡፡
“ጥሩ፡፡ በሉ ምርጫውን አሳኩት” ተባሉ፡፡
አንበሳ አስመራጮችን ሰብስቦ “እህስ? እንዴት እናድርግ ትላላችሁ?” አለ፡፡
አህያ፤ “ማናቸውንም በሸክም ዙሪያ ያለ ሥራ ለእኔ ይሰጠኝ” አለች፡፡
ነብር፤ “በፈጣንነቴ የትኛውም የጫካው ድንበር ድረስ ሮጬ የተሰጠኝን መልዕክት አደርሳለሁ” አለ፡፡
አያ አንበሶም፤ “እሺ እመት ጦጣስ? ምን እናድርግ ትያለሽ? መቼም መላ የሚጠበቀው ካንቺ ነው?!” አላት፡፡ ጦጣም፤ “መቼም አያ አንበሶ! የአህያም ሥራ ሸክም መሆኑ በሙያዋ ነው፡፡ የነብርም ሩጫ የተፈጥሮ ክህሎቱ ነው፡፡ እጅግ ከባዱ ጥያቄ ግን በእኔና በእርሶ በጌታዬ በአያ አንበሶ ጫንቃ ላይ ነው የወደቀው፡፡”
ይሄኔ ነብሮ፤ “ምን አዲስ ነገር አለ አንቺ የምትጨምሪልን?” አለና ጠየቃት፡፡
አህያም፤ “ነገሩን ከማስተባበርና ምርጫው በሰላም እንዲያልቅ ከማድረግ በስተቀር ምን የምታከናውኑት ተግባር ይኖራል?” ሲል ጦጣን ጠየቃት፡፡ አያ አንበሶም፤ “እስቲ አትቸኩሉ! የጦጣን ብልህነት አጥታችሁት ነው አሁን? የምትለውን በጥሞና እናዳምጣት” አለ፡፡
ጦጢትም፤ “መልካም እኔ ልል የፈለግሁት፤ ምንም ዓይነት ምርጫ ቢካሄድ አንድ ወሳኝ ቁምነገር መኖሩን አንርሳ ነው”
ነብሮ፤ “እኮ ቁምነገሩ ምንድን ነው?”
አህያ፤ “እኮ ቁም ነገሩን ንገሪና?”
ጦጢት “ታገሡኛ! ዓመት አላወራ! ይሄውላችሁ፤ ወሳኙ ቁም ነገር - የሚመረጠው እንስሳ ማንም ይሁን ማ ለአያ አንበሶ አገዛዝ የሚመች መሆን አለበት!”
ነብሮ፤ “እሱማ ጥርጥር የለውም!”
ጦጢት ቀበል አድርጋ፤ “ስለዚህ” አለችና ቀጠለች፤ “ስለዚህ አሁኑኑ ማን መሆን እንዳለበት እንወስን”
ነብሮ፤ “ለምን እኛ እንወስናለን?”
ጦጢት፤ “1ኛ/ ጊዜ እንቆጥባለን
2ኛ/ አራዊቱ ማንን እንምረጥ እያሉ ግራ እንዳይጋቡ እናግዛቸዋለን
3ኛ/ ተመራጩ ብቁ ነኝ ብቁ አደለሁም፤ ተዘጋጅቻለሁ አልተዘጋጀሁም? እያለ ራሱን እንዳያስጨንቅና በፍርሃት ኃላፊነቱን አልቀበልም እንዳይል፤ ከወዲሁ እናመቻቸዋለን” ስትል አስረዳች፡፡
አያ አንበሶም፤
“ድንቅ ነው! እኔ ጦጢት አስመራጭ ትሁን ያልኩት ይሄንን ጭንቅላቷን አመዛዝኜ ነው! በእኔ እምነት መመረጥ ያለበት ዝንጀሮ ነው፡፡ በሰውና በእንስሳ መካከል ያለ እሱ በመሆኑ እሱ ይመረጥ! በቃ ተመካከሩና ማንን እንደምናስመርጥ ንገሩኝ፡፡ እኔ ትንሽ አረፍ ልበል” ብሎ እየተጐማለለ ወደ ማረፊያው ሄደ፡፡
***
“ንጉሡ የወደዱትን ሁሉ ህዝብ መውደድ አለበት” ከሚል አስተሳሰብ ይሰውረን፡፡ ካህኑ የወደደውን ምዕመኑ ሊወድድ ግን ግድ ሊሆን ይችላልና ጥኑ ጥንቃቄ ይፈልጋል፡፡ አንድም፤ የዓለምን - የዓለምን ቢሉም የኃያላንን ፍላጐት - እናሙዋላ ዘንድ ግዴታችን ነውን? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ የሃይማኖት ውዝግባችን የኃያላንን ፍቃድ ማሟላት ነውን? ብሎ በጥሞና ለመመርመር ወቅቱ አሁን ነው፡፡ የእኛ ባህል፣ የእኛ ሃይማኖት ብሎም የእኛ ሰላም መኖርና መሰንበት፤ ዐይናቸውን የሚያቀላው ሃያላን መንግሥታት፤ እንደልብ የሚያሽከረክሩን አሻንጉሊቶች እንዳንሆን መጠንቀቅ ይገባናል፡፡ የተራቀቀውን የኑክሊየር ሳይንስና ቴክኖሎጂ ከመዋጀት፤ “በአንድ መርፌ አናት ላይ ስንት መላዕክት ይቀመጣሉ?” የሚለው መንፈሳዊ ምላሽ የሚሻ ምርምር የተሻለ ዋጋ እንዳለው አንዘንጋ! ከፈረሱ ጋሪው የሚቀድምበትን ሁኔታ ማስተዋል የዲሞክራሲን፣ የምርጫንና የፍትህን ነገረ-ሥራ እንድናይ በእጅጉ ይረዳናል፡፡ ባለቅኔው ዮሐንስ አድማሱ ስለ ዮፍታሄ ንጉሤ ሲፅፍ “ቅኔ የንባብና የፀዋትወ ዜማ፣ ደጀን የትርጓሜ መፃህፍት ፊታውራሪ ነው… ቅኔን ከፀዋትወ ዜማ በፊት፣ ከትርጓሜ ወፃህፍት በኋላ ለመማር በፍፁም አይቻልም፡፡ ይኸውም ከዘር በፊት ቡቃያ፣ ከባል በፊት ልጅ ይሆናል” ይለናል፡፡ ዲሞክራሲም እንደዚያው፡፡ ከምርጫ በፊት መከበር ያለበት ዲሞክራሲ ነው፡፡ ዲሞክራሲን ሳይዙ እኩልነት የሰፈነበት፣ ፍትሐ ርትዕ የበለፀገበት ሥርዓት እገነባለሁ ማለት “እንሥራዋን ጥላ ወንዝ ወረደች” እንደሚባለው ይሆናል፡፡
በአገራችን አንዳች ነገር ምን ስለመሆኑ ከመፃፍ ምን ስለአለመሆኑ መፃፍ ይቀላል፡፡ የሚገባንም አሉታዊ ዘዴ እንጂ አዎንታዊ ገፅታ አይደለም፡፡ ኑሮአችንም ጉዞአችንም አድካሚ አቀበት የሚሆንብን ለዚህ ነው፡፡ ለምሳሌ ዲሞክራሲ ቀናውና ግልፁ ጉዞ ሆኖ ሳለ ሚስጥራዊ ወይም ምትሃታዊ ብናደርገው እንመርጣለን፡፡ የቅኔ ትምህርትን ማወቅ የምንደክመውን ያህል ዲሞክራሲን ማወቅም የዚያኑ ያህል አድካሚ ነው፡፡ ባለቅኔው ዮሐንስ አድማሱ በዚያው መፅሐፉ የዲሞክራሲንና የቅኔን ቁርኝት እንድናፀኸይ እድል ይሰጠናል፡፡ “የቅኔ ትምህርት… የትውልድ አገርን ትቶ፣ ጋራ ዙሮ ወንዝ ተሻግሮ፣ ወጥቶ ወርዶ፣ ከውሻ ተከላክሎ፣ ቁራሽ እንጀራ ለምኖ፣ ደበሎና ማቅ ለብሶ፣ ተዋርዶ ተንከራትቶ፣ ብዙ ፈተና ተቀብሎ፣ አይመስሉ መስሎ፣ ቀይ የነበረው ጠቁሮ፣ ረዥም የነበረው አጥሮ፣ ተርቦ ተጠምቶ፣ ፀዋትወ መከራውን ሁሉ ታግሶ የሚማሩት የተባሕት ትምህርት ነው” ይላል፡፡ ስለዲሞክራሲም የምንናገረው ይሄንኑ ያህል ነው፡፡ እንደምን ቢሉ፤ ዲሞክራሲም እንደቅኔ ትምህርት ጋራ ዙሮ ወንዝ ተሻግሮ የሚገኝ እንጂ የምቾትና የቅንጦት ባለመሆኑና፣ ብዙ መከራ የታቀፈ ስለሆነ፤ ብዙ ፈተና በማስከፈሉ፣ እንዲሁም፤ እንደ ቁራሽ እንጀራ ሁሉ ኢኮኖሚን በመንተራሱ ነው! “እኔ እምሻውን ብቻ እስከፈፀምክ ድረስ ዲሞክራሲ ማለት ያ ነው” ብለን መንገዳችንን ማስተካከል ከቶም አይቻልም፡፡ ያ ከሆነ ስህተቱንና ህፀፁን እንገነዘብ ዘንድ፤ “ጥቁር ይሁን እንጂ ማንኛውን ቀለም መቀባት ትችላላችሁ” ያለውን፤ ሀብታም መኪና - አስቀቢ መርሳት ነው፡፡ You can paint it any colour; provided it is black.

ባለፈው ሳምንት በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌደሬሽን ካፕ ላይ ከሜዳ ውጭ የተጫወቱት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት በሰፊ የግብ ልዩነት ተጋጣሚዎቻቸውን አሸንፈው ወደ መጀመርያ ዙር ማጣርያ የሚገቡበትን እድል አሰፉ፡፡ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ቅዱስ ጊዮርጊስ ካዛንዚባሩ ጃምሁሪ ጋር ተገናኝቶ 3ለ0 ሲያሸንፍ ጎሎቹን ፍፁም ገብረማርያም፤ ኡመድ ኡክሪ እና ጆሴፍ ከመረብ አዋህደዋል፡፡ በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ ደግሞ ደደቢት የሴንትራል አፍሪካውን አንጌስ ዴፋቲማ 4ለ0 ሲረታ ግቦቹን ያስቆጠሩት ጌታነህ ከበደ፤ አዲስ ህንፃ፤ በሃይሉ አሰፋ እና ዳዊት ፍቃደ ናቸው፡፡ በቀጣይ ሳምንት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት በቅድመ ማጣርያው የመልስ ጨዋታቸው ተጋጣሚዎቻቸውን በአዲስ አበባ ያስተናግዳሉ፡፡ ሁለቱም ክለቦች በአህጉራዊ ውድድሩ ወደ የሚቀጥለው የመጀመርያ ዙር የማጣርያ ምእራፍ ለመሸጋገር በመልስ ጨዋታቸው በቀላሉ አቻ መውጣት እና ማሸነፍ ይበቃቸዋል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ የዛንዚባሩን ጃምሁሪ በቅድመ ማጣርያው ጥሎ ሲያልፍ በሻምፒዮንስ ሊጉ የመጀመርያ ዙር ማጣርያ ቀጣይ ተጋጣሚው የማሊው ክለብ ዲ ጆሊባ ይሆናል፡፡ ደደቢት ደግሞ አንጌስ ዲ ፋቲማን ጥሎ ካለፈ በኮንፌደሬሽን ካፑ የመጀመርያ ዙር ማጣርያ የሚያገኘው የሱዳኑን ክለብ አሊሂላል ሼንዲ ነው፡፡
በአፍሪካ ሁለት ትልልቅ የክለብ ውድድሮች ቅዱስ ጊዮርጊስና ደደቢት ኢትዮጵያን በመወከል በነበራቸው ተሳትፎ ከሜዳቸው ውጭ ብዙ ጎል አግብቶ በማሸነፍ ያስመዘገቡት ውጤት በአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ በአገሪቱ እግር ኳስ የተፈጠረውን መነቃቃት አስቀጥሏል፡፡ በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለተሳተፈው ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ሁለቱ ክለቦች በጋራ 17 ተጨዋቾችን በማስመረጥ ግንባር ቀደም ነበሩ፡፡ በእነዚህ የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾቻቸው በአፍሪካ ዋንጫው ያገኙት ልምድ ደግሞ በአህጉራዊው የክለቦች ውድድር ከቀድሞው የተሻለ ውጤት እንዲያስመዘግቡ ምክንያት ሆኖላቸዋል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ እና ኮንፌደሬሽን ካፑ አጀማመር ላይበሁለቱ ክለቦች ከተመዘገቡት 7 ግቦች አራቱን ለብሄራዊ ቡድን ያስመረጧቸው ተጨዋቾች ከመረብ አዋህደዋል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊግ በሚወዳደረው ቅዱስ ጊዮርጊስ ውስጥ የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች የሆኑት አምበሉ ደጉ ደበበ ፤ ግብ ያስቆጠረው ኡመድ ኡክሪ እና አማካዩ ሽመልስ በቀለ በዛንዚባሩ ጨዋታ ምርጥ ብቃት እንደነበራቸው ተገልጿል፡፡ በኮንፌደሬሽን ካፕ ተሳታፊ የሆነው ደደቢት የሴንተራል አፍሪካውን አንጌስ ዴፋቲማ በሰፊ የግብ ልዩነት ሲያሸንፍ 3 ጎሎችን ያስመዘገቡት የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾቹ ነበሩ፡፡ ሌሎቹ የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች አዲስ ህንፃ የጨዋታው ኮከብ እንደነበረና ግብ ጠባቂው ሲሳይ ባጫ በርካታ ግብ ሊሆኑ የሚችሉ ኳሶችን በማዳን ምርጥ ብቃት ማሳየታቸው ታውቋል፡፡
ቅዱስ ጊዮርጊስ በሻምፒዮንስ ሊግ
ለዘንድሮው የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ከ1 ወር በላይ የተዘጋጀው የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ከቅድመ ማጣርያው አንስቶ በሶስት ዙር የሚደረጉትን የማጣርያ ምእራፎች በማለፍ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ወደ ሻምፒዮንስ ሊጉ የምድብ ድልድል ውስጥ ለመገባት አቅዷል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ዛንዚባር ሲያቀና ወሳኙን የግብ አዳኝ አዳነ ግርማን ከደረሰበት ጉዳት ባለማገገሙ አልያዘም ነበር፡፡ አዳነ በአዲስ አበባ ለሚደረገው የመልስ ጨዋታ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ መሰለፉ ቢጠበቅም ጨዋታው ያን ያህል አስጨናቂ ባለመሆኑ ካለበት ጉዳት በተሟላ ሁኔታ እንዲያገግም ሊደረግ ይችላል፡፡
በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግን ለ25 ጊዜያት ሻምፒዮን በመሆን ክብረወሰን የያዘው ቅዱስ ጊዮርጊስ የዘንድሮው የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎው ለ10ኛ ጊዜ ሲሆን ውድድሩ አፍሪካን ካፕ ኦፍ ሻምፒዮንስ ክለብስ እየተባለ ደግሞ 10 የውድድር ዘመኖችን ተካፍሎበታል፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን ደግሞ ጊዮርጊስ በካፍ ኮንፌደሬሽን ካፕ ለመጀመርያ ጊዜ መሳተፉ አይዘነጋም፡፡በወቅቱ በቅድመ ማጣርያው የተገናኘው ከኤስ ማንጋ ስፖርት ጋር ነበር፡፡ በዚሁ የደርሶ መልስ ፍልሚያ በመጀመርያው ጨዋታ ከሜዳ ውጭ 1ለ0 አሸንፎ ከተመለሰ በኋላ በመልሱ ጨዋታ እዚህ አዲስ አበባ ላይ ማንጋ ስፖርት 4ለ0 በመርታት ወደ መጀመርያው ዙር ገብቶ ነበር፡፡ በመጀመርያው ዙር የተገናኘው ከቱኒዚያው ክለብ አፍሪካን ነበር፡፡ የመጀመርያውን ጨዋታ በሜዳው ሲያደርግ 1ለ1 ተለያየ ከዚያም በመልስ ጨዋታው በክለብ አፍሪካን 2ለ0 ተሸንፎ ከውድድሩ ውጭ ሆኗል፡፡
በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የኢትዮጵያው ቅዱስ ጊዮርጊስ ተጋጣሚ የሆነው የዛንዚባሩ ክለብ ጃምሁሪ በአፍሪካ ክለቦች ውድድር ብዙም ልምድ የለውም፡፡ ጃምሁሪ አምና በኮንፌደሬሽን ካፕ ለመጀመርያ ጊዜ የተሳተፈ ሲሆን በዛንዚባር ሊግ ሻምፒዮን ሆኖ የሚያውቀው አንዴ ብቻ ነው፡፡ የ2013 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ በታሪኩ ለ47ኛ ጊዜ በአዲስ የውድድር ስርዓት መካሄድ ከጀመረ ደግሞ ለ17ኛ ጊዜ የሚከናወን ነው፡፡ በዘንድሮው ውድድር ከ45 የእግር ኳስ ፌደሬሽኖች የተወከሉ 56 ክለቦች ይሳተፉበታል፡፡
ደደቢት በኮንፌደሬሽን ካፕ
ላይ ደደቢት በአፍሪካ የክለቦች ውድድር ካለው የአጭር ጊዜ ልምድ የተሻለ ታሪክ ለማስመዝገብ የሚያስችለውን የአሸናፊነት ስነልቦና መያዙን ወደ መካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ ሲጓዝ በተደረገለት ሽኝት እንደተገለፀ የሚታወስ ነው፡፡ በቅድመ ማጣርያው ከሜዳው ውጭ 4ለ0 በማሸነፍ የተመዘገበው ውጤት ይህን ያረጋገጠ ነበር፡፡ ደደቢት ከሁለት የውድድር ዘመን በፊት በኮንፌደሬሽን ካፕ ተሳታፊ ነበር፡፡በቅድመ ማጣርያው ከታንዛኒያው ያንግ አፍሪካንስ ጋር ተገናኝቶ በመጀመርያው ጨዋታ ከሜዳው ውጭ 4ለ4 ተለያይቶ በመመለስ በመልሱ ጨዋታ እዚህ አዲስ አበባ ላይ 2ለ0 አሸንፎ ጥሎ ማለፍ ችሏል፡፡ ከዚያይ በመጀምርያ ዙር ማጣርያ ከግብፁ ሃራስ ኤልሁዳድ ጋር ነበር የተገናኘው፡፡ በመጀመርያ ዙር ከሜዳው ውጭ በሃራስ ኤልሁዳድ 4ለ0 ተሸንፎ በመልሱ ጨዋታ አዲስ አበባ ላይ አንድ እኩል አቻ በመውጣት ከውድድሩ ተሰናብቷል፡፡
በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ የደደቢት ተጋጣሚ የሆነው የመካከለኛው አፍሪካ ክለብ አንጌስ ዴፋቲማ በአገሩ የሊግ ውድድር 5 ጊዜ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃ ሲሆን ስታድዬሙ በዋና ከተማው ባንጉዊ የሚገኝ ነው፡፡ በአፍሪካ ሻምፒዮን ክለቦች ውድድር 5 ጊዜ፤ በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ 2 ጊዜ፤ እንዲሁም በካፍ ኮንፌደሬሽን ካፕ 1 ጊዜ ተሳትፎ ከመጀመርያ ዙር አላለፈም፡፡ በታሪኩ ለ10ኛ ጊዜ በሚደረገው የ2013 የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ ከ41 ፌደሬሽኖች የተውጣጡ በአጠቃላይ 59 ክለቦችን ያሳትፋል፡፡
የሁለቱ ክለቦች አርዓያነት
ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት በኢትዮጵያ የክለብ እግር ኳስ በአርዓያነት ሊወሰድ የሚገባ አስተዳደርን ይከተላሉ፡፡ ሁለቱ ክለቦች ለዋና ቡድኖቻቸው መሰረት የሆኑ የቢ እና የሲ ቡድኖችን በመያዝ፤ ለተጨዋቾች ጠቀም ያለ የፊርማ ክፍያ በመስጠት እና ከፍተኛ ደሞዝ በመክፈል፤ ከተለያዩ የውጭ አገራት ተጨዋቾችን በመቅጠር፤ ስለክለባቸው የተሟላ መረጃ ማግኘት የሚቻልባቸውን ድረገፆች በማንቀሳቀስ፤ የሴት እግር ኳስ ክለቦችን በመዋቅራቸው በማካተት ይሰራሉ፡፡ ሁለቱም ክለቦች በዙርያቸው ድጋፍ ሰጭ ስፖንሰሮችን በማሰባሰብም ብዙ ርቀት ተጉዘዋል፡፡
ፈረሰኞቹ በሚል ቅፅል ስሙ የሚታወቀው ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሁለት ዓመት በፊት የተመሰረተበትን 75ኛ ዓመቱን ሲያከብር በኦፊሴላዊ ድረገፅ የክለቡ ፕሬዝዳንት አቶ አብነት ገብረመስቀል ባሰፈሩት መልእክት ክለባቸው ለኢትዮጵያ እግር ኳስ በሚጫወተው ፈርቀዳጅ ሚና እንደሚቀጥል ገልፀው ነበር፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ደጋፊዎቹን በአባልነት በመመዝገብ እና ባለድርሻ አካል እንዲሆኑ በማድረግ ፤ የውጭ አገር ተጨዋቾችን በመቅጠር እንዲሁም የውጭ አገር አሰልጣኝ በሃላፊነት በማሰራት ቅዱስ ጊዮርጊስ አርዓያ መሆኑን ፕሬዝዳንቱ በኩራት ይገልፃሉ፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ከ20 ዓመታት በፊት የራሱ ቢሮ እንዳልነበረው በመልእክታቸው የጠቀሱት አቶ አብነት አሁን ክለቡ የራሱን ስታድዬም በመገንባት ላይ እንደሚገኝ፤ የወጣቶች አካዳሚ ገንብቶ ስራ እንደጀመረ ገልፀው ክለቡን በአውሮፓ ሞዴል ለማስተዳደር በተቃና መንገድ እየሰራን ነው ብለዋል፡፡ የአርሰናል ክለብ እና የአሰልጣኝ አርሰን ቬንገር አድናቂ መሆናቸውን በዚሁ መልእክታቸው የገለፁት አቶ አብነት ክለባቸው ቅዱስ ጊዮርጊስ በሁሉም ረገድ እንደአርሰናል ቢሆን ፍላጎቴ ነው ይላሉ፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ የራሱን ስታድዬም በመገንባት የያዘው ጅምር ለሁሉም የኢትዮጵያ ክለቦች አርዓያነቱን ያጎላዋል፡፡ ክለቡ ለስታድዬም ግንባታው የሚኖረውን ወጭ 80 በመቶ ከክቡር ሼህ መሃመድ አላሙዲ ያገኛል፡፡ የክለቡን ደጋፊዎች ባለድርሻ አካል ያደረገውና የአባልነት መታወቂያ ይዘው ክለቡን በወርሃዊ መዋጮ እንዲደግፉ በማድረግ የተሳካለት የቅዱስ ጊዮርጊስ አስተዳደር ትልልቅ ኩባንያዎችን በስፖንሰርሺፕ አብረውት እንዲሰሩ በማድረግም አርዓያ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ የስፖንሰርሺፕ ድጋፉን ከቢጂአይ፤ ከዳሸን ባንክ እና ከፔፕሲ ኢትዮጵያም ይሰበስባል፡፡
በቅፅል ስሙ ሰማያዊው ጦር የሚባለው ደደቢት ከተመሰረተ 15 ዓመት ሲሆነው የእግር ኳስ ክለቡ ፕሬዝዳንት ኮለኔል አዎል አብድራሂም ናቸው፡፡ ‹‹ህልማችን እውን ይሆናል›› የሚለውን ያነገበው ክለቡ የልምምድ ሜዳውን በአበበ ቢቂላ ስታድዬም ያደረገ ሲሆን ሳርቤት አካባቢ በተሟላ የመዝናኛ አገልግሎት የሚሰጥበት የተጨዋቾች ካምፕን ይጠቀማል፡፡ የደደቢት እግር ኳስ ክለብ ስፖንሰሮችን በማስተባበር ይሰራል፡፡ ለክለቡ በመጀመርያ ደረጃ ስፖንሰርነት ድጋፍ የሚያደርገው የብረታብረት እና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ሲሆን፤ በ2ኛ ደረጃ ስፖንሰር የሚያደርገው ደግሞ የመከላከያ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ ነው፡፡ በ3ኛ ደረጃ ስፖንሰርነት የመከላከያ የኮንስትራክሽን ግብዓቶች ማምረቻ ኢንተርፕራይዝ እንዲሁም በ4ኛ ደረጃ ስፖንሰርነት የአርሚ ፋውንዴሽን ክለቡን እየደገፉ እንደሆነ ከድረገፁ የተገኘ መረጃ ይገልፃል፡፡ የክለቡ የማልያ ስፖንሰር ደግሞ ሳምሰንግ ነው፡፡