Administrator

Administrator

“ቦቃፍ ቡሬ” የተሰኘ አዲስ የኦሮምኛ ኮሜዲ ፊልም፣ የኪነጥበብ ባለሙያዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ባለፈው ሳምንት ሐምሌ 12፣ በኦሮምያ የባህል ማዕከል በተከናወነ ደማቅ ስነ-ስርዓት የተመረቀ ሲሆን በሲዲ ለሽያጭ እንደቀረበም ታውቋል፡፡
በታምራት አዳሙ ተጽፎ በታዴማ ሚዲያ ኤንድ ኢቨንት ኦርጋናይዘር ኤክስኪዩቲቭ ፕሮዲዩሰርነት እና በኢሉ ኮ ፕሮዳክሽን ተሰርቶ የቀረበውን #ቦቃፍ ቡሬ#፣ ዳይሬክት ያደረገው ራሱ ታምራት ሲሆን የአንድ ሰዓት ከ30 ደቂቃ ርዝማኔ አለው፡፡ሰርቶ ለማጠናቀቅ 7 ወር በፈጀው በዚህ ፊልም ላይ አንጋፋው ተዋናይ አድማሱ ብርሃኑና ኦሊ ነጋ በመሪ ተዋናይነት የተጫወቱበት ሲሆን ሌሎች ከ15 በላይ አንጋፋና ወጣት ተዋንያንም ተሳትፈውበታል ተብሏል፡፡

 በመስከረም አበራ የተፃፉ የተለያዩ ፖለቲካዊ መጣጥፎችን ያካትተው “ስለ ስልጣን” የተሰኘ አዲስ መፅሃፍ ሰሞኑን ታትሞ ለንባብ ቀረበ፡፡ መፅሃፉ በ7 ምዕራፎች የተከፋፈለ ሲሆን  “የብሄር ፖለቲካችን”፣ “የአቶ መለስ ትዝታዎች”፣ “ቅይጥ ፖለቲካዊ ጉዳዮች” እና ሌሎችም ርዕሶችን አካትቷል፡፡
በ230 ገፆች የተቀነበበው “ስለ ስልጣን”፤ በ57 ብር ከ65 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡
ፀሃፊዋ በተለያዩ የፕሬስ ውጤቶች ላይ ፖለቲካዊ መጣጥፎችን በማቅረብ ትታወቃለች፡፡

Monday, 27 July 2015 11:15

የኪነጥበብ ጥግ

(ስለ ኮሜዲ)
እኔ ጣቴን ስቆርጥ ትራጄዲ ነው፡፡ አንተ ክፍት ቱቦ ውስጥ ገብተህ ስትሞት ኮሜዲ ነው፡፡
ሜል ብሩክስ
ህይወት፡- ለብልሆች… ህልም፣
       ለሞኞች… ጨዋታ፣
       ለሃብታሞች … ኮሜዲ፣
       ለድሆች … ትራጀዲ ነው፡፡
                    ሻሎም አሌይቼም
የኮሜዲ ሥራ ሰዎችን እያዝናኑ ከጥፋታቸው ማረም ነው፡፡
ሞሌር
ኮሜዲበ ሌሎች ሰዎች ላይ የሚከሰት ትራጄዲ ነው፡፡
አንጄላ ካርተር
ሳቅንና ስቃይን፣ ኮሜዲንና ትራጄዲን፣ ጨዋታንና ጉዳትን የሚለይ ቀጭን መስመር አለ፡፡
ኢርማ ቦምቤክ
ህይወት በቅርት ሲታይ ትራጀዲ፣ በርቀት ሲታይ ኮሜዲ ነው፡፡
ቻርሊ ቻፕሊን
የኮሜዲ ትርኢት ላይ የምትመጡት ለመዝናናት ነው፡፡
ቢል ኮስቢ
የራስን ዝምታ ማዳመጥ የኮሜዲ ቁልፍ ነው።
ኢላይኔ ቡስለር
ኮሜዲ ለሰው ልጅ ብቸኛ ተስፋ ነው፡፡
ሮዝአኔ ባር
ነፃ ትግል ለእኔ እንደ ስታንድ አፕ ኮሜዲ ነበር፡፡
ዲዋይኔ ጆንሰን
እውነተኛ ኮሜዲ ሰዎች እንዲስቁና እንዲያስቡ ብቻ ሳይሆን እንዲስቁና እንዲለወጡም ያደርጋል፡፡
ሳም ኪኒሶን
ኮሜዲ የሚመነጨው ከውዥንብር ነው፡፡
ቪር ዳስ
ኮሌጅ በመሄድ ፋንታ ኮሜዲ መስራትን መረጥኩ፡፡
ቦ ቡርንሃም

    ክብደትን መቀነስ የልብ በሽታን ለማስወገድ ትክክለኛውመንገድ ነው፡፡ ከፍተኛ የሰውነት ክብደት የደም ቅዳ ሴሎቻችን እንዲጠቡ ያደርጋቸዋል፡፡ በዚህ ሳቢያም የኮሌስትሮል ዝቃጮች እንዲሰበሰቡና እጢ እንዲፈጠር ያደርጋል፡፡ ይህ ደግሞ አደገኛ የልብ ህመም እንዲከሰትብዎ ምክንያት ይሆናል፡፡ ክብደትዎን በመቀነስ በተለይም የሆድ አካባቢ ቦርጭዎን በማጥፋት የደም ቅዳ ሴሎች ሥራቸውን በአግባቡ እንዲያከናውኑ ይርዱዋቸው፡፡

         የምግብዎን ዓይነት እና መጠን ያስተካክሉ

    ለመልካም ጤንነት ከሚመከረው የምግብ ዓይነትና መጠን በላይ መመገብ ለከፍተኛ የሰውነት ክብደትና የኮሌስትሮል መጠን ያጋልጣል፡፡ የሚመገቡት ምግብ በዓይነቱና በመጠኑ የተስተካከለ እንዲሆን ያድርጉ፡፡ ከየዕለታዊ  የምግብ ገበታዎ ላይ አትክልትና ፍራፍሬዎች መኖራቸውን ያረጋግጡ፡፡ ገበታዎ የተመጠነ እንዲሆንም ያድርጉ፡፡
ጭንቀትዎን ያስወግዱ
ከፍተኛ ጭንቀት የደም ግፊት ይጨምራል፡፡ በደም ቅዳዎች ውስጥ እጢ እንዲፈጠር የሚያደርጉ ነገሮችንም ያባብሳል፡፡ ይህም ለልብ በሽታ ያጋልጣል፡፡ ከልብ በሽታ ለመጠበቅ ከፈለጉ ጭንቀትና ውጥረትን ያስወግዱ፡፡
ያልተፈተጉ/ ገለባቸው ያልተለየ/ እህሎችን ለምግብነት ይምረጡ
ገለባው ያልተነሳላቸውት (ያልተፈተጉ/እህሎች ጥሩ የአሰርና የሌሎች አልሚ ምግቦች ምንጮች ናቸው፡፡
    እንደ ቫይታሚን ኢ፣ ታያሚን፣ ሪቦፍላቪንና ናያሊን ያሉ ቫይታሚኖች እንዲሁም ማግኒዚየም፣ ፎስፈረስ፣ ዚንክና ብረት መሰል ማዕድናት የሚገኙት ባልተፈተጉ እህሎች ውስጥ ነው፡፡ ባልተፈተጉ እህሎች ውስጥ የሚገኙት ቫይታሚኖችና ማዕድናት፣ የደም ግፊትንና የልብ ጤንነትን በመቆጣጠሩ ረገድ የሚጫወቱት ሚና ከፍተኛ ነው፡፡ ከእነዚህ መካከል ለምሳሌ ለመጥቀስ ያህል ካልተፈተገ ገብስ ወይም ስንዴ የተሰሩ ዳቦዎች፣ ቡናማ ሩዝ፣ ካልተፈተገ በቆሎ የሚሰሩ ምግቦች ተጠቃሽ ናቸው፡፡
አነስተኛ የስብ መጠን ያላቸውን የፕሮቲን ምንጮች ይምረጡ
ቀይ ሥጋ፣ ዶሮና ዓሳ አነስተኛ የስብ መጠን ያላቸው የፕሮቲን ምንጮች ናቸው፡፡ የእንቁላል ነጩ ክፍል፣ የወተት ተዋፅኦዎችም ከአነስተኛ የስብ መጠን ውስጥ የሚመደቡ ናቸው፡፡ ዓሣ አነስተኛ የስብ መጠን ያለው የፕሮቲን ምንጭ ነው፡፡ የተወሰኑ የዓሣ ዓይነቶች ደግሞ የደም ውስጥ ስቦችን በመቀነስ በድንገተኛ የልብ ህመም የመሞት አደጋን በሚቀንሱትና ኦሜጋ 3 ፋቲ አሲድ ተብለው በሚታወቁ ማዕድናት የበለፀጉ ናቸው፡፡ ሌሎች ኦሜጋ 3 ፋቲ አሲዶች ምንጮች አኩሪ አተርና ተልባ ናቸው፡፡
በምግብ ውስጥ የሚኖረውን የጨው መጠን ይቀንሱ
ብዙ ጨው መመገብ ለከፍተኛ የደም ግፊት አስተዋፅኦ በማድረግ ለስርዓተ ልብ መዛባት ችግር ያጋልጣል፡፡ በምግባችን ውስጥ የሚገኘውን ጨው መቀነስ ጤናማ ልብ እንዲኖረን ከሚረዳን የአመጋገብ ሥርዓት ውስጥ ዋንኛው ነው፡፡ አንድ ጤናማ ሰው በቀን ውስጥ መውሰድ የሚኖርበት የጨው መጠን ከአንድ የሻይ ማንኪያ መብለጥ የለበትም፡፡
ኦቾሎኒ ለልብ ጤንነት
እንደ መክሰስ ያለ ነገር ካማረዎ፣ ኮሌስትሮል በመቀነስ የታወቀውን ኦቾሎኒ ይጠቀሙ፡፡
ኦቾሎኒ ጉዳት በማያስከትሉ ስቦች የተሞላና ጎጂ ስቦችን ከሰውታችን በማስወገድ የሚታወቅ ምግብ ነው፡፡     በርካታ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት፤ በየዕለቱ ጥቂት ኦቾሎኒን የሚመገቡ ሰዎች ከልብ በሽታ የመያዝ ዕድላቸው በእጅጉ ቀንሶ ተገኝቷል፡፡ ኦቾሎኒ በከፍተኛ ስብና ካሎሪ የተሞላ ስለሆነ በአንድ ጊዜ ከአንድ እፍኝ  በላይ አይጠቀሙ፡፡ በስኳር ወይም በቸኮሌት ጣፍጠው ከተዘጋጁ ኦቾሎኒዎች ይጠበቁ፡፡
የአካል እንቅስቃሴ ያድርጉ
በሳምንት ለ5 ቀናት በቀን ለ30 ደቂቃ ያህል ቀለል ያሉ የአካል እንቅስቃሴዎችን ያድርጉ፡፡ እንደ ኤሮቢክስ ያሉ ወይንም የልብን ጡንቻዎች ለማሰራት ይጠቅማሉ እንደሚባሉት የእግር ጉዞ አይነት እንቅስቃሴዎች በልብ ድካምና በሌሎች የልብ በሽታዎች የመጠቃት ዕድልን ይቀንሳሉ፡፡ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች በበዙ ቁጥር ጠቀሜታቸውም በዚያው ልክ እየጨመረ ይሄዳልና፣ በየዕለቱ አካላዊ እንቅስቃሴ ያድርጉ፡፡

  የታይፎይድ አምጪ ባክቴሪያ የሚከሰተው በሰው ላይ ብቻ ነው
            ለበሽታው የሚታዘዙ አብዛኛዎቹ መድኀኒቶች ከበሽታው ጋር ተላምደዋል
    አብዛኛውን ጊዜ በተበከለ ምግብና ውሃ ሳቢያ ከሰው ወደ ሰው የሚተላለፈውና በተለምዶ የአንጀት ተስቦ እየተባለ የሚጠራው ታይፎይድ መነሻው “ሳልሞኔላ ታይፊ” የሚባል ባክቴሪያ ነው፡፡ ይህ ባክቴሪያ የሚኖረው (ህይወት የሚያገኘው) በሰው ልጅ አንጀት ውስጥ ብቻ ነው፡፡
በሽታው በሽታ አምጪ በሆነው ባክቴሪያ በተበከለ ምግብና መጠጥ አማካኝነት በወረርሽኝ መልክ ሊከሰት ይችላል፡፡
በበሽታው የተያዘ ሰው በጥቂት ቀናት ውስጥ ምልክቶችን ማሳየት ይጀምራል፡፡ ከበሽታው ምልክቶች መካከል ትኩሳት ዋንኛው ሲሆን ራስ ምታት፣ ሰውነትን የመቀረጣጠፍና መገጣጠሚያ አካባቢ የሚኖር የህመም ስሜት ከምልክቶቹ መካከል የሚጠቀሱ ናቸነው፡፡
እ.ኤ.አ በ1862 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩትን 16ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት አብርሃም ሊንከን ለሞት ማብቃቱ የሚነገርለት ታይፎይድ አሁንም በዓለማችን በየዓመቱ ከ220 ሺህ በላይ ሰዎችን ለሞት እየዳረገ ይገኛል፡፡
ከጥቂት የሰሜን አፍሪካ አገራትና ከደቡብ አፍሪካ በስተቀር በመላው የአፍሪካ አገራት በስፋት መኖሩ የሚነገረው የታይፎይድ በሽታ በተለይ የሃሞት ከረጢት እና እጢ ያለባቸው ሰዎች በይበልጥ ያጠቃል፡፡ ባክቴሪያው ከአንጀት ውስጥ በደም ተሸካሚነት ወደ ሃሞት ከረጢት ሊሄድና በዚያ ተደብቆ ህመምተኛውን ሊያጠቃና በሰገራ አማካኝነት ወደሌሎች ሰዎች ሊተላለፍ ይችላል፡፡
ሳልሞኔላ ታይፊ በሚባል ባክቴሪያ ሳቢያ የሚከሰተውን ይህንኑ የታይፎይድ በሽታ ለማከም ጥቅም ላይ የሚውሉት መድኀኒቶች በአብዛኛው ከበሽታው ጋር የመላመድ ባህርይን አምጥተዋል፡፡
ቀደም ሲል በጥቅም ላይ ይውሉ የነበሩና የታይፎይድ በሽታን ለማከም ያገለግሉ ከነበሩ መድኀኒቶች መካከል አሞክሳሲሊን፣ ክሎሞፌኒከልና፣ ስትሬፕቶማይሰን የተባሉት መድኀኒቶች ሙሉ በሙሉ ከበሽታው ጋር በመላመዳቸውና የሚያስከትሉት የጎንዮሽ ጉዳቶችም እየጨመሩ በመምጣታቸው ከአገልግሎት ውጪ እንዲሆኑ እየተደረጉ ነው፡፡
 በአሁኑ ወቅት አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኘው ሲፕ ሮፋሎክሳሲን የተባለው መድኀኒት ነው፡፡
በሽታው በወቅቱ ህክምና ካላገኘ ለሞት ሊዳርግ የሚችልና በቀላሉ ከሰው ወደሰው በተበከለ ምግብና መጠጥ ሳቢያ ሊተላለፍ የሚል በሽታ ነው፡፡
 በተለይ እንዲህ ክረምት በሚሆንባቸው ወቅቶች ለመጠጥነት የምንጠቀመውን ውሃና የምንመገበውን ምግብ በጥንቃቄ መያዙ በታይፎይድ ከመያዝ እንደሚታደገን ባለሙያዎች ይመክራሉ፡፡

ሳምሰንግ ኤሌክትሮኒክስ ለምርቶቹ የጥገና አገልግሎት የሚሰጥበት የደንበኞች አገልግሎት ማዕከል በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ከፈተ፡፡
ለሳምሰንግ ሞባይልና ለሁሉም የሳምሰንግ ኤሌክትሮኒክ ምርቶች የጥገና አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል የተባለውንና በአዲስ አበባ ከተማ ቴሌ መድኀኒዓለም አካባቢ የተቋቋመውን የደንበኞች አገልግሎት ማዕከል ከትናንት በስቲያ መርቀው የከፈቱት የኩባንያው የኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጅ አቶ ታዲዮስ አወል ናቸው፡፡ ማዕከሉ ከጥገና በተጨማሪ (Software upgrades, application installation, new devises setup) አገልግሎቶችን ይሰጣል፡፡ አጠቃላይ የማማከር አገልገሎትም ለደንበኞቹ እንደሚሰጥ አቶ ታዲዮስ ተናግረዋል፡፡
ማዕከሉ የዋስትና ፈቃድ ላላቸውም ሆነ ለሌላቸው የሳምሰንግ ምርቶች አገልግሎቱን እንደሚሰጥ የጠቆሙት አቶ ታዲዮስ፤ ደንበኞች ጥራት ባላቸው የመለዋወጫ ዕቃዎች በሙያው በተካኑ ባለሙያዎች የህግና ሌሎች አገልግሎቶችን በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲያገኙ እንደሚደረግ ገልፀዋል፡፡
 እንደፍሪጅ እና የልብስ ማጠቢያ ማሽን ላሉና የትራንስፖርት ወጪን ለሚጠይቁ የሳምሰንግ ምርቶች የማዕከሉ የጥገና ባለሙያዎች ቤት ለቤት በመሄድ አገልግሎቱን እንደሚሰጡና ይህንንም አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተገልጿል፡፡

 አስደማሚ … አስገራሚ … አስደናቂ እውነታዎች!?
          የኬንያው ጠንቋይ፤ “ኦባማ የአባቱን አገር ይጎበኛል” ሲል ተነበየ
             “የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ይሆናሉ ብሎ ተንብዮ ነበር” (USA Today)
   ባራክ ኦባማ በፕሮግራም መጣበብ የተነሳ በኬንያ ቆይታቸው የአባታቸውን የትውልድ ሥፍራ (ኮጌሎ) ለመጎብኘት እንደማይችሉ እየተነገረ ቢሆንም ዕውቅ አንድ የኬንያ ጠንቋይ ፕሬዚዳንቱ የአያት ቅድመ አያቶቻቸውን አገር ይጎበኛሉ ሲል ሰሞኑን ተንብየዋል፡፡
ጆን ዲሞ የተባለው የኮጌሎ ጠንቋይ፤ ኦባማ በእርግጠኝነት የአባታቸውን የትውልድ ቀዬ እንደሚጎበኙ ታይቶኛል ብሏል፡፡ ኦባማ እስካሁን ኮጌሎን እንደሚጎበኙ ማረጋገጫ ባይሰጡም የመንደሩ ነዋሪዎች ግን አሁንም በተስፋ እየጠበቁ ነው፡፡ ስለዚህም ምናልባት ከመጡ በሚል ዝግጅታቸውን ቀጥለዋል፡፡
“እመኑኝ … ኦባማ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ይሆናል ብዬ ነበር፤ ሆነ፡፡ አሁንም የወላጆቹን የትውልድ ቀዬ የመጎብኘት ዕቅድ እንዳለው ታይቶኛል፡፡ ይመጣል፡፡” ሲል ተንብየዋል ዲሞ፡፡ ጆን ዲሞ እ.ኤ.አ በ2006 ዓ.ም ኦባማ ፕሬዚዳንት ይሆናሉ ብሎ መተንበዩን “ዩኤስኤ ቱዴይ” አስታውሷል፡፡ “ውጤቱ ኦባማ ኮጌሎ እንደሚመጣ ነው የሚጠቁመው፡፡ ይሄ ትልቅ ምስጢር ነው፡፡ የቅድመ አያቱን አገር እንደሚጎበኝ ለማንም መንገር የለበትም!” በማለት ጠንቋዩ በጉጉት ለተሞሉት የመንደሯ ነዋሪዎች ተናግሯል፡፡ ኦባማ በትላንትናው ዕለት ኬንያ የገቡ ሲሆን የሦስት ቀናት ጉብኝት ያደርጋሉ፡፡ በምዕራባዊ ኬንያ የሚገኘው የኮጌሎ መንደር፤ የአያቱ የሳራ ኦባማ የትውልድ ሥፍራ ሲሆን የአባቱ የባራክ ኦባማ (ሰር) የቀብር ስፍራም ያለው እዚያው ነው፡፡
           

  የዛሬ 8 ዓመት ኦባማ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሆነው መመረጣቸውን ተከትሎ በመላው ዓለም ዝናቸው በእጅጉ ናኝቶ ነበር፡፡ ለዚህም ይመስላል ከኬንያ የአባታቸው የትውልድ መንደር አንስቶ እስከ አየርላንድ ገጠር ድረስ ስማቸው ታዋቂ የሆነው፡፡ በተለይ በኬንያ በእሳቸውም ስም ያልተሰየመ ነገር ያለ አይመስልም፡፡ የአንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች፣ ኪዮስኮች፣ መደብሮች… ኧረ ህፃናትም አልቀሩ፡፡ ሁሉም የባራክ ኦባማን ስም የታደሉ ይመስላሉ፡፡ አንዳንድ በኦባማ ስም የተሰየሙ ነገሮች ደግሞ አግራሞትን የሚፈጥሩ ናቸው፡፡ ራሷ ኬንያ ኦባማ መባል ነው የቀራት፡፡ እስቲ Tuko.co.ke የተሰኘው ድረ-ገፅ በኦባማ ስም የተሰየሙ ነገሮችን በተመለከተ ያወጣቸውን መረጃዎች እናስቃኛችሁ፡፡

                “ኦባማ ተራራ”

   አንቲጓ የተባለችው የኬንያ ግዛት በኦባማ ስም የሚሰየም ትንሽ ነገር ያጣች ትመስላለች፡፡ በግዛቱ ያለ አንድ ትልቅ ተራራ በፕሬዚዳንቱ ስም ተሰይሟል፡፡ “ኦባማ ተራራ” ይባላል፡፡ “ቦZ ፒክ” በአንቲጓ በጣም ረዥሙ ተራራ ሲሆን ኦባማ የሚለው ስም የተሰጠው እ.ኤ.አ በ2009 በፕሬዚዳንቱ የልደት ቀን ነበር ተብሏል፡፡

            “ኦባማ ሹሩባ”

     ኦባማ ፀጉራቸውን ሹሩባ ተሰርተው ባያውቁም በአያቶቻቸው መንደር በኮጌሎ ግን አንድ የሹሩባ አሰራር በሳቸው ስም ተሰይሟል - “ኦባማ ሹሩባ” ተብሎ፡፡ አንዳንዶች “የወንዶች የፀጉር አቆራረጥ እንኳን ቢሆን ምንም አልነበር፤ ክፋቱ ግን ይሄ የፀጉር አሰራር ስታይል ያለው በሴቶች የውበት ሳሎን ነው…” ሲሉ ቅሬታቸውን ይገልፃሉ፡፡ የሰማቸው ወይም የሚሰማቸው ግን ያለ አይመስልም፡፡ በነገራችን ላይ በመዲናችን በሚገኙ የወንዶች ፀጉር ሴቶች የኦባማን ምስል (ፖስተር) በተለያዩ የፀጉር አቆራረጥ ስታይሎች ማየት የተለመደ ነው፡፡

             የአይሪሾቹ አልባሰም?! (“ኦባማ ነዳጅ ማደያ”)

      የኬንያውያን እንኳ እሺ… ምክንያት አላቸው፡፡ የአገራችን ልጅ ነው ቢሉ ያምርባቸዋል፡፡
የሚያስገርሙት አይሪሾች ናቸው፡፡ ድንገት ተነስተው እኮ ነው የኦባማን ስም የሙጥኝ ያሉት፡፡
ያውም በአየርላንድ እልም ያለ ገጠር መሃል፡፡ በዱብሊን እና ሊመሪክ መሃል ኦፋሊ ውስጥ የሚገኘው የነዳጅ ማደያ አሁን በይፋ በአሜሪካ ፕሬዚዳንት ስም ተሰይሟል፡፡ “ኦባማ ነዳጅ ማደያ” ነው የሚባለው፡፡ ይሄን እንኳን ራሳቸው ኦባማም የሚያውቁት አይመስለኝም፡፡

               የዬል ዩኒቨርሲቲ ሳይንቲስቶችስ?

   በአሜሪካ የሚገኘው የዬል ዩኒቨርሲቲ ሳይንቲስቶች ደግሞ ምን እንዳሰቡ አይታወቅም፡፡ ከምድረገፅ ጠፍቷል የሚባል ፍጡር በስማቸው ሰይመዋል ተብሏል፡፡ “ኦባማዶን” በዓለም ረዥሙ (አንድ ጫማ ርዝመት አለው) እንሽላሊት ሲሆን እንደ በቆሎ የተደረደሩ ጥርሶች እንዳሉት ሳይንቲስቶቹ ገልፀዋል፡፡ ለዚህ ተሳቢ ፍጥረት ስሙን ያወጡለት ሳይንቲስቶች እ.ኤ.አ በ2012 የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፣ ኦባማ ማሸነፋቸው በይፋ እስኪነገር ድረስ ዝም ብለው ሲጠብቁ ነበር፡፡ ለምን ቢባል… ድንገት ኦባማ ቢሸነፉ እንደ እንሽላሊቱ “ከምድረ ገፅ የጠፉ” የሚል በአግቦ ወይም በሾርኒ የተነገረ ስድብ እንዳይመስልባቸው ስለፈሩ ነበር፡፡

            አሁንስ አበዙት ያሰኛል!
    ይሄኛውስ ደስ አይልም፡፡ ኬንያውያን መካሪ የላቸውም እንዴ? ያሰኛል፡፡ የፀጉር ትሎች የተገኙት የኦባማ አባት የትውልድ ስፍራ በሆነችው ኮጌሎ መሆኑን የጠቆመው Tuko.co.ke የተሰኘው ድረ-ገፅ፤ እንደተለመደው አዲስ የተገኘው ትል በፕሬዚዳንቱ ስም ተሰየመ ይለናል፡፡ ለአሜሪካው መሪ ክብር ሲባልም የትሉ ሳይንሳዊ ስም “Paragordius Obamai” ተብሏል፡፡ ግን አይገርምም… የኦባማ ስም?! (ለአፍ ስለሚመች ይሆን?)   

 የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ከሆኑ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የአባታቸውን የትውልድ አገር ኬንያን በመጐብኘት ላይ የሚገኙት ባራክ ኦባማ፤ ትላንት Air Force One በተሰኘው ልዩ አውሮፕላናቸውን ኬንያ ገብተዋል፡፡
ከዋይት ሃውስ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ Air Force One የአውሮፕላን ስም አይደለም፡፡ የአሜሪካ ፕሬዚዳንትን የሚጭን ማንኛውም የአሜሪካ አየር ሃይል አውሮፕላን በዚህ ስም ነው የሚጠራው፡፡
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት በወታደራዊ አውሮፕላን  ላይ ከተሳፈሩ “Army One” ተብሎ ይጠራል፡፡ በልዩ ሄሊኮፕተራቸው ላይ ከተሳፈሩ ደግሞ አውሮፕላኑ “Marine one” ይባላል፡፡
ፕሬዚዳንቱ Air Force One በሚል ስያሜ የሚበሩ በልዩ ትእዛዝ የተሰሩ 2 ቦይንግ 747 ጀቶች ያሏቸው ሲሆን እኒህ ጀቶች የባለ 6 ፎቅ ህንፃ ከፍታ አላቸው ተብሏል፡፡
“Air Force One” በከፍተኛ ፍጥነት ሲበር በሰዓት 1ሺ 126 ኪ.ሜ ገደማ መጓዝ የሚችል ሲሆን አውሮፕላኑ በ45ሺ 100 ጫማ ከፍታ ላይ ነው የሚበረው፡፡ ተመሳሳይ የተጓዦች ቦይንግ 747 አውሮፕላን የሚበረው በ30ሺ ጫማ ገደማ ከፍታ ላይ ነው፡፡
አውሮፕላኑ አንዴ ነዳጅ ጢም ተደርጐ ከተሞላ (Full tank) የዓለምን አጋማሽ ማካለል የሚችል ሲሆን ዳግም ለመሙላት መሬት ላይ ማረፍ አያስፈልገውም፡፡ በአጋማሽ አየር ላይ ሆኖ ነዳጅ የመሙላት አቅም አለው፡፡ ከዚያም ይሄ ነው ለማይባል ጊዜ በአየር ላይ ሊቆይ ይችላል፡፡
የፕሬዚዳንቱ አውሮፕላን የአየር ጥቃት መቋቋም ይችላል፡፡ የእሳት ብልጭታ በመርጨት ሚሳየሎችን ከዒላማቸው ውጭ ከማድረጉም በተጨማሪ የጠላት ራዳርንም አገልግሎት አልባ ያደርጋል፡፡ ሌሎችም ለደህንነት ሲባል በምስጢር የተያዙ ገፅታዎች እንዳሉት ታውቋል፡
ግዙፉ የፕሬዚዳንቱ የአየር ላይ ቢሮ በሚል የሚታወቀው Air Force One  ለሰራተኞች፣ ለኃላፊዎችና ለእንግዶች የመኖሪያ ክፍሎች አሉት፡፡
በአውሮፕላኑ ውስጥ እጅግ ከሚያስደንቁ ገፅታዎች መካከል ብዛት ያላቸው የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎች ይጠቀሳሉ፡፡ አውሮፕላኑ ፕሬዚዳንቱንና ሰራተኞቹን በአየር ላይ ሆነው ከመላው ዓለም ጋር መገናኘት የሚያስችላቸው አስተማማኝ የስልክ መስመር ያለው ነው፡፡ ከተለያዩ የቢሮ እቃዎች በተጨማሪም 85 ስልኮች፣ 19 ቴሌቪዥኖች፣ ፋክስ ማሽኖችና ሬዲዮኖች ተገጥሞለታል፡፡
የፕሬዚዳንቱ አውሮፕላን 96 ተጓዦችና የበረራ ሰራተኞችን የመጫን አቅም አለው፡፡

                ለኦባማ በወንድና በሴት መካከል ያለውን ልዩነት እናሳያለን ይላሉ
  የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በስልጣን ዘመናቸው 11ኛ ሰዓት ላይ የፈቀዱት የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻ በአገራቸው ተቃውሞ አላስነሳባቸውም ይሆናል፡፡ በአባታቸው አገር ኬንያ ግን ተዝቶባቸው ነበር፡፡ ኦባማ በኬንያው ጉብኝታቸው የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻ መብትን የተመለከተ ጉዳይ እንዳያነሱ የሪፐብሊካን ሊበርቲ ፓርቲ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ ድጋፍ ሲያሰባስብ ነው የሰነበተው፡፡
የፓርቲው መሪ ቪንሰንት ኪዳላ፤ 1ሺ እርቃን ሴቶችና 4ሺ እርቃን ወንዶች በተቃውሞ ሰልፉ እንደሚሳተፉ አስታውቀው ነበር፡፡ በኦባማ የኬንያ ጉብኝት ዋዜማ ላይ ሊካሄድ ታቅዶ የነበረው የተቃውሞ ሰልፍ፤ ለፕሬዚዳንቱ የወንድና የሴትን ልዩነት ለማሳየት ያለመ ነበር ተብሏል፡፡በመጨረሻው ሰዓት ላይ ግን የእርቃን ተቃውሞው ለጊዜው መሰረዙን የሰልፉ አደራጅ አስታውቋል፡፡ የሪፐብሊካን ሊበርቲ ፓርቲ መሪ ቪንሰንት ኪዳላ፤ ከመንግሥት ቢሮ ስልክ ተደውሎ የእርቃን ተቃውሞ ሰልፉን እንዲሰርዙ መገደዳቸውን ተናግረዋል፡፡
“ስልክ ደዋዩ፤ የኬንያው ፕሬዚዳንት ዩሁሩ ኬንያታ ከባራክ ኦባማ ጋር በግብረ ሰዶማውያን መብት ዙሪያ ለመወያየት እንዳላቀዱና የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻን እንደማይደግፉ ገልጾልኛል” ሲሉ የፓርቲው መሪ ሚዲያ ተናግረዋል፡፡ከብሄራዊ ደህንነት ኮሚቴም ስልክ ተደውሎ፣ የተቃውሞ ሰልፉ እንዳይደረግ ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው ኪዳላ ገልፀዋል፡፡ ማንነቱን ያልገለፀው ደዋይ፤ “የተቃውሞ ሰልፉን ማድረግ የሽብር ጥቃት ከመፈፀም እኩል ነው” ብሎኛል ሲሉ የፓርቲው መሪ አስረድተዋል፡፡
የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻን በመቃወም ሊካሄድ ታስቦ የነበረው ሰልፍ ለጊዜው ይሰረዝ እንጂ ከእነአካቴው እንደማይቀር አዘጋጆቹ አስታውቀዋል፡፡ ፓርቲው በሰጠው መግለጫም፤ ሰልፉ ለሌላ ጊዜ ተላልፏል ነው ያለው፡፡ ጊዜውን ግን አልገለፀም፡፡ ለማንኛውም ኦቦማ አምልጠዋል!!