Administrator

Administrator

        የቴሌኮም መሰረተ ልማት አቅራቢው ዜድቲኢ ኩባንያ፤ በኢትዮጵያ በሁለት አይነት መስኮች ተሰማርቷል፡፡ ሞባይል ስልኮች አምርቶ ያቀርባል። በሌላ በኩል የኔትወርክ ዝርጋታ ያከናውናል። በአሜሪካ ገበያ በስማርት ስልኮች የገበያ ድርሻ ኩባንያው በሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡  በአውሮፓና በእስያም ቢሆን ድርሻው ሰፊ ነው፡፡ በአፍሪካ በተለይ በኢትዮጵያ ኩባንያው በስማርት ስልኮች ያለውን የገበያ ድርሻ እያሰፋ ሲሆን ከ6 ያላነሱ የተለያዩ ሞዴል ስማርት ስልኮችን ወደ ገበያ አስገብቷል፡፡
አላማችን በኢትዮጵያ እያደገ ለመጣው የስማርት ስልኮች ፍላጎት ጥራት ያላቸውን ስልኮች በተመጣጣኝ ዋጋ ማቅረብ ነው የሚሉት የኩባንያው ተርሚናል ቢዝነስ ማኔጂንግ ዳይሬክተር  ሣም ዊ፤ ኩባንያው በሀገሪቱ በኔትወርክ ዝርጋታ ውስጥ እየተሳተፈ በመሆኑ ስማርት ስልኮቹ በኔትወርክ አይታሙም፤ ከፍተኛ የኔትወርክ ጥራት አላቸው ይላሉ፡፡ ዜድቲኢ በኢትዮጵያ የስማርት ስልኮች ፋብሪካ ለማቋቋም በሂደት ላይ እንደሆነም ተገልጿል፡፡
አብዛኛው ሰው ዜድቲኢን ከዚህ ቀደም የሚያውቀው የCDMA፣ 1x ከመሳሰሉ ቴክኖሎጂዎች ጋር በተገናኘ ሲሆን በስማርት ስልኮች ግን እምብዛም የተሰማራ አልነበረም፡፡ ጥራት ያላቸውን የዜድቲኢ ምርቶች ኢትዮጵያውያን ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማሰብ፣ ኩባንያው የስማርት ስልክ ዘመናዊ ምርቶቹን ወደ ኢትዮጵያ አስገብቷል፤ እንደ ዳይሬክተሩ ገለፃ፡፡
በአትሌቲክስ የበርካታ ሪከርዶች ባለቤት የሆነው አትሌት ኃይሌ ገ/ሥላሴ ደግሞ እነዚህን የኩባንያውን ምርቶች በማስተዋወቅ የዜድቲኢ አምባሳደር ሆኖ እየሰራ ነው፡፡ ኃይሌ ምርቶቹን ተጠቅሞባቸው ጥራታቸውን በሙከራ ካረጋገጠ በኋላ አምባሳደር እንደሆነ የጠቀሱት ሚ/ር ሣም፤ ኩባንያው ይሄን ያደረገው በምርቶቹ ጥራት ስለሚተማመን ነው ይላሉ፡፡ በተለይ ምርቶቹ በኔትወርክ በኩል ያላቸው ጥራት በገበያ ውስጥ ከፍተኛ ተቀባይነት እንዲያገኙ አድርጓል የሚሉት ሚ/ር ሣም ሁሉም ምርቶች በአማራጭነታቸውም ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። ምርቶቹ ከፋብሪካ ከመውጣታቸው በፊት ጥብቅ ፍተሻና ሙከራ ተደርጎባቸው ጥራታቸው እንደሚረጋገጥም ገልፀዋል፡፡
ዲዛይናቸው ለአያያዝና ለእይታ እንዲያመቹና ማራኪ እንዲሆኑ ተደርገው የተዘጋጁ ሲሆን የውስጥ ጥራታቸውም አስተማማኝ ነው ይላሉ ዳይሬክተሩ። Grands 52 የተሰኘ ሰፊ ስክሪን ያለው የ4ጂ ተቀባይ ስልክ የኢትዮጵያን  ገበያ ከተቀላቀሉት ስማርት ፎኖች መካከል የሚጠቀስ ሲሆን ምርቶቹ ተቀባይነት እያገኙ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡
ዜዲቲኢ በአሁን ወቅት አዳዲስ ምርቶቹን በኢትዮጵያ ገበያ በሰፊው እያስተዋወቀ ሲሆን አትሌት ኃይሌ የምርቶቹ አምባሳደር ሆኖ መስራቱ ውጤታማ እያደረገው መሆኑንም ዳይሬክተሩ ገልፀዋል፡፡ ጥራት ያለው ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ የማቅረብ እቅድ ያለው ኩባንያው፤ ከሁለት ኢትዮጵያውያን አንዱ የዜድቲ ምርት ተጠቃሚ እንዲሆን ጠንክሮ ይሰራል ያሉት ሚ/ር ሣም፤ በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች የመሸጫ መደብሮችን ለመክፈት እቅድ እንዳለውም ጠቁመዋል፡፡
በቀጣይ በኢትዮጵያ የሚቋቋመው የስማርት ፎኖች መገጣጠሚያ ፋብሪካ ለኢትዮጵያውያን የስራ እድል ከመፍጠሩ ባሻገር በኢትዮጵያና በተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ምርቶቹን የሚያቀርብበትን እድል ለኩባንያው ይፈጥርለታል ተብሏል፡፡
ኩባንያው ከቢዝነስ ጐን ለጐን በኢትዮጵያ የተለያዩ ማህበራዊ ተሳትፎዎች ላይም የተሰማራ ሲሆን በቅርቡ የተከናወነውን “ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ”ን የወርቅ ደረጃ ስፖንሰር ሆኗል፡፡ በወጣቶች ስፖርት አካዳሚ የተዘጋጀውን የስፖርት ኤክስፖም በዳይመንድ ደረጃ ስፖንሰር አድርጓል። ኩባንያው በቀጣይ በኢትዮጵያ ጥራት ያለው ኔትወርክ ከመዘርጋት ባሻገር  ደረጃቸውን የጠበቁ እጅግ ዘመናዊ ስማርት ፎኖችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ፣ ከሁለት ኢትዮጵያውያን የሞባይል ተጠቃሚዎች አንዱ የዜድቲኢ ምርት ተጠቃሚ ለማድረግ አቅዶ እየሰራ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡


      የኢትዮ-ኮርያ የቢዝነስ ፎረም የተካሄደ ሲሆን ከኮርያ የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ኩባንያዎች ለመጡ 40 ያህል የኢንዱስትሪው ኃላፊዎች በኢትዮጵያ በዘርፉ ስላለው የኢንቨስትመንት ሁኔታ ገለጻ ተደርጓል፡፡
ከትናንት በስቲያ በካፒታል ሆቴል የተካሄደውን የቢዝነስ ገለጻ ከኮርያ የንግድ ኢንዱስትሪና ኢነርጂ፣ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ ከኮርያ ጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪ ፌዴሬሽን፣ ከጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪዎች ማኅበር፣ ከኮርያ የንግድ ም/ቤትና ከ17 የኮርያ ኩባንያዎች የተውጣጡ የቢዝነስ ልዑካን ተከታትለውታል፡፡
የፎረሙ ዓላማ በሁለቱ አገር ኩባንያዎች መካከል ያለውን ትብብር ከፍ ለማድረግ፣ አዳዲስ የቢዝነስ አማራጮችን መፍጠር፣ በሁለቱ አገሮች መካከል በስትራቴጂያዊ ትብብርና በከፍተኛ ባለስልጣናት ደረጃ የቢዝነስ ጉባኤዎች ማካሄድ መሆኑ ታውቋል፡፡
ኢትዮጵያ ለጨርቃጨርቅና  አልባሳት፣ ለቆዳና ቆዳ ውጤቶች፣ … ኢንቨስትመንት አመቺ መሆኗን የጠቀሱት የኢንዱስትሪ ሚ/ር ዴኤታ አቶ ታደሰ ኃይሌ፣ በቦሌ ለሚ ተሰርቶ አገልግሎት ከጀመረው የኢንዱስትሪ ፓርክ በተጨማሪ፣ በሀዋሳ፣ በመቀሌ፣ በኮምቦልቻ፣ በባህርዳርና በጅማ የኢንዱስትሪ ፓርኮች እየተገነቡ መሆኑነ ገልጸዋል፡፡
6.000 ሜጋ ዋት የሚያመነጨው ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ግንባታ እየተጋመሰ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ታደሰ፤ ኢትዮጵያ በቅርቡ ከ10 ሺህ ሜጋ ዋት በላይ ኤሌክትሪክ ኃይል እንደሚኖራት፣ በአሁኑ ወቅት ለጂቡቲ የኤሌክትሪክ ኃይል መሸጧን፣ ለሱዳንና ለኬንያም ለመሸጥ መዋዋላቸውን ተናግረዋል፡፡
ኢትዮጵያ በርካታ የኢንቨስትመንት አማራጮች እንዳላት የጠቀሱት የኮርያ የልማት ስትራቴጂ ተቋም የፕሮግራም ኦፊሰርና የልማት አማካሪ ዶ/ር ሊ-ጃ-ሁን፣ ኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥቅም የሚታፈስባት አገር ናት፡፡ ለምሳሌ 200 ሺህ ዶላር ኢንቨስት ብታደርግ ሰባት እጥፍ ጥቅም ታገኛለህ፡፡ ይህ ትልቅ አጋጣሚ ነው፡፡ ስለዚህ በቀላል ኢንዱስትሪ ጀምሮ ወደ ትልቅ ማሳደግ ይቻላል ብለዋል፡፡
የኮርያ የጨርቃጨርቅና የአልባሳት ኢንዱስትሪዎች በአሁኑ ወቅት እየሰሩ ያሉት በባንግላዴሽ፣ በጓቲማላ፣ … እንደሆነ የጠቀሱት ዶ/ር ሉጃ-ሁን፣ ወደዚህ የመጡት በኢትዮጵያ ያሉትን የኢንቨስትመንት ሁኔታ ለማየት ነው፡፡ ኢትዮጵያ በርካታ የኢንቨስትመንት መሬት፣ በቀላሉ የሚሰለጥንና በርካሽ የሚሰራ የሰው ኃይል አላት፡፡ ይህ መልካም አጋጣሚ ሲሆን ችግሮችም አሉ፡፡ ዋናው ችግር የሎጂስቲክስ ዋጋ በከፍተኛ መጠን መናር ነው። ከጅቡቲ አዲስ አበባ የተዘረጋው የባቡር መስመር ከወር በኋላ ሥራ ሲጀምር ይህ ችግር እንደሚቃለል እርግጠኛ ነኝ በማለት አስረድተዋል፡፡

Saturday, 05 December 2015 09:17

ፀደኒያ ምስጋና አቀረበች

  በቅርቡ በናይጄሪያ ሌጎስ በተከናወነው “አፊርማ” የሙዚቃ ውድድር፤ “የምስራቅ አፍሪካ ምርጥ ሴት ድምፃዊት” ዘርፍ አሸናፊ የሆነችው ዝነኛዋ ድምፃዊት ፀደንያ ገ/ማርቆስ ድጋፋቸውን ለቸሯትና በተለያየ መንገድ ለደገፏት አድናቂዎቿ ባለፈው ማክሰኞ ባዘጋጀችው የምሽት ፕሮግራም ላይ ምስጋናዋን አቅርባለች፡፡

Saturday, 05 December 2015 09:12

የሙስና ጥግ

አፍሪካውያን ስለ ሙስና)
- ሙስና ከአፍሪካ የሚጠፋ ከመሰላችሁ
ሃሳባችሁን ዳግም ፈትሹት፡፡ በሴራሊዮን
አንድ የፖሊስ መኮንን ለትራፊክ ሥራ
ከመሰማራቱ በፊት ሚስቱ ምድጃው ላይ
ውሃ እንድትጥድ ነግሯት ነው የሚወጣው።
ወደ ቤት ሲመለስ ታዲያ በእርግጠኝነት
አንዲት ከረጢት ሩዝ መያዙ የተረጋገጠ
ነው፡፡ እስቲ ንገሩኝ፤ ቀንደኞቹ ዋናዎቹ
ሙሰኞች በሆኑበት ሁኔታ ሆነው ማነው
ህጉን የሚያስፈፅመው? (ሴራሊዮን)
* * *
- ማንነትህ ወይም ከየትኛውም የአፍሪካ
ክፍል መምጣትህ ደንታ አይሰጠኝም።
እውነቱ ግን በሙስና ተዘፍቀሃል ወይም
በበርካታ የሙስና ተግባራት ውስጥ
ተሳትፈሃል፡፡ ሙስና የአፍሪካ ባህል
አንድ አካል ነው፤ የኑሮ ዘይቤ ሆኗል፡፡
ነገሮች እንደምትፈልገው እንዲያልቅልህ
ከፈለግህ፣ አንድ ነገር በእጅ ማለት ነው፡
፡ ምስጋናን የመግለጪያ መንገድ ሆኗል፡
፡ (ቶጎ)
* * *
- ሙስና ሥር ሰድዷል፡፡ ሙሉ በሙሉ
ከመጥፋቱ በፊት ጥቂት ጊዜ መውሰዱ
አይቀርም፡፡ አሁንም ቢሆን ግን በመላው
ዓለም ላይ ጥቂት ሃቀኛ፣ ትጉህ፣ ቅንና
ቁርጠኛ አፍሪካውያን አሉ፡፡ እንደነዚህ
ያሉ ሰዎች ሥልጣን ሲይዙ በአፍሪካ
የሚመጣውን ተዓምራዊ ለውጥ
ታዩታላችሁ፡፡ (ቻድ)
* * *
- የሙስና ባህል በአጠቃላይ በአፍሪካና
በተለይ በናይጄሪያ፣ ህብረተሰቡ
የተገነባበትን ዋና መሰረት ቦርቡሮታል።
በትራንስፖርት አውቶብስ ውስጥ
ተሳፋሪው ከገንዘብ ተቀባዩ ለማጭበርበር
ይሞክራል፡፡ ገንዘብ ተቀባዩ በተራው
ከሹፌሩ፣ ሹፌሩ ደግሞ ከአውቶብሱ
ባለቤት ለማጭበርበር ይሞክራል፡፡ ነገሩ
ወደዚህ ደረጃ ከመዝቀጡ በፊት ግን
በመንግስት ባለስልጣናት ብቻ የሚፈፀም
ጉዳይ ነበር፡፡ (ናይጄሪያ)

Saturday, 05 December 2015 09:07

የዘላለም ጥግ (ስለ ተስፋ)

ከትላንት ተማር፣ ዛሬን ኑር፣ በነገ ተስፋ
አድርግ፡፡ ዋናው ነገር መጠየቅን አለማቆም
ነው፡፡
አልበርት አንስታይን
- ተስፋ፤ ያለ አበቦች ማር የሚሰራ ብቸኛው
ንብ ነው፡፡
ሮበርት ግሪን ኢንገርሶል
- ተስፋ ዓለምን ደግፎ የያዘ ምሰሶ ነው፡፡
ተስፋ ከእንቅልፍ የነቃ ሰው ህልም ነው፡፡
ፕሊኒ ዘ ኤልደር
- ተስፋ እንደ ሰላም ነው፡፡ የእግዚአብሔር
ስጦታ አይደለም፡፡ አንዳችን ለሌላችን
የምንለግሰው ስጦታ ነው፡፡
ኤሊ ዊሴል
- ያለ ተስፋ መኖር ከህይወት መፋታት ነው፡፡
ፍዮዶር ዶስቶቭስኪ
- ሁልጊዜ ታላላቅ ተስፋዎችን አስተናግዳለሁ።
ሮበርት ፍሮስት
- ነገ፤ ከትላንት አንድ ነገር እንደተማርን ተስፋ
ያደርጋል፡፡
ጆን ዋይኔ
- የበዛ ተስፋ ከበዛ መከራ ይወለዳል፡፡
በርትራንድ ራስል
- አንድን ሁኔታ ወይም ሰው ተስፋ-ቢስ
ስትሉ በእግዚአብሔር ፊት ላይ በሩን
እየደረገማችሁት ነው፡፡
ቻርለስ ኤል. አለን
- ርዕይ በሌለበት ተስፋ የለም፡፡
ጆርጅ ዋሺንግተን ካርቨር
- ዛሬ ጤንነቴን መጠበቄ ለነገ የተሻለ ተስፋ
ይሰጠኛል፡፡
አኔ ዊልሰን ስሻት
- ተስፋ የማልቆርጥበት ምክንያት ሁሉም ነገር
በመሰረቱ ተስፋ ቢስ ስለሆነ ነው፡፡
አኔ ላሞት
- ተስፋ የእውነትን እርቃን መሸፈኚያ
የተፈጥሮ ዓይነ እርግብ ነው፡፡
አልፍሬድ ኖብል

Saturday, 05 December 2015 09:06

የቀልድ ጥግ

አንድ ጎልማሳ በትልቅ ሱፐርማርኬት ውስጥ
ወደ አንዲት በጣም ቆንጆ የሆነች ሴት ቀረብ
ይልና፤ “ይሄውልሽ ሚስቴ እዚሁ ሱፐርማርኬት
ውስጥ ጠፍታብኛለች፡፡ ለጥቂት ደቂቃዎች
ልታዋሪኝ ትችያለሽ?” ይላታል::
“ለምን?” አለች ቆንጅየዋ ሴት ኮስተር ብላ፡፡
“ሚስቴ ሁልጊዜ ከቆንጆ ሴት ጋር ሳወራ
ድንገት ከሆነ ቦታ ትከሰታለች”
* * *
አንድ ትንሽ ልጅ ከእናቱ ጋር ሰርግ ይሄዳል።
እዚያም ሙሽሮቹንና ሚዜዎቹን ሲመለከት
ይቆይና ለእናቱ ጥያቄ ያቀርባል፡-
“ማሚ፤ ለምንድነው ሴቷ ነች የለበሰችው?”
እናትየዋም፤ “ሙሽራዋ ነች የለበሰችው ደስ
ስላላት ነው፤ ዛሬ የደስታዋ ቀን ነው” ስትል
መለሰችለት፡፡
ልጁ ትንሽ አሰብ አደረገና፤ “ታዲያ ሰውየው
ለምን ጥቁር ለበሰ?”
(እውነት ሙሽራው ለምንድነው ጥቁር
የሚለብሰው?)

Saturday, 05 December 2015 09:03

የጸሐፍት ጥግ

 ፀሐፊ፤ የሰዎች ነፍስ መሃንዲስ ነው፡፡
ጆሴፍ ስታሊን
- ፀሐፊ ተመልካች ነው፤ ሁሉንም ነገር በላቀ
የሰላ ዓይን የሚመለከት፡፡
በርናርድ ማላሙድ
- ፀሐፊ፤ የገጣሚ እቅጩነት፣ የሳይንቲስት
ምናብ ሊኖረው ይገባል፡፡
ቭላድሚር ናቦኮቭ
- ፀሐፊ ነኝ፤ እናም መፃፍ የምሻውን
እፅፋለሁ፡፡
ጄ.ኬ.ሮውሊንግ
- ጆሮ፤ ብቸኛው እውነተኛ ፀሐፊና ብቸኛው
እውነተኛ አንባቢ ነው፡፡
ሮበርት ፍሮስት
- ዝነኛ ፀሐፊ ማለት እንደ ጄን ኦዩስተን መሆን
ይመስለኝ ነበር፡፡
ጄ.ኬ.ሮውሊንግ
- ለፀሐፊ ትልቁ ሃጢያት አሰልቺነት ነው፡፡
ካርል ሃያሴን
- እያንዳንዱ ፀሐፊ የየራሱን የአፃፃፍ ስልት
መፈለግ አለበት፡፡
ማርጋሬት ማሂ
- ፀሐፊ በአትኩሮት መመልከትን ማፈር
የለበትም፡፡ የእሱን ትኩረት የማይፈልግ
ምንም ነገር የለም፡፡
ፍላነሪ ኦ‘ኮኖር
- የፀሐፊ የመጀመሪያ ሥራው ሃቀኝነት ነው፡፡
ኧርቪን ዌልሽ
- መፃፍ ከዝምታ ጋር የሚደረግ ትግል ነው፡፡
ካርሎስ ፉንቴስ
- የምናብ ፈጠራ የሆኑ ታሪኮች ምናብ
የሌላቸውን ሰዎች ያበሳጫሉ፡፡
ቴሪ ፕራትሼት
- እኔ በእግዜር እጅ እንዳለ ትንሽዬ እርሳስ
ነኝ። እሱ ነው የሚፅፈው፡፡ እርሳሱ ከፅሁፉ
ጋር ግንኙነት የለውም፡፡
ማዘር ቴሬዛ
- ሁሉም ፅሁፍ የሚመነጨው ከእግዚአብሔር
ፀጋ ነው፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኢመርሰን

     ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አቴናዊና አንድ ቲቤታዊ መንገድ ላይ ይገናኛሉ። ከዚያም ውይይት ማድረግ ጀመሩ፡፡ መንገደኞች ትንሽም ይሁን ትልቅ ነገር ማንሳታቸው የተለመደ ነው፡፡ የተለያዩ ጉዳዮችን ካነሱ በኋላ ስለጀግኖች ወሬ ጀመሩ፡፡ ሁለቱም የየራሳቸውን ጀግኖች ማወደስ ያዙ፡፡
አቴናዊው፤
“የእኔን አገር ከተማ ጀግኖች የሚያክል ማንም የለም” አለ፡፡
ቲቤታዊው፤
“ኧረ አፍ አውጥተህ እንዲህ ያለ ድፍረት አትናገር፤ ቲቤት ምን የመሳሰሉ ጀግኖች ያፈራች ከተማ መሆኗን አለማወቅህ ገርሞኛል” ይላል፡፡
አቴናዊው፤
“የጀግና ልክ አታቅም ማለት ነው፡፡ ቴሲየስን የሚያክል ጀግና ያለን ነን እኛ፡፡”
ቲቤታዊው፤
“ሒርኩለስን የሚያክል ጀግና በዓለም ላይ እንዳልነበረ በታሪክ የተመሰከረ ነው። በአማልክቱ ዘንድ ትልቁን ሥፍራ የተሰጠው ጀግና ነው፡፡”
አቴናዊው፤
“ቴሲየስ ይህ ነው የማይባል ሀብት ያለውና ሔርኩለስን ሳይቀር አገልጋዩ ማድረግ የቻለ ነበር፡፡”
ይህን ሲል ሙግቱ ሚዛን አነሳ፡፡ እንደ ብዙዎቹ አቴናውያን አንደበተ ርቱዕና አሳማኝ ነው፡፡
ቲቤታዊው በክርክሩ የተሸነፈ መሆኑነ አውቆ በመከፋት፤
“ይሁን፡፡ መንገድህ የራስህ ነው፡፡ እኔ ተስፋ እማደርገው ጀግናዎቻችን በእኛ የተናደዱ ለታ፤ አቴናውያን የሄርኩለስ ንዴት ሰለባ ይሆናሉ፡፡ ቲቤታውያን ደግሞ ቴሲየስ የተናደደ ለታ የእሱን ሥቃይ ይቀበላሉ፡፡
*        *       *
ዕጣ ፈንታችን በጀግና መሪዎች ንዴትና ትኩሳት ላይ የተጣለ ከሆነ ህዝቦች እየተመራን ሳይሆን እየተነዳን ነው ማለት ነው፡፡ መሪዎች፤ ኃላፊዎችና አመራሮች ስሜታቸውን የሚቆጣጠሩ ሆደሰፊነታቸውን ያስመሰከሩ፣ ሁኔታዎችን በጥሞና አይተው የሚፈርዱ መሆን አለባቸው፡፡ ከባለሙያዎች ጋር መክረው፣ ዘክረው የሚተገብሩት ተግባር ፍሬው አመርቂ ይሆናል፡፡ ፍርድ ሁሉ የብቻዬ ነው፤ ሁሉን ወሳኝ እኔ ነኝ ማለት ውሎ አድሮ ብሶትን፣ ምሬትንና በቀልን እንጂ ዲሞክራሲያዊ ትሩፋትን አያስገኝም፡፡ የምናጭደው የዘራነውን ነው! የዘራነውን ብቻ ነው!
ለራስህ ታማኝ ሁን፡፡ ያኔ ሌላውን ሰው አትዋሽም (To thine own self be true. Thou canst be false to any man) ይለናል ሼክስፒር፡፡ ለራሱ ታማኝ የሆነ ሰው ልበ - ሙሉ የሆነ ሰው ነው፡፡ ልበ - ንፁህም የሆነ ሰው ነው! ለራስ ታማኝ መሆን ከሥልጣን መባለግ ያድናል፡፡ ለራስ ታማኝ መሆን ከሙስና ራስን ለማዳን ይጠቅማል፡፡ ለራስ ታማኝ መሆን ሌሎችን በወገን፣ በጎሣ፣ በዘር፣ በሃይማኖት ነጥሎ ከማየትና ከመበደል ሙሉ ልቦናን ይሰጣል፡፡ ለራስ ታማኝ መሆን ሌሎችን ላለመጠራጠርና በራስ መተማመንን ያበለፅጋል፡፡ ለራስ ታማኝ መሆን መማርንና መመራመርን ስለሚያበረታታ፤ “ከመጠምጠም መማር ይቅደም” የሚለውን ብሂል፣ በወጉና በቅጡ እንድንረዳ ያደርገናል፡፡ ለራስ ታማኝ መሆን መልካም አስተዳደርን በሀቅ እንድንረዳ፣ በሀቅም እንድንተገብር ያግዘናል! ለራስ ታማኝ መሆን ለህግ የበላይነት ታማኝ እንድንሆን ያደርገናል! በመጨረሻም ለራስ ታማኝ መሆን ለሀገር ታማኝ እንድንሆን በሩን ይከፍትልናል!
አገራችን ወደፊት ትጓዝ ዘንድ በራሳቸው የሚተማመኑ ጎበዛዝት ያስፈልጓታል! እኒያ ጎበዛዝት ከአሁኑ ትውልድ የሚፈልቁ ናቸው፡፡ ይህ ትውልድ በትምህርት፣ በዕውቀት እና በጥበብ የለማና የዳበረ መሆን አለበት፡፡ በሀገር ፍቅር የበለፀገ መሆን አለበት፡፡ ለዚህ ደግሞ ትሁት ግብረገብነት ወሳኝ ነው፡፡ ግብረገብነት በተለይ ዛሬ ለሀገር ወሳኝ ነው! “የጠፋው በግ” ግብረ ገብነት ነው! ለዚህ መንግሥት፣ ህዝብ፣ ቤተሰብ፣ ት/ቤቶች ትልቅ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ ይህን ኃላፊነት ለመወጣት ሁሎችም መተባበር ወቅታዊም፣ ታሪካዊም ርብርብ ያሻሉ፡፡! የዛሬው ጥሪያችን ግብረገብነት ያለው ሀቀኛ ትውልድ መፍጠር ነው!
“የኔ ቀበሌ፣ የኔ ክፍለ ከተማ፣ የኔ ክልል፣ የኔ ከተማ፣ የኔ ብሔር - ብሔረሰብ ጀግና ነው” ማለት ሳይሆን እኔ ለሀገሬ ምን እያደረግሁ ነው ብሎ ራስን መፈተሽ ብቻ ነው ሀገራችንን ከገባችበት ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ቀውስ የሚያወጣት፡፡ የራስን ሰፈር ብቻ የተሻለ ለማድረግ ማሰብ ለዲሞክራሲ ሩቅ ነው። ትምክህትም ሆነ ጥበት ዞሮ ዞሮ የጥፋት መፈልፈያ ነው፡፡ ይህን ማረም “የሌሊት ጀግና ባሌ ነው፣ ትላለች የሌባ ሚስት” የሚለውን ተረት ማወቅ ነው!

“ማስተር ፕላኑ ልማትን ያሻሽላል፤ በረብሻ የተሳተፉ ይከሰሳሉ” - መንግሥት

     “የአዲስ አበባና የፊኒፊኔ ዙሪያ ልዩ ዞን ማስተር ፕላን” ላይ፣ ሰሞኑን በበርካታ የኦሮሚያ ከተሞች  በተቀሰቀሰው ተቃውሞ፣ ከፖሊስ ጋር ግጭት ተፈጥሮ፣ ሶስት ሰዎች የሞቱ ሲሆን፣ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ)፤ መንግስትን ተጠያቂ አድርጓል፡፡ የክልሉ ፖሊስ በበኩሉ፤ በረብሻው የተሳተፉ ሰዎች ይከሰሳሉ፤ የተቃዋሚ ፓርቲዎች እጅ አለበት ብሏል፡፡
አምና ተመሳሳይ ግጭትና ተቃውሞ ተፈጥሮ እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን፤ “ማስተር ፕላኑ የአዲስ አበባ አስተዳደር፤ በዙሪያው የሚገኙ የኦሮሚያ ከተሞችን እንዲጠቀለል የሚያደርግ ነው፤” የሚለው ተቃውሞ ከሰሞኑ እንደገና ተሰንዝሯል፡፡ “የከተሞቹ የአስተዳደር መዋቅር በማስተር ፕላኑ አይቀየርም” የሚለው መንግስት በበኩሉ፤ መሰረተ ልማትን በጋራ እንዲሰሩ የሚያስችል ነው ሲል ቆይቷል፡፡
“የአዲስ አበባ አስተዳደር፤ በዙሪያው ወዳሉ የኦሮሚያ አካባቢዎች እየሰፋ መጥቷል” በማለት የሚከራከረው ኦፌኮ፤ “ማስተር ፕላኑን አንቀበልም፤ መሬታችን አጥንታችን ነው፤ አንነቀልም” በማለት መግለጫ አውጥቷል፡፡ በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ ከተሞች (ግንጪ፣ ደንቢዶሎ፣ ዲላላ፣ ወሊሶ፣ መደወላቡ፣ ሀረማያ፣ አይራ ጉይሶና በሌሎችም) ለተነሳው የተማሪዎች  ተቃውሞ፤ መንግስት ሰላማዊ ምላሽ መስጠት አለበት የሚለው ኦፌኮ፤ እየደረሰ ላለው ጉዳት መንግስት ኃላፊነቱን ይወስዳል ብሏል፡፡
እስር፣ ድብደባና ግድያ እየተፈጸመ፣ መሆኑን በማውገዝ፤ መንግሥት ይህን ድርጊት በአስቸኳይ ማቆም አለበት ብሏል- ኦፌኮ፡፡ “የአዲስ አበባ ወሰን፤ ከ1987 ዓ.ም በፊት  ወደነበረበት መመለስ አለበት፤ ከወሰን አልፈው የተከናወኑ ግንባታዎች በሙሉ በኦሮሚያ ክልል ስር መተዳደር አለባቸው” ሲልም ፓርቲው ጠይቋል፡፡ የከተሞች ፕላን የፌደራል መንግስት ጉዳይ አይደለም ያለው ኦፌኮ፤ ማስተር ፕላኑ ራስን በራስ የማስተዳደር መብትን ይጻረራል ብሏል፡፡  
ለልማት ተብሎ ከመሬታቸው የሚነሱ ገበሬዎች የህንፃዎች ጠባቂ እየሆኑ ነው ያሉት የኦፌኮ አመራር ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ ገበሬዎቹ የባለሀብትነት ድርሻ ሊኖራቸው ይገባል ብለዋል፡፡  
ዓለም ባንክ ማስተር ፕላኑን መደገፍ የለበትም ያለው ኦፌኮ፤ ባንኩ እጁን ያንሳ ሲል ጠይቋል፡፡ የፈረንሳይዋ ሊዮን ከተማ አስተዳደር ለማስተር ፕላኑ ድጋፍ በመስጠትም አሁን ለተፈጠረው ችግር አስተዋጽኦ ስላደረገ ይቅርታ መጠየቅ ይኖርበታል ብሏል - ኦፌኮ፡፡  
የመንግስት በደልና ግፍ ካልቆመ፣ የአገሪቱን ሰላምና አንድነት ስጋት ላይ ይጥላል ያሉት ዶ/ር መረራ፤ መንግስት ለህዝቡ ጥያቄዎች ምላሽ የማይሰጥ ከሆነ በአገር ውስጥም ሆነ በውጪ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ እንደሚገደድ ተናግረዋል፡
“በአዲስ አበባ ዙሪያ፣  በኦሮሚያ ላይ ሰፊ የመሬት እና የባህል ወረራ ተካሂዷል  ያሉት ዶ/ር መረራ፤ ከ25 ዓመት በፊት በአዲስ አበባ አካባቢ የነበሩ 28  የገበሬ ማህበራት ዛሬ የሉም ብለዋል፡፡ መንግስት በርካሽ የካሳ ክፍያ ከገበሬዎች መሬት እየወሰደ  በሚሊዮን ብሮች በጨረታ ይሸጣል ያሉት ዶ/ር መረራ፤ ሱሉልታ አካባቢ ገበሬዎች በ50 ሺህ ብር ካሳ ይፈናቀላል ብለዋል፡፡
ሰኞ እለት በሃረማያ ዩኒቨርሲቲ የተነሳውን ተቃውሞ ተከትሎ ከፖሊስ ጋር በተነሳ ግጭት በርካታ ተማሪዎች ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን፣ ትምህርት ተስተጓጉሎ ሰንብቷል፡፡  ዩኒቨርስቲው በበኩሉ፣  በተቃውሞ ምክንያት ትምህርት ሙሉ ለሙሉ እንዳልተቋረጠና የግቢው ሁኔታ እንደተረጋጋ ገልጿል፡፡
ተቃውሞው በበርካታ ከተሞች በሚገኙ ዩንቨርስቲዎችና ት/ቤቶች የተስፋፋ ሲሆን ፣ በአንዳንዶቹ  አካባቢዎችም  ነዋሪዎች እንደተሣተፉበት ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የኦሮሚያ ክልል መስተዳደር በበኩሉ፤ በረብሻው የሰው ህይወት መጥፋቱንና ንብረት መውደሙን በመግለፅ ተቃዋሚዎችን ተጠያቂ አድርጓል፡፡ ማስተር ፕላኑ የፌደራል ስርአቱን አይጥስም ያለው መስተዳድሩ፤ የኦሮሚያ መሬትንም ቆርሶ ለሌላ አካል አይሰጥም ብሏል፡፡  ሁከት የሚሹ ሃይሎች፤ ለማስተር ፕላኑ የተሣሳተ ትርጉም ሰጥተውታል፣ በዚህም ለጠፋው ህይወትና ለወደመው ንብረት ተጠያቂ ናቸው ብሏል መስተዳድሩ ፡፡
ባለፈው አመት በዩንቨርስቲዎችና በተለያዩ የኦሮሚያ ከተሞች ማስተር ፕላኑን ተመሳሳይ ተቃውሞ ተቀስቅሶ፤ ከፖሊስ ጋር በተፈጠረ ግጭት 10 ሰዎች መሞታቸው ይታወሳል፡፡

ከቡድኑ ጋር ወደ አገራቸው እንዳይመለሱ፣ ፓስፖርታቸውን ተነጥቀው ነበር
  በሴካፋ ዋንጫ ለመሳተፍ ወደ ኢትዮጵያ የመጣውን የኬንያ ብሄራዊ ቡድን ልኡካን የመሩት የክለቡ ማናጀር ዊሊስ ዋሊያውላ፤ ስድስት የቡድኑ ልኡክ አባላት ለአስር ቀናት አርፈውበት ለቆዩት “እንዳለ እና ቤተሰቡ ቸርቺል ሆቴል መከፈል የነበረበትን 41 ሺህ 154 ብር መክፈል ባለመቻላቸው፣ ከሆቴሉ እንዳይወጡ ታግደው ከቆዩ በኋላ ከትናንተ በስቲያ ተለቀቁ፡፡
የኬንያው ብሄራዊ ቡድን “ሃራምቤ ስታርስ” ከሩብ ፍጻሜ ውድድሩ ውጭ ሆኖ ባለፈው ረቡዕ ምሽት ወደ አገሩ ቢመለስም፣ ዊሊስ ዋሊያውላ ግን ከቡድኑ ጋር የመጡት ስድስት ተጨማሪ የልኡካን ቡድን አባላት በሆቴሉ የቆዩበትን ወጪ መክፈል ባለመቻላቸው ከሆቴሉ እንዳይወጡ ታግደው ከቆዩ በኋላ፣ የኬንያ የስፖርት ሚኒስቴር ክፍያውን በመፈጸሙ ትናንት ወደ አገራቸው መመለሳቸውን “ሲቲዝን ቲቪ” የተባለው የአገሪቱ ቴሌቪዥን ዘግቧል፡፡ የቡድኑ መሪ የሆቴሉን ዕዳ ሳይከፍሉ ወደ አገራቸው እንዳይመለሱ ፓስፖርታቸውን ተቀምተው ነበር ያለው ዘገባው፤ የኬንያ የእግር ኳስ ፌዴሬሽን የልኡካን ቡድኑን ለመሩት ለእኒሁ ግለሰብ ወጪውን እንዲሸፍኑ 250ሺህ የኬንያ ሽልንግ መላኩን ጠቁሟል፡፡
የሴካፋ አዘጋጆች፤ ኬንያ 20 ተጫዋቾችንና አምስት የልኡካን ቡድን አባላትን ብቻ እንድትልክ ቢያስታውቁም፣ የኬንያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ግን 23 ተጫዋቾችንና የልኡካን ቡድን አባላትን በመላኩና ተጨማሪ ስድስት አባላት በመኖራቸው የገንዘብ እጥረቱ ሊከሰት እንደቻለ ዘገባው ጠቁሟል፡፡