Administrator

Administrator

የመጀመሪያው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ታትሞ ለንባብ የበቃው ታህሳስ 29 ቀን 1992 ዓ.ም ነበር - የዛሬ 25 ዓመት በዕለተ ቅዳሜ፡፡ ከዚያን ጊዜ አንስቶ ያለ አንድ ቅዳሜ በስተቀር ጋዜጣው ያልታተመበት ጊዜ የለም፡፡ ያም ቢሆን የተከሰተው በ97 ምርጫ ማግስት በተፈጠረው ፖለቲካዊ ቀውስ ሳቢያ ነበር፡፡
የዛሬ 20 ዓመት፣ የአዲስ አድማስ ጠንሳሽ፣ መሥራችና ባለቤት አሰፋ ጎሳዬ (አሴ) በድንገተኛ ህመም ህይወቱ ባለፈበት ወቅት እንኳን ጋዜጣው ሳይታተም አልቀረም፡፡ ረቡዕ ከቀብር በኋላ ቢሮ ገብተን የቅዳሜውን ጋዜጣ ስናዘጋጅ ነበር፡፡ ከሃዘናችን ጋር እየታገልንም ቢሆን የቅዳሜውን ሳምንታዊ ጋዜጣ በጉጉት ለሚጠብቁን ውድ አንባቢያን አድርሰናል፡፡ በዚህም ኩራትና ክብር ይሰማናል፡፡ የጋዜጣው መሥራች አሰፋ ጎሳዬም ቢሆን፣ ከምንም በፊት ቅድሚያና ትኩረት የሚሰጠው ለአንባቢያን ነበርና፡፡
እነሆ አዲስ አድማስ ከዚያም በኋላ ሁለት አሰርት ዓመታትን አስቆጥራ፣ በብዙ ውጣ ውረዶችና ተግዳሮቶች አልፍ፣ እነሆ ለ25ኛ ዓመቷ በቅታለች፡፡ ኮረኮንች በበዛበት የአገራችን የግል ፕሬስ፣ ሩብ ክፍለዘመን ቀላል ዕድሜ አይደለም፡፡ ረዥም ዕድሜ ነው፡፡ ትልቅ ስኬትም ነው ማለት ያስደፍራል፡፡
ለዚህ የደረስነው ግን በውድ አንባቢያን ገንቢ አስተያየትና ድጋፍ ነው፡፡ ስለዚህም በዚህ አጋጣሚ ልባዊ ምስጋናችንን ለማቅረብ እንወዳለን፡፡ ለአዲስ አድማስ ህልውናና በስኬት መቀጠል ከእኛ ከአዘጋጆቹ እኩል የሚጨነቁና የሚጠበቡት የረዥም ጊዜ ጽሁፍ አቅራቢዎችም ሌሎቹ ትልቅ ምስጋና የምንቸራቸው ባለውለታዎች ናቸው፡፡
ማስታወቂያቸውን በጋዜጣችን ላይ የሚያወጡ የንግድ ድርጅቶችና የመንግሥት ተቋማትም ሁነኛ አጋሮቻችን ናቸውና ከልብ ልናመሰግናቸው እንወዳለን፡፡
መጪው ጊዜም ነጻ ሃሳብ በነጻነት የሚንሸራሸርበት፣ ዕውቀትና ሥልጡንነት የሚያብብበት፣ የንባብ ባህል የሚዳብርበት እንዲሆን እንመኛለን፤ ለዚያም በትጋት መሥራታችንን እንቀጥላለን፡፡
እንኳን አደረሳችሁ፤ አደረሰን!!

 

የመጀመሪያው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ታትሞ ለንባብ የበቃው ታህሳስ 29 ቀን 1992 ዓ.ም ነበር - የዛሬ 25 ዓመት በዕለተ ቅዳሜ፡፡ ከዚያን ጊዜ አንስቶ ያለ አንድ ቅዳሜ በስተቀር ጋዜጣው ያልታተመበት ጊዜ የለም፡፡ ያም ቢሆን የተከሰተው በ97 ምርጫ ማግስት በተፈጠረው ፖለቲካዊ ቀውስ ሳቢያ ነበር፡፡
የዛሬ 20 ዓመት፣ የአዲስ አድማስ ጠንሳሽ፣ መሥራችና ባለቤት አሰፋ ጎሳዬ (አሴ) በድንገተኛ ህመም ህይወቱ ባለፈበት ወቅት እንኳን ጋዜጣው ሳይታተም አልቀረም፡፡ ረቡዕ ከቀብር በኋላ ቢሮ ገብተን የቅዳሜውን ጋዜጣ ስናዘጋጅ ነበር፡፡ ከሃዘናችን ጋር እየታገልንም ቢሆን የቅዳሜውን ሳምንታዊ ጋዜጣ በጉጉት ለሚጠብቁን ውድ አንባቢያን አድርሰናል፡፡ በዚህም ኩራትና ክብር ይሰማናል፡፡ የጋዜጣው መሥራች አሰፋ ጎሳዬም ቢሆን፣ ከምንም በፊት ቅድሚያና ትኩረት የሚሰጠው ለአንባቢያን ነበርና፡፡
እነሆ አዲስ አድማስ ከዚያም በኋላ ሁለት አሰርት ዓመታትን አስቆጥራ፣ በብዙ ውጣ ውረዶችና ተግዳሮቶች አልፍ፣ እነሆ ለ25ኛ ዓመቷ በቅታለች፡፡ ኮረኮንች በበዛበት የአገራችን የግል ፕሬስ፣ ሩብ ክፍለዘመን ቀላል ዕድሜ አይደለም፡፡ ረዥም ዕድሜ ነው፡፡ ትልቅ ስኬትም ነው ማለት ያስደፍራል፡፡
ለዚህ የደረስነው ግን በውድ አንባቢያን ገንቢ አስተያየትና ድጋፍ ነው፡፡ ስለዚህም በዚህ አጋጣሚ ልባዊ ምስጋናችንን ለማቅረብ እንወዳለን፡፡ ለአዲስ አድማስ ህልውናና በስኬት መቀጠል ከእኛ ከአዘጋጆቹ እኩል የሚጨነቁና የሚጠበቡት የረዥም ጊዜ ጽሁፍ አቅራቢዎችም ሌሎቹ ትልቅ ምስጋና የምንቸራቸው ባለውለታዎች ናቸው፡፡
ማስታወቂያቸውን በጋዜጣችን ላይ የሚያወጡ የንግድ ድርጅቶችና የመንግሥት ተቋማትም ሁነኛ አጋሮቻችን ናቸውና ከልብ ልናመሰግናቸው እንወዳለን፡፡
መጪው ጊዜም ነጻ ሃሳብ በነጻነት የሚንሸራሸርበት፣ ዕውቀትና ሥልጡንነት የሚያብብበት፣ የንባብ ባህል የሚዳብርበት እንዲሆን እንመኛለን፤ ለዚያም በትጋት መሥራታችንን እንቀጥላለን፡፡
እንኳን አደረሳችሁ፤ አደረሰን!!

 

Tuesday, 28 January 2025 19:36

ቅድመ ታሪክ

ቅድመ ታሪክ
ማግባት ምፈልገው
አሪፍ ገንዘብ ያለው
ምርጥ ቪላ ያለው
ሐብታም ነጋዴ ነው ማለትሽ መልካም ነው።
በተዘዋዋሪ
እንደዚህ ዓይነት ሐሳብ
ሊፈጠር “ሚችለው ከቆንጆ ሴት ላይ ነው .....
ይህ ማለት ምንድ ነው?....
እንዲህ ዓይነት ሐሳብ በብዛት ሚሰማው
በየቡና ቤት ነው።
ስለዚህ .....
በዛም አለ በዚህ
አንቺም በውበትሽ የምትፈልጊው
የቡና ቤቷም ሴት የምትፈልገው
ቪላና ገንዘብ ነው።
ታዲያ በዚህ አገር - የፍቅር ማደርያው የትኛው ልብ ነው?
(ከኤፍሬም ሥዩም፤ “ፍቅር እዚህ ቦታ ፈገግ ብሎ ነበር” ከተሰኘው መድበል)
****
ጭር ያለውን ሰፊ ሜዳ የመረጥኩት፣
ለመሮጥ ሳይሆን ለዕረፍት፣
በኑሮ ላይ የሸፈትኩት፣
ራሴ መንፈስ ውስጥ ለመተኛት፡፡
ከእንግዲህ---፤ ባዶ አዳራሽ ውስጥ ቦታ ስትመርጪ.
በድካም ሰዓት ጥግ ስታጪ፣
አስታውሺኝ፣
ጥጉ እኔ ነኝ፡፡
ያልተቀመጥሽበትም ወንበር፣
በሃዘን ሰዓት ትንሽ ፈገግታ ስትሰሚ፣
በጨለማ ውስጥ የሚያጠራጥር ቅርጽ
ስታይ፣
አስታውሽኝ፣
ትንሷ ፈገግታ እኔ ነኝ፡፡
የተጠራጠርሽውም ነገር፣
ከዕለታት አንድ ቀን ምን አልባትም ሌላ ቀን፣
እታይሽ ይሆናል በጨለማው፣
እሞቅሻለሁም በሚበርደው፡፡
(ከሰዓሊ መስፍን ሀብተ ማርያም)

 

የአንጋፋው የ 'ጣምራ ጦር' ደራሲ ገበየሁ አየለ ታሪክ ላይ ያተኮረ አጭር ዘጋቢ ፊልም

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በመዲናዋ የሚስተዋለውን የኑሮ ውድነት ጫና ለመቀነስና ገበያውን ለማረጋጋት በማለም፣ በተለያዩ አካባቢዎች የገበያ ማዕከላትን አስገንብቶ ወደ ሥራ ማስገባቱ ይታወቃል፡፡ በከተማዋ አምስቱም መግቢያ በሮች ላይ የተገነቡት እነዚህ ዘመናዊ የገበያ ማዕከላት፤ ለማሕበረሰቡ የግብርና ምርቶችንና አትክልትና ፍራፍሬዎችን በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ ይገኛሉ፡፡
በእነዚህ ማዕከላት ነጋዴዎች ምርቶችን ከህገ ወጥ ደላሎች ውጭ፣ ከገበሬዎች በቀጥታ የሚረከቡ ሲሆን፤ ጥራት ያላቸው የግብርና ምርቶችን ከመደበኛ ገበያዎች ከ15 – 20 በመቶ ባነሰ ዋጋ በማቅረብ ማሕበረሰቡን ተጠቃሚ በማድረግ ላይ ናቸው፡፡ በሁሉም የመንግሥት የገበያ ማዕከላት የሚሸጡ ምርቶችን የዋጋ ተመን የሚያወጣው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ንግድ ቢሮ ሲሆን፤ የአንድ ሳምንት የዋጋ ተመን ለማውጣት ቢሮው በየሳምንቱ ጥናት በማድረግ፣ ነጋዴዎች የሚሸጡበትን ዋጋ ይተምናል፡፡
የከተማ አስተዳደሩ በመዲናዋ ከገነባቸውና ለአገልግሎት ክፍት ካደረጋቸው የገበያ ማዕከላት መካከል የለሚ ኩራ ሁለገብ የግብርና ምርቶች መገበያያ ማዕከል ተጠቃሽ ነዉ፡፡ በዚህ ሁለገብ የገበያ ማዕከል ተገኝተን የግብርና ምርቶችን ሲገበያዩ ያገኘናቸው ሸማቾች፣ ማዕከሉ ለነዋሪዎች እያበረከተ ያለውን አስተዋፅኦ አስመልክተው አስተያየታቸውን አጋርተውናል፡፡
ወ/ሮ ፋጡማ መሀመድን በማዕከሉ ግብይት ሲፈጽሙ ነው ያገኘናቸው፡፡ በማእከሉ የተለያዩ የግብርና ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ በመቅረባቸው ኑሮ በማረጋጋት ረገድ ጠቀሜታ እንዳለው ገልጸዋል፡፡ በተመሳሳይም የተለያዩ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶች እንዲሁም ዱቄት ለተጠቃሚዎች በተመጣጣኝ ዋጋ መቅረቡን ጠቁመዋል፡፡ ማእከሉ የግብርና ምርቶችን ለተጠቃሚዎች ተደራሽ በማድረግ የኑሮ ውድነቱን ለማረጋጋት የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ መሆኑንና የዋጋው ሁኔታ ከውጭ ከሚሸጠው ጋር ሲነጻጻር ማእከሉ የተሻለ አማራጭ መሆኑን ጭምር ገልጸዋል፡፡
አቶ ብርሃኑ ወልዴ በማእከሉ ሲገበያዩ ያገኘናቸው ሌላኛው ተጠቃሚ ናቸው። ጥቅል ጎመን፣ ካሮት፣ ቲማቲም፣ አቮካዶ፣ ሽንኩርት፣ ድንችና ሌሎች አትክልቶች በማዕከሉ መቅረቡን ጠቁመው፤ ዋጋውም ተመጣጣኝ መሆኑን ተናግረዋል። ሆኖም ወደ ማእከሉ የሚገቡ ምርቶች በብዛት እንዲቀርቡና የምርት ጥራትም ትኩረት እንዲሰጠው ጠይቀዋል፡፡ በአካባቢያቸው ማእከሉ ተገንብቶ አገልግሎት መስጠቱ፣ የግብርና ምርት በአነስተኛ ዋጋ በማቅረብ የነዋሪዎችን ኑሮ በማረጋጋት፣ በግብይት ይጠፋ የነበረውን ጊዜ በመቆጠብ፤ ካላስፈላጊ ወጪ ማዕከሉ እንደታደጋቸው ተናግረዋል፡፡
በማእከሉ ምርት እያቀረቡ ከሚገኙት የግብርና ምርት አቅራቢዎች መካከል አቶ አለማየሁ አሮጎ ይገኝበታል፡፡ በቀጥታ ምርት በማቅረብ ሽያጭ ሲያከናውን ያገኘነው ሲሆን፤ በዋናነት ሽንኩርት፣ ድንች፣ ቲማቲም እንዲሁም እንደ ማንጎ፣ ፓፓዬና ሃብሃብ የመሳሰሉ ፍራፍሬዎችን በማምጣት ከመደበኛው ገበያ ከ15 እስከ 20 በመቶ የዋጋ ቅናሽ በማድረግ፣ ለሸማቹ ማሕበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ ገበያ እያረጋጉ መሆኑን ገልጿል። የምርት አቅርቦት በተወሰነ መጠን ከእርሻው እንደሚያገኝ የገለጸው አቶ አለማየሁ፤ የተቀሩትን ከሌሎች አምራቾች በመውሰድ ለሸማቾቹ እንደሚያቀርብ ይናገራል፡፡
የገበያ ማዕከሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሰለሞን አበራ፣ በዚህ ማዕከል በዋናነት አትክልትና ፍራፍሬ፣ የሰብል ምርትና ጥራጥሬ፣ የኢንዱስትሪ ምርቶች እንዲሁም የእንስሳት ተዋጽኦና ውጤቶች በቅናሽና በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረበ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡
ሌላው የቃኘነው የአቃቂ ቃሊቲ የገበያ ማዕከልን ነው፡፡ የማዕከሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሳሙዔል ጫኔ፤ የገበያ ማዕከሉ እንቅስቃሴ ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ መምጣቱን ይገልፃሉ፤ በማእከሉ የግብርና ምርቶች ከ15 እስከ 20 በመቶ የዋጋ ቅናሽ ተደርጎባቸው ስለሚሸጡ፣ ሸማቾች ከመደበኛ ገበያዎች ይልቅ ማዕከሉን እንደሚመርጡና ራቅ ካሉ አካባቢዎች ጭምር እየመጡ እንደሚሸምቱ ገልጸዋል።
የአካባቢው ነዋሪ በማዕከሉ አገልግሎት ተጠቃሚ መሆኑን የሚናገሩት ዋና ሥራ አስኪያጁ፤ ለሸማቾች ትልቅ ጥቅም በመፍጠሩ የሚፈልጉትን ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ መርጠው በአቅራቢያቸው መሸመት ችለዋል ብለዋል፡፡
ሜሮን ሰራዊት በአቃቂ ቃሊቲ የገበያ ማዕከል የእህል ምርቶችን የሚያቀርብ ድርጅት በሥራ አስኪያጅነት ትመራለች፡፡ ገበያው ጥሩ ነው የምትለው ሜሮን፤ ሆኖም ሰው በሚፈለገው ደረጃ አያውቀውም፣ የማስተዋወቅ ሥራ ቢሰራልን የበለጠ ገበያ ይመጣል ብዬ አስባለሁ ትላለች፡፡ የቦታው አለመታወቅ ነው እንጂ ቢታወቅ፣ ሸማቹ ህብረተሰብ በደንብ ተጠቃሚ ይሆናል ብላ እንደምታምን ትናገራለች፡፡
የሚያቀርቡት ምርቶች ዋጋ ከመደበኛው ገበያ ዋጋ ከፍተኛ ልዩነት እንዳለውም ትገልጻለች፡፡ “እኛ አምራች ገበሬ ነን፤ በቀጥታ ነው ምርት የምናስገባው” የምትለው ሜሮን፤ “ውጪ ላይ ማኛ ጤፍ የሚሸጠው 140 እና 145 ብር ነው፤ እኛ ጋ ግን 118 እና 120 ብር ነው የሚሸጠው” በማለት ለአብነት ጠቅሳለች፡፡
በመለጠቅ የቃኘነው የኮልፌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 7 የገበያ ማዕከልን ሲሆን፤ ማዕከሉ የተለያዩ የገበያ እንቅስቃሴዎች እንደሚታይበት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ወ/ት ትዕግስት አይችሉህም ጠቁመዋል፡፡ በገበያ ማዕከሉ የተሻለ የገበያ እንቅስቃሴ የሚታይባቸው የእህል ምርት ሽያጭ መሆናቸውን የገለጹት ምክትል ሥራ አስኪያጇ፤ ምርት በቀጥታ ከገበሬዎች እንደሚያስመጡም ይናገራሉ፡፡
በአትክልትና ፍራፍሬ አቅራቢዎች በኩል የሽንኩርት ምርት በቀጥታ ተረክበው የሚያቀርቡ ነጋዴዎች ወደ ማዕከሉ መግባታቸውንና ቲማቲምና ሙዝ በተወሰነ መልኩ እየገቡ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡
ከአርባ ምንጭ ሙዝና ፍራፍሬ እያስመጣ ለኮልፌ የገበያ ማዕከል የሚያቀርበው አቶ ግርማ ማላ፤ የገበያው እንቅስቃሴ ጥሩ መሆኑንና ዓለም ባንክ አካባቢ ከሚገኘው መጋዘኑ ሙዝ እያመጣ በመሸጥ ገበያውን እያለማመደ መሆኑን ይገልጻል፡፡ “እስካሁን ባለውም ጥሩ ተስፋ አለው ብዬ እገምታለሁ።” ይላል፡፡
ግርማ አክሎም ሲናገር፤ ”የገበያ ማዕከሉ የሚገኝበት ቦታ ማሕበረሰቡ እየለመደው አይደለም። በመንገድ ችግር ምክንያት ሊሆን ይችላል። እኛ ግን እያስለመድነው እንገኛለን። ወደፊት ያለውን ውስን ችግር በመፍታት የተሻለ ሁኔታ እንደሚፈጠር ተስፋ አለን” ብሏል፡፡
ዮሐንስ ቱፋ ደግሞ በኮልፌ የገበያ ማዕል የበቆሎ ዱቄት፣ ቂንጬ ፣ጤፍና ሩዝ አቅራቢ ነው፡፡ የፋብሪካው ወኪል በመሆንም ምርት እያከፋፈለ እንደሚገኝ ነው የገለጸው። በኮልፌ የገበያ ማዕከል ሥራ የጀመርነው በቅርቡ ነው የሚለው ዮሐንስ፤ ከዚህ ቀደም እህል በረንዳ ይሰሩ እንደነበርና አሁን በማዕከሉ ምርቶቻቸውን እያከፋፈሉ በመሆኑ የገበያ እንቅስቃሴው የተሻለ ነው ብሎ ያምናል፡፡ “ጤፍን ጨምሮ ሁሉም አይነት የእህል ምርት ስለሚገኝ፣ ከዚህ ቀደም ወደ መሳለሚያ በመሄድ ለሚገዛ ሸማች፣ አሁን በአቅራቢያው ለመግዛት የሚያስችል ሁኔታ ተመቻችቶለታል፤ ስለዚህም እዚህ መጥቶ እንዲሸምት እያስተዋወቅን ነው” ይላል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የንግድ ቢሮ ሃላፊ ወ/ሮ ሃቢባ ሲራጅ፣ “በመዲናዋ የገበያ ማዕከላት የተከፈቱበት መሰረታዊ ዓላማ፣ የነዋሪውን የኑሮ ውድነት ጫና ለማቃለል እንዲሁም ሸማቹንና አምራቹን በማገናኘት ከደላላ ሰንሰለት ውጪ አርሶአደሩ ምርቱን ወደ ሱቅ በማምጣት፣ ሸማቹ በቀጥታ ሄዶ እንዲገዛ ነው።” ይላሉ፡፡

 


አንዳንድ የገበያ ማዕከላት ሙሉ በሙሉ ወደ ስራ ባይገቡም፣ ስራ የጀመሩት ማዕከላት ግን ገበያውን ማረጋጋት ችለዋል የሚሉት ሃላፊዋ፤ አብዛኛዎቹ ሱቆች የተሰጡት ለአምራቾች መሆኑንና የተወሰነው ለቸርቻሪዎች መሰጠቱን ይናገራሉ፡፡
አሁን ላይ እየሰሩ ያሉት ኮልፌ፣ አቃቂ፣ ንፋስ ስልክ ላፍቶ እና ለሚ ኩራ የገበያ ማዕከላት እንደሆኑ የጠቆሙት ወ/ሮ ሃቢባ፤ ሁሉም የማስፋፊያ ስራ እየተሰራላቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የአዲስ አበባ የንግድ ሥርዓት በአብዛኛው የተጠላለፈው በደላላ ነው የሚሉት የቢሮ ሃላፊዋ፤ ከሌሎች ገበያዎች ጋር ስናነጻጽረው፣ የገበያ ማዕከላቱ ውስጥ ያለው የደላላ ሰንሰለት በጣም የቀነሰ ነው፤ ይላሉ፡፡ “ሥራ የሚያቀላጥፉ ህጋዊ ደላላዎች በተወሰነ ቁጥር አሉ፡፡ የገበያ ስርዓቱን የሚያስተጓጉል የደላሎች አካሄድ ግን በገበያ ማዕከላቱ ውስጥ የለም።” ሲሉም ያስረዳሉ፡፡
አምራቾች በገበያ ማዕከላቱ ውስጥ ስራ ለመጀመር ከፈለጉ፣ ሦስት መስፈርቶችን ማሟላት ይገባቸዋል፤ ይላሉ የቢሮ ሃላፊዋ፡፡ አንደኛ፤ ከ15 እስከ 20 በመቶ በሚያቀርቧቸው ምርቶች ላይ ቅናሽ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ምክንያቱም የሚከፍሉት ኪራይ አነስተኛ ነው። ወጪያቸውም የአስተዳደር ክፍያ ብቻ ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ፣ የምርት አቅርቦት መኖር አለበት። የአምራቹ የራሱ የእርሻ ማሳ መኖር አለበት፤ ወይም ኢንቨስተር ሆኖ በእርሻ ስራ ላይ መሰማራቱን እናረጋግጣለን። ትልቁ መስፈርት ደግሞ ዓመቱን በሙሉ ምርት ማቅረብ መቻሉ ነው። አምራቹ ይህንን ሲያሟላ ነው ወደ ውል መፈራረምና ኪራይ የሚገባው። ይህንን መስፈርት ያሟሉ አርሶአደሮች ወደ ማዕከሉ ከገቡ በኋላ ለቸርቻሪዎቹ ምርት ያከፋፍላሉ ብለዋል፤ ወ/ሮ ሃቢባ፡፡
የመሰረተ ልማት መሟላትን አስመልክቶ ለተነሳላቸው ጥያቄ በሰጡት ማብራሪያም፤ “የመሰረተ ልማት ማሟላት ስራዎች ከሞላ ጎደል እየተጠናቀቁ ቢሆንም፣ የመንገድ ስራ ይቀረናል፡፡ የመንገዶች ባለስልጣን እንደነገሩን ከሆነ፣ በዚህ ወር ውስጥ ሰርተው ይጨርሳሉ። አንዳንድ ነጋዴዎች ከማዕከሉ የሚወጡት በመንገድ ምክንያት ነው።” ሲሉ ተናግረዋል፡፡
“የኮልፌ የገበያ ማዕከል ብቻ ሳይሆን፣ የለሚ ኩራ ማዕከል ጭምር መብራት የገባለት በቅርብ ጊዜ ነው። በተመሳሳይ መልኩ፣ የኮልፌ ማዕከል የመንገድና የመብራት ችግር አለበት። አቃቂም ላይ የመንገድ ችግር አለ። እነዚህን ችግሮች ለመቅረፍ ከአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ጋር በመመካከር ወደ ስራ ተገብቷል።” ሲሉም አስረድተዋል፡፡
የምርት አቅርቦትን በተመለከተም የንግድ ቢሮ ሃላፊዋ እንዲህ ይላሉ፤ “ከሁሉም የገበያ ማዕከል በየቀኑ ዕለታዊ መረጃ እንወስዳለን። በየገበያ ማዕከላቱ ያሉ ምርቶችንና የሸማቹን ፍላጎት እንጠይቃለን። አንደኛው ገበያ ላይ የተትረፈረፈ ምርት ካለ፣ ነጋዴዎቹን የምርት እጥረት ወዳለበት እንዲወስዱ እናደርጋለን፡፡ እስካሁን ግን ያን ያህል የምርት እጥረት ችግር አልገጠመንም። አዲስ አበባ ላይ ተፈልጎ የታጣ ምርት የለም።”
በገበያ ማዕከላቱና በመደበኛው ገበያ ላይ ያለው የዋጋ ልዩነት የሚገናኝ አይደለም የሚሉት የቢሮ ሃላፊዋ፤ በጤፍ ዋጋ ላይ በትንሹ የ2500 ብር የዋጋ ልዩነት መኖሩን ይጠቅሳሉ፡፡ “ሆኖም ሌሎች ገበያዎች ላይ ያለው የሸማች እንቅስቃሴ በገበያ ማዕከላቱ ላይ አይታይም፡፡ በእኛ በኩል ማሕበረሰቡ አላወቀም ብለን ነው የምናስበው።” ይላሉ፡፡
ማዕከላቱን የማስተዋወቁ ስራ ላይ የሚቀሩ ነገሮች እንዳሉ በግምገማችን ለይተናቸዋል፤ ባይ ናቸው፡፡ ለዚህም በቀጣዮቹ ስድስት ወራት የገበያ ማዕከላቱ ከሌሎች የገበያ ስፍራዎች ያላቸውን የዋጋ ልዩነት ፍንትው አድርገው የሚያሳዩ የማስተዋወቅ ሥራዎች ለመሥራት ዕቅድ መያዙን ጠቁመዋል፡፡
በቀጣይ እየሰሩ ያሉትን ሥራ አስመልክተው ወ/ሮ ሃቢባ ሲራጅ ሲናገሩ፤ ከአዲስ አበባ ቴክኖሎጂ ቢሮ ጋር በመተባበር፣ በየገበያ ማዕከላቱ የሚገኙ ካሜራዎችን የማስተሳሰር ሥራ እንሰራለን፤ ይላሉ። “ካሜራዎችን ካስተሳሰርን በኋላ፣ የየገበያ ማዕከላቱን ዕለታዊ ዋጋ የምናወጣው እኛ ነን። በማዕከላቱ ውስጥ ስክሪን ስላለ፣ ዋጋው በዚያ በኩል እንዲታይ ይደረጋል። በተጨማሪም፣ በየገበያ ማዕከላቱ ያለውን ዕለታዊ ዋጋ የሚያሳውቅ መተግበሪያ እያዘጋጀን ነው። ማንኛውም ሸማች ባለበት ቦታ ሆኖ የየማዕከላቱን ዋጋ በቴክኖሎጂ አማካይነት እንዲያውቅ ነው እየሰራን ያለነው።” ሲሉ አስረድተዋል፡፡
እነዚህ ሁሉ በሂደት እየተሟሉ ሲመጡ የገበያ ማዕከላቱ በእርግጠኝነት የታለመላቸውን ግብ ሙሉ በሙሉ እንደሚያሳኩ አያጠራጥርም፡፡ አሁንም ግን የኑሮ ውድነትን ጫና እያቃለሉና ገበያውን እያረጋጉ ስለመሆናቸው ምስክሮቹ ራሳቸው ሸማቾቹ ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የስፖርት ፌስቲቫል በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዮኒቨርስቲ አዘጋጅነት ዛሬ ይጀመራል። የስፖርት ፌስቲቫሉ በተለያዩ ምክንያቶች ለዘጠኝ ዓመታት ተቋርጦ የቆየ ነበር። በአዲስ መልክ እንዲጀመር የኢትዯጵያ ዩኒቨርሲቲዎች የስፖርት ማህበርና የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ልዮ ትኩረት በመስጠት ተንቀሳቅሰዋል።
የስፖርት ፌስቲቫሉ እስከ ጥር 27 በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዮኒቨርስቲና በአካባቢው በሚገኙ የስፖርት ሜዳዎች የሚካሄድ ሲሆን 49 የኢትዯጵያ ዩኒቨርሲቲዎች እንደሚሳተፉበት ይጠበቃል። በአምስት የስፖርት አይነቶች እግር ኳስ ፤ አትሌቲክስ ፤ ዎርልድ ቴኳንዶ ፤ ቼዝና የባህል ስፖርት ውድድሮች እንደሚካሄዱም ታውቋል።
የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ደረጀ እንግዳ እንደተናገሩት ስፖርት በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እንዲስፋፋ መስራት ያስፈልጋል። “ስፖርት ለአንድነትና ለጋራ እድገት” በሚል መርህ ፌስቲቫሉ እንደሚካሄድ ጠቅሰው ዮኒቨርስቲያቸው ለፌስቲቫሉ ተሳታፊዎች የምግብና የማደርያ አገልግሎት ለመስጠት መዘጋጀቱን የስፖርት ውድድሮችን በግቢው እና በአቃቂ ቃሊቲ ሌሎች ሜዳዎች ላይ እናስተናግዳለን ብለዋል።
በፌስቲቫሉ ላይ በአህጉራዊና ዓለምአቀፋዊ ውድድሮች ኢትዮጵያን መወከል የሚችሉ ፕሮፌሽናል ስፖርተኞች ማፍራት እንደሚቻል የገለፁት ደግሞ የኢትዯጵያ ዩኒቨርሲቲዎች የስፖርት ማህበር ፕሬዝዳንት አቶ አባይ በላይሁን ናቸው። በኢትዮጵያ ስፖርት ላይ መነሳሳትን እንደሚፈጥርና በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የስፖርት ማዘውተሪያዎችን ልማት ለማጠናከር እንደሚያግዝም አብራርተዋል። በፌስቲቫሉ ላይ ከሚገኙት 49 ዮኒቨርስቲዎች 46 በእግር ኳስ ቡድኖቻቸው መሳተፋቸውን የጠቆሙት አቶ አባይ በእግር ኳስ ላይ የሚሰሩ ክለቦች፤ የክለብ ባለቤቶችና መልማዮች ፌስቲቫሉን በመታደል እድሎችን እንዲፈጥሩ ጥሪ አቅርበዋል።
ከሚቀጥለው ዓመት ጀምሮ በየክልሎቹና በከተማ መስተዳድሮች ያሉ ዮኒቨርስቲዎች በክላስተር አደራጅቶ የውስጥ ውድድሮች በማካሄድ በአሸናፊዎች አሸናፊ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የስፖርት ፌስቲቫልን ለማከናወን መታቀዱን የኢትዯጵያ ዩኒቨርሲቲዎች የስፖርት ማህበር ፕሬዝዳንት አቶ አባይ በላይሁን አስታውቀዋል።

እጅግ አድርገው ቀልድ ወዳጅ የነበሩ አንድ ሀብታም ጌታ ነበሩ፡፡ እንደ ጌታው ቀልድ ወዳጅ የሆነ አንድ አጋፋሪም ነበራቸው፡፡ አንድ ቀን ጌታው አንዲት ያልተገራች በቅሎ ይገዛሉ፡፡ በቅሎይቱ ለአገሩ እንግዳ ለሰው ባዳ ናት፡፡ ስለዚህም ጌትዬው አጋፋሪውን ይጠሩና “እቺን በቅሎ ጫንና መንገድ አሳያት” ብለው አዘዙት፡፡ አጋፋሪውም ትዕዛዙን ተቀብሎ፣ በቅሎዋን ጭኖ፣ ተቀምጦባት መጭ አለ፡፡ አንድ መንታ መንገድ ላይ ሲደርስ፣ ዱብ አለና በቅሎዋን፤
“በቅሎ ሆይ፤ ያውልሽ እንግዲህ፡፡ የሸዋ መንገድ ይህ ነው፡፡ የጎጃም መንገድ ይህ ነው፡፡ የጎንደርም መንገድ ይህ ነው፡፡ የትግሬም መንገድ ይህ ነው፡፡ ጌታሽ መንገድ አሳያት ብለውኛልና የወደድሺውን መንገድ ይዘሽ ሂጂ” ብሎ እንደተጫነች ለቀቃትና እሱ ወደ ቅልውጡ ሄዶ አምሽቶ ወደ ጌታው ተመለሰ፡፡ ጌታውም፡- “ለበቅሎዋ መንገድ አሳየሃት? ሲሉ ጠየቁት፡፡
“አዎን ጌታዬ የአራቱንም አገር መንገድ አሳይቼአት ሳበቃ የወደድሺውን ያዥና ሂጅ ብዬ ለቀቅኋት፡፡” ብሎ መለሰ፡፡ ጌትየው በጣም ተናደዱ፡፡ በነጋታው “ተነሱ ፍለጋ እንሂድ” ብለው አሽከሮቻቸውን ሁሉ አስከትለው ፍለጋ ተሰማሩ፡፡ በቅሎዋ ድራሿ ጠፋ፡፡ በመጨረሻ ያ የጣላት አጋፋሪ ራሱ መልሶ አገኛት፡፡ ዳሩ ግን ገሚስ ጎንዋን ጅብ ተጋብዟት ነው ያገኛት፡፡ በመካያው አጋፋሪው በሌላ አቅጣጫ ወደሄዱት ወደ ጌታው ዘንድ አመራ፡፡
ጌትየው፡- “እህስ ምንም ፍንጭ የለም?” አሉና ጠየቁት ገና ሲያዩት፡፡
“እንዴት ፍንጭ አይኖርም፤ አለ እንጂ ጌታዬ! ግማሿን በቅሎ አግኝቻታለሁ፡፡ ግማሿን ለጅብ አካፍላዋለች” ሲል መለሰላቸው፡፡
* * *
በማንኛውም ወቅት የጅብ ሲሳይ እንዳንሆን መንገድ የሚያሳይ እንጂ መንገድ ላይ የሚጥለን መሪ፣ ኃላፊ፣ ሹም አይጣልብን ማለት ደግ ፀሎት ነው፡፡ አቅጣጫ ሳይለዩ አለ በተባለው በተለመደው መንገድ ሁሉ ጊዜ - አለጊዜ መሄድ ትርፉ እንደ በቅሎዋ መበላት ነው፡፡ አዲስ መንገድ ማየትና መልመድ የሚቻለው በመጀመሪያ ያ መንገድ ሁነኛው መንገድ፣ ጅብ የማያስበላው መንገድ፣ መሆኑን ልብ እንድንል የሚያደርግ በአገር ጉዳይ የማይቀልድ፣ የማያስበላን አጋፋሪ ሲገኝ ነው፡፡
ወደ ዘላቂ ኢኮኖሚያዊ እድገት የሚያደርሰን መንገድ የቱ ነው? ከሙስና የፀዳ ሹምና ሿሚ የምናገኝበት መንገድ የቱ ነው? ፍትህ ወደሰፈነበት፣ ወገናዊነት ወዳልተንሰራፋበት፣ ሰው በሰውነቱ ወደሚከበርበት፣ በጠባብ አመለካከት ወደማንታወርበት፣ “ከእኔ በስተቀር ለሌላ ጌታ አትደር” የሚል ክፉና ቀናኢ ጌታ ወደማይኖርበት፣ ሰፊ የፖለቲካ ሥርዓት የሚወስደን አውራ ጎዳና የትኛው ነው? የተለያዩ የፖለቲካ ቡድኖች ወደሚቋደሱበት የስልጣን ገበታ የሚወስደው፤ “ጎንህ እንዲያርፍ፣ የጓደኛህ ጎን ይረፍ” ለማለት የሚችሉ የተለያየ አመለካከት ያላቸው ወገኖች ለሀገር ሲሉ ልዩነቶቻቸውን አቻችለው በአንድ መድረክ ወደሚነጋገሩበት የፖለቲካ ጀማ የሚያመራው፣ “አፈ-ቅቤ ልበ-ጩቤ” ወደማይበዛበት ብሄራዊ ሸንጎ የሚያቀናው ሁነኛ ጥርጊያ መንገድ የቱ ነው? አዲስ ብለን የመረጥነው አቅጣጫ፣ አዲስ ብለን የሾምነው ሹም፣ አዲስ ብለን የጠመቅነው አስተሳሰብ፣ “አሮጌ ጠላ በአዲስ ጋን” ወደማይሆንበት “የአካሄድ”ና “የሥርዓተ-ሲመት” እንዲሁም “የአቋቋም” ፖሊሲዎቻችን መልሰው እግ -ተወርች ወደማያስሩበት ወግ (Order) የምንደርሰውስ በምን መላ ነው? ነገ የሚታለመው ሥርዓት ሁሉ በአንድ ተውኔት ውስጥ በምፀት እንደተጠቀሰው፤ “ዐይናማው ብለነው እውር ሆኖ ቢወለድስ?”፣ “ክንዴ ብለነው ክንደ-ቆራጣ ቢሆንስ?” ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡
“የአዛውንቶች ልብ ባህር ነው፣ ግን አይዋኝበትም” እንዲል መፅሐፈ-ትግሬ፣ የአዋቂዎቻችንን፣ የብልህ አረጋውያንን እውቀት ለመጠቀም የሚያስችለን መንገድ የትኛው ነው? ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ “አስተዋይ ሰው ወይ ገለል ሲል፣ ወይ አገር ለቅቆ ሲሄድ ይታወሳል” ይባላልና በየሰበብ አስባቡ ከአገር ወጥተው በውጭ አገር የሚገኙ አስተዋይ ኢትዮጵያውያንን አእምሮስ የምንጠቀምበት ምን ዓይነት መንገድ አለ? ብሎ መጠየቅ ያሻናል፡፡ ለሀገርና ለህዝብ ሲባል የሚጠየቅ ጥያቄ ይህ ወሰንህ፣ ይህ ዲካህ የሚባል አይደለም፡፡ የተመኘነው እስኪገኝ፣ የጎደለው እስኪሞላ መጠየቅ አለበት፡፡ የሚመለከተው ክፍልም ደከመኝ፣ ታከተኝ ሳይል መልስ መስጠት አለበት፡፡ ትክክለኛ መንገዶችን መጠ|ቆም፣ ማሳየት፣ እንዴትስ እንደሚኬድበት መነጋገር የግድ ነው፡፡
መቼም “አገርና አውድማ መክደኛ አለው” ይሏልና ለየጉዳዩ ሁሉ ቁልፍ ማበጀት፣ መፍትሄና መንገድ ማግኘት አስፈላጊ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ከእንግዲህ የየሥርዓቱ የቤተ-ሙከራ መፈተኛ - እንስሳ (Guinea-pig) መሆንን የምትሸከምበት ጥኑ ትከሻ የላትም፡፡ የእርስ በርስ ጦርነትና ግጭቷ፣ ማህበራዊ ቀውሷ፣ የኑሮ ውድነቷ፣ የሹመኞች ሙስና፣ የዜጎች ተስፋ ማጣት ---. ሁሉም የችግር ጠርዞች መፈናፈኛ እያሳጧት ወደ ሌላ የፖለቲካና የሥነ-አዕምሮ አለመረጋጋት ወጀብ ውስጥ እንዳይከታት ብርቱ ጥንቃቄን ይጠይቃል፡፡ የምንሰራው ሁሉ ባይሳካም እንደገና እንሞክረዋለን ወደሚልና ሌላ የሙከራ -ቅጽ ወደመሙላት የሚያስኬድ የሚያወለዳ ሁኔታ ከቶ የለም፡፡
“በልታ በልታ ጨው የለውም፣ ሄዳ ሄዳ መንገድ የለውም አለች” እንደሚባለው፤ ጉዟችን ለዕድገት ወደሚከፈት በር እንጂ ወደተገደገደ - አጥር (Dead-end) ከሆነ ለሀገር ትልቅ እርግማን ነው፡፡ ከዚያ ይሰውረን፡፡

- ከ60 አገራት የተውጣጡ 100 እንግዶች ይሳተፋሉ

ዓለማቀፍ የቁርአንና አዛን ውድድር በኢትዮጵያ ለሁለተኛ ጊዜ ሊካሄድ መሆኑ ተገለፀ። የፊታችን ጥር 25 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ስቴዲየም በሚካሄደው ታላቅ ዓለም አቀፍ የቁርአን ውድድር ላይ ከ60 አገራት የሚመጡ 100 የሚደርሱ ተወዳዳሪዎች፣ የልኡካን ቡድን ተሳታፊዎች እንዲሁም ኢንቨስተሮችና ታዋቂ ግለሰቦች እንደሚገኙ ተጠቁሟል።

በዛሬው ዕለት ምሽት በዚህ ውድድር ላይ የሚሳተፉ የውጭ አገር እንግዶች ወደ ኢትዮጵያ መግባት እንደጀመሩ አዘጋጆቹ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

የውድድር መድረኩ ቱሪስቶችን ወደ አገራችን ለመሳብ ትልቅ ሚና እንደሚኖረው የተገለፀ ሲሆን፤ የአገር ገጽታ ግንባታ አበርክቶውም የጎላ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

በዘይድ እብን ሳቢት የቁርዓን ማህበር አዘጋጅነትና በኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤት የበላይ ጠባቂነት የሚካሄደውን ይህን የቁርዓን ውድድር አስመልክቶ፣ ባለፈው አርብ ጥር 16 ቀን 2017 ዓ.ም በኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል መግለጫ ተሰጥቷል።

ውድድሩ በሁለት መርሃ ግብር የተከፋፈለ መሆኑን ያብራሩት አዘጋጆቹ፣ የመጀመሪያው የማጣሪያ ውድድር በዛሬው ዕለት ጥር 19 ቀን 2017 ዓ.ም በኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል የተካሄደ ሲሆን፤ ሁለተኛውና የፍፃሜው ውድድር ደግሞ በአዲስ አበባ ስቴዲየም ጥር 25 ቀን 2017 ዓ.ም በዕለተ እሁድ በደመቀ ሁኔታ ይካሄዳል ተብሏል።

ዓለማቀፍ የቁርአንና አዛን ውድድሩ ለመስተንግዶ ከፍተኛ ባጀት እንደሚጠይቅ የተናገሩት አዘጋጆቹ፤ የዚህ ውድድር ባለቤት የኢትዮጵያ ህዝብ በመሆኑ አብዛኛው የፋይንስ ምንጭም ባለቤቱ የኢትዮጵያ ህዝብ ነው ብለዋል።

ለዚህም አጋዥ ይሆን ዘንድ አማራጭ የመግቢያ ትኬቶች መዘጋጀታቸው ተጠቁሟል። የቪአይፒ ትኬት 5ሺ ብር፣ የመደበኛ ትኬት 800 ብርና የተማሪዎች መግቢያ ትኬት ደግሞ በ400 ብር መዘጋጀቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ታላላቅ የዓለም አቀፍ ሚዲያዎችን ትኩረት እንደሚስብ በተነገረለት በዚህ የቁርአንና የአዛን ውድድር፤ ከተለያዩ የዓለም አገራት 100 የሚደርሱ እንግዶች ይመጣሉ ተብሏል። ከአገራቱም መካከል አሜሪካ፣ ህንድ፣ ቱርክ፣ ሩሲያ፣ ኖርዌይ፣ ኳታር፣ ሳኡዲ አረቢያ፣ አልጀሪያ፣ ፍልስጤም፣ ጅቡቲና ሌሎች አገራት እንደሚገኙበትም ተነግሯል።

የቁርአን ውድድሩ አዘጋጆች እንደሚያስረዱት፤ ይኼ ታላቅ ዓለማቀፍ ውድድር ከሃይማኖቱ ባሻገር ከፍተኛ አገራዊ ፋይዳ ያለው ነው። በአንድ በኩል ብዝሃነታችንን እንዲሁም የተፈጥሮ ሃብታችንን ለዓለም የምናሳይበት መልካም አጋጣሚ ነው የሚሉት አዘጋጆቹ፤ ቱሪስቶችን ወደ አገሪቱ ለመሳብም ትልቅ አስተዋፅኦ ያደርጋል ብለው ያምናሉ፡፡ ከመካከለኛው ምስራቅ አገራት ጋር ያለንን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ለማጠናከርም ፋይዳው የጎላ መሆን ያስረዳሉ።

ለውድድሩ ወደ አዲስ አበባ የሚገቡ ተሳታፊዎችና እንግዶች ለሳምንት ያህል በመዲናዋ እንደሚቆዩ የገለፁት አዘጋጆቹ፤ ነዋሪው እንግዶቹን ሁሌም በሚታወቅበት ኢትዮጵያዊ መስተንግዶ እንዲቀበል ጥሪ አቅርበዋል፡፡

ዓለም አቀፍ የቁርዓንና የአዛን ውድድር ሽልማት ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያ የተካሄደው የዛሬ 3 ዓመት በ2014 ዓ.ም ሲሆን፤ ይሄኛው ዓለማቀፍ ውድድር ሲካሄድ ለሁለተኛ ጊዜ መሆኑ ነው፡፡

ዓለም አቀፍ የቁርአን ንባብ ውድድር ባህላዊ፣ መንፈሳዊና ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮችን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች ትልቅ ፋይዳ እንዳለው የእስልምና ሃይማኖት ታሪክ ተመራማሪና ደራሲ የሆኑት ተሾመ ከድር ብርሃኑ ይናገራሉ፡፡ እነዚህ ውድድሮች፤ ተሳታፊዎችና ታዳሚዎች ስለ ቁርአንና ኢስላማዊ አስተምህሮ ያላቸውን ግንዛቤ እንዲያሳድጉም ያበረታታል ይላሉ፡፡

በተጨማሪም፤ አስተናጋጅ ሀገራት ተሳታፊዎችን፣ ቤተሰቦችንና ተመልካቾችን ጨምሮ በሺዎች የሚቆጠሩ ጎብኚዎችን ይስባሉ። ይህም ለአካባቢው ኢኮኖሚና ቱሪዝም ዘርፍ ገቢ እንደሚያስገኝ ይገልጻሉ፡፡

መድረኩ የአስተናጋጅ ሀገር ባህላዊና ታሪካዊ ቅርሶችን ያሳያል፣ ወደፊትም ብዙ አለም አቀፍ ጎብኚዎችን ይስባል፤ ሲሉ መሰል የቁርአን ውድድሮች ያላቸውን ፋይዳ አስረድተዋል፡፡

አርቲስት ተስፋዬ ማሞ ሁለገብ የኪነጥበብ ሰው ነው፡፡ በማስታወቂያ ሥራዎቹ ይታወቃል፡፡ ደራሲና የፊልም ባለሙያም ነው፡፡ የሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጅም ነው፤ ተስፋዬ ማሞ፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጣ 25ኛ ዓመትን አስመልክተን ቃለምልልስ አድርገንለታል፡፡
ከአዲስ አድማስ ጋር እንዴት እንደተገናኘና እንደተዋወቀ ያወጋናል፡፡ ጋዜጣው ብዙ ዋጋ እንደተከፈለበትም ይናገራል፡፡ ሁሉንም ከባለቤቱ አንደበት እነሆ፡-

 ለመሆኑ ተስፋዬ እና አዲስ አድማስ ጋዜጣ እንደምን ተገናኙ?

ከአዲስ አድማስ ጋር የተገናኘነው ገና ሳትወለድ በፊት ነው። መጀመሪያ የተዋወቅነው ከአሰፋ ጎሳዬ ጋር ነው። አሰፋ የዓለምን ካርታ በአማርኛ ከሰራ በኋላ ማስታወቂያዎችን ይሰራ ነበር። ለፒኤስአይ፣ ለዲኬቲ ኢትዮጵያ የሚሰራቸው ማስታወቂያዎች ነበሩ። እናም፣ እነዚህን ማስታወቂያዎች እኔ ነበርኩ በድምጽ የማነብለት። በዚህ ምክንያት ከአሰፋ ጋር የወንድም ያህል ጓደኛሞች ነበርን። የማንነጣጠል -- አብረን የምንበላ፣ አብረን የምንጠጣ፣ አብረን የምንዞር፣ አብረን የምንውል -- ጓደኛሞች፡፡ እና፣ አሰፋ ህልሙን ሲያልም ጀምሮ አውቃለሁ፤ አዲስ አድማስን። ምክንያቱም አዲስ አድማስ ከመምጣቱ ከዓመታት በፊት -- ጋዜጣው እስከሚወለድበት፣ እስከ 1992 ድረስ ጽሁፎችን ይሰበስብ ነበር። አሪፍ ጽሁፎችን ሲያገኝ ይሰበስባል፡፡ አዲስ አድማስ ላይ ይወጡ የነበሩ የባሴ ሃብቴ ጽሁፎች በሙሉ በዚያ ጊዜ የተሰበሰቡ ናቸው። ጥሩ ጽሁፍ፣ ጥሩ ሃሳብ ካገኘ አንድ ቀን አንድ ነገር “ሊሆን ይችላል” እያለ ይሰበስብ ነበር፡፡ ”አዲስ አድማስ” ተብሎ ስም አይውጣለት እንጂ የሕትመት ስራ እንደሚሰራ ያውቅ ነበር፤ አሰፋ። በዚህም ምክንያት ጽሁፎችን ሲያከማች ነው የቆየው፡፡ እየተረጎምን ጽሁፎችን እናስቀምጥ ነበር። እኔ ዘንድ የ“ሪደርስ ዳይጀስት” በጣም ብዙ ቅጾች ነበሩ፡፡ “ጉድ ሃውስ ኪፒንግ” የሚባል መጽሔቶችም ነበሩኝ። እነዚያን መጽሔቶች ይዘን፣ በእነርሱ ላይ ተመስርተን ሃሳቦችን እንከትብ ነበር። የዓመታት ድምር ሃሳቦች ውጤት ነው አዲስ አድማስን እንዲወለድ ያደረገው። አዲስ አድማስ ከአድማስ አድቨርታይዚንግ ነው የወጣው፤ የአሰፋ መሰረት አድማስ ነውና፣ “አዲስ አድማስ ጋዜጣ” የሚባል ተመሰረተ።
መንገዱ ግን እንዲህ እንደማወራልህ አልነበረም፤ በጣም ከባድና በጣም አስቸጋሪ ነበር፡፡ እንግዲህ ከ1990 በፊት በነበሩት ጊዜያት፣ ገና ከጽንስ በፊት የሃሳብ መብላላቶች ውስጥ ነው አብረን የነበርነው። እንዲያውም የማልረሳው አሰፋ ወሎን በጣም ነበር የሚወደው፤ የወሎን ትውፊቶች፣ ታሪኮቹን በጣም ስለሚወድ፤ እኔም አወራው ስለነበር፤ “ሁኔታዎች ቢመቻቹ እያንዳንዱ የወሎ አውራጃ ውስጥ አንድ አንድ ወር ተቀምጠህ ታሪኮች ተጽፈው ቢመጡ” ይለኝ ነበር፡፡ ምክንያቱም ወሎ በጣም ብዙ ትውፊትና በጣም ብዙ ታሪክ ያለበት አገር ስለሆነ፣ እዚያ ድረስ አሰፋ ለጽሁፍ ክምችት በጣም ያስብ ነበር።
እንግዲህ ይህ ሁሉ የጽሁፍ ክምችት ተሰበሰበ፣ አጠቃላይ ሂደቶች ተከናወኑና ወደ ሕትመት ሊገባ ነው። የሕትመት ቅድመ ዝግጅቱ ምን ይመስል ነበር?
የአድማስ አድቨርታይዚንግ ቢሮ ራስ ሆቴል ፊት ለፊት ነው የነበረው። በዚያ ቢሮ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ይሰሩበት ነበር፡፡ አዲስ አድማስ እንደ ጋዜጣ ስም ወጥቶለት፣ ሥራ ለማስጀመር ሲታሰብ ግን ንግድ ማተሚያ ቤት አካባቢ፣ አንድ ቤት ለአጭር ጊዜ ተከራየ፡፡ የመጀመሪያው የአዲስ አድማስ የሥራ ቦታ እዚያ ነው የነበረው። ብዙ ሠራተኛ አልነበረውም።
ምን ያህል ሠራተኞች ነበሩ?
አሰፋ ራሱ፣ ሰለሞን ጎሳዬ፣ ሰዓሊው መስፍን ሃብተማርያም፣ የውብዳር የምትባል ጸሐፊ... እና ጌታቸው አበራ ነበረ። በተረፈ አዳዲስ -- ገና ብቅ ብቅ የሚሉ ልጆች ናቸው የነበሩት። እነ ነቢይ መኮንን ያኔ አልመጡም ነበር። ነቢይ በኋላ እዚህኛው ቢሮ ከተቀየረ በኋላ ነው የመጣው። የቅድመ ዝግጅትና የመጀመሪያዎቹ የአዲስ አድማስ ሕትመት የጀመረው እዚህ ንግድ ማተሚያ ቤት አካባቢ የነበረው ቢሮ ነው። እርሱ ቦታውም፣ ሁኔታውም ጥሩ ስላልነበር -- ሦስት ወይም አራት ወር መቆየቱን እርግጠኛ አይደለሁም -- ያን ያህል ጊዜ አልቆየም። ለአጭር ጊዜ ነው የቆየው። እርሱ ተለቅቆ ለም ሆቴል አካባቢ አንድ ሌላ ቢሮ ውስጥ ተገባ። ሲጀመር፣ እንደ ኮቴጅ (ጎጆ) ኢንዱስትሪ በቤተሰብ፣ በጓደኛና በዙሪያው ባለን ሰዎች ነው የተጀመረው። እኔ ሁለት ዓምዶችን ይዤ ነበር፤ “ካሰብነው ይገርማል” የሚል እና አንድ ሌላ “በሳምንቱ ውስጥ ምን አለ? ምን ትጠብቃላችሁ?” የሚል። በኋላ እነ ነቢይ መኮንን መጡ። እነ ሰለሞን ገብረ እግዚአብሔር መጡ፡፡ እነ ሰለሞን አበበ ቸኮል (ሰአቸ) መጡ። ከዚያ እያደገ ሄደ።
አዲስ አድማስ ጋዜጣ መታተም እንደጀመረ በቀላሉ አልተለመደም፤ በርካታ ኮፒዎች ከገበያ ይመለሱ ነበር። ይታተማል፤ ተመልሶ ይመጣል። ለማስለመድ የነበረው መከራ ቀላል አልነበረም፡፡፡ አንዳንድ ሰዎች፤ “አሰፋ፣ ይህ ብርቱካናማ ቀለም ይቀየር፣ ሰውን የሚገፋብን ቀለሙ ነው” ይሉት ነበር። አሰፋ ደግሞ፤ “የአባቴን ቤት እስከመሸጥ እሄዳለሁ እንጂ ይህንን ሎጎ አልቀይረውም። ከአቋሜ፣ ከያዝኩት ስታንዳርድ አንዲት ኢንች ዝቅ አልልም” ይል ነበር። ምክንያቱም ያኔ ጊዜው የገተር ፕሬስ (Gutter Press) -- የእነ”ጎዳናው” -- ጊዜ ነው የነበረው። አሁን ፌስቡክ ላይ እንዳለው፣ መንችፎ የመሮጥ ዓይነት ነገር የለም? በብዛት የሚነበቡት እንደእነርሱ ዓይነት ጋዜጦች ነበሩ። ሆሮስኮፕ ያላቸው፣ የፈረንጅ ታሪኮች ተተርጉመው የሚወጡባቸው ጋዜጦች ነበሩ የተለመዱት። በዚያ መሃል ቁምነገሮችና ዕውቀት የሚያስጨብጥ፣ ፍልስፍናን የተሸከሙ ሃሳቦች ያሉት አዲስ አድማስ ጋዜጣ መጣ። ያልተለመደ ነበር፤ በዚህም የተነሳ በነጻ እስከመበተን ተደርሷል፤ ለማስለመድ፡፡ ምሁሩና የማንበብ ፍላጎት ያለው ሰው ዘንድ እንዲደርስ በጣም ብዙ ተሰርቷል፤ በሸክም ወጥቶ በሸክም እየተመለሰ፣ አዟሪዎች እጅ ላይ ይቆይ ነበር፡፡ ደግነቱ አዲስ አድማስ ሳምንትም፣ ወርም፣ ዓመትም ቆይተህ ብታነብበው፣ አያልፍበትም፡፡ ሁሌም የሚነበብ ጋዜጣ ነው፡፡
እንዲህ እንዲህ እያለ ቀስ በቀስ አዲስ አድማስ በየሳምንቱ ቅዳሜ በናፍቆትና በጉጉት የሚጠበቅ ጋዜጣ ለመሆን በቃ። ግን ብዙ ዋጋ ተከፍሎበታል፤ ዝም ብዬ ቀለል አድርጌ እንደምነግርህ አይደለም፡፡ ያ ሁሉ ተለፍቶ፣ ያ ሁሉ ጽሁፍ ተጠራቅሞ የሚሰራው ስራ እስኪለመድ እየተመለሰ ሲመጣ ምን ያህል አስቸጋሪ እንደነበረ መገመት ይቻላል፡፡ ...persistence የሚባለውን ነገር እኔ ያየሁት ያኔ ነው፡፡ አሰፋ በዚህ በጣም የሚገርም ሰው ነበር፡፡ “የአባቴ ቤት ካስፈለገ ይሸጣል እንጂ አላፈገፍግም” የሚል አቋም ስለነበረው፣ በአቋሙ ጸንቶ ከደረጃው ዝቅ እንዳይል በደረጃው እንዲያድግ አድርጎ፣ በዙሪያውም ሌሎች ብዙ ሰዎች እንዲሰሩ በማድረጉ ምክንያት ነው ለተወዳጅነት የበቃው።
ከመጀመሪያው ዕትም በአዕምሮህ ውስጥ ጎላ ብሎ የሚታወስህ ዓምድ የትኛው ነው?
ጋዜጣው በቂና ሙሉ ዝግጅት የተደረገበት በመሆኑ ምሉዕ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ እያንዳንዱ ዓምድ ራሱን ችሎ የቆመ ነበር፤ አንደኛው ከሌላኛው ጋር የሚነጻጸር አልነበረም፡፡ ሁሉም በራሱ ሙሉ ነው፡፡ ከሳምንት ሳምንት የሚነበብ ጋዜጣ ነው የነበረው፡፡ የካርቱን ምስሎቹ፣ የገጽ ቅንብሩ፣ መልኩ ሁሉ የሚያምር ጋዜጣ ነው። በዝግጅት በአቀራረብና በይዘት፣ በቅንብርም ደረጃ የተስተካከለና የተሟላ እንዲሆን ብዙ ጥረት የተደረገበት ጋዜጣ ነው፡፡ ስለዚህ የምትጥላቸው ጽሁፎች አልነበሩም።
በዚህ መልኩ የጀመረው አዲስ አድማስ የዘለቀበትን መንገድ እንደ አንድ አብሮ እንደነበረና ኋላም በቅርብ ርቀት ሆኖ እንደሚከታተል ሰው የጋዜጣውን ዕድገት እንደምን ነበር የምትገመግመው?
እኔ ረዥሙን ጊዜ ከጋዜጣው ጋር አብሬ ነበርኩ፤ አልጻፍና ወደ ራሴ ስራ አልምጣ እንጂ። ምክንያቱም ከጅማሮ አንስተህ አብረህ የነበርክበት ስራ ወይም አንድ ልጅ ተወልዶ ሲያድግ ዓይንህ መከተሉ አይቀርም። ስለዚህ በተመሳሳይ ሁኔታ አዲስ አድማስን እከተል ነበር። አዲስ አድማስ እንደነገርኩህ ሲጀመር በጣም ከፍ ተደርጎ ነው የተጀመረው፡፡ ስለዚህም ሰዎች አንብበው የማይጥሉት ጋዜጣ ነው የሆነው፡፡ ብዙ ቦታዎች ላይ ክበቦች፣ ትናንሽ የጓደኛሞች ስብስብ ነበሩ፤ አዲስ አድማስን ቅዳሜ ቅዳሜ ጠብቀው ቁጭ ብለው አንብበው የሚወያዩ። አዲስ አድማስ ጋዜጣ የመወያያ፣ የመነጋገሪያ አጀንዳ ነው የነበረው፡፡ ከዚያም በናፍቆት የሚጠበቅ ጋዜጣ ሆኖ ነው የዘለቀው፡፡ በሁሉም ዘንድ የሚወደድ፣ ሁሉም ሰው ሊጽፍበት የሚፈልግ፤ ሃሳቦቹን የሚያንጸባርቅበት፣ ጽሁፎቹን የሚልክበት ጋዜጣ ነው የሆነው፡፡ አዲስ አድማስ ውስጥ ባሉ አዘጋጆችና ተባባሪ አዘጋጆች ብቻ ሳይሆን ከውጭ እንደ ጋሽ ስብሐት ገብረእግዚአብሔር፣ ኤፍሬም እንዳለ፣ መስፍን ሃብተማርያም ወዘተ ያሉ በርካታ ዕውቅ የብዕር ሰዎች ይጽፉበት ነበር። እነ አብርሃም ረታ ዓለሙን የመሳሰሉ ጸሃፍት ሁሉ የሚጽፉበት ነበር፡፡ አገሪቱ ውስጥ አሉ የተባሉ ጸሃፍት በሙሉ የሚጽፉበት ትልቅ ጋዜጣ ለመሆን የበቃ ነው፡፡
ገጣሚ ነቢይ መኮንን በዋና አዘጋጅነት በጋዜጣዋ ላይ በሰራባቸው ዓመታት የነበረውን ሚና እንዴት ትገልጸዋለህ?
አየህ፣ አሰፋ አርቆ አሳቢ ነበር። አርቆ አሳቢ በመሆኑ ምክንያት አዲስ አድማስ ጋዜጣን ሲጀምር፣ እንደገና “አድማስ ፕሮዳክሽን” በሚል -- ወደ ቴሌቪዥን የማደግ ፍላጎት ነበረው---- እሱን ለማቋቋም ሲሰራ፣ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ የጋዜጣውን ሃላፊነት ለነቢይ ሰጥቶት ነበር። ነቢይ ደግሞ ከአድማስ በፊት በሜጋ ኪነ ጥበባት መጽሔት ያዘጋጅ ስለነበር፣ መልክ ያለው ጋዜጣ እንዲሆን አድርጎታል። ነቢይ ጥሩ ኤዲተር ነው። የቋንቋ ችሎታው በጣም አስደማሚ ነው። ሃሳብን የማዋዛት አቅሙ የላቀ ነው፡፡ በተረት እያዋዛ የሚጽፋቸው ርዕሰ አንቀጾቹ ጎልተው ወጡ እንጂ የግጥም ጥጎቹ ራሳቸው የሚገርሙ ነበሩ። በየሳምንቱ “የግጥም ጥግ” በሚል ግጥሞች የሚያወጣበት ጥግ ነበረው፡፡ ነቢይ አትኩሮ ይሰራ በነበረባቸው ዘመናት ሁሉ ጋዜጣው መልክ ኖሮት እንዲቀጥል የሚችለውን ያህል ጥረት አድርጓል።

የኢሮብ ሕዝብ በኤርትራ ጦር በደል እየደረሰበት መሆኑን የገለፀው የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)፤ የፌደራል መንግስት ይህንን በደል ለማስቆም ምንም ያደረገው ነገር የለም ሲል ተችቷል።
“የትግራይ ሕዝብ አሳር ሊያበቃ ይገባል” በሚል ርዕስ የኢሕአፓ የትግራይ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ባለፈው ረቡዕ ጥር 14 ቀን 2017 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ፣ አንዳንድ የትግራይ ክልል ወረዳዎች ከነሐሴ 28 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ በኤርትራ ጦር መያዛቸውን አመልክቷል። በተለይም “ከፍተኛ በደል እያስተናገደ ነው” ሲል ፓርቲው የጠቀሰውን የኢሮብ ሕዝብ ለመታደግ የፌደራል መንግስት “ምንም ዓይነት መፍትሔ” ሲሰጥ አለመታየቱን ጠቅሷል።
አያይዞም፣ የኤርትራ ጦር የኢሮብ ወጣቶችን በገፍ እያፈሰ ወደ ሳዋ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ተቋም እየወሰዳቸው እንደሚገኝ የጠቆመው ኢሕአፓ፤ “የትምሕርት ስርዓቱን በመቀየር በኤርትራ የትምሕርት ስርዓት እያስተማረ ይገኛል” ሲል በመግለጫው አትቷል። “ከፍተኛ የአገር ሉዓላዊነት ወረራ” መሆኑን የጠቆመው ፓርቲው፤ የፌደራል መንግስቱ ድርጊቱን የማስቆም ሃላፊነት እንዳለበት አሳስቧል።
በሌላ በኩል፣ በህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) አመራሮች መካከል የተፈጠረው መከፋፈልና መወነጃጀል የትግራይ ሕዝብ ሰላምና መረጋጋትን እንዳያገኝ ማድረጉን ፓርቲው አስታውቋል። “እነዚህ በሕዝብ ስም እየማሉ ሕዝብን ለመከራ በዳረጉ ሁለት ሃይሎች የመከኑ ፍላጎቶች የተነሳ የትግራይ ሕዝብ ሁሌም ከጎረቤቶቹ ጋር ጦርነት እየተማዘዘ ሰላም ርቆት ሊኖር አይገባም” ብሏል።
“ሕጋዊ እና ፍትሐዊ” ምርጫ ተካሂዶ የትግራይ ሕዝብ በእንደራሴዎቹ እስኪወከል ድረስ ሁሉንም ሕጋዊ ፓርቲዎች ያካተተ የመማክርት ምክር ቤት እንዲቋቋምም ኢህአፓ ጠይቋል። በህወሓት አመራሮች መካከል በተፈጠረው ውዝግብ የተነሳ የተፈጠሩት ሁለት አንጃዎች “በንግግርና በመቻቻል” አስቸኳይ ሰላማዊና ፖለቲካዊ መፍትሔ ማበጀት እንዳለባቸውም ፓርቲው አሳስቧል።
“በኢትዮጵያ ያሉ ብዙዎቹ የፖለቲካ ፓርቲዎች የትግራይ ሕዝብን የረሱት በሚመስል ሁናቴ አንድም ቀን ስለሕዝቡ ሲጨነቁ አይታይም” በማለት የነቀፋው ኢሕአፓ፤ አገራዊ ፓርቲዎች “ስለትግራይ ሕዝብነ ሲሉ ፖለቲካዊ መፍትሔ ማበጀት” ላይ እንዲሳተፉ ጥሪ አቅርቧል።

 

Page 3 of 753