Administrator

Administrator

የስነ ጥበብ ስራዎችን ለህብረተሰቡ በማቅረብ አማራጭ መድረክ የመፍጠርና ለጥበብ አፍቃሪያን በተለያዩ አጋጣሚዎችና ስፍራዎች የስነ ጥበብ ስራዎችን የመመልከት፣ የማድነቅና ቁምነገር የመቅሰም ዕድል የመፍጠር አላማ ይዞ የተቋቋመው ጉራማይሌ የስነ ጥበብ ማዕከል፣ ትናንት ምሽት ተመርቆ ተከፈተ፡፡
የማዕከሉ መስራችና ዳይሬክተር አቶ ሚፍታ ዘለቀ እንደተናገሩት፤ ጉራማይሌ የስነ ጥበብ ማዕከል፣ ስነጥበባዊ ዋጋው ከፍ ያለ ማህበረሰብ የመፍጠር፣ የስነ ጥበቡን ማህበረሰብ ከሰፊው ህብረተሰብ ጋር የማቀራረብ፣ ስነ ጥበብን መሰረት ያደረገ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ እንዲሁም መንፈሳዊ ብልጽግናን የመፍጠር ግብ ይዞ ነው የተቋቋመው፡፡
ትናንት ምሽት በተከናወነው የማዕከሉ የምረቃ ስነ ስርዓት ላይ፤ ታደሰ መስፍን፣ ደረጀ ደምሴ፣ ዘላለም ግዛው፣ ዳዊት አድነውና ሌሎች አንጋፋና ወጣት ሰኣሊያን የተሳተፉበት “ጉራማይሌ - አንድ” የተሰኘ የስዕል ትርዒት ለእይታ በቅቷል፡፡

በርካታ የሀገሪቱን ተዋንያን መፍለቂያ የሆነው እና ፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ የሚገኘው “ሚያዚያ 23” አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት እያከበረ ነው፡፡  በ1956 ዓ.ም “አስፋወሰን ካሳ” በሚል መጠሪያ ሥራ የጀመረው “ሚያዚያ 23” በመጪው ሐሙስ ከጧቱ ሦስት ሰዓት በሚከናወን ደማቅ ሥነ-ሥርአት የቀድሞ ተማሪዎቹ እና ያሁኖቹ የሀገሪቱ አንጋፋና ታዋቂ ከያንያንና ጋዜጠኞች በትምህርት ቤቱ እንደሚገኙ የተናገሩት የትምህርት ቤቱ ርእሰ መምህር አቶ ጌታቸው አዋሽ፤ እነዚሁ ከያንያን ልምድና ተሞክሮአቸውን እንዲሁም ትዝታቸውን ለአሁን ተማሪዎችና ተጋባዥ እንግዶች እንደሚያቀርቡ ጠቁመዋል፡፡ በተጨማሪም የተለያዩ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶች የሚቀርቤ ሲሆን 50ኛ ዓመቱን አስመልክቶ እየተካሄደ ያለው የእግር ኳስ ውድድርም ይጠናቀቃል፡፡ ሥራ ሲጀምር ከ120 በታች ተማሪዎች የነበሩት ትምህርት ቤቱ፤ አሁን 1560 ያሕል ተማሪዎች ያሉት ሲሆን ከቀድሞ ተማሪዎቹ መካከል አርቲስት ጥላሁን ዘውገ፣ ጋዜጠኛ አለምነህ ዋሴ፣ የቶክሾው አቅራቢው ሰለሞን ሹምዬ፣ አርቲስት ግርማ ተፈራ፣ አርቲስት አለልኝ መኳንንት እና ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት የኤፍኤም ጣቢያዎች ዳይሬክተር የነበረው ጋዜጠኛ ሳሙዔል እንዳለ ይገኙበታል፡፡

     በሽመልስ ይፍሩ (ጤርጢዮስ ከቫቲካን) የተዘጋጀው “የተመለሱና ያልተመለሱ ጥያቄዎቼ” የተሰኘው መፅሃፍ ታትሞ እየተሸጠ ነው፡፡
መጽሃፉ፤ አንዱን ቅዱስ መጽሐፍ እያነበቡ በተለያየ ስም የተጠሩበትንና የተለያየ አቋም የያዙበትን ዐብይ ምክንያት እንደሚፈትሽ የገለፀው አዘጋጁ፤ ርዕሰ ጉዳዩም ስለ እግዚአብሔር፣ ስለ ሰውና ስለ ክርስቶስ ባላቸው የእምነት ግንዛቤ ላይ ብቻ የሚያተኩር ነው ብሏል፡፡
በመፅሃፉ ውስጥ የኦርቶዶክስ፣ የካቶሊክ፣ የፕሮቴስታንት፣ የሐዋርያዊት (በተለምዶ Only Jesus የሚባሉቱ) ቤተክርስቲያናት እና የይሖዋ ምስክሮች አገልጋዮች ተሳታፊ ሆነዋል፡፡ መጽሐፉ በ50 ብር እየተሸጠ ሲሆን በጃፋር የመጽሀፍት መደብር እየተከፋፈለ ይገኛል፡፡

  በቴዎድሮስ ኃይሉ ተፅፎ በሰለሞን ሙሄ የተዘጋጀው “አንላቀቅም” የተሰኘ ሮማንስ ኮሜዲ ፊልም፤ የፊታችን ሰኞ ከቀኑ በ11 ሰዓት በአቤል ሲኒማ ይመረቃል፡፡ በቴዎድሮስ ፊልም ፕሮዳክሽን በቀረበው በዚህ ፊልም ላይ ማህደር አሰፋ፣ ሰለሞን ሙሄ፣ ሙሉዓለም ጌታቸው፣ ነብዩ ኤርሚያስ፣ ሄኖክ አለማየሁና ሌሎች አንጋፋ ባለሙያዎች እንደተሳተፉበት ታውቋል፡፡

    የተለያዩ የቢዝነስ፣ የሞቲቬሽን እና መሰል መፅሀፍት በማዘጋጀት የሚታወቁት ዶ/ር አቡሽ አያሌው፤ ያዘጋጁት “ካይዘን” የተሰኘ መፅሀፍ በትላንትናው እለት በግራንድ ዮርዳኖስ ሆቴል ተመርቋል፡፡ ሩቅ ምስራቃዊያን ሳይንሳዊ እውነታውን ቀድመው በመረዳት ካይዘንን ተለውጠውበታል የሚሉት ዶ/ር አቡሽ፤ ሀገራችንም ካይዘንን ተግባራዊ ካላደረገች ያሰበችው ለውጥ ላይ እንደማትደርስ በማሰብ፣ የካይዘንን ግንዛቤ በህብረተሰቡ ውስጥ ለማስረፅ እንደተዘጋጀ ተናግረዋል በመፅሀፉ ምረቃ ላይ የተለያዩ እንግዶች የተገኙ ሲሆን በመፅሀፉ ዙሪያም ውይይት ተካሂዷል፡፡

    ነዋሪነታቸውን በለንደን ባደረጉት ኢ/ር ወንድሙ ነጋሽ ተፅፈው የተዘጋጁት “የአዕምሮ አስተዳደር ሞዴል” እና “ፍቅር ምንድን ነው” መፃህፍት ዛሬ ረፋድ ላይ በብሄራዊ ቴአትር አዳራሽ ይመረቃሉ፡፡
መፃህፍቶቹ ስሜትን ስለመቆጣጠር፣ በራስ ስለመተማመን፣ በአላማ ስለመፅናት፣ ስለ ደስታና የፍቅር ያለንን ግንዛቤ የሚያሰፉ ሲሆን “ፍቅር ምንድነው?” በሚለው መፅሀፍ ውስጥ ፍቅር ምንነትና መሰል ጉዳዮች ተዳስሰውበታል፡፡ መፃህፍቱ በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ ዛሬ ሲመረቁ ውይይት ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ፀሐፊው ኢንጂነር ወንድሙ ነጋሽ ላለፉት 15 ዓመታት በእንግሊዝ የጦር መርከቦችን ከአደን የመከላከል ሲስተም መሀንዲስ በመሆን ከመስራታቸውም በተጨማሪ በስነ-ልቦና ላይ የተመሰረቱ ተከታታይነት ያላቸው ጥናታዊ መፃህፍት በመፃፍ ላይ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡

የተለያዩ የኢትዮጵያ ታሪክ፣ ቅርሶችና የብሔር ብሄረሰቦችን ባህልና ትውፊት በአንድ ላይ በማሰባሰብ ለማስጎብኘት የሚያስችል ነው የተባለ የባህል ማዕከል የፊታችን ሐሙስ ሊከፈት ነው፡፡
“ብርሃን ኢትዮጵያ የባህል ማዕከል” የሚል ስያሜ የተሰጠው የባህል ማዕከል፤ ኢትዮጵያን ቀደምት ታሪኮች የሚያወሱ ቅርሶች፣ ለአገሪቱ ታሪካዊ ቦታዎች ምሳሌ የሚሆኑ ስራዎች፣ ከአፄ ቴዎድሮስ እስከ አሁን ድረስ ያሉ የአገሪቱ መሪዎች ምስሎችና አጫጭር ታሪኮችና ብሔር ብሔረሰቦች ባህላዊ ቤቶችን አካቶ የያዙ መሆኑ ታውቋል፡፡
የማዕከሉ ዋና ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ ሳቤላ በላይነሽ አባይ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ ማዕከሉ ህብረተሰቡ ባህሉን በአግባቡ ለማወቅና ጎጂውን ለማስቀረት፣ ጠቃሚውን ደግሞ ለመያዝ እንዲችል የሚያግዝ መሆኑን ጠቅሰው፣ ቱሪስቶች በአንድ ጊዜ ሁሉንም አካባቢዎች ለመጎብኘት እንዲችሉ እድሉን ያመቻቸ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በአዲስ አበባ ቄራ ቡልጋሪያ ማዞሪያ አካባቢ የተሰራው የባህል ማዕከል፣ የፊታችን ሐሙስ በይፋ ተመርቆ እንደሚከፈትም ታውቋል፡፡  

Saturday, 26 April 2014 13:02

የግጥም ጥግ

ዝም ብንል ብናደባ
ዘመን ስንቱን አሸክሞን፤
የጅልነት እኮ አይደለም
እንድንቻቻል ነው ገብቶን፡፡
 ባለቅኔ ሎሬት ጸጋዬ ገ/መድኅን
ቅልስልሱ ይሁዳ
ይሁዳማ ቅልስልስ ነው
አቅፎና ደግፎ
ክርስቶስን ሰጠ
ለሞት አሳልፎ፤
የኛ ዘመን ሰው ግን
ሰቅሏችሁ ሲያበቃ
በፈገግታ ክቦ፤
አቅፎ ይስማችኋል
አይኑን በጨው አጥቦ፡፡
                                       አማኑኤል  መሀሪ
ስሙነኛ ስንኝ
የህዝቦች ልቦና
በታሪክ አንደበት፤
‹‹ንጉሥ ነህ!!›› ባለ አፉ
የሆሳዕና ለት፤
‹‹ስቀለው!!!›› ይልሀል
ውሎ አድሮ እንደ ዘበት፡፡
                                        ፈለቀ  አበበ                           


        በየመን በረሃ የአልቃይዳ ድብቅ ካምፕ ውስጥ የነበሩ 55 የቡድኑ መሪዎችና ታጣቂዎች ሰሞኑን መገደላቸውን የዘገበው አሶሼትድ ፕሬስ፣ ጥቃቱ የተፈፀመው በአሜሪካ ሰው አልባ አውሮፕላን (ድሮን) እንደሆነ ገልጿል፡፡
የአሜሪካ ሰው አልባ አውሮፕላኖች ከነባር የስለላ ቅኝት በተጨማሪ የሚሳኤል ጥቃት መፈፀም የጀመሩት በቀድሞው ፕሬዚዳንት ጆርጅ ቡሽ ትዕዛዝ ቢሆንም፤ የአውሮፕላኖቹ ስምሪት እጥፍ ድርብ የተበራከተው በፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ዘመን ነው - በአፍጋኒስታን፣ በኢራቅ፣ በፓኪስታን፣ በየመን፣ በሶማሊያ፣ በሊቢያ ወዘተ፡፡
የሰው አልባ አውሮፕላኖች ስምሪት ለማበርከትም ነው፤ አውሮፕላኖቹን የሚቆጣጠሩ አብራሪዎችም በብዛት እየሰለጠኑ ሲመረቁ የቆዩት፡፡ ዛሬ ወደ 10ሺ ከሚጠጉ የአሜሪካ የጦር አውሮፕላን አብራሪዎች መካከል 5ሺ ያህሎቹ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን ለመቆጣጠር የሰለጠኑ ፓይለቶች ናቸው፡፡
አሜሪካ የጦር ካምፕ ውስጥ በኮምፒዩተሮች ቁሳቁሶችና ስክሪኖች ያሸበረቀ ቢሮ ውስጥ በስራ የተጠመዱት የድሮን ፓይለቶች፤ ጌም የሚጫወቱ ነው የሚመስሉት፡፡ ግን የምር ጦርነት ውስጥ ናቸው፡፡ በየመን ሰማይ የስለላ ካሜራዎችንና ሚሳዬሎችን የተሸከመ ሰው አልባ አውሮፕላን አልቃይዳ ካምፕ ላይ ጥቃት እንዲሰነዝር ትዕዛዝ እየሰጡት ነው፡፡
ከአስር ሺ ኪሎ ሜትር ርቀት ሆነው ይዋጋሉ፡፡ ምን አለፋችሁ? የአልቃይዳ ዋና መሪዎችና ወታደራዊ መሪዎች በአብዛኛው የተገደሉት በድሮን ሚሳዬል ነው፡፡ ውጤታማነታቸውን በማየትም፤ የአሜሪካ ኮንግረስ፣ ለውጤታማ ድሮን አብራሪዎች የጦር ሜዳ ኒሻን ለመስጠት የሚያስችል ህግ አዘጋጅቷል፡፡ በአካል የጦር ሜዳን ባይረግጡም፤ ለውጊያ አደጋዎች ባይጋለጡም፤ በውጊያ የጦርነት ድል ሲያስመዘግቡ የጀብድ ኒሻን ሊበረከትላቸው እንደሚገባ ይገልፃል - አዲሱ ህግ፡፡ ግን በዚሁ የሚያበቃ አይመስልም፡፡ የዛሬዎቹ ሰው አልባ የጦር አውሮፕላኖች፣ የርቀት ተቆጣጣሪ ፓይለት ያስፈልጋቸዋል፡፡
አሁን እየተሰሩ የሚገኙ አዳዲስ የጦር አውሮፕላኖች ግን የርቀት ተቆጣጣሪ ፓይለት አያስፈልጋቸውም፡፡ ራሳቸው ችለውታል እኮ! ሃላፊነት እየተቀበሉ የመሰማራትና ወታደራዊ እርምጃ የመውሰድ አቅም አላቸው፡፡ ያኔስ የጀብድ ኒሻንና ወታደራዊ ማዕረግ ለማን ይበረከታል? ለአውሮፕላኖቹ፡፡

       ከኢትዮጵያ በእጥፍ የሚበልጥ ሕዝብ የያዘችው ናይጄሪያ በአንድ ምሽት፣ ተዓምረኛ የኢኮኖሚ እድገት አስመዘገበች - 90 በመቶ እድገት። እውነት ነው። ግን፣ “አስመዘገበች” የሚለውን ቃል በቸልታ አትዝለሉት።
ነገሩ ቀላል አይደለም። በፈጣን እድገት እየተንደረደረች መሆኗ የሚነገርላት ኢትዮጵያ፣ አሁን ካለችበት ደረጃ ተነስታ በተዓምረኛ ፍጥነት የ90 በመቶ እድገት እውን ለማድረግ፣ ሰባት አመታት ይፈጅባታል - ከ2500 ቀናት በላይ መሆኑ ነው።
ዎልስትሪት ጆርናል (wsj) እንደዘገበው፤ እስከ መጋቢት 20 ቀን ድረስ፣ በጠቅላላ የኢኮኖሚ ምርት፣ ደቡብ አፍሪካ የአህጉሩ ቀዳሚ ነበረች። የደቡብ አፍሪካ አመታዊ የምርት መጠን 370 ቢሊዮን ዶላር ይገመታል። ከኢትዮጵያ በአስር እጥፍ የሚበልጥ ማለት ነው። በሁለተኛ ደረጃ ላይ ደግሞ ናይጄሪያ ነበረች - በ270 ቢሊዮን ዶላር አመታዊ ምርት።
ይሄ የደረጃ ሰንጠረዥ ከመጋቢት 21 ቀን በኋላ ተቀይሯል። ናይጄሪያ በጠቅላላ አመታዊ ምርት፣ የአፍሪካ ቁንጮ መሆኗን አውጃለች - ለዚያውም በሰፊ ልዩነት። የአገሪቱ አመታዊ ምርት 510 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ ነው የተገለፀው። በሌላ አነጋገር፤ ናይጄሪያ በአንድ ምሽት የ240 ቢሊዮን ዶላር (ወደ ሩብ ትሪሊዮን ዶላር የተጠጋ) እድገት አስመዝግባለች። ኢትዮጵያ በፈጣን እድገት ብትገሰግስ፣ አመታዊ ምርቷ ሩብ ትሪሊዮን ዶላር የሚደርሰው ከ20 ዓመት በኋላ ነው። በናይጄሪያ የአንድ ምሽት ጉዳይ ሆኗል።
ጉደኛውን የናይጄሪያ ዜና የዘገቡ እነ wsj እና ዘ ኢኮኖሚስት የመሳሰሉ የሚዲያ ተቋማት፤ ነገሩ ትንግርት ወይም ምትሃት እንደሚመስል ገልፀዋል። ግን፣ “ሐሰት ነው” ወይም “ስህተት ነው” ብለው አልተቹም። የናይጄሪያ አመታዊ ምርት፣ ከግማሽ ትሪሊዮን በላይ ነው በሚል ተስማምተዋል።
ግን፤ በምንኖርባት ዓለምም ሆነ በሌላ ዓለም፤ “ተዓምር”፣ “ትንግርት”፣ “ምትሃት” የሚባል ነገር የለም። እና ናይጄሪያ በአንድ ምሽት ያስመዘገበችው ወደ ሩብ ትሪሊዮን ዶላር የተጠጋ እድገት፣ “የናይጄሪያ ብሔራዊ ተዓምራት” ውስጥ የማይካተት ከሆነ ምን ተብሎ ሊሰየም ነው? ትክክለኛው ስያሜ፣ “የናይጄሪያ መንግስታዊ ዝርክርክነት” የሚል ነው።
የአንድ አገር አመታዊ ምርት ምን ያህል እንደደረሰ የሚታወቀው፣ ጓዳ ጎድጓዳውን፣ ፋብሪካና ገበያውን፣ የእርሻ ማሳና የከብቶች በረትን ሁሉ እያግበሰበሱ ቆጠራ በማካሄድ አይደለም። በየአመቱ አገር ምድሩን ማሰስ አይቻልም። ታዲያ በመላ አገሪቱ፣ 15 ሚሊዮን የገበሬ ቤተሰቦች ቢኖሩ፤ የሁሉንም አመታዊ ምርት በድምር ለማወቅ ምን መላ አለ? ለምሳሌ፣ ከአንድ ሺ ገበሬዎች መሃል የአንዱ ገበሬ ምርት ላይ በማተኮር ጥናት ማካሄድና በአንድ ሺ ማባዛት ነው መፍትሄው። በዚህ የናሙና ጥናት፣ የ15ሺ ገበሬዎችን የምርት መጠን ላይ መረጃ ይሰባሰባል። ከዚያ፤ ይህ ውጤት በአንድ ሺ ይባዛል - ጠቅላላ የአገሪቱ ገበሬዎች አመታዊ ምርት ለማወቅ። በአንድ ሺ ማባዛት የሚያስፈልገው፤ የአንድ ገበሬ ምርት፣ የአንድ ሺ ገበሬዎችን ምርት ይወክላል ከሚል የጥናት መነሻ ስለተነሳን ነው።
አስር ሺ ትልልቅና ትናንሽ ፋብሪካዎች ቢኖሩ፤ የአንድ ሺ ናሙና ፋብሪካዎችን እንቅስቃሴ በማጥናት በመቶ ማባዛት ይቻላል። የትራንስፖርት፣  የጤና፣ የስልክ፣ የኤሌክትሪክ፣ የባንክ፣ የሸቀጥ አቅርቦት የመሳሰሉ አገልግሎቶችም ላይ ተመሳሳይ የናሙና ጥናት ይካሄድና፤ እንደ ውክልናው ክብደት (weighted mean) በመቶም ይሁን በሺ  እያባዛን ጠቅላላ አመታዊ የአገልግሎት ወይም የምርት መጠን ላይ እንደርሳለን። በሌላ አነጋገር፤ እያንዳንዱ ዘርፍና ንዑስ ዘርፍ፤ እያንዳንዱ አካባቢና መረጃ ... ከላይ እስከ ታች በኢኮኖሚ ውስጥ ምን ያህል ድርሻ እንዳለው በቅጡ ተገንዘበን፣ እንደ የድርሻ ተገቢውን የውክልና ክብደት እስከሰጠነው ድረስ፤ አስተማማኝ ቀመርና ስሌት ይኖረናል ማለት ነው።
በሆነ ምክንያት፣ የውክልናው መጠን ወይም ክብደት ከአመት አመት ቢቀያየርስ? ከጊዜ ወደ ጊዜ ብዙ ነገሮች እንደሚቀየሩ አይካድም። የሕዝብ ብዛትን መጥቀስ ይቻላል። ግን ችግር የለውም። በየአመቱ የሚከሰቱና የተለመዱ ጥቃቅን ለውጦችን ሳንዘነጋ በቀመራችንና በስሌታችን ውስጥ በማስገባት መስመር እናስይዘዋለን። በየአመቱ የገጠር የሕዝብ ብዛት በምን ያህል እንደሚጨምር ይታወቃላ። ግን ባልተለመደ ሁኔታና ፍጥነት፤ ለምሳሌ የአገሪቱ የገበሬዎች ብዛት ወደ አስር ሚሊዮን ቢቀንስ ወይም ወደ ሃያ ሚሊዮን ቢያሻቅብስ? ያኔ ለናሙና ጥናት የምንጠቀምበት ቀመርና ስሌት ላይ ችግር ይፈጠራል። ለምሳሌ፤ ከሃያ አመት በፊት፣ የአበባ እርሻ በአገሪቱ ኢኮኖሚ ውስጥ ከቁጥር የሚገባ ድርሻ አልነበረውም።
የፊልምና የቪዲዮ ዝግጅትም እንዲሁ። የዛሬውን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ፤ በቀድሞው ቀመርና ስሌት ለመመዘን ስንሞክር፣ የምናገኘው ውጤት የተሳሳተ ይሆናል። የናይጄሪያ መንግስት ሲጠቀምበት የቆየው ቀመርና ስሌትም እንዲሁ፤ ከሃያ አመታት በፊት የነበረውን የኢኮኖሚ መዋቅር ላይ የተመሰረተ ስለሆነ የዛሬውን ሁኔታ በትክክል የማሳየት አቅም አልነበረውም። በናይጄሪያ ባልተለመደ ፍጥነት የተስፋፉት የቴሌኮምና የባንክ አገልግሎት፤ የቴክኖሎጂና የኮንስትራክሽን ቢዝነስ፣ እንዲሁም የፊልምና የቪዲዮ ሥራዎች፤ በኢኮኖሚ ውስጥ ያላቸው ድርሻ እየፈረጠመ መጥቷል። ለሃያ አመታት ያልተለወጠው የመንግስት ቀመርና ስሌት ግን፤ በኢኮኖሚ ውስጥ እየጎሉ ለመጡት ለውጦች ተመጣጣኝ የውክልና ክብደት የሚሰጥ አይደለም። እናም የአገሪቱን አመታዊ ጠቅላላ ምርት በትክክል የማወቅ ወይም የመገመት አቅም አልነበረውም። በየአመቱም የግምቱ ስህተት እየተደራረበ ነው የመጣው። ከሳምንት በፊት የመንግስት ቀመርና ስሌት ተለወጠ። ለሃያ አመታት የተጠራቀመው ስህተትም ተስተካከለ። ይሄ ተዐምር አይደለም። ለበርካታ አመታት የዘለቀ ዝርክርክነት እንጂ።