Administrator

Administrator

ፈር መያዣ:- “በታላቁ የሥነጽሑፍና የቋንቋ ሊቅ በዶ/ር ዮናስ አድማሱ ሕይወትና የኑሮ ልምድ ዙሪያ አንዳች ነገር የሚጽፍ እርሱ ማን ነው?” ብላችሁ ስትጠይቁት ተሰማው፡፡ እርሱም ቀድሞ ጠርጥሮ ነበር - ጋሽ ዮናስ ለዚህ ጽሑፍ ቅራቢ በድህረ ምረቃ መርሃ ግብር አስተማሪውና አማካሪው ነበር፡፡ በተለይ ይህ ፀሐፊ፣ የመመረቂያ ወረቀቱን ከ1951-1960 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በንጉሱ ፊት ሣይቀር ይቀርቡ በነበሩ “የኮሌጅ ቀን ግጥሞች” እና ገጣሚያን ማህበረ ፖለቲካዊ አመለካከትና ሂስ ላይ በማድረጉ ጋሽ ዮናስን የበለጠ ለማወቅ እድል አገኘ፡፡
ጋሽ ዮናስ የታላቅ ወንድሙን የዮሐንስ አድማሱን ፈለግ ተከትሎ፣ ከነሐይሉ ገብረዮሐንስ (ገሞራው)፣ ታምሩ ፈይሳ፣ አበበ ወርቄ፣ ኢብሣ ጉተማ ወዘተ. ጋር በውድድር ያሸነፈባቸውን ግጥሞች በኮሌጅ ቀን አቅርቧል፡፡ ዶ/ር ዮናስ እራሱም ተጠኝ የኮሌጅ ቀን ገጣሚ ስለነበረ የዚህን ጽሑፍ አቅራቢ ነፍስ ገዝቶ፣ በነፈስም በስጋም ተጣብቷል፤ ስለዚህ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ፣ ስለሞጋቹ የሥነጽሑፍ ባለሟል ሕይወትና ክህሎት በወፍ በረርም ቢሆን ለመመስከር፣ ለአቅመ ፀሐፊነት ደርሷል፡፡
ለዛሬ በሕይወት ልምዱና ገጠመኞቹ ዙሪያ በጥቂቱ እናወጋለን፡፡ በአማርኛ ሥነጽሑፍ ንድፈ ሃሳብ አፍላቂነቱና በምርምር ሥራዎቹ ዙሪያ መረጃዎችን እያጣቀስን አካዳሚያዊ መጣጥፍ ለማስነበብ ደግሞ ለሣምንት ቀጠሮ እንይዛለን፡፡
ፀሐፊው፣ የእስከዛሬ አንቱታውን ትቶ፣ “አንተ” እያለ የተረከው፣ የመገናኛ ብዙሐን ቀልብ የሚስበው የዶ/ር ዮናስ የኪነጥበብ ሰውነት ሙያው ከሚፈቅደው የአነጋገር ዘልማድ ጋር እንደሰመረ እንዲፀና በሚል የተደረገ ትጋት እንጂ፣ አጉል ድፍረት እንዳልሆነ በትሁትነት ይገልፃል…
ከረሜላ፣ ቸኮሌትና ማስቲካ ይዞልን የሚመጣ መምህራችን…
በወርሃ ጥር፣ 2000 ዓ.ም ጋሽ ዮናስ የግማሽ መንፈቀ ዓመቱን ኮርስ ማጠቃለያ ሲያስተምር እጅግ ተመስጦ ነበር፡፡ “ለማስተማር ብቻ ተብለው የሚፈጠሩ የተለዩ ሰዎች አሉ፤ ሁሉም መምህር መሆን አይችልም!” የሚለውን የሥነ ትምህርት ፈላስፎችን አባባል ለማመን ከፈለጉ፣ ዶ/ር ዮናስ ሲያስተምር መመልከት ነበረብዎት… የውጭና የሀገር በቀል ንድፈ ሃሳቦችን እያረቀቀ፣ የአማርኛ ሥነጽሑፍን ሲያስተነትንና ሲፈክር ተማሪዎቹ አፋችንን እንደከፈትን እንቀራለን… በአካዳሚክ እውቀቱና በሕይወት ልምድ እውነቱ የሚያረቃቸው የሥነጽሑፍና የቋንቋ ሀቲቶች (ዲስኩርስ) እንደ ባህርማዶ ለስላሳ ሙዚቃ በተመስጦ ነው የምናዳምጣቸው፡፡ የሀቲቶቹን እና/ወይም የንድፈ ሃሳቦቹ ረቂቅነትን የምንመረምረው፣ የተመስጦ ሰበካውን ገታ አድርጐ እነዛኑ ሀቲቶች ገልብጦ “በፈርሱ” የጠየቀን ጊዜ ነበር…
ጋሽ ዮናስ ለማድነቅም ንፉግ አይደለም፡፡ ከተመስጦው መለስ ብሎ የሚጠይቀውን ውስብስብና አመራማሪ ጥያቄ የመለሰን ተማሪ፣ እስከ ጥግ ነው በአድናቆት የሚያመሰግነው፡፡

ያን ጊዜም አንድ ተማሪ የጋሼን ውስብስብ ጥያቄ መልሶ፣ ወሰብሰብ ያለ ሌላ ጥያቄ ጋሼን ሲጠይቀው …ጋሼ በሀሴት ፊቱ በራ… ወዲያው “…በዚህ ኮርስ A (ኤ) ሰጥቼሃለሁ… በዚህ ክፍለ ጊዜ አለመምጣት ትችላለህ! በቃ! ” አለው፡፡ የጋሽ ዮናስን ውስብስብ ጥያቄ መልሶ አድናቆት ማግኘት ትልቅ ክብር ስለሆነ፣ ሁላችንም በመላሹ ተማሪ ቀንተናል፡፡
በዚህ ጊዜ ታዲያ፣ ጋሽ ዮናስ ከኪሱ የተለያዩ ከረሜላዎችን አውጥቶ ለእያንዳንዳችን የድህረ ምረቃ ተማሪዎቹ በፍቅር ሰጠን፤ ወዲያው፣ በደስታና በአክብሮት ከረሜላችንን መብላት ጀመርን፤ ምክንያቱም፣ የያን ጊዜው የ65 ዓመቱ ጋሽ ዮናስ እሱም ከኛ ጋር ከረሜላውን ወደ አፉ ብሎ ነበርና፡፡ በነገራችን ላይ ዶ/ር ዮናስ ተማሪዎቹን ለመፈተን ሲጠራ፣ ቀድሞ በመፈተኛ ክፍሉ የእያንዳንዳችንን የፈተና ወረቀት በየመቀመጫችን አስቀምጦልን ይቆያል፡፡ ከፈተና ወረቀቶቹ ላይ ታዲያ ከረሜላ፣ ማስቲካና ቸኮሌት አይጠፉም…
በ”አማርዝኛ” የሚሳለቀው የቋንቋዎች ሊቅ
ዶ/ር ዮናስ፣ ተማሪዎቹ ይሁኑ የሥራ ባልደረቦቹ፣ በእውቀትም ይሁን በድንገት አማርኛና እንግሊዝኛ እየቀላቀሉ ጉራማይሌ ሲያወሩ ከሰማ፣ እንደሁኔታው ለዘብ አድርጐ በስላቅ ሊተቻቸው ይችላል፤ “ኧረ ይኼ አማርዝኛ አልገባኝም” በማለት፡፡ ወይም በቁጣ ሊወርፋቸው ይችላል፤ ‹‹አንጀባ አታብዙ!... ይኼ አማርዝኛችሁ አገር አጠፋ›› በማለት፡፡ “አማርዝኛ” ጋሽ ዮናስ፣ ለአማርኛና ለእንግሊዝኛ ድብልቅ የቋንቋ አጠቃቀም የሰጠው ስያሜ ይመስላል… ጋሼ ዮናስ የግዕዝ፣ የአማርኛና የእንግሊዝኛ ቃላት ስንጽፍ ወይም ስናነብ ከተደናቀፍን የቃሉን ስርወቃል (ወይም ግንድ) ከምንጩ እየቀዳ በየትኛውም ጊዜና ቦታ ሳይታክት ያርመናል… በቋንቋዎቹ ካለው ጥልቅ እውቀቱ የበለጠ፣ እኛ ተማሪዎቹን ለማረም ያለው ቀናነቱ በብዙዎቻችን አዕምሮ ገዝፎ ይታያል…
አስገራሚው የዶ/ር ዮናስ ቢሮ
የጋሽ ዮናስ ቢሮ፣ በስድስት ኪሎ ግቢ በማህበራዊ ሳይንስ ህንፃ ውስጥ፣ ከባህር ጠለል በላይ ሦስተኛ ፎቅ ጋ ይገኛል፡፡ በበርካታ መጻሕፍት የተጨናነቀው ይህ ቢሮ፣ ከበሩ ፊት ለፊት ሲቆሙ በስተቀኝ፣ ታዋቂው የሥነጽሑፍና ፎክሎር መምህርና ተመራማሪ የዶ/ር ፈቃደ አዘዘ ቢሮ ያዋስነዋል፡፡ በፊት ለፊት የታዋቂው የሥነልሣን ሊቅ የፕሮፌሰር ባየ ይማምና ባልደረቦቻቸው ቢሮዎች ያዋስኑታል… “ያለ ቀጠሮ ወደ ጋሼ ቢሮ መዝለቅ ፈጽሞ የተከለከለ ነው” ባይባልም፣ እንዲሁ ዘው ማለት የሚያስከፍለው ነገር ይኖራል፡፡ ዶ/ር ዮናስ በተለይ አጣዳፊ ሥራ ይዞ፣ ኮምፒውተሩ ላይ ተጥዶ ካገኙት ዝም ብሎዎት ሥራውን ሊሠራ ይችላል፤ በተለይ ያለ ቀጠሮ ከሆነ የመጡት፡፡ በሩን ደጋግመው እየቆረቆሩ ሰላም ከነሱት “የለሁም!” በማለት በመጀመሪያ በለሆሳስ ሊመልስ ይችላል፡፡ ደግመው ከቆረቆሩ ብስጭት ብሎ በመነሳት “የለሁም ስል አትሰማም!” በማለት ሊቆጣ ይችላል፡፡ ድንግጥ ብለው ከቆሙ፣ አያስችለውም ወዲያው መለስ ይልና፣ “ምን ፈልገህ ነው?“ ይላል… የጋሼን ጸባይ ያለመደ ተማሪ እንኳን ቢሮው ድረስ ሄዶ ቀርቶ፣ በመንገድ ሲያገኘው ሁሉ ይሸሻል፣ ይርበተበታል … ጋሽ ዮናስ ግን ይሄን አይነት መሸማቀቅ አይፈልገውም፤ ባህሪውን ያወቀ ተማሪ ግን የምሩን ተናዶ ቢቆጣ እንኳ፣ ሳይፈራ የደቂቃዎችን ክፍልፋይ ዝም ብሎ ካሳለፈው ወዲያው ምልስ ይላል… ጋሼ ሆዱ ገርና ቅን እንደሆነ፣ በአፉ ቢቆጣ እንኳን በሆዱ እንደማይቆርጥ ታዲያ፣ ከተወሰነ የጊዜ ቆይታ በኋላ ሁሉም ተማሪዎቹ ያውቃሉ፤ ያውቁታልም…
ጋሽ ዮናስ ሲቀልድ፣ በዘመንኛ ቋንቋ “ሲፎግር”፣ ሲጫወት… ይችልበታል፤ ተማሪዎቹ የማታለል ሙከራ ካደረግን፣ “እሣት የላስኩ የሱማሌ ተራ ጩልሌ ነኝ… ” በማለት ስቆብንና ተሳልቆብን ያልፋል…
አንድ ቀን የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ ተመካሪው እያለ፣ ደውሎ ለመምጣት ቀጠሮ ይቀበላል፡፡ በበነጋው ጋሽ ዮናስ ወደ ቢሮው ሲገባ ጠብቆ በቀጠሮው መሠረት ወደ እዚያው ያቀናል፡፡ ቢሮው ገርበብ ብሎ ሲያገኘው ከፈት አድርጐ ይገባና ይቆማል፡፡
ጋሽ ዮናስ “ምን ልታደርግ መጣህ?” አለው በቁጣ፡፡ ቀጠሮ እንዳለው ተናግሮ ተዝናንቶ ሲቆም፣ ጋሼ፣ “እኔ በእናንተ ማበድ አለብኝ… ደውለህ ነው መምጣት አላልኩህም!” በማለት ብስጭት ብሎ የሚማታበት “አለንጋ” ከጠረጴዛው ሲፈለግ፣ ተመካሪ የድህረምረቃ ተማሪው ፍንጥር ብሎ ከቢሮው ወጣ፡፡
የጋሽ ዮናስን ጸባይ ስለሚያውቅ ብዙ አልተደናገጠም፡፡ አንድ ሁለት እርምጃ ተራምዶ ሞባይሉን አወጣና ደወለ… ጋሼ ከቢሮው ውስጥ ሲስቅ ይሰማዋል፡፡ ወዲያው ስልኩ ተነሳ፤ “ምን ፈለግህ?” የሚል የለሆሳስ ድምጽ ተሰማ… “አይ ዛሬ ቀጠሮ ነበረኝ፤ ደውዬ እንዳስታውስ ተነግሮኛል!” ከማለቴ የጋሼ ሣቅ፣ ከሞባይሌም ከቢሮውም ተሰማኝ፡፡ እየሳቀ፣ “ና! አሁን ” አለኝ፡፡
ስህተቴ ሲገባኝ፣ ከቢሮው ሣልርቅ ወዲያው ደውዬ መጠየቄ ገርሞታል… በመልካም ፈገግታ ለ40 ደቂቃ ስመከር ቆየሁ… ወደ ዶ/ር ዮናስ ቢሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ከሆነ የሚገቡት ብዙ የሚገርምዎት ነገር ሊያጋጥምዎት ይችላሉ… ጠረጴዛው በካኪ ፖስታ ታሽገው የሚታረሙ ወይም የታረሙ ወረቀቶች ተቆልለው ያያሉ - በአንድ ጠርዝ ላይ፡፡ የተለያዩ የታሸጉ ምግቦች፣ በጠርሙስ የተሞሉ የተለያዩ የከረሜላ፣ የቸኮሌት አይነቶች ይመለከታሉ፡፡
በጠረጴዛው ሌላኛው ጫፍ፣ ሽንኩርት፣ እንቁላል፣ በላስቲክ የታሸጉ የተለያዩ ቅመማ ቅመሞች ሊያዩ ይችላሉ፡፡
በጠረጴዛው መካከል ላይ የተለያዩ መፃሕፍት ለንባብ ተሰድረዋል … ገሚሶቹ መፃሕፍት ተገልጠው ተገልጠው በአፋቸው ተደፍተው ያያሉ… በጠረጴዛው በውስጥ በኩልም (በግርጌው) የተለያዩ መዝገበ ቃላት፣ የጥናት መጽሄቶች /ጆርናሎች/… መቆለላቸውን የሚያዩት፣ አንድ መጽሐፍ ገልጦ ከእንግዳ መቀበያ ወንበር ተነስተው ወደ እርሱ ጠረጴዛ ቀርበው ካነበቡ ወይም የተሰወረበትን መፃሕፍት እንዲያፋልጉት ከፈቀደ ነው፡፡
ከጠረጴዛው ጀርባ ታዲያ፣ ከምሣ በኋላ የሚያርፉበት ይመስለኛል ባለ ሦስት ቀጫጭን ስፖንጅ ተጣጣፊ ፍራሽ፣ በስርአት ተጣጥፎ የጠረጴዛውን እግር ተደግፎ ሊያዩ ይችላሉ፡፡
ትንሽ የኤሌክትሪክ ምድጃ፣ ተቀምጧል፡፡ የአንድ የመካከለኛ ሰው እጅ መዳፍ የሚጨብጠው ዓለት የሚመስል ድንጋይ ጠረጴዛው ስር ወይም ላይ ቁጭ ብለው ቢያዩ አይደንግጡ… ጋሼ ተማሪዎቹ ቶሎ ከቢሮው አንወጣለት ስንል ድንጋዩን እያሳየ ያስፈራራናል - እየቀለደና እየሳቀ ነው፡፡ ተማሪዎቹም ጋሽ ዮሐንስ ለየት ያለና ዘመናዊ ሰው እንደሆነ እናውቃለን… በነገራችን ላይ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ የጠረጴዛውን ጀርባ ለመጨረሻ ጊዜ ያየው በሀምሌ ወር 2002 ዓ.ም ነበር፡፡
የህልፈተ ህይወት ጊዜውን የተነበየበት አጋጣሚ
በጥር ወር 2004 ዓ.ም በዋቢሸበሌ ሆቴል፣ የበድሉ ዋቅጂራን (ዶ/ር) ሁለተኛ የግጥም መጽሐፍ /“እውነት ማለት የኔ ልጅ”ን/ ለማስመረቅ “ዛጐል ቤተመፃሕፍት” ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡ ዶ/ር በድሉ የግጥም ስብስቡ “መታሰቢያነቱ ሀውልት ላልቆመላቸው ለዮሐንስ አድማሱ እና ለደበበ ሰይፉ” እንዲሆንለት በማድረጉ፣ ዶ/ር ዮናስ በዚህ ዕለት በመድረክ ላይ ንግግር እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ፣ ወደ መድረኩ ሲመለከት፣ የመጽሐፍ ምረቃ በሚያበስረው “ባነር” ላይ አንድ ቃል ያያል፤ የዛጐል ቤተመፃሕፍት ሥራ አስኪያጅ የሆነውን እንዳለጌታ ከበደን ጠርቶ፣ “ዶ/ር ዮናስ ያን ካየ መናገሩ አይቀርም - መላ ፈልግ” ይለዋል፡፡
ጋሽ ዮናስ ወደ መድረክ ሲጋበዝ፣ “… ይኸው! የግጥም ‹መድብል› አይባልም፤ መድበል እንጂ!” በማለት የቃሉን ሥርዎ አመጣጥ በማብራራት ንግግሩን ጀመረ፡፡ ስለ ዮሐንስ አድማሱ ሕይወትና ሥራዎች አብራራ… በተለይ ዮሐንስ በባለቅኔውና ፀሐፌ ተውኔቱ ዮፍታሔ ንጉሴ ሕይወትና ሥራዎች ዙሪያ የሠራውን የምርምር ሥራ “በአሰናኝነት” አሰናድቶ እያጠናቀቀ መሆኑን ተናገረ፡፡ በመጨረሻ፣ “…ይኼ መጽሐፍ ታትሞ ሳላየው እግዚአብሔር እንዳይገለኝ!” በማለት “ፈጣሪውን” በሰከነ መንፈስ የተማፀነበት አጋጣሚ በቦታው የነበረን ሰው ሁሉ አሳዝኗል፡፡
ጋሽ ዮናስ፣ የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበረ ባሳተመው “የዘመን ቀለማት” የግጥም መድበል ላይ፣ “ህዳር 6 ቀን 1935 ዓ.ም ቅዳሜ ሌሊት በዐሥር ሰዓት በአዲስ አባ ከተማ በደጃች ውቤ ሠፈር” መወለዱን እራሱ በከተበው የሕይወት ታሪኩ ተናግሯል፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱሱ ገድለኛ፣ ከነቢዩ ዮናስ ስሙን ብቻ ሳይሆን ግብሩንም የወረሰ የሚመስለው ዶ/ር ዮናስ አድማሱ፣ ህልፈቱ እስከታወቀበት የካቲት 1 ቀን 2005 ዓ.ም ድረስ፣ የዶክትሬት ዲግሪ ተማሪዎቹን እያማከረ፣ እያነበበ፣ እየፃፈ ያለፈ ታላቅ ምሁር መሆኑ በተግባር አሳየ፤ እስከመጨረሻዋ የሕይወት ጠብታ መፃሕፍት ታቅፎ ለዘላለሙ ያንቀላፋ የቀለም ቀንድ!
እውቀት የሚቀምርባት አስገራሚ ቢሮውም ወዳጇ ጋሽ ዮናስ ለዘላለሙ ከተለያት በኋላ ሁሉ፣ የሥነጽሑፍ ሊቀሊቃውንቷ ህልፈት በስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ እስከታወጀበት የደቂቃዎች ክፍልፋይ ድረስ፣ ይህቺ የቀለም መጥመቂያ ቢሮው፣ በበር ሥር የተላከላትን የተመካሪ ተማሪዎች የምርምር ፕሮፖዛል በአደራነት ስትቀበል ነበር… የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ የዶ/ር ዮናስን እርፈት ከቀኑ 8 ሰዓት አካባቢ ከመስማቱ በፊት፣ የጋሽ ዮናስ የዶክትሬት ዲግሪ ተመካሪ ተመሪው የፕሮፖዛል ወረቀቷን ወደ 5 ሰዓት አካባቢ በበር ስር ማስገባቱን ሰምቷል…
የተስፋዋን ቀን ለማየት 12 ቀን ሲቀራት የተነጠቀች ነፍስ
ታዋቂው ባለቅኔና ለውጥ አራማጁ መምህር ዮሐንስ አድማሱ በ1967 ዓ.ም በድንገት በ37 ዓመቱ ሲቀሰፍ፣ በዮፍታሔ ሕይወትና ክህሎት ዙሪያ እያገባደደው የነበረውን የምርምር ሥራ አጠናቆ ማሳተም፣ በታናሽ ወንድሙ በጋሽ ዮናስ አድማሱ ትከሻ ላይ አረፈ፡፡
ከ35 ዓመት በላይ ሳይታተም የቆየውን የምርምር መጽሐፍ የህትመት ብርሃን እንዲያይ፣ እነ ፕሮፌሰር ማስረሻ ፈጠነ፣ ዶ/ር ዮናስን ሲያበረታቱ ቆይተዋል…
የተለያዩ ሃገራዊ ጉዳዮችን የሚያወሱ ዘመን ተሻጋሪ መጻሕፍት፣ ከተቀበሩበት ጉድጓድ እየወጡ፣ ከሻገቱበት ቦታ እየተራገፉ እንዲታተሙ ያደረጉትና ለዘላቂ የህትመት ሥራ መሠረት የጣሉት እነ ፕሮፌሰር ማስረሻ እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬስ የቦርድ አባላት፣ ፕሮፌሰር ማስረሻ፣ በዶ/ር ዮናስ አሰኛኘት ለህትመት የበቃውን መጽሐፍ፣ በልዩ ሁኔታ ለማስመረቅ ከሌሎች ባልደረቦቻቸው ጋር የቁርጥ ቀን ቀጠሮ ይዘዋል… የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ አርታኢና የጋዜጣ አምደኛው ብርሃኑ ደቦጭ የካቲት 13 ቀን 2005 ዓ.ም “በብሔራዊ ትያትር” አዳራሽ የዮሐንስን መጽሐፍ ለማስመረቅ ደፋ ቀና እያለ፣ ከዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ ጋር ተገናኙ፡፡
ጋሽ ዮናስ የመጽሐፉን ህትመት ሳላይ እንዳልሞት በማለት በጉጉት የሚጠብቃትን ዕለት፣ የሦስት ታላላቅ የሥነጽሑፍ ባለሟሎች ጠንካራ የኪነት ክንድ ያረፈበት መጽሐፍ የሚመረቅባትን ያቺን ቀን እኔም በጉጉት እየጠበቅሁ ነው፤ በዚች ታሪካዊ ዕለት፣ ዮሐንስ አድማሱን የሚዘክር አንድ የሥነ ጽሑፍ ሥራ ለማቅረብ እየተሰናዳሁ ነበርና፡፡
የዶ/ር ዮናስ አድማሱ ነፍስም ከ35 ዓመት በላይ ታግሣ የጓጓችለትን የተስፋ ቀን ለማየት 12 ቀናት ብቻ ቀርተዋት እያለ፣ እኔም ወጉ ደርሶኝ ከመምህሬ ከጋሽ ዮናስ ፊት፣ አብዮተኛው የኮሌጅ ቀን ገጣሚ ዮሐንስ አድማሱን ለማውሳት 12 ቀናትን እየተጠባበቅሁ እያለ፣ የታላቁ የቀለም ቀንድ የጋሽ ዮናስን ህልፈተ ሕይወት በድንገት መስማት ምን ያህል ያስደነግጥ!?

 


ባንተ በኩል ፈካች
ነ.መ
የልቤን ማኅደር፣ ቆፍሬ ቆፍሬ፤
ያገር ውለታህን ልናገር አምርሬ፡፡
ምንም ቢደባለቅ፣ ብስሉ ከጥሬ
የፊደል ልሣኑ፣ ያው ይጫሃል ዛሬ፡፡
ምን ቢበረክቱ፣ የእኛ ነው የሚሉ
አገሩና ህዝቡ፣ ድሉም ሆነ ትግሉ
ቢከትቡ፣ ቢያውጁ፣ ገድል ቢያሳቅሉ
በደም የተፃፈ፣ ይጎላል ከሁሉ!!...(“ጐ” እና “ላ” ይላላል)
ለመሰነባበት፣ ጊዜው አልነበረን…(“መ” እና “ሰ” ይጠብቃል)
መቼስ ያቃል ኖሮን፡፡
ለመሰነባበት ጊዜም አልነበረህ…(“መ” እና “ሰ” ይላላል)
መቼስ ያቃል ኖሮህ!!
ብቻህን ሄደሃል፣ ያው ብቻህን ኖረህ፡፡
እንደ ጊዜው ባህል፣ ጥንት እኔ እንደማቅህ
ከመሬቱ በታች፣ ከዕውነት ጋር ተቀብረህ
መብራት የማያቆም፣ የንቁ ኮከብ ነበርክ፡፡
ጥንት ገና ዱሮ፣ ሰው የነበርን ቀን
ጭቆና ሲመረን፣ ግፍ ሲያንገፈግፈን
ልብ ለልብ ማውራት፣ እንዲህ ሳይቸግረን፤
የብዕሬን ዕንባ
ለአገሬ ሳነባ፤
ብታይልኝ ብዬ -
“አበባ” እሚል፣ ግጥም ልኬልህ ነበረ፡፡
እንዲህ መለስክልኝ
መቼም አይረሳኝ:-
“በጧት ቸግነሃል፣
በጧት ጀግነሃል፣
የለብህም ዕዳ፤
አበባህ ግጥም ናት፣ ሁልጊዜ ትፈንዳ!”
ይኸው ላንተም ተርፋ፣ ባንተ በኩል ፈካች
ታሪክ ያለው ትውልድ፣ መኖሩን አወጀች!!
(ለዮናስ አድማሱና ለትውልዳችን)
የካቲት 8/2005

 

አንድ ጊዜ አንድ መንገደኛ ቡድሀ ላይ ያለ የሌለውን የስድብ መዓት ያወርድበታል፡፡ ቡድሀ ዝም ብሎ በእርጋታ ሲያዳምጥ ይቆይና ለመንገደኛው ጥያቄ ያቀርብለታል፡፡ “ስጦታ የተበረከተለት ሰው ስጦታውን አልቀበልም ካለ ስጦታው የማን ይሆናል?” ሰውየውም፤ የሰጪው በማለት መለሰ፡፡ ቡድሃም፤ “ስጦታህን አልቀበለም፤ እነሆ ተረከበኝ” ብሎት ጥሎት ይሄዳል፡፡ አቶ ቶማስ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት ከታሪክ ጋር ተመሳሳይ ስለሆኑ የመፅሐፍ ቅዱስ ታሪኮች ሊነግሩን ወይም ሊሰብኩን ከፈተኛ ተጋድሎ አድርገዋል፡፡

በእርግጥ ከክፋት ሳይሆን ከበጐነት በመነጨ ነው ይሄን ያደረጉት፡፡ እንዴት ቢሉ እኛ የሀገራቸው ልጆች አለም የደረሰበትን ሚስጥር እንድናቅላቸው በመጓጓት ነው ታሪኮቹን የነገሩን፡፡ የአቶ ቶማስ ሀሳብ ምንም እንኳን ተራና በጣም ካለማወቅ የመጣ እንደሆነ ቢገባኝም እንደ ቡድሀ ፊቴን አዙሬ መሄድ ግን አልቻልኩም፡፡ ምክንያቱም ይሄ ለከት ያጣ ሃሳባቸው አንዳንድ ሰዎችን ሲያሳስት አስተውያለሁና ፀሃፊው ምን ያህል እንደተሳሳቱ እንዲያውቁ ማድረግ ይገባል ብዬ አምናለሁ፡፡እንግዲህ ለወደፊቱም አንድ ሰው በእግዚአብሔር ቃልና በዚህች የእግዚአብሔር ቅኔ በሆነች ሀገር ላይ አንዳች ፍልስፍናዊ ወይም ሳይንሳዊ አልያም በአለማዊ ምልከታ የተሞላ ተጠራጣሪና ተቺያዊ አስተያየት ከማቅረቡ በፊት በደንብ በነገሩ እንዲያስብበት እመክራለሁ፡፡

የሚስጥራዊ ነገሮች አነፍናፊ የሆነው ግርሀም ሀንኩክ በመጨረሻ አክሱም ላይ መስገዱን መዘንጋት አይገባም፡፡ ሰውየው የሰገደው ለፅላቱ መኖር ከመሰለን አሁንም ሰውየውን አተኩረን አላየነውም ማለት ነው፡፡ (በቅዱስ መፅሀፍ የሚያምን ቢሆን እንኳን እሱ ያለው አለማዊ እውቀት ይሄ ዘመን ለታቦቱ የመስገጃ ጊዜ እንዳልሆነ እንዲያስብ የሚገደድ ሰው ነው) ሀንኩክ የሰገደው ላጠቃላዩ የአምላክ ቅኔ ነው፡፡ የአምላክ መንገድ ቀላል ነው፤ ቅኔውንም መፍታት ቢሆን፡፡ ግን በቅንነት መፈለግ ይገባል፡፡ አንድ ሰው ይህንን መንገድ ሲፈልግም በመጀመሪያ ማድረግ ያለበት በአለማዊ እውቀቶች የተቃኘውን አይምሮ ለጊዜው ገለል አድርጐ አዲስ በሆነ አጀማመር ቅዱስ ቃሉን ማየት ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ሀሳቦች የሚጋጩት (በእግዚአብሔር ቃሎች ውስጥ) በብዙ የአለም እውቀቶች ተወጥሮ በዛ መነፅር መፅሐፍ ቅዱስን ከማንበብ እንዲሁም ራሱን መፅሐፍ ቅዱስን ትኩር ብሎ ካለማየት ነው፡፡

ይህን ደግሞ በዚህ ሀሳብ ዙሪያ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በተከታታይ አስተያየታቸውን ከሰጡና በሁለት አፅናፍ ባሉ ሰዎች በተካሄደው እሰጥ አገባ በትክክል መረዳት ይቻላል፡፡ አንዱ (አቶ ቶማስ) በቂ ባልሆነ አለማዊ እውቀት ተዓብዮ፣ ሌላው (ዶ/ር ፈቃደ) ሃይማኖቱ ሊነካ አይገባም በሚል መነፅር እየተመለከቱ ነው ሀሳባቸውን የሰነዘሩት፡፡ በሁለቱም ሰዎች ሀሳብ ውስጥ ግን በተለይ በአቶ ቶማስ ፅሁፍ ትክክለኛዎቹ መልሶች ቁልጭ ብለው ተቀምጠዋል፡፡ ሆኖም ያጠለቋቸው መነፅሮች እነዛን መልሶች ሊያሳዩአቸው አልቻሉም፡፡ አሁን እንግዲህ የእነዚህን ሰዎች መነፅር እናውልቅና መልሶቹን ከፅሁፎቹ ውስጥ እየነቀስን እናውጣቸው፡፡ በእርግጥ አቶ ቶማስ በጣም ቅንና ስሜታዊ መሆናቸውን መገንዘብ አልተሳነኝም፡፡ ልክ መሆናቸውን ለማሳየት ማናቸውንም መስዋእትነት ከመክፈል ወደኋላ አይሉም፡፡ ይሄን ወድጄላቸዋለሁ፡፡ ነገር ግን ያሳስታሉና እፈራቸዋለሁ፡፡

አሁን ወደ ዋናው ጉዳይ እንግባ፤ እንግዲህ አቶ ቶማስ በሦስት ሳምንት ከፃፏቸው ሀሳቦች ውስጥ ሁለት ነገሮችን መምዘዝ ይቻላል፡፡ 1ኛው፡- በመፅሀፍ ቅዱስ ወስጥ የተፃፉ የተወሰኑ ታሪኮች ከዛ በፊት በነበሩ ዘመናት በተመሳሳይ ሁኔታ ተፈፅመዋል፤ ስለዚህም በመፅሀፍ ቅዱስ ውስጥ ያሉ የተወሰኑ ታሪኮች ካለፉ ታሪኮች የተኮረጁ ናቸው የሚል አንደምታ ያለው ነው፡፡ 2ኛው፡- ሀሳብ ደሞ እራሱ መፅሀፍ ቅዱስ ውስጥ ብዙ የተጋጩና የማይመስሉ ታሪኮች አሉ የሚል ሲሆን እነዛንም ሀሳቦች ከመፅሀፍ ቅዱስ ውስጥ እያወጡ ሊያስረዱን ሞክረዋል፡፡ እኔም እሳቸው እየለቀሙ ያወጧቸውን ታሪኮች ዋና ዋናዎቹን ከሳቸው ፅሁፍ ውስጥ ለቅሜ አውጥቼ ምን ያህል እንደሳቱ ለማሳየት እሞክራለሁ፡፡ ፀሃፊው ሀሳባቸውን ለማስረዳት ከተጠቀሟቸው ማስረጃዎች የተወሰኑትንና ዋና ዋናዎቹን ከራሳቸው ፅሁፍ እጠቅሳለሁ፤ ከዛም ይህንን በስህተት የተሞላ ትንታኔያቸውን ለማስተካከል እሞክራለሁ፡፡ 1ኛ/ “…ከአራት ሺህ አመት በላይ እድሜ ባስቆጠረው ጥንታዊ የግብፅ ሃይማኖታዊ ፅሁፍ ውስጥ የሰፈረውን ዝርዝር አንብቡ፡፡

3ሺህ አመት እድሜ እንዳለው ከሚነገርለት የሙሴ አስርቱ ትእዛዛት ጋር ተመሳሳይ ሆኖ ታገኙታላችሁ” 2ኛ/ “…ለምሳሌ የኦሪት መፅሐፍትንና የጥንት ግብፃውያንን የሃይማኖት ፅሁፎች በማስተያየት ስለ አማልክት ታሪክ ተመሳሳይነት መገንዘብ ይቻላል፡፡ ቃል በቃል አንድ አይነት የሆኑ የሃይማኖት ህግጋትና ትእዛዛት እንደሏቸው በማመሳከር እናያለን፡፡” 3ኛ/ “…እንግዲህ የአምላክ ልጅነት፣ ንግስና፣ ውልደትና የሰላሳ አመት ጥምቀት፤ የሞትና ትንሳኤ በጥንታውያኑ የግብፅ ሃይማኖት ውስጥ ምን ያህል ቦታ እንዳለው የሆረስ ታሪክ ከኢየሱስ፣ ከሚትራ፣ ከክሪሽናና ከዲየስየስ ይመሳሰላል የሚባልበት አንዱ ምክንያት ከእንደዚህ አይነት ትረካዎች የተነሳ ነው፡፡” ሌላው ደሞ ይህንን መኮራረጅ እንደ አቶ ቶማስ ሀሳብ፣ በክርስቲያኑ አለም ያሉ ሰዎችም (ጳጳስ ቤኔዴክት የመሰሉ) ተቀብለውታል በሚል ምን እንዳሉ ሳይገባቸው ለሀሳባቸው ማረጋገጫነት ተጠቅመውበታል፡፡ ለሳቸው ቅኔ የሆነባቸው የጳጳሱ ትክክለኛ ሀሳብ ምን ያህል ከእሳቸው ምልከታ ጋር እንደሚለያይ በስተመጨረሻ ላይ አሳያለሁ፡፡

አቶ ቶማስ ለሦስት ሳምንት ያህል ብዙ ቢዳክሩም ዋናው ሀሳባቸው ከዚህ በላይ እየለቀምኩ ባወጣኋቸው ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ ናቸው መጀመሪያ በዓምላክ ቃል ላይ ነው የተገዳደሩትና ከሱ ስም እንጀምር፡፡ እሳቸው የዓምላክ ስሞች ብለው የጠቀሷቸው ያህዌ፤ ኤሎሄ፣ አብና ወልድን ነው፡፡ ይሄ ደግሞ መፅሐፍ ቅዱስን በወፍ በረር አንብበው ሊተቹ መሞከራቸውን ያረጋግጣል፡፡ ከጠቀሷቸው አራት የተከበሩ ቃላቶች ውስጥ የአምላክ ስም (ምንም እንኳን በትክክል እየጠራነው እንደሆነ እርግጠኞች ባንሆንም) አንዱ ብቻ ነው፡፡ ይሄውም ያህዌ የሚባለው ነው፡፡ በተረፈ ኤሎሄ ማለት “አምላኬ” ማለት እንጂ ስም አይደለም፤ የመለኮት መገለጫ ነው፡፡ አብና ወልድ ደሞ አባትና ልጅ ማለት ሲሆን የአምላክን ሦስትነትና በምድር መገኘት የምናውጅበት ምሳሌ ነው፡፡ አሁን ደግሞ ፀሃፊው ግራ ተጋብተው ግራ ሊያጋቡን ወደሞከሩበት የኦሪት ዘፍጥረት ትንታኔያቸው እንሂድ፡፡ እሳቸው እንዲህ ነው የፃፉት፤ 2ኛ/ “…አንደኛው ትረካ በፍጥረት ምዕ.1 ላይ መጀመሪያ ቀንና ሌሊት፣ በሁለተኛው ቀን ሰማይን፣ በሦስተኛው ቀን ምድርን፣ ባህርን እንዲሁም እፅዋትን፣ በአራተኛው ቀን ፀሐይ፣ ጨረቃን ኮከቦችን ፈጠረ” አቤት ጉድ! በአምላክ ጥበብ በጣም በጣም ተሰብስቦና አጥሮ (ምን ሊባል እንደተፈለገ ሳይዘነጋ) የተሰጠንን አቶ ቶማስ የበለጠ አሳጥረው ሲነግሩን፣ በዚህ የማሳጠር ጥበባቸው ውስጥ ምን ያህል እንደሳቱና ምን ያህል የተሰጡንን መልእክቶች እንደገደፉ ቢገነዘቡ ኖሮ እንዴት ክው ብለው እንደሚደነግጡ እገምታለሁ፡፡

እስቲ የመጀመሪያዋን የመፅሐፍ ቅዱስ ክፍል (ዘፍ.1.1-5) እንጥቀስና ትልቁን ስህተታቸውን እንመልከት፡- መፅሀፍ ቅዱስ በኦሪት ዘፍጥረት 1፡1-5 እንዲህ ነው የሚለው፡- “በመጀመሪያ እግዚአብሄር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ፡፡ 2/ምድርም ባዶ ነበረች፤ አንዳችም አልነበረበባት፤ ጨለማማም በጥልቁ ላይ ነበረ፤ የእግዚአብሄርም መንፈስ በውሃ ላይ ሰፍኖ ነበር፡፡ 3/እግዚአብሄርም ብርሃን ይሁን አለ ብርሃንም ሆነ 4/እግዚአብሄርም ብርሃኑ መልካም እንደሆነ አየ፤ እግዚአብሄርም ብርሃንና ጨለማን ለየ 5/እግዚአብሄርም ብርሃኑን ቀን ብሎ ጠራው፣ ጨለማውንም ሌሊት አለው፡፡ ማታም ሆነ ጥዋትም ሆነ፣ አንድ ቀን…” እንግዲህ እዚህች ጋ የተሰራች ግድፈት እንዴት መላውን ሃሳባቸውን እንዳበላሸ እናያለን፡፡ የዘፍጥረት ታሪክ እንደሚነግረን እና መላውን መፅሀፍ ቅዱስ ስናነብ እንደሚገለፅልን በምዕራፍ 1 ቁ 1-2 እና ከቁጥር 3-5 ባለው ክፍተት ውስጥ ብዙ ጉዳዮች አሉ፡፡ ሰማይና ምድር በመጀመሪያው ቀን ሳይሆን የተፈጠሩት ቀደም ባለው ሌላ ጊዜ ውስጥ ነው፡፡ አምላክ ሰውንና በምድር ላይ ነዋሪዎችን ለመፍጠር ሲነሳ ምድርን ከፈጠራት ቆይቶ ነበር፤ በመጀመሪያው ቀን እግዚአብሔር የፈጠረው ነገር ብርሃንና ጨለማን መለየት ነው፡፡ ይህንንም በትክክል አተኩሮ ያነበበው ሰው ይረዳዋል፡፡

ለርስዎ አላዋቂነት ስንል ግን አንዳንድ መረጃዎች እንስጥዎት፡፡ አዳምና ሄዋንን አሳሳተ ብለው የጠቀሱት እባብ ወይም ሰይጣን (ከየት መጣ አለማለትዎ ገርሞኛል) የአጥቢያ ኮከብ ይለዋል መጽሐፍ ቅዱስ፡፡ የተፈጠረው እንደመልአክት ነበር፤ ትልቅ ስልጣን ነበረውም፡፡ በትምክህቱና መመለክንም ስለፈለገ ከሰማይ ወደ ምድር ተጥሏል፤ ስለዚህም መባረሩ ብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ይነግሩናል፡፡ እናም ሰይጣን ወደ ምድር የተጣለው በዚህ ክፍተት መሀል ባሉት ዘመናት ነው፤ ከዛም ምድር ጨለማ ሆና ለዘመናት ቆይታለች፡፡ ከዛ ነው እንግዲህ እግዚአብሔር ጨለማ የነበረችውን ምድር ከብዙ ዘመናት በኋላ ብርሃን ትሁን ብሎ ፈጠራውን የጀመረው፡፡ ሌላው እርስዎ በጥበብዎ አሳጥረው “በሶስተኛው ቀን ምድርን ባህርን እንዲሁም እጽዋትን ፈጠረ” ያሉትን በቀጥታ ከመጽሐፍ ቅዱስ ስንገለብጠው እንዲህ ይላል፡- ምዕ 1-11 “እግዚአብሔርም ምድርን ዘርን የሚሰጥ ሣርንና ቡቃያን፣ በምድርም ላይ እንደወገኑ ዘሩ ያለበትን ፍሬን የሚያፈራ ዛፍን ታብቅል አለ” እንዲሁም ሆነ፡፡

ሌላው አስደንጋጭ ግድፈትዎት ደግሞ ይሄ ነው፡፡ እግዚአብሔር በሶስተኛው ቀን እጽዋትን አልፈጠረም፤ እንዲበቅሉ አዘዘ እንጂ፡፡ ይህ ፈጠራ ሳይሆን ትእዛዝ የተሰጠበት ምክንያት የእጽዋት ዘር በምድር መሀፀን ውስጥ ስለነበሩ ነው፡፡ አዎ ቀደም ብሎ ብርሃን ይሁን ከማለቱ ብዙ ዘመን በፊት ምድርን ሲፈጥር እጽዋትን ፈጥሮ ነበር (አንዳንድ ብርሃነ ልቦና የሆኑ የእግዚአብሔር ሰዎች እንደሚያስቡትም ከሰው ውጭ ሌሎች ፍጥረታት ከብዙ ዘመናት በፊት ተፈጥረው ነበር) በመሃል ሰይጣን በማመፁ እግዚአብሔር እቅዱን እንዳዘገየ ይታመናል፤ ያም ሆነ ይህ እግዚአብሔር የነገረን እጽዋትን በዛ ጊዜ እንዳልፈጠረ ነው፤ እንዲበቅሉ አዘዘ እንጂ፡፡ ስለዚህ ጌታው አቶ ቶማስ የማያውቁትን ታላቅ ሚስጥራዊ መጽሐፍ ለመተንተን መነሳትዎ ትልቅ ስህተት ነው ባይ ነኝ፡፡ ሌላው “አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ ይለዋል፤ ይሄ ታዲያ የእግዚአብሔር አምሳል ነው” እና “…በእርግጥ እባቡ እንዳለው ፍሬውን ሲበሉ አልሞቱም፤ አይኖቻቸው ተከፈቱ…” የሚለው ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ምን ይላል መሰልዎት? “ለናንተ ወተት ወተቱ ነው መሰጠት ያለበት፤ ለጠንካራ ትምህርት ገና ናችሁና” ቅዱስ ጳውሎስ ይሄንን ያለው አማኞች ለሆኑት ግን በመንገዳቸው ገና ላልጠነከሩት ነው፡፡ ለእርስዎ ምን እንደሚሰጥዎ ግራ መጋባቱ አይቀርም፡፡ አምላክ ይህን ህግ ባፈረሳችሁ ግዜ ወይም ከዚህች ተክል በበላችሁ ግዜ ትሞታላችሁ ሲላቸው፣ ስለመንፈሳዊ ሞት እየነገራቸው ነው - ስጋ መንፈሳዊ ክብርን ተሸካሚ ነው፡፡

እኛ መንፈሳዊ አካላትነታችን የበዛ ፍጥሮች ነን፡፡ እግዚአብሔር መንፈስ ነው፡፡ የተናገረውም ስለመንፈሳዊ ሞት ነው፡፡ ከዛ መንፈስ የተገነጠለ ሰው ጐስቋላ ነው፡፡ ሁሉንም የሚተች ደግሞ ሁሉን የሚጠላ ነው፡፡ ለዚህም ነው አይናቸው የተከፈተው አዳምና ሄዋን በአካላቸው እራቁትነት አፍረው ከአምላክ ለመሸሸግ የሞከሩት፡፡ በመቶዎች ለሚቆጠሩ የምድር ፍጥረታት ስም ማውጣት የቻለውና የዳበረ አይምሮ ባለቤት የነበረው አዳም፤ በገነት ዛፎች ውስጥ ከአምላክ ለመሸሸግ ሞከረ፡፡ አዎ ብዙዎቻችን እስካሁንም እየሸሸን ነው፡፡ ከምን እንደምንሸሽ ባናውቅም፡፡ ወደ ታሪካዊ መኮራረጁ ከመሄዳችን በፊት የአቶ ቶማስ ታላቅ ስህተት የሆነው የኖህ ታሪክ እንመልከት፡፡ አንዱ ጥያቄያቸው ወይም ለመተቸት የሞከሩት እንዲህ ብለው ነው፡- “ኖህ ከአዳም አስረኛ ትውልድ ነው፤ እንዴት በ10 ትውልድ አለም በሰው ልጆች ቆሻሻ ተሞላች” ሲሉ የጠየቁት ግራ የሚያጋባ ነው፡፡ ወይስ መደመርም አይችሉም ልበል? ኖህ እኮ የነበረው አዳም ከገነት ከወጣ በኋላ 2ሺህ 1 መቶ 56 አመት (2156) በኋላ ነው፡፡ ምናልባት ከመቶ አመት በኋላ መስሎዎት ይሆን እንዴ? በኖህ ጊዜ ህዝቦች በምድር ላይ ለ2156 አመታት ያህል ኖረዋል፡፡

ሌላው አንድ ሚሊዮን እንኳን አይደርሱም ነው ያሉት (እንዴ? ትንሽ ያስቡ እንጂ!) አንድ ሚሊዮን ሊሞሉ እንደማይችሉ ለማስረዳት የተጠቀሙት ደሞ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ያለዎትን እውቀት የሚያስገምት ነው፡፡ አዳም ስድስት ልጅ ነው የወለደው ነው ያሉት፡፡ እስቲ ስለዚህ ጉዳይ መጽሐፍ ቅዱስ የሚለውን እንይ፡- ዘፍጥ ም5፡ 4 እንዲህ ይላል “አዳም ሴትን ከወለደ በኋላ የኖረው ሰባት መቶ ዓመት ሆነ፤ ወንዶችንም ሴቶችንም ወለደ፤ አዳም የኖረበት ዘመን ሁሉ ዘጠኝ መቶ ሰላሳ አመት ሆነ” አዪ ምን ያህል ቅዱሱን መጽሐፍ እንዳላነበቡ!! ዓምላክ ለእብራውያን በሰጠው ቅዱስ ቃሉ ላይ በስም የገለፃቸው አባቶች የመሲሁን (የክርስቶስን) ግንድ የያዙትን ብቻ ነው፡፡ በኖህ ሰዓት ስለነበሩት ህዝቦች ብዛት ግን ትንሽ ሂሳብ ቢሰሩ ተቀራራቢ ግምት ይኖርዎት ነበር፤ ነገር ግን አዳም የ500 አመት ሰው በነበረበት አካባቢ እስከ 10.000 ሰዎች እንደሚኖሩ ይገመታል፤ ይህም በትክክለኛ ሂሳብ የተቀመጠ ነው፡፡ ያንን ሂሳብ ለእርስዎ ለማሳየት ብሞክር ግን የጋዜጣውን ቦታ መሻማት ይሆናል፡፡ ነገር ግን በኖህ ዘመን ከ50 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ ይገመታል፡፡

(አስፈላጊ ከሆነ ሂሳቡ እንዴት እንደሚሰራ በግልዎ ልልክልዎት እችላለሁ፡፡) ሌላው ስለኖህ መርከብ ጉዳይ ነው፡፡ እንዴት አንድ ኳስ ሜዳ የሚያህል መርከብ ያን ሁሉ ፍጥረታት ቻለ፡፡ አይ የኢንተርኔት ዘመን - ችግሩ ይሄ ነው ጥራዝ ነጠቅ ያደርጋል! የአለም የኳስ ሜዳዎች ምን ያህል ህዝብ እንደሚይዙ አያውቁም ልበል፡፡ ከ5000 አመት በፊት አምላክ መርከቡን እንዲህ አድረገህ ስራ ነው ያለው ዘፍጥ 7፡16 ላይ “…የመርከቢቱን በር በጐንዋ አድርግ፤ ታችኛውንም ሁለተኛውንም ሦስተኛውንም ዓርብ ታደርግለታለህ” ከዓርቡም በተጨማሪ በጣራው ወጋግራ ላይ ብዙ ፍጥረታት ሊቀመጡ እንደሚችሉ ሊያስቡ ይገባል፡፡ ሌላው ደሞ ስለ ፍጥረቶቹ ብዛት የገለፁት የተሳሳተና ከ5000 ዓመታት በላይ የጊዜ ልዩነትን ያላገናዘበ ነው፡፡ ለምሳሌ የድመት ዘሮች የሚባሉትን ካወቁ ከዚህ በታች ያለው ለኖህ የተነገረው የእግዜአብሔር ቃል ይገባዎት ይሆናል፡፡ ቁጥር 20 ላይ “ከወፍ እንደ ወገኑ ከእንስሳም እንደወገኑ ከምድር ተንቀሳቃሽ ሁሉ እንደወገኑ በህይወት ይኖሩ ዘንድ ሁለት ሁለት እየሆኑ ወደ አንተ ይግቡ” በተጨማሪም የአለማት ፈጣሪ ፀጋ በመሃላቸው እንዳለ አይዘንጉ፡፡ ወደ ሁለተኛው የመኮራረጅ ነገር ስንሄድ አቶ ቶማስ እንደማስረጃ የተጠቀሙበት የጳጳስ ቤኔዴክት አባባል እሳቸው እንዳሰቡት እንደማይል ከራሳቸው ትርጉም ተነስቼ ለማብራራት እሞክራለሁ፡፡ በነገራችን ላይ አቶ ቶማስ ስለፃፉት የግብፆችም ሆነ የባቢሎን ሙሴ የኦሪት መጽሐፍት ከመፃፉ በፊት ስላሉ ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የሚመሳሰሉ ታሪኮች በህዝቦች ታሪክ ላይ ስለመፃፉ አንዳችም ተቃውሞ የለኝም፡፡ እንደውም እነዛ ታሪኮች ባይኖሩ ነበር አስገራሚ የሚሆነው፡፡ አሁን ወደ ጳጳሱ አባባል ልመለስ፡፡ እንዲህ ነው ያሉት፣- “የሰው ልጅ ነፍስ በአንዳች መንገድ እጁን ወደ አዳኝ አምላኩ እንደዘረጋ ነው” ይህ ምን ለማለት ነው? ይህን ለማብራራት ወደ ዘፍጥረት ታሪክ መመለስ ይኖርብናል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ አዳምን በሰራው ሀጥያት ከገነት ሲያስወጣው ያደረገው ነገር ቢኖር ለአዳምና ለሄዋን ቆዳ ማልበስ ነው፡፡ አዎ ቆዳው ዝም ብሎ የመጣ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር አንድ እንስሳን በመሰዋት ለአዳም ያለ መስዋዕት እንደማይድን ሲያመላክተው ነው፡፡ በመጨረሻው ዘመንም ልጁን ልኮ በልጁ መስዋዕትነት እንደሚያድነው ሲነገርው ነው፡፡ አቶ ቶማስ እንደመሰላቸው በሙሴ የተፃፉት ህጐች ከ3000 አመታት በፊት የታወቁ ሳይሆን አዳም ገና ከገነት ሲወጣ ከዛሬ 7500 አመታት በፊት ይታወቁ ነበር፡፡ ለሙሴ የተሰጡ ህጐች ስለመሲሁ የተሰጡ ተስፋዎች፣ ከአዳም ስህተት በኋላ ለው ልጅ መዳኛ የተዘጋጁ እቅዶች ናቸው፡፡ አዳም ከገነት ሲወጣ ይህንን ተስፋ ተሸክሞ ነው፡፡ አምላክ ያጠፋ ፍጥሩን ዝም ብሎ ሜዳ ላይ አለቀቀውም፡፡ ህጉንና ተስፋውን ሰጥቶት እንጂ፡፡ ስለዚህም ነው እሱ የነገራቸው አቤልና ቃየል መስዋዕትን የፈፀሙት፡፡ በሀዲስ ኪዳን ዘመን ጳውሎስ እንዳለው፤ “በእግዚአብሔርና በሰው ውስጥ ያለው መንፈስ ቅዱስ አሰራሩ አንድ ስለሆነ፣ ለእግዚአብሔር ያለውን ወስዶ በመንፈሱ አማካኝነት ለሰዎች ይነግራቸዋል” ስለዚህም ከአዳም በኋላ ያሉ ህዝቦች የአምላክን ተስፋ፣ የአዳኛቸውን የእግዚአብሔር ልጅ በምድር ላይ የሚያደርገውን ድርጊት በሙሉ ያውቁ ነበር፡፡ ምርጦቹ ያንን ተስፋ በሩቅ እያዩ ሩጫቸውን አስተካክለው ይጓዙ ነበር፡፡ ስለዚህም ነው ህጉን ስላላከበሩ፣ የሰጠውን ተስፋውን ስለናቁ በኖህ ጊዜ ሰዎች በጥፋት ውሃ የተቀጡት፡፡ ኖህ መንገዱን ከእግዚአብሔር ጋር ስላደረገ ይህንን ህግና ተስፋ ለልጆቹ ነግሮአቸዋል፡፡ ልጆቹም ለልጅ ልጆቻቸው፡፡ እንግዲህ ከኖህ በኋላ ያሉ ከዛሬ (550) አመት በፊት መሆኑ ነው፡፡

አንዳንዶች መንገዱን ሲከተሉ (እንደ ኢዮብና አብርሃም ያሉት) ሌሎቹ ደሞ በራሳቸው መንገድ ተርጉመው ተጠቀሙበት፡፡ አንዳንዶቹም “እኔ ነኝ ያ ነብይ” ብለው ታሪክ ፃፉ፤ ታሪክ አስፃፉ፡፡ ንጉሱ በሀውልቱ ላይ የፃፈውን ከድንግል ነው የተወለድኩት፣ በሰላሳ አመቴ ተጠመቅሁ ወይም በትክክል የእግዚአብሔር ልጅ (እውነተኛው) የሚያደርገውን የሰው ልጆችን ተስፋ ጽፎ ወይም አስጽፎ፡፡ ከኖህ የተላለፈውን የእግዚአብሔርን ህግም የኛ ነው ብሎ አስፍሮ ቢገኝ ምን አስገራሚ ይሆናል፡፡ እንግዲህ ሙሴ ከ3000 አመት በፊት የፃፈው ከአዳም ጀምሮ የሚታወቅ ህግና ተስፋን ነው፡፡ ሙሴ የክርስቶስን መንገድ የሚያመቻቹ ህዝቦች አሰልጣኝ ነው፡፡ እግዚአብሔር በሰይጣን የተታለለው ህዝብ በትክክል እንደምኞቱ ሊሆንለት ስላልቻለ፣ ከመረጠው ሰው (ከአብርሃም) ከሀጥያት የራቀ ህዝብ ለማሰልጠን ጀመረ እናም ያንን ለዘመናት በልቡ የነበረውን ለአዳም የሰጠውን ህግና ተስፋ ሰጣቸው፡፡ ስለዚህም ጳጳሱ ሊሉ የሞከሩት “በዘመናት ሁላ የሰው ልጆች በትክክልም ይሁን በተሳሳተ መንገድ እጃቸውን ወደ አምላካቸው እንደዘረጉ ነበር” ነው፡፡ በኖህና በሙሴ መካከል ባለው ዘመን የኖሩ የዓለም ህዝቦች በሙሉ አምላክ ለአዳምና ለነብያቱ የነገራቸውን ህግና ተስፋ በተለያየ መንገድ (በተለያየ አረዳድ ሰምተው ነበር፡፡) ስለዚህም አቶ ቶማስ፤ ግብፆች ይሁኑ ባቢሎናውያን ከማርስ ወይም ከጁፒተር እስካልመጡ ድረስ ለአዳም የተሰጠው ተስፋ አካል ናቸው፡፡

ምንም እንኳን ነገስታቶቻቸውና ካህናቶቻቸው ቢያምታቷቸውና ተስፋዎቹን ቢበሩዙባቸውም ወይም ታላቁን ተስፋ ከሌሎች አማልክት ቢሰጡባቸውም ስለ ሁሉም ነገር ያውቁ ነበር፡፡ (በተጣመመ መንገድ ቢሆንም) አሁን እንግዲህ እዚህ ጋ የሚመጣው ጥያቄ፤ ከነዚህ ሁሉ በዘመናት ካለፉ የእውነተኛውን የአምላክ ልጅ ታሪክ የኛ ነው ካሉ የአዳም ልጆች መሀል ትክክለኛው የእግዚአብሔር ልጅ አዳኙ ማነው የሚል ነው፡፡ ለዚህ መንገድ ማሳያ ከሐዋሪያት ስራ አንድ ሃሳብ እጠቅሳለሁ፡፡ እነ ጴጥሮስን ስለ ክርስቶስ በመስበካቸው ሊያስሯቸው ፈልገው ለያዟቸው ፈሪሳውያን አንድ ገማልያል የተባለ ፈሪሳዊ ሊቅ እንዲህ አላቸው፤ “ከዚህ ዘመን በፊት አንዱ እንዲሁ ተነሳ፤ ብዙዎችን አስከተለ፤ ከእግዚአብሔር ስላልሆነ ጠፋ፡፡ እነዚህም ከእግዚአብሔር ካልሆኑ ይጠፋሉ፡፡ ከእግዚአብሔር ከሆኑ ግን ምንም ልታደርጓቸው አትችሉም፡፡ ይልቁንስ ከእግዚአብሔር ስትጣሉ እንዳትገኙ” እንግዲህ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር የሆነው የክርስቶስ ወንጌል በሚያስገርም ፍጥነት በመላው አለም ተሰብኳል፡፡ ተስፋፍቷልም፡፡ ለእውነትነቱ ምስክርም ህያውነቱ ነው፡፡ ለዛሬ ይሄን ያህል ካልኩ ይበቃኛል፡፡ ከአቶ ቶማስ ጋርም የተግባባን ይመስለኛል፡፡ ለነገሩ ባንግባባም ችግር የለውም፤ እውነቱ ግን ይሄው ብቻ ነው!!

ከእለታት አንድ ቀን አንድ ተፈላሳፊ ሰው ታርኖፖል የሚባል ቦታ ይኖር ነበር፤ ይላል አንድ የአይሁዶች ተረት፡፡ ይህ ፈላስፋ እያነበበና እየተመራመረ ሳለ የሰፈር ወጣቶች መጥተው “ምክር ስጠን፣ አስተምረን፣ አንድ ታሪክ ንገረን” እያሉ አስቸገሩት፡፡ ፈላስፋውም “ለምን አንድ የውሸት ተንኮል ፈጥሬ አላባርራቸውም?” ሲል ያስብና፤ “ልጆች ወደዚያ አሮጌ የእምነት ቦታ፣ ወደ ምኩራቡ ሂዱ፡፡ እዛ አንድ ትልቅ የባህር ጭራቅ ታያላችሁ፡፡ አምስት እግር፣ ሶስት ዐይን እና እንደ ፍየል ያለ ጢም ያለው ሲሆን መልኩ አረንጓዴ ነው” አላቸው፡፡ ልጆቹ ወደተባለው ቦታ ሮጡ፡፡ ፈላስፋው ምርምሩን ይሠራ ጀመር፡፡ እነዚያን ደደብ ወጣቶች ተጫወትኩባቸው እያለ በሆዱ ፈገግ አለ፡፡ ሆኖም ጥቂት እንደቆየ የብዙ ሰዎች ዱካ ሰማ፡፡ በመስኮት ሲመለከት መአት አይሁዶች ሲሮጡ ተመለከተ፡፡ “ወዴት ነው የምትሮጡት?” ሲል ጠየቃቸው “ወደ አሮጌው የእምነት ቦታ” አሉት፡፡ “አልሰማህም እንዴ? አንድ አረንጓዴ፣ ባለአምስት እግር የባህር ጭራቅ ታየኮ?” ሲሉ ጠየቁት፡፡ ፈላስፋውም በሆዱ “ተንኮሌ ሠራ ማለት ነው!” ብሎ ተደሰተ፡፡

ጥናቱን ቀጠለ፡፡ ከጥቂት ደቂቃ በኋላ ግን ሌላ ግርግር ሰማ፡፡ በመስኮት ሲመለከት፤ ሴቱ፣ ህፃኑ፣ ሽማግሌው ሁሉ ይሮጣል፡፡ “ምን ተፈጠረ?” ብሎ ጠየቀ፡፡ “አንተ ፈላስፋ አይደለህም እንዴ? ስለ ጭራቁ አላወቅህም? አንድ ትልቅ የባህር ጭራቅ ከእምነቱ ቦታ ፊት ለፊት አለ፡፡ እሱን ልናይ መሄዳችን ነው! እንደ ፍየል አይነት ጢም ያለው አረንጓዴ ጭራቅ!!” ፈላስፋው እየሳቀባቸው ሳለ ዋናው አይሁዳዊ ቄስ - የእምነቱ ቦታ ኃላፊ፤ ከህዝቡ ጋር ሲሮጡ አያቸው፡፡ “የሰማያቱ ያለህ! ዋናው የእምነት አባት ካሉበትማ አንድ የታየ ጭራቅ ቢኖር ነው፡፡ እሳት ከሌለ ጭስ አይታይም!” አለና ፈላስፋው ባርኔጣውን አድርጐ፤ ካፖርቱን ደርቦ፤ ከዘራውን ይዞ፤ “ማን ያውቃል የጭራቁ መታየት እውነት ቢሆንስ?” እያለ ከህዝቡ ጋር መሮጥ ጀመረ፡፡ *** “አካፋን አካፋ እንጂ ትልቅ ማንኪያ ነው አንበል” ይላሉ ኬንያውያን፡፡ ይህን አባባል ስለማንነታችን፣ ስለዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታችን፣ ስለፓርቲያችን፣ ስለሀገራችን፣ ስለመከላከያችን፣ ስለሥልጣናችን፣ ስለልማታችንም ሆነ ስለዲሞክራሲያችን ስናወሳ ብናስታውሰው ይበጀናል፡፡

የመዋሸት መጥፎነቱ ልክ እንደፈላስፋው እኛኑ ተብትቦ መልሶ እውነት እንዲመስለን ማድረጉ ነው፡፡ ስለግልፅነት እያወራን የበለጠ ሚስጥራዊ የምንሆን ከሆነ ያው መዋሸት ነው፡፡ ዛሬ ያልነውን ነገ ካልደገምነው ያው መዋሸታችን ነው፡፡ ሰውን በሸራ ኳስ እያጫወትን እኛ በካፖርተኒ የምንጫወት ከሆነ ያው ማጭበርበራችን ነው፡፡ ያለአቅማችን ጉልበተኛ ነን ማለትም ሆነ ጉልበተኛ ሆነን ምስኪን ኮሳሳ ነን ማለትም ያው መዋሸት ነው፡፡ እያየን አላየንም፣ እየሰማን አልሰማንም፣ እያጠፋን አላጠፋንም ማለትም ያው መቅጠፍ ነው! “ያብዬን እከክ ወደ እምዬ ልክክም” ያው መዋሸት ነው! “ካፈርኩ አይመልሰኝ” ማለትም ያው መዋሸት ነው! አስገድደን የምንፈፅመውም ሆነ ዋሽተን የምናሳምነው፣ አሊያም በገንዘብ የምንደልልው፤ የዘወትሩን ሰው ቢያስጨበጭብልንም የክቱን ሰው ያሳዝናል፡፡

በመዋሸት የተገነባ አመኔታ ከጥርጣሬ የፀዳ አይሆንም፡፡ አንድ ፀሀፊ እንዲህ ይለናል፤ “የመጠራጠር አዝማሚያችን፤ ከምክንያታዊነታችንና ከእውነታው እያራቀ እሚወስደን፤ በቡድናዊ አመለካከት ውስጥ ስንገባ ነው፡፡ ሁላችንም በየውስጣችን ያለውን ጥርጣሬ፤ የህዝብ ሞቅ-ሞቅና የመንገኝነት ባህል ያበረታታዋል፤ ያጋግለዋል፡፡ ዕምነተ-ሰብ (cultist) የሚያጠቃው ደጋፊ (ቲፎዞ) በቀላሉ ሥልጣን ይሰጣል የሚባለው ለዚህ ነው፡፡ ተንኮለኛ አገዛዝን በፈለግህ ጊዜ፡- በሰዎች ያልተፈፀሙ ምኞቶች ላይ በመጫወት እነዚያን ህዝቦች እንደመንጋ ልትነዳቸውና ፍፁም ሠልጣን ልትጐናፀፍባቸው ትችላለህ፡፡ በፅኑ ማስታወስ የሚገባህ ነገር ደግሞ፤ እጅግ ስኬታማ የምትሆነው ሃይማኖትን ከሳይንስ ጋር ቀላቅለህ ስትጠቀም ነው፤ በጣም የረቀቀውን ቴክኖሎጂ ወስደህ፤ ከአንዳች ክቡር ዓላማ፣ ከማይጨበጥ እምነት ወይም አዲስ አይነት ፈውስ ጋር አጣብቀው፡፡ ያኔ መንጋው ህዝብ ይከተልሃል፡፡ አንተ ሳትሻ ልዩ ልዩ ትርጉም ይሰጥልሃል፡፡ አንተ የሌለህንና ያላሰብከውን ችሎታና ሥልጣንም ሰጥቶህ ቁጭ ይላል!” ይሄ እርግማን ነው፡፡ እርግማኑ በመንግሥትም፣ በተቃዋሚም፣ በሰባክያንም፣ በምዕመናንም አንፃር ብናሰላው ያው ነው፡፡ ህዝብን ማታለል ክፉ እርግማን ነው፡፡ የማታ ማታም ያስከፍላል፡፡

የሌለ ጀግና መፍጠርም ሆነ፤ ያለን ጀግና መካድ ሁለቱም ማታለል ነው፡፡ በከፋ መልኩ ሲታይ ራስንም ማታለል ነው፡፡ የሰው ዓላማ የኔ ነው ማለትና የሌላውን ስም የራስ ማድረግ፤ ከኢኮኖሚ ዘረፋም የከፋ ዘረፋ ነው፡- “ገንዘቤን የወሰደ ሰው፣ ወሰደ እንበል ከንቱ ነገር የእኔም የእሱም የዚያም ነበር፡፡ ግና ስሜን የሰረቀኝ፤ የማያከብረውን ወስዶ፣ እኔን በግልፅ አደኸየኝ!” ይለናል እያጐ፤ በፀጋዬ ገ/መድህን ብዕር ልሳን፡፡ ውሸት እንደማግኔት መግነጢሳዊ ኃይል አለው፡፡ ማግኔት፤ በአንዳች የማይታይ ኃይል ባካባቢ ያሉ ነገሮችን ይስባል፡፡ እነዚያ ነገሮችም በፈንታቸው የመሳብ ኃይል ያበጃሉ - ባካባቢያቸው ያሉትን ነገሮች በተራቸው ይስባሉ፡፡ ያንን ኃይል ይዘው ይቆያሉ፡፡

ሰዎችም በአንድ ውሸት ሲሳቡና ያንን ውሸት የራሳቸው ሲያደርጉ ከዚያ የሚለያቸው ኃይል አይኖርም፡፡ ኦርጅናሌ ዋሾውን እንደተአምረኛ ያዩታል፡፡ በዙሪያው ይከባሉ፡፡ እንደመንጋም ይነዳሉ፡፡ (ግሬት ዴ ፍራቼስኮ) በየፖለቲካና ኢኮኖሚያዊ ጉዳያችን አንፃር የሌለንን አለን፣ ያለንን የለንም ብለን ከዋሸንና ካሳመንን፤ ተከታያችን ሊደሰትበት፣ አልፎም ሊኮራበት ይችላል፡፡ ያም ሆኖ እንደማናቸውም ነገር ውሸትም ከጥቅም ውጪ የሚሆንበት ጊዜ (expiry date) አለው፡፡ የዘንድሮ ካፒታሊዝማችን በሶሻሊዝማችን ላይ፤ ዲሞክራሲያችንም በፊውዳላዊ መሰረታችን ላይ፣ “ቫለንታይን ዴይም” በሌለ ፍቅራችን ላይ የተጣደ ከሆነ፤ በሽሮ ላይ ቅቤ ባናቱ ጠብ እንደማድረግ አይነት ነው፡፡ ሹሯችን ዛሬም ያችው ሹሯችን ናትና! ዋናው ነገር እውነቷን፣ እቅጯን አለመርሳት ነው፡፡ “ሸንጐ ተሰብስቦ ለሚስቱ እውነቱን የማያወራ ባል አያጋጥምሽ!” ነው ነገረ-ዓለማችን!

በከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት በሽብርተኝነት ወንጀል ተጠርጥረው የተፈረደባቸውና በማረሚያ ቤት የሚገኙት የጋዜጠኛ እስክንድር ነጋና የአንድነት ዋና ፀሐፊ የእነ አንዷለም አራጌ የይግባኝ ጉዳይ ለ40 ቀን ተራዘመ፡፡ ባለፈው ወር ክርክሩ ለውሳኔ ተቀጥሮ የነበረ ሲሆን የአንድነት ፓርቲ የባህር ዳር አመራሮች ሻምበል የሺዋስ ይሁንአለምና አንዷለም አያሌው ከእነ እስክንድር ነጋ ጋር በአንድ መዝገብ ቢከሰሱም ይግባኝ የጠየቁት ግን በተለያየ መዝገብ በመሆኑ መዝገቡን አንድ ላይ ለማየትና ውሳኔ ለመስጠት ለትናንትና ተለዋጭ ቀጠሮ መሰጠቱ ይታወሳል፡፡

በትላንትናው ዕለት የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የግራ ዳኛ የሆኑት ዳኛ ብላቸው አንሶ የእነ እስክንድር የውሳኔ ቀጠሮ ለ40 ቀናት የተራዘመበትን ምክንያቶች ሲያስረዱ፤ አንደኛ:- የዕለቱ የመሀል ዳኛ ዳኜ መላኩ በሌላ ዕክል ምክንያት አለመገኘታቸውንና የእነ እስክንድር መዝገብም ሰፊ ውይይትና ጊዜን የሚፈልግ በመሆኑ ከሥር ፍርድ ቤት እንዲመጣ ታዝዞ፣ ሰፊ ውይይት እየተደረገበት በመሆኑ ይህ ሁሉ ተጠናቆ ውሳኔ ለመስጠት ለመጋቢት 18 ቀን 2005 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መሠጠቱን ተናግረዋል፡፡

በእነ አንዱአለም አራጌ የክስ መዝገብ ሥር ያሉትና ተፈርዶባቸው ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የሚገኙት ሻምበል የሺዋስ ይሁንአለም፣ ክንፈሚካኤል ደበበ፣ ናትናኤል መኮንን እና ዮሐንስ ተረፈ ችሎቱ ከተበተነ በኋላ ፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የደረሱ ቢሆንም ይህንኑ ውሳኔ በመስማት ወደ ማረሚያ ቤት ተመልሰዋል፡፡

የስድስተኛው ፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ፤ ካህናትና ምእመናን ስድስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባት ሊኾን ይገባል የሚሉትን ዕጩ እንዲጠቁሙ ያወጣው የስምንት ቀን መርሐ ግብር ትላንት፣ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ የተጠናቀቀ ሲሆን ለፓትርያሪክነት የተጠቆሙት ዕጩዎች ዛሬ ይለያሉ፡ እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን ቅን መሪ እንዲሰጥ፣ የወደደውንና የፈቀደውን በመንበረ ፕትርክናው እንዲያስቀምጥ ካህናትና ምእመናን አምላካቸውን በጸሎት እንዲጠይቁ የታዘዘው የአንድ ሳምንት የጸሎት ሱባኤ እስከ ምርጫው ፍፃሜ የካቲት 21 ቀን 2005 ተጠናክሮ እንዲቀጥል መልዕክት ተላልፏል፡፡ ዐዋጅም መፈጸሙ ተነግሯል፡፡ በምርጫው መሪ ዕቅድ መሠረት፣ በዛሬው ዕለት ካህናትና ምእመናን የዕጩ ፓትርያሪክ ጥቆማ የሰጡበትን ቅጽ የያዘው የታሸገ ሣጥን ተከፍቶ ተጠቋሚዎቹን የመለየት ሥራ እንደሚሠራ የአስመራጭ ኮሚቴው ሕዝብ ግንኙነት ሓላፊ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

በዕጩ ፓትርያሪክ ጥቆማው ካህናት፣ ምእመናንና ገዳማውያን ሳይቀሩ በንቃት መሳተፋቸውን የተናገሩት ሓላፊው አቶ ባያብል ሙላቴ፤ ጥቆማውን ኮሚቴው በዕጩነት ለሚለያቸው አምስት አባቶች ዋነኛ ግብአት አድርጎ እንደሚጠቀምበት ገልጸዋል፡፡ ኮሚቴው በዛሬው ዕለት ለጥቆማው አቀባበል በተዘጋጀው ቅጽ ላይ ካህናትና ምእመናን የጠቆሟቸው አባቶች ለፓትርያሪክነት ለሚመረጡ ዕጩዎች የተቀመጡትን መመዘኛዎች ማሟላት አለማሟላታቸውን ከግል መረጃዎቻቸው ጋር እያነጻጸሩ የመለየትና የማጣራት ሥራዎች እንደሚሠራ አቶ ባያብል አስረድተዋል፡፡

ሓላፊው አያይዘውም በፓትርያሪክነት መመዘኛው መሠረት ተጠቋሚዎቹን የመለየትና ተጨማሪ የማወዳደር ሥራዎች ከተሠሩ በኋላ፣ ኮሚቴው የካቲት 16 ቀን 2005 ዓ.ም ለተጠራው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የሚቀርቡትን አምስት ዕጩዎች ለይቶ የካቲት 14 ያስታውቃል ብለዋል፡፡ 
‹‹በአንድ ሰውም ይኹን በአንድ ሺሕ ሰው የተጠቆሙ የተለያዩ አባቶች ቢኖሩ ኮሚቴው የሚወስደው ለዕጩነት መጠቆማቸውን ነው፤›› የሚሉት አቶ ባያብል፣ ተጠቋሚው በዕጩነት ሊያዝ የሚችለው፣ በምርጫ ሕገ ደንቡ የፓትርያሪክነት መመዘኛውን አሟልቶ ሲገኝ እንጂ በብዙ ሰው ስለተጠቆመ ብቻ ባለመኾኑ የዕጩ ጥቆማውን ጥያቄ ከመምረጥ ወይም ምርጫ ሂደት ጋር ማሳሳት ተገቢ አለመኾኑን ገልፀዋል፡፡
ኮሚቴው ባለፈው ሳምንት ባወጣው መግለጫ ላይ የተጠየቁትን የድጋፍ ደብዳቤዎች አሟልተው የቀረቡ ዕጩ ጠቋሚዎች የተስተናገዱት በግላቸው እንደነበር የጠቆሙት አቶ ባያብል፣ በተለያዩ አጋጣሚዎች እገሌን ለዕጩነት ጠቁመናል ወይም እገሌን መርጠናል በሚል በቡድን የቀረቡ ማመልከቻዎችን ሳይቀበሉ መመለሳቸውን አስታውቀዋል፡፡

ከዚህ አኳያ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርት ብፁዕ አቡነ ሳሙኤልን በዕጩ ፓትርያሪክነት በመጠቆም እንዳቀረቡት የተገለጸው ደብዳቤ ተቀባይነት የሚኖረው፣ ደቀ መዛሙርቱ በነፍስ ወከፍ የኮሌጅ ተማሪነታቸውን ከኮሌጁ አስተዳደር በተጻፈ ደብዳቤ አስደግፈው ለጥቆማ ሲቀርቡ እንደኾነ ሓላፊው አስረድተዋል፡፡
አስመራጭ ኮሚቴው ባለፈው ሳምንት መግለጫው፣ የካቲት 21 ቀን በሚካሄደው የስድስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ የሚሳተፉት የመራጮች ብዛት 800 እንደኾኑ ካስታወቀ በኋላ በሂደት እየተለዩና ዕውቅና እየተሰጣቸው የተጨመሩ መራጮች መኖራቸው ተመልክቷል፡


በዚህም መሠረት ቤተ ክርስቲያኒቷ በሀገር ውስጥ ካሏት 53 አህጉረ ስብከት መካከል 790 መራጮች ይሳተፋሉ፤ ከሀገር ውጭ ባሏት ስምንት አህጉረ ስብከት ከእያንዳንዳቸው አራት (ከሥራ አስኪያጁ ጋር ካህናትን፣ ምእመናንን፣ ሰንበት ት/ቤቶችን የሚወክሉ አንድ አንድ) መራጮች፣ ከግብጽ ኮፕት ቤተ ክርስቲያን ጋር ባለው የሁለትዮሽ ስምምነት መሠረት አራት መራጭ ተወካዮች በአጠቃላይ ማስተካከያው እስከተነገረበት ጊዜ ድረስ 826 መራጮች እንደሚሳተፉ ታውቋል፡፡

 

የሩሲያዊው ሐኪምና ደራሲ የአንቶን ቼሆቭ 153ኛ የልደት በዓል የፊታችን ሰኞ ከቀኑ 11 ሰዓት ጀምሮ በፑሽኪን አዳራሽ በሙዚቃ ዝግጅት እንደሚከበር የሩስያ የሳይንስና የባህል ማዕከል አስታወቀ፡፡ በዕለቱ የሩስያ የፒያኖ እና የኦፔራ ሙዚቀኞች ናታሊያ ኮርሹኖቫ እና አሌክሲ ፓርፌኖቭ ሥራዎቻቸውን ለታዳሚው  ያቀርባሉ ተብሏል፡፡“ሥነፅሁፍ ውሽማዬ ሕክምና የሕግ ሚስቴ” ይል የነበረው ሩስያዊው ሐኪምና ደራሲ አንቶን ቼሆቭ፣ ሩስያ ካፈራቻቸውና ሥራዎቻቸው በዓለም ዙርያ ከናኙ የአጭር ልቦለድ ፀሐፍት አንዱ ነው፡፡ የሰኞ አመሻሹ ዝግጅት በሩስያ የባህላዊ ሻይ አፈላል (ሳሞቫር) የሚታጀብ ሲሆን ለታዳሚዎች የሻይ ግብዣ እንደሚኖር የባህል ማዕከሉ ጠቁሟል፡፡

የኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር ጐንደር ቅርንጫፍ ባለፈው ሳምንት አርብ መፅሐፍ ሲያስመርቅ የቀረበ አንድ የግጥም መፅሐፍ በስድስት ሺህ ብር ተጫርቶ ተሸጠ፡፡ “አፈርሳታ” የተሰኘው ይኸው መፅሐፍ በጐንደር ከተማ ሲመረቅ ጨረታውን አሸንፎ የገዛው ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ ነው፡፡ “አፈርሳታ” በከተማዋ ኗሪ ወጣት በሪሁን አሰፋ የተገጠሙ ማህበራዊ ጉዳዮችን ያካተተ የግጥም መፅሐፍ ነው፡፡

የ”አዲስ ነገር” ጋዜጣ መስራች እና ምክትል ዋና አዘጋጅ የነበረው ግርማ ተስፋው የገጠማቸው ግጥሞች የተካተቱበት “የጠፋችውን ከተማ ኅሰሳ” የግጥም መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ ገጣሚው በአራት የአለማችን ከተሞች ላይ ተመስርቶ የፃፋቸውን 69 ግጥሞች በአራት ክፍሎች ያቀረበ ሲሆን የመፅሐፉ ዋጋም 25 ብር ነው፡፡
ግርማ ተስፋው “አዲስ ነገር” ጋዜጣ ከተዘጋ በኋላ በ”አዲስ ነገር ኦንላይን” እና በኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጦች ላይ ፅሁፎቹ የታተሙ ሲሆን እ.ኤ.አ በ2011-12 ዓ.ም የትምህርት ዘመን በስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲ የናይት (Knight) ጆርናሊዝም ፌሎ ነበር፡፡

Saturday, 09 February 2013 12:41

“LIFE’S LIKE THAT” ለገበያ ቀረበ

የሥነፅሁፍ መምህር የሆኑት አቶ ገረመው ገብሬ ያዘጋጁአቸው አጫጭር የእንግሊዝኛ ልቦለዶች የተካተቱበት የምናብ ታሪኮች መድበል ሰሞኑን ለገበያ ቀረበ፡፡ LIFE’S LIKE THAT AND OTHER STORIES በሚል ርእስ ለንባብ የበቃው ባለ 44 ገፆች መፅሃፍ ለሀገር ውስጥ ገበያ በ25 ብር፣ ለውጭ ሀገራት 1.33 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡
16 ታሪኮች የተካተቱበትን መፅሐፍ ሔሪቴጅ ፕሪንቲንግ ኤንድ ትሬዲንግ ኃ.የተ.የግ.ማህበር ነው ያሳተመው፡፡ አቶ ገረመው ካሁን ቀደም የንግግር እንግሊዝኛ (Spoken English) መፅሃፍ አሳትመዋል፡፡

የግጥም በጃዝ የግጥም እና የሙዚቃ ዝግጅት የፊታችን ረቡዕ ከቀኑ 11፡30 እንደሚቀርብ አዘጋጆቹ ገለፁ፡፡ በራስ ሆቴል ትልቁ አዳራሽ የሚቀርበው 19ኛ ወርሀዊ ዝግጅት የመግቢያ  ዋጋ በሰው 50 ብር ነው፡፡አርቲስት ሜሮን ጌትነት መድረኩን በምትመራበት ዝግጅት ላይ አቶ አብዱ አሊጅራ ዲስኩር የሚያቀርቡ ሲሆን አርቲስት ጌትነት እንየው፣አበባው መላኩ፣ ዮሐንስ ገብረመድህን እና አለማየሁ ታደሰ የ”አንቲገን” ትያትርን ቅንጭብ በጃዝ ሙዚቃ ታጅበው እንደሚጫወቱ ተገልጿል፡፡