Administrator

Administrator

     ከአንድ ወር በፊት ኢትዮጵያን የጎበኙት የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በአዲስ አበባ በነበራቸው የሁለት ቀናት ቆይታ ለሆቴል 1.3 ሚ. ዶላር ማውጣታቸውን ዊክሊ ስታንዳርድ ድረገጽ ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡
ኦባማ እና አብረዋቸው የመጡ የደህንነትና የልኡካን ቡድን አባላት በአዲስ አበባ በሚገኙ አራት ሆቴሎች ማረፋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በሁለት ቀናት ቆይታቸው ለሆቴሎቹ በድምሩ 1.3 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር መከፈሉን ገልጿል፡፡የጉብኝቱ አዘጋጆች በመጀመሪያ ከሂልተን ሆቴል ጋር የ412ሺ 390 ዶላር ውል መፈጸማቸውንና በቀጣይም ከኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል ጋር የ246ሺ 877 ዶላር፣ ከካፒታል ሆቴልና ስፓ ጋር ደግሞ የ178ሺ 433 ዶላር ውል መፈጸማቸውን የጠቀሰው ዘገባው፤ በመጨረሻም ከሸራተን አዲስ ሆቴል ጋር የ488ሺ 141 ዶላር ስምምነት መፈጸማቸውን ጠቁሟል፡፡የልኡካን ቡድኑ አባል የሆነ አንድ የዋይት ሃውስ ፎቶ ግራፍ አንሺን እማኝነት በመጥቀስ ዘገባው እንዳለው፣ ኦባማ በሁለት ቀናት ቆይታቸው ያረፉት በሸራተን አዲስ ሆቴል እንደነበር መረጋገጡንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡

     በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ከሚገኙ የተለያዩ ትምህርት ቤቶች ከፍተኛ ነጥብ አምጥተው ዩኒቨርሲቲ ለገቡ ከ2 ሺ 500 በላይ ሴት ተማሪዎች ትላንት የሽኝት ፕሮግራም ተደረገ፡፡
“ዘር ኢትዮጵያ” በተባለ ድርጅት በአፍሪካ ህብረት አዳራሽ በተካሄደው ፕሮግራም፤ በተለያዩ የሥራ መስኮች ስኬታማ የሆኑ ሴቶች ለተማሪዎቹ ከህይወት ልምድና ተሞክሮአቸው አካፍለዋል፡፡
ሴት ተማሪዎቹ በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው የሚገጥሟቸውን በርካታ ችግሮችና መሰናክሎች በአሸናፊነት ለመወጣት የዓላማ ፅናት ሊኖራቸው እንደሚገባ የተነገራቸው ሲሆን ለዚህም ከወዲሁ ራሳቸውን ማዘጋጀት እንደሚኖርባቸው ምክር ተለግሰዋል፡፡ለወጣት ተማሪዎቹ የህይወት ልምድና ተሞክሮአቸውን ካጋሩ ስኬታማ ሴቶች መካከል የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የኢንፎርሜሽን ሲስተም ምክትል ፕሬዚዳንት ወ/ሮ መሊካ በድሪ፣ በመከላከያ ሚኒስቴር የስነ ምግባር መከታተያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ብ/ጄ ዘውዱ ኪሮስና  የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አዜብ ወርቁ ይጠቀሳሉ፡ሽኝት የተደረገላቸው ሴት ተማሪዎች በአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ በኩል የተመረጡ መሆናቸው ታውቋል፡፡
የፕሮግራሙ አዘጋጅ “ዘር ኢትዮጵያ”፤ አራት መቶ ሴትና አንድ መቶ ወንድ ተማሪዎችን በየወሩ 200 ብር ድጋፍ እያደረገ ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ የሚያበረታታ ሲሆን በቀጣዩ ዓመት ድጋፍ የሚደረግላቸውን ተማሪዎች ቁጥር ወደ  1000 ለማድረስ እቅድ መያዙ ተገልጿል፡፡  

     በመዲናዋ ባሉ ክፍለ ከተሞች በተመረጡ 10 ወረዳዎች ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ዘመናዊ የሰፈሮቹ የአድራሻና አቅጣጫ መጠቆሚያ ስርአት ሊዘረጋላቸው እንደሆነ እያካሄደ መሆኑን የአዲስ አበባ አስተዳደር የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ አስታወቀ፡፡
የቢሮው የኮሙኒኬሽን የሥራ ሂደት መሪ አቶ ማርቆስ አለማየሁ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ ዝርጋታው አቅጣጫ ጠቋሚ ምልክቶችን፣ ብሎክና የቤት ቁጥር ታፔላዎችን ያካትታል፡፡ የአድራሻ ስርዓቱ በዋናነት ለፖስታ አገልግሎት፣ የእሳት አደጋ መኪኖች ፈጥነው እንዲደርሱ እንዲሁም የአምቡላንስ አገልግሎት ለማግኘትና ወንጀልን ለመከላከል ወሳኝ መሳሪያ ይሆናል ተብሏል፡፡
ስርአቱን ለመዘርጋትም ካርታ የማዘጋጀት ስራ ሲከናወን የቆየ ሲሆን ታፔላዎቹ ደረጃቸውን ጠብቀው እንዲመረቱ ከብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን፣ ከህብረት ማኑፋክቸሪንግ ማሽን ኢንዱስትሪ ጋር የ40 ሚሊየን ብር ውል መገባቱን የጠቆሙት አቶ ማርቆስ፤ አሁን የስራው የመጀመሪያ ምዕራፍ ወደ ሆነው ምልክት ተከላ ተሸጋግሮ ስራው እየተገባደደ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
ከአስሩም ክፍለ ከተሞች አንድ አንድ ወረዳ የተመረጠ ሲሆን ለአብነትም ጉለሌ ወረዳ 10፣ የካ ወረዳ 13፣ ቂርቆስ ወረዳ 2 እና አዲስ ከተማ ወረዳ 9ን ጠቅሰዋል፡፡ የእነዚህ ወረዳዎች ተከላ እንደተጠናቀቀም 30 የሚሆኑ ወረዳዎች ላይ ወደ ተግባር ለመግባት በዝግጅት ላይ ነን ብለዋል - የሥራ ሂደት መሪው፡፡

መንግስት ለአስቸኳይ እርዳታ 33 ሚ. ዶላርቢያሰባስብም፣ ተመድ 230 ሚ. ዶላር ያስፈልጋል ብሏል
• “አብዛኛው ተረጂ የሚገኘው በኦሮምያ ክልል ነው”

   የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኢትዮጵያ በተከሰተው የዝናብ እጥረት ሳቢያ የምግብ እህል እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ከዚህ በፊት ከተገመተው በላይ በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንና 4.5 ሚሊዮን መድረሱን አስታወቀ፡፡
አንድ ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣን በበኩላቸው፤ ችግሩን ለመፍታት ክልሎች ራሳቸው ከሚመድቡት በጀት በተጨማሪ መንግሥት 700 ሚ. ብር መድቦ ለተረጂዎች ድጋፍ ለማድረግ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ጠቅሰው ከተረጂዎች መካከል 40 በመቶ ያህሉ በኦሮምያ ክልል እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ያወጣውን ሪፖርት ጠቅሶ አጃንስ ፍራን ፕሬስ ትናንት እንደዘገበው፣ በአመቱ የዝናብ መጠኑ ከተገመተው በታች መሆኑን ተከትሎ የምግብ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ከተገመተው 2.9 ሚሊዮን የ55 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 4.5 ሚሊዮን ደርሷል፡፡
በኢትዮጵያ የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ሃላፊ ዴቪድ ዴል ኮንቴ እንዳሉት፤ በዝናብ እጥረቱ ክፉኛ የተጎዱት የአገሪቱ አካባቢዎች ምስራቃዊ አፋርና ደቡባዊ ሶማሌ ክልሎች ሲሆኑ በአንዳንድ የኦሮምያ፣ የትግራይና የአማራ ክልሎች አካባቢዎችም፣ ባልተለመደ ሁኔታ የከብቶች ግጦሽና የውሃ ሃብቶች እጥረት ተከስቷል፡፡በአሜሪካ መንግስት የሚደገፈው “ፋሚን ኧርሊ ዋርኒንግ ሲስተምስ ኔትወርክ” የተባለ የርሃብ ቅድመ ማስጠንቀቂያ የሚሰጥ ተቋምም፤ በኢትዮጵያ በርካታ እንስሳት በመኖ እጥረት ተጠቂ ሊሆኑ እንደሚችሉ ማስጠንቀቁንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡የኢትዮጵያ መንግስት ለአስቸኳይ የምግብ እርዳታ 33 ሚሊዮን ዶላር አሰባስቧል ያለው ዘገባው፤ ይሄም ሆኖ ግን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ መንግስት በመጪዎቹ አራት ወራት ጊዜ ውስጥ 230 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልገው ማስታወቁን አመልክቷል፡፡የእርዳታ ሰጪ ድርጅቶች ሃላፊዎች ችግሩ በተከሰተባቸው አካባቢዎች ምግብ የማከፋፈሉ እንቅስቃሴ ፈጣን አለመሆኑ እንዳሳሰባቸው ጠቁሞ፣ ለዚህ ችግር መከሰት አስተዋጽኦ ካበረከቱ ጉዳዮች መካከልም በጅቡቲ ወደብ ያለው መጣበብ አንዱ ነው ብሏል፡፡

- ፖሊስ በህገ ወጥነት የተጠረጠሩ 66 ሺህ ያህል ድረ ገጾችን እየመረመረ ነው
       - ቻይናውያን በአሜሪካ ላይ 700 ያህል የኢንተርኔት ጥቃቶችን ፈጽመዋል


     የቻይና ፖሊስ የአገሪቱን ደህንነት አደጋ ላይ በሚጥሉ አገር አቀፍና አለማቀፍ የኢንተርኔት ወንጀል ተግባራት ላይ ተሰማርተው ተገኝተዋል ያላቸውን 15 ሺህ ያህል ዜጎች በቁጥጥር ስር ማዋሉን ባለፈው ማክሰኞ ማስታወቁን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
የቻይና የደህንነት ሚኒስቴርን መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ የአገሪቱ ፖሊስ ከኢንተርኔት ጋር የተያያዙ 7 ሺህ 400 የወንጀል ክሶችን ሲመረምር ቢቆይም የተጠቀሱት 15 ሺህ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር የዋሉት በምን ያህል ጊዜ ውስጥ እንደሆነ አልገለጸም፡፡
የቻይና መንግስት ባለፈው ወር ኢንተርኔትን ማጽዳት የተሰኘ መሰል ወንጀሎችን መከላከል የሚያስችል የስድስት ወራት ብሄራዊ ዘመቻ ተግባራዊ ማድረግ መጀመሩን የጠቆመው ዘገባው፤ ተጠርጣሪዎችን በማሰር የተጀመረው እርምጃ በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የአገሪቱ የደህንነት ሚኒስቴር ማስታወቁን ገልጿል፡፡
ዘመቻው በኢንተርኔት የሚሰሩ ወንጀሎችን ከመከታተልና ተጠርጣሪዎችን ለፍርድ ከማቅረብ በተጨማሪ ተደራጅተው በኢንተርኔት ወንጀል የሚሰሩ ቡድኖችን የማጥፋት ተልዕኮ እንዳለውም ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የቻይና ፖሊስ ህገወጥና ጉዳት የሚያስከትሉ መረጃዎችን በሚያስተላልፉ እንዲሁም የወሲብ፣ የጦር መሳሪያዎችና የቁማር ማስታወቂያዎችን በሚያሰራጩ 66 ሺህ ያህል የአገሪቱ ድረገጾች ላይ ምርመራ ሲያደርግ መቆየቱንም አስረድቷል፡፡
ኤንቢሲ ኒውስ በበኩሉ፤ የተደራጁ ቻይናውያን የኢንተርኔት ዘራፊዎች የአሜሪካን ከፍተኛ የደህንነት ባለስልጣናት የኢሜይል ቁልፍ ሰብረው በመግባት የተለያዩ የወንጀል ድርጊቶችን እንደፈጸሙ መረጋገጡን ዘግቧል፡፡
ቻይናውያን የኢንተርኔት አጭበርባሪዎች ባለፉት አምስት አመታት በአሜሪካ ላይ ለ700 ጊዜያት ያህል ጥቃት ፈጽመዋል ያለው ዘገባው፤ ከ600 በላይ የሚሆኑት ስኬታማ ጥቃቶች የተፈጸሙትም በአሜሪካ የመንግስት፣ የግልና የኩባንያ ድረገጾችና የኢሜል አድራሻዎች ላይ መሆኑንም ገልጿል፡፡

20 ኪሎ ሜትር ቁመት ይኖረዋል፣ “የጠፈር አሳንሰር” ይገጠምለታል
   ቶዝ ቴክኖሎጂ የተሰኘው የካናዳ የጠፈር ምርምር ቴክኖሎጂ ኩባንያ በዓለማችን ትልቁ እንደሚሆን የተነገረለትንና 20 ኪሎ ሜትር ቁመት ያለውን ሰማይ ጠቀስ ማማ በመገንባት፣ ረጅሙን የጠፈር አሳንሰር ሊዘረጋ መሆኑን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
የጠፈር ተመራማሪዎችን ያለ መንኮራኩር በቀጥታ ወደ ጠፈር ማጓጓዝ የሚችለው  አሳንሰር፤ ጠፈርተኞችን በመንኮራኩር ወደ ጠፈር ለመውሰድ ከሚያስፈልገው ነዳጅ 30 በመቶ ያህል ያነሰ ነዳጅ እንደሚጠቀምና ወጪ ቆጣቢ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
የጠፈር አሳንሰሩ ዲዛይነር የሆኑት ዶ/ር ብሬንዳን ኩይኔ እንዳሉት፣ ጠፈርተኞች በአሳንሰሩ ተሳፍረው ከመሬት በ20 ኪሎሜትሮች ርቆ ከሚገኘው የማማው አናት ላይ ከወጡ በኋላ፣ በቀላሉ በጠፈር አውሮፕላኖች እየተሳፈሩ ወደ ጠፈር ጠልቀው የሚገቡበትና ስራቸውን የሚያከናውኑበት ዕድል ይፈጠርላቸዋል፡፡
አሳንሰሩ የሚገጠምበት ሰማይ ጠቀስ ማማ፣ በአሁኑ ወቅት የአለማችን ረጅሙ ህንጻ በመሆን ክብረ ወሰን ይዞ ከሚገኘውና 830 ሜትር ርዝማኔ ካለው የዱባዩ ቡርጂ ከሊፋ ህንጻ በ20 እጥፍ ያህል ቁመቱ እንደሚረዝም የጠቆመው ዘገባው፤ ማማው  ከዚህ በተጨማሪም ለነፋስ ሃይል ማመንጫነት፣ ለኮሙኑኬሽንና ለቱሪዝም አገልግሎት እንደሚውልም ገልጿል፡፡
ማማው ቁመተ ረጅም ከመሆኑ ጋር በተያያዘ በንፋስ የመገንደስ አደጋ ሊገጥመው አይችልም ወይ ለሚለው የብዙዎች አስተያየት ምላሽ የሰጡት የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ካሮሊን ሮበርትስ፤ ስጋት አይግባችሁ፣ መሰል አደጋዎችን መቋቋም እንዲችል አድርገን ነው ንድፉን የሰራነው ብለዋል፡፡
የአሜሪካ የፈጠራ መብቶች ቢሮ፤ የካናዳው ኩባንያ ላቀረበው ልዩ የሆነ የጠፈር ማማና አሳንሰር ፈጠራ እውቅና መስጠቱንና ፕሮጀክቱም ተቀባይነት ማግኘቱን ዘገባው አክሎ ጠቁሟል፡፡ 

  ፌስቡክ  በግማሽ ደቂቃ 5 ሺ 483 ዶላር ገቢ ያገኛል

   በድረ-ገጾች አማካይነት በአለማቀፍ ደረጃ የሚከናወነው “የኤሌክትሮኒክ ንግድ” በየግማሽ ደቂቃው በድምሩ የ1.2 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እያስገኘ መሆኑ በጥናት መረጋገጡን ዘ ሂንዱ ታይምስ ረቡዕ ዕለት ዘገበ፡፡
አሶቻም ዲሎይት የተባለው አለማቀፍ የጥናት ተቋም ሰሞኑን ይፋ ያደረገውን የጥናት ውጤት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በከፍተኛ ሁኔታ በመስፋፋት ላይ በሚገኘውና ትርፋማነቱ እየጨመረ በመጣው የኤሌክትሮኒክ ንግድ ከፍተኛ ገቢ እያገኙ ካሉት የአለማችን ታላላቅ ኩባንያዎች መካከል ቀዳሚነቱን የያዘው ታዋቂው የማህበራዊ ድረ-ገጽ ፌስቡክ ነው።
ፌስቡክ በኤሌክትሮኒክ ንግድ በየሰላሳ ሰከንዱ 5 ሺህ 483 ዶላር ገቢ ያገኛል ያለው ጥናቱ፤ ፒንተረስት እና ትዊተር የተባሉት የማህበራዊ ድረ ገጾችም በ4 ሺህ 504 እና በ4 ሺህ 308 ዶላር የግማሽ ደቂቃ ገቢ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃዎችን የያዙ የአለማችን የኤሌክትሮኒክ ንግድ ገቢ ቀዳሚ ኩባንያዎች ናቸው ብሏል፡፡
ማህበራዊ ድረገጾች መስፋፋታቸው በአለማቀፍ ደረጃ በኤሌክትሮኒክ ንግድ ገቢና ትርፍ ረገድ ከፍተኛ እድገት እንዲመዘገብ ቁልፍ ሚና ተጫውቷል ያለው ዘገባው፤ ማህበራዊ ድረ ገጾቹ የኩባንያዎችን ምርቶችና አገልግሎቶች በተመለከተ ፈጣን መረጃዎችን በማሰራጨትና ንግዱን በስፋት በማቀላጠፍ ረገድ አስተዋጽኦ እንዳደረጉ ዘገባው ገልጿል፡፡
ኤሌክትሮኒክ የክፍያ ስርአቶች በስፋት መዘርጋታቸውም ንግድ በአለማቀፍ ደረጃ የተቀላጠፈ እንዲሆንና ገዢና ሻጮችን ለአደጋ ከሚያጋልጠው የካሽ ግብይት ወደ ኤሌክትሮኒክ ክፍያ ፊታቸውን እንዲያዞሩ ያደረገ ሲሆን የኤሌክትሮኒክ ንግድ እንዲስፋፋም የራሱን አስተዋጽኦ አበርክቷል ተብሏል፡፡

 ሌላ የልጅ ልጃቸውም በድብደባ ወንጀል ተከስሶ ነበር
   የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንትና የጸረ አፓርታይድ ታጋይ የኔልሰን ማንዴላ የልጅ ልጅ የሆነው ማንዴላ፣ አንዲትን ደቡብ አፍሪካዊት የ15 አመት ልጃገረድ አስገድዶ በመድፈር ወንጀል ተከስሶ ባለፈው ሰኞ ፍርድ ቤት መቅረቡን ዘ ጋርዲያን ዘገበ።
ልጃገረዷን ጆሃንስበርግ ውስጥ በሚገኝ አንድ መጠጥ ቤት ውስጥ አስገድዶ ደፍሯል በሚል በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋለው የ24 አመቱ ቡሶ ማንዴላ፤ ባለፈው ሰኞ  ለመጀመሪያ ጊዜ ፍርድ ቤት የቀረበ ሲሆን በሳምንቱ መጨረሻ በጆሃንስበርግ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቀርቦ ጉዳዩ እንደሚታይ ይጠበቃል፡፡
ቡሶ ማንዴላ ከሁለት ሳምንታት በፊት ልጃገረዷ በመጠጥ ቤቱ መጸዳጃ ቤት ውስጥ ሳለች ተከታትሏት ሄዶ አስገድዶ ደፍሯታል መባሉን የጠቆመው ዘገባው፣ ጥቃቱ የደረሰባት ልጃገረድ ክስ መመስረቷን ተከትሎ ባለፈው ሳምንት በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉንም አስታውሷል፡፡
ተጠርጣሪው የማንዴላ የልጅ ልጅ ስለሆነ ብቻ ከሌሎች ወንጀለኞች ተለይቶ የሚታይበት ምክንያት የለም ያለው የጆሃንስበርግ ፖሊስ፤ እንደማንኛውም ተጠርጣሪ እንደሚያዝና ጉዳዩ በፍርድ ቤት ተጣርቶ የአገሪቱ ህግ ባስቀመጠው መሰረት ተገቢው ውሳኔ እንደሚሰጠው አስታውቋል፡፡
ተከሳሹ ማንዴላ ከሶስቱ ሚስቶቻቸው የመጀመሪያዋ ከሆነችው ኤቭሊን ማሴ ከወለዷቸው ልጆች ከአንዷ እንደተወለደና አያቱ ማንዴላ በህይወት ሳሉ በተናዘዙለት መሰረት 300 ሺህ ዶላር እንደወረሰ ያስታወሰው ዘገባው፤ ማንድላ ማንዴላ የተባለው ሌላ የኔልሰን ማንዴላ የልጅ ልጅም ከወራት በፊት አንድን የ40 አመት ደቡብ አፍሪካዊ ደብድቧል በሚል ተከሶ ፍርድ ቤት ቀርቦ እንደነበርም አክሎ ገልጿል፡፡

  ባለፈው ሳምንት ለገበያ የቀረበው ሌላው መፅሐፍ በደራሲ ተስፋዬ ገብረሥላሴ የተደረሰው “ጣፊናስ” የተሰኘ ልብወለድ ነው፡፡ አሁን በህይወት የሌለው ደራሲና ሃያሲ መስፍን ኃብተማርያም በመጽሐፉ የጀርባ ሽፋን ላይ በሰጠው አስተያየት፤ “…በታሪኩ ሂደት ለጥቅም የቆሙና ከአገርና ከህዝብ እንቅደም ያሉ ኢትዮጵያውያን የመኖራቸውን ያህል ለአገራቸው የሚሟገቱና መስዋዕትነት ለመክፈል የቆረጡ ውድ የኢትዮጵያ ልጆችም ስሜትን ወጥረው ይይዛሉ…” ብሏል፡፡ የቅድስት ማርያም ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ ያሳተመው “ጣፊናስ”፤ 308 ገፆች ያሉት ሲሆን ዋጋው 68 ብር ነው፡፡

የጥበብ መጀመሪያ ነገሮችን በትክክለኛ ስማቸው መጥራት ነው፡፡
የቻይናውያን አባባል
ሃቀኛ ዜጋ በራሱአገር ስደተኛ ነው፡፡
የአሜሪካውያን አባባል
ላንተ ሲል የዋሸ፣ ባንተ ላይም መዋሸቱ አይቀርም፡፡
የቦስንያ አባባል
ተረት ወደ እውነታ የሚያሻግር ድልድይ ነው።
የአረቦች አባባል
የእውነት ባሪያ የሆነ ሰው ነፃ ነው፡፡
የአረቦች አባባል
ሁልጊዜ እውነትን በቀልድ መልክ ተናገር፡፡
የአርመናውያን አባባል
ከሚያቆስል እውነት የሚፈውስ ውሸት ይሻላል፡፡
የቼኮች አባባል
እውነት ሁልጊዜ ቤት አልባ ናት፡፡
የዳኒሾች አባባል
ያለጊዜው የሚነገር እውነት አደገኛ ነው፡፡
የግሪካውያን አባባል
እውነትን አለመግለፅ ወርቅን መደበቅ ነው።
የግሪካውያን አባባል
እውነትን በራሷ ድምፅ ታውቃታለህ፡፡
የይሁዳውያን አባባል
ከዋሾ ጓደኛ ሃቀኛ ጠላት ይሻላል፡፡
የጀርመናውያን አባባል
የጎረቤትህን ሃቀኝነት በራስህ አትለካ፡፡
የአሜሪካውያን አባባል
እግዚአብሔር በሃቀኛ ልብ ውስጥ ይኖራል።
የጃፓናውያን አባባል