Administrator

Administrator

     ቅልጥጥ ያሉ የሀብታም ገበሬ ልጅ ናቸው፡፡ ሐጂ አባመጫ አባደጋ፡፡ አባታቸውም ሆኑ አያታቸው በርካታ ጋሻ የቡና መሬት የነበራቸው ሀብታሞች እንደነበሩ አጫውተውናል፡፡ ሐጂ አባመጫ አሁን የሚኖሩት አጋሮ ከተማ ውስጥ ቢሆንም የተወለዱት ከከተማው ትንሽ ወጣ በምትል ኪሎሌ በተባለች የገጠር መንደር ነው፡፡
ሐጂ አባመጫ እድሜያቸውን በትክክል አያውቁትም፡፡
74 ወይም 75 ዓመቴ ነው ቢሉም ከዚያ በላይ እንደሚሆናቸው መገመት ይቻላል፡፡ አባታቸው በልጅነት ቢሞቱባቸውም አቶ ሺበሺ ገብረየስ የተባሉ ሞግዚት ተሹሞላቸው በቅምጥል ነው ያደጉት፡፡ አገር መጐብኘት የጀመሩት በልጅነታቸው ሲሆን የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚበርባቸውን ከተሞች ሁሉ ማየትና መጐብኘታቸውን ይናገራሉ፡፡ ከጂማ ጐሬ፣ ከጂማ አዲስ አበባ፣ ከጂማ ጋምቤላ፣ ከጂማ አስመራ፣ ከጂማ… ብዙ ቦታዎችን ጐብኝተዋል፡፡ ሐጂ ወደ ሳዑዲ የሄዱትም በልጅነታቸው እንደሆነ አውግተውናል፡፡ከቦታ ቦታ የሚዘዋወሩት በአውሮፕላን ቢሆንም፣ የዚያን ጊዜ አውሮፕላኖች አይመቹም፡፡ ቡና፣ ቆዳ፣ በርበሬ፣ ቅመማ ቅመም፣… ይጫንባቸዋል፡፡ ሰውና ዕቃ የሚጫነው አንድ ላይ ነበር፡፡ ይህ ነገር ለወጣቱ ሐጂ አባመጫ አልተመቻቸውም፡፡ “የራሴ አውሮፕላን ቢኖረኝ!” እያሉ ማሰብ ጀመሩ፡፡
በአንድ ወቅት ተከሰው አዲስ አበባ መጥተው ነበር፡፡ ከራስ አደፍርስ 20 ጋሻ የቡና መሬት ገዝተው ነበር፡፡ ሳይገብሩ ብዙ ይቆያሉ፡፡ ራስ አደፍርስ ከስሰው አዲስ አበባ አስጠሯቸው፡፡ ሞግዚታቸውን አቶ ሺበሺ፣ ቅጥረኛ ፀሐፊዎቻቸውን፣ ሌሎች አጃቢዎችንም አስከትለው መጡ፡፡ ራስ አደፍርስ “የግብር አልከፈላችሁ፣ ማር አልጫናችሁ… ምንድነው ነገሩ?” ብለው ተቆጡ፡፡
ጥፋታቸውን አምነው፣ ግብሩንም ለመክፈል ተስማምተው ተመለሱ፡፡የግል አውሮፕላን እንዲኖራቸው የመፈለግ ጉጉታቸው እየጨመረ ሄዶ ለመግዛት ወሰኑ፡፡ እንዳጫወቱን፤ አጋሮ እንደተመለሱ በ13 ዓመታቸው፤ ማርትሬዛ በስልቻ ሞልተው ብቻቸውን አዲስ አበባ መጥተው ራስ አደፍርስን “አውሮፕላን መግዛት እፈልጋለሁ” አሏቸው፡፡ ራስም ግራ በተጋባ ስሜት፤ “ለመሆኑ አውሮፕላን በስንት ብር ነው የምትገዛው?” በማለት ጠየቋቸው፡፡ ሐጂ አባመጫም፤ “ጠይቀህ ንገረኝ እንጂ!” ሲሉ መለሱላቸው፡፡ ወሬው ራስ መስፍን ስለሺ ጋ ደረሰና በንዴት ጦፉ፡፡“ብሩን አምጣ፡፡ እኔ እገዛልሃለሁ” በማለት የያዙትን ገንዘብ ተቀበሏቸው፡፡ በዚህ ብቻ አላበቁም፡፡ “ጨምር!” አሏቸው፡፡ “አውሮፕላኑን ሳላይ እንዴት እጨምራለሁ? እኔ ከዚህ በላይ የለኝም” አሉ ሐጂ አባመጫ፡፡ ራስ መስፍን፣ “እንዴት አውሮፕላን ለመግዛት ትነሳለህ? ወንጀል መሆኑን አታውቅም?” በማለት ሊያስሯቸው ፈለጉ፡፡ሐጂ “እኔ ውንጀላ መሆኑን አላወኩም” አሉ፡፡ ራስ አደፍርስና የቢትወደድ እንዳልካቸው መኮንን አባት ሽምግልና ገቡና “አሁን ይኼ ልጅ ምኑ ይታሰራል? ወጣት ነው፤ የመግዛት ፍላጐት አደረበት፣ ለመግዛት ተነሳ፡፡ ከዚህ ጥፋ ብሎ ማባረር ነው እንጂ ምኑ ይታሰራል?...” በማለት ሸመገሉ፡፡ በዚህ አይነት ሐጂ አባመጫ ከእስር ድነው፣ ሉክስ (አዲስ) ላንድሮቨር ገዝተው ወደ አገራቸው ተመለሱ፡፡ሐጂ አባመጫ ለቤተሰባቸው ሁለተኛ ልጅ ናቸው፡፡ ታላቃቸው ደግሞ ሴት ናቸው፡፡ ስለዚህ በተለያየ ቦታ ያለውን የቡና እርሻ የሚያስተዳድሩት እሳቸው ናቸው፡፡ በአንድ ወቅት ከወረሱት ሌላ በግላቸው 12 ጋሻ መሬት ቡና ነበራቸው፡፡ ታዲያ ቡና ተለቅሞ ሲሸጥ በሺዎች ኩንታል ነበር፡፡
“የቡና ዋጋ እንዳሁኑ ቢሆን ኖሮ አውሮፕላኑም ይገዛ ነበር” በማለት ቀልደዋል፡፡ ታዲያ ምን ያደርጋል? አዱኛ ብላሽ! እንደሚባለው አብዮት መጣና ሙልጫቸውን አስቀራቸው፡፡
አሁንም ግን አጋሮ ከተማ ውስጥ ቦታ ገዝተውና ቤት ሰርተው እየኖሩ ነው፡፡ ኑሮአቸው ጥሩ ነው፡፡ ቤታቸው ሰፊ ሲሆን ሁለት ግቢ አለው፡፡ አራቱ ወንዶች ልጆቻቸው አሜሪካ ይኖራሉ፡፡ ሁለት ሴቶች አዲሳባ አሉ፡፡ ሌሎቹ አጋሮ ከተማ አብረዋቸው ይኖራሉ፡፡

      ወ/ሮ ካሙላ ፊጣ ሦስት ልጆቿን በሰላም ነው የተገላገለችው፤ ሁለቱን በቤት አንዱን በጤና ጣቢያ፡፡ አራተኛው ፅንስ ግን ለመወለድ አልታደለም፡፡ 4 ወር ሲሆነው በሆዷ ሞቶ ደም ስለፈሰሳት ወ/ሮ ካሚላ ወደ ሰከቻ ክሊኒክ ተወሰደች፡፡ የክሊኒኩ ባለሙያዎች አይተው ከአቅማቸው በላይ ስለሆነ፣ ሪፈር ጽፈው፣ አምቡላንስ ጠርተው ወደ በደሌ ሆስፒታል ላኳት፡፡ የሆስፒታሉ ባለሙያዎችም በሆዷ የሞተውን ሽል በመሳሪያ አውጥተውላት እፎይቷ ሰጧት፡፡
የሦስት ልጆች እናት የሆነችው ወ/ሮ ያማቱ ናስር፤ ወደ በደሌ ሆስፒታል የመጣችው አራተኛ ልጇን ለመገላገል ነው፡፡ ወ/ሮ ያማቱ እርግዝናዋን በአካባቢዋ ባለ ጤና ጣቢያ ስትከታተል ነበር፡፡ ምጥ ስለመጣባት ወደ ባሌ ከተማ ሆስፒታል መጥታ አልጋ ላይ ሆና መውለጃዋን እየተጠባበቀች ነው፡፡ በሆስፒታሉ የማዋለጃና የመቆያ ክፍሎች ብዙ እናቶች አሉ፡፡
ሁሉም ወላዶች አልጋ ላይ ተኝተዋል፡፡ በደሌ ቢራ ምስጋና ይግባውና ሁሉም እናቶች አልጋ ላይ መውለድ ችለዋል፤ ብለዋል - የሆስፒታሉ ሥራ አስኪያጅ አቶ ታመነ ወርቅነህ፡፡
አቶ ታመነ መንግሥት በበደሌ ከተማ ያሰራው ሆስፒታል 64 አልጋዎች እንዳሉት ጠቅሰው፣ የሆስፒታሉ አስተዳደር 20 ክፍሎች ጨምሮበት፣ የአልጋዎቹ ቁጥር 84 መድረሱን ተናግረዋል፡፡ ነገር ግን ሆስፒታሉ አገልግሎት የሚሰጠው በ10 ወረዳ ለሚገኙ 710, 900 ሰዎች ስለሆነ በቂ አይደለም፡፡ ባለፈው ዓመት 1,652 እናቶች ናቸው በሆስፒታሉ የተገላገሉት፡፡
በአማካይ በየቀኑ 5 ሴቶች ይወልዱ ነበር ማለት ነው፡፡ ሁለትና ሦስት የሚወለድበት ቀን ቢኖርም 15 ሴቶች የሚወልዱበት ጊዜም አለ፡፡ አልጋ ሲጠፋ መሬት ላይ የሚወልዱ እናቶች ነበሩ፡፡ አሁን ማስፋፊያው ከተሰራ በኋላ መሬት የምትወልድ እናት የለችም፡፡ እናቶችን ከመሬት አንስተን አልጋ ላይ ማስተኛት ችለናል ብለዋል፡፡
በደሌ ቢራ አ.ማና ሄኒከን አፍሪካ ፋውንዴሽን በበደሌ ከተማ ሆስፒታል ውስጥ በ5.6 ሚሊዮን ብር ያሰሩት የማስፋፊያ ፕሮጀክት ባለፈው ሳምንት የተመረቀ ሲሆን 12 አዲስ የእናቶች ማዋለጃና 24 የሕፃናት ማቆያ ክፍሎች ያላቸው ሁለት ብሎኮች በ3.1 ሚሊዮን ብር አስገንብቷል፡፡ ለህክምናና ለላብራቶሪ መሳሪያዎች፣ ለጨቅላ ህፃናት ማቆያ ኢንኩቤተር፣ ለሥልጠና፣ … 2.5 ሚሊዮን ማውጣቱን አቶ ታመነ አስረድተዋል፡፡ ቀደም ሲል ከክፍሎች ጥበት የተነሳ የቤተሰብ ምጣኔ፣ ኤችአይቪ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ፣ ክትባትና ከወሊድ በኋላ ክብካቤ የሚሰጠው በአንድ ክፍል ውስጥ ነበር፡፡ የሄይኒከን ቢራ አ.ማ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ሚ/ር ጌሪት ቫን ሉ፤ “የማስፋፊያው ፕሮጀክት ለእናቶችና ከ5 ዓመት በታች ላሉ ህፃናት፣ የተሻለና ጥራት ያለው አገልግሎት መስጠት እንደሚያስችል እናምናለን” ብለዋል፡፡
ሚ/ር ቫን ሉ ባለፉት 4 ዓመታት ፋብሪካውን ለማዘመንና ደረጃውን ከፍ ለማድረግ 100 ሚሊዮን ብር ማውጣታቸውን ጠቅሰው፤ ለአንድ ሄክቶ ሊትር ቢራ ጠመቃ ያስፈልግ የነበረውን 11 ሊትር ውሃ ወደ 5.5 ሄክቶ ሊትር ማውረዳቸውን እንዲሁም ለቢራ ጠመቃ የተጠቀሙበትን ውሃ ለማጣራትና ከብክለት ነፃ ለማድረግ፣ 23 ሚሊዮን ብር ማውጣታቸውን ተናግረዋል፡፡ በደሌ ቢራ በቀረጥ ለመንግስት የሚያስገባው ገቢ በአራት እጥፍ ያህል ማደጉን የጠቀሱት ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ፣ በ2000 ዓ.ም 71.9 ሚሊዮን የነበረው ታክስ፤ በ2006 ዓ.ም 280.9 ሚሊዮን ብር መድረሱን ገልጸዋል፡፡ ለቢራ ጠመቃ በጣም አስፈላጊ የሆነውን ገብስ 48 ከመቶ ከሀገር ውስጥ እንደሚያገኙ ጠቅሰው፣ በቀጣይ ዓመታት ከውጭ የሚመጣውን 20ሺህ ሜትሪክ ቶን ገብስ በአገር ውስጥ ለማምረት፣ ከ20ሺህ ገበሬዎች ጋር እየሰሩ መሆኑን ሚ/ር ጌሪት ቫሉ አስረድተዋል፡፡

Saturday, 17 October 2015 09:44

የዘላለም ጥግ

• ትላቁ ክብራችን ጨርሶ አለመውደቃችን
ሳይሆን፤ በወደቅን ቁጥር መነሳታችን
ነው፡፡
ኮንፉሺየስ
• ታሪክ፤ ጥቂት ኦሪጂናሌና ብዙ ቅጂዎች
የሚገኙበት የስዕል ጋለሪ ነው፡፡
አሌክሲስ ዲ. ቶክኪውቪሌ
• ታሪክ ምንድን ነው? ሰዎች
የተስማማሙበት ተረት አይደለም?
ናፖሊዮን ቦናፓርቴ
• በውስጡ እየኖርክበት ሳለ፣ ታሪክ ፈፅሞ
ታሪክ አይመስልም፡፡
ጆን ደብሊው ጋርድነር
• ታሪክ፤ ሊወገዱ የሚችሉ ነገሮች ድምር
ውጤት ነው፡፡
ኮንራድ አዴናውር
• ታሪክ፤ ስምምነት ላይ የተደረሰበት
የውሸት ስብስብ ነው፡፡
ናፖሊዮን ቦናፓርቴ
• ታሪክ፤ ትልቅ የቅድምያ ማስጠንቀቂያ
ስርአት ነው፡፡
ኖርማን ከዝንስ
• ታሪክን እንደ ህብረተሰብ ዝግመተ-ለውጥ
መመልከት አለባችሁ፡፡
ዣን ችሬቲን
• የታሪክ ባለሙያ፡- ያልተሳካለት የረዥም
ልብወለድ ፀሃፊ ነው፡፡
ኤች.ኤል.ሜንኬን
• እግዚአብሄር ያለፈውን መቀየር
ባይችልም፤ የታሪክ ባለሙያዎች ግን
ይችላሉ፡፡
ሳሙኤል በትለር
• የእኔ ትልቁ ጠላቴ ጊዜ ነው፡፡
ኢቪታ ፔሮን
• የቀድሞ ታሪካቸውን፣ አመጣጣቸውንና
ባህላቸውን የማያውቁ ህዝቦች፣ ስር
እንደሌለው ዛፍ ናቸው፡፡
ማርከስ ጋርቬይ
• በሰው ልጅ ታሪክ ድንቁርና ከእውቀት
የተሻለበትን ዘመን ጨርሶ አላውቅም፡፡
ኔይል ዲግራሴ ታይሰን
• ቤተ-መፃህፍት የሃሳቦች ማዋለጃ ክፍል
ነው፤ ታሪክ ነፍስ የሚዘራበት ስፍራ፡፡
ኖርማን ከዝንስ
• የነፃ ሰዎች ታሪክ ጨርሶ በእድል የተፃፈ
አይደለም፤ በምርጫ እንጂ፡፡ በራሳቸው
ምርጫ!!
ድዋይት ዲ. አይዘንሃወር
(ስለ ታሪክ)

በድህነትና በመስኖ እርሻ እጦት ሳቢያ፣ ከ8 ሚ. በላይ ኢትዮጵያዊያን ለረሃብ በተጋለጡበት አመት!

   በመስኖ እርሻ፣ በፋብሪካ፣ በኤሌክትሪክ እጦት... በድህነት ላይ የምትገኝ አገር ላይ፤ ሂዩማን ራይትስ ዎች “መስኖና ፋብሪካ በዛ” የሚል አለማቀፍ ዘመቻ ሐሙስ እለት ጀምሯል።
ተቋሙ ያሰራጨው፣ ባለ 103 ገፅ ሪፖርት፣ በፓሪስ ለሚካሄደው ‘የአካባቢ ጥበቃ’ ጉባኤ ታስቦ የተዘጋጀ, የዘመቻ፣ ሰነድ እንደሆነ ተጠቅሷል። “አለማቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ዘመቻ”!
የዘመቻው ዋናው ርዕሰ ጉዳይ ደግሞ፣ ኢትዮጵያን መወንጀል ነው - ‘በኬንያ ለሚገኘው ቱርካና ሐይቅ ተቆርቋሪ ነኝ’ በማለት። የኢትዮጵያ ግድብ፣ መስኖ እና ፋብሪካ፣... የቱርካና ሐይቅን ይጎዳሉ በማለት ውግዘቱን ይዘረዝራል።
እስካሁን የሐይቁ መጠን እንዳልቀነሰ ግን፣ በሪፖርቱ ውስጥ አልተገለፀም።
በኬንያ የተካሄደው የግድብ ግንባታና የመስኖ እርሻም፣ አንድም ጊዜ በሪፖርቱ አልተነሳም። ታዲያ ለምን፣ የኢትዮጵያ ግድብ፣ ፋብሪካና መስኖ ላይ፣ አለማቀፍ ዘመቻ ይካሄዳል? ለዚያውም፣ የፋብሪካና የመስኖ እጥረት ባለበት አገር ላይ ነው፣ የውግዘት ዘመቻ የተከፈተው።
የአካባቢ ጥበቃ ዘመቻ... ትርጉም
“የአካባቢ ጥበቃ”... ምን ማለት እንደሆነ እስካሁን ያልተገነዘቡ ሰዎች፣ ትርጉሙን... ሂዩማን ራይትስ ዎች ካዘጋጀው የዘመቻ ሰነድ፣ በግላጭ መረዳት ይችላሉ። “የአካባቢ ጥበቃ” ማለት፣... ችግኝ መትከልና የአካባቢን ንፅህና መጠበቅ... ማለት አይደለም።
የመስኖ እርሻንና ኢንዱስትሪን መቃወም ማለት ነው - የአካባቢ ጥበቃ ማለት። ነባር የአካባቢ ገፅታ፣ የሰው እጅ ሳያርፍበት ‘ተጠብቆ’ እንዲቀጥል፤ ነባሩ ኋላቀር አኗኗር ሳይለወጥና ሳይሻሻል መቀጠል አለበት። በተለይ ግድብና የመስኖ እርሻ፣ ኢንዱስትሪና የፋብሪካ ምርት... ዋና ጠላቶች ናቸው። በሌላ አነጋገር፣ ዋናው ‘የአካባቢ’ ጠላት፣ ‘ሰው እና የሰው ስራ’ ናቸው።
እንግዲህ፣ ለሰዎች መብት እከራከራለሁ የሚለው ሂዩማን ራይትስ ዎች፣ አሁን “የአካባቢ ጥበቃ” ፊታውራሪ በመሆን ነው - አለማቀፍ የዘመቻ ሰነድ ያሰራጨው።
ሰነዱ፣ በገፅ 12፣ እንዲህ ይላል።    
ኢትዮጵያ፣ ባለፉት አመታት፣ ትላልቅ የግድብ ግንባታዎችን፣ እንዲሁም ለስኳርና ለጥጥ ምርት፣ የመስኖ እርሻዎችን ስታዘጋጅ ቆይታለች። እነዚህ ፕሮጀክቶች፣ ወደ ቱርካና ሐይቅ የሚደርሰውን ውሃ እጅጉን ይቀንሱታል። የመስኖ እርሻዎቹ፣ የወንዙን 50 በመቶ ያህል ውሃ ሊቀንስ ይችላል።...
ለዚህ የሪፖርቱ አባባል፣ አንድ ጥናት በማስረጃነት ተጠቅሷል - አንድ ጥናት!
ለዚያውም፣ ይሄው ጥናት ራሱ፣ የኢትዮጵያ የመስኖ ፕሮጀክቶች፣ ወደፊት የወንዙን 26% ያህል ለእርሻ ሊያውል ይችላል ነው የሚለው። የሂዩማን ራይትስ ዎች፣ ይህንን አድበስብሶ ያልፋል። ይህም ብቻ አይደለም። ከኦሞ ወንዝ ውሃ ውስጥ፣ ሰላሳ በመቶ ያህሉ፣ ወደ ግድብ ሳይገባ በቀጥታ ወደ ቱርካና ሐይቅ እንደሚገባ ሳይገለፅ ታልፏል።
ለነገሩ፣ ወደ ጊቤ ግድብ ከሚገባው ውሃ ውስጥም፣ በአብዛኛው ለመስኖ ሊውል አይችልም። ምክንያቱም፣ መፍሰስ አለበት - ኤሌክትሪክ ለማመንጨት። ከፈሰሰ ደግሞ፣ መድረሻው ቱርካና ሐይቅ ነው። ይህም እውነታ፣ በሂዩማን ራይትስ ዎች ሳይጠቀስ ታልፏል።
ደግሞስ፣ ኢትዮጵያ ከኦሞ ወንዝ፣ 50 በመቶ ያህሉ ለመስኖ ብትጠቀም ችግሩ ምንድነው? እንዴት ይወገዛል?
ሂዩማን ራይትስ ዎች ግን፣ ከማውገዝም አልፎ፣ ለአለማቀፍ ዘመቻ ተነስቷል - ሌሎችም እንዲያወግዙ።  
ለምሳሌ፣ “የኬንያ መንግስት፣ የኢትዮጵያ የግድብ ግንባታን በይፋ መቃወም ትቷል” ሲል ወቅሷል - ተቋሙ። (ገፅ 64)
የቱርካና አካባቢ አስተዳደርም፣ በአብዛኛው በዝምታ የሚመለከትና የመስኖ ልማት እቅድ ውስጥ ስለ ሀይቁ ምንም አይናገርም።
ለጊቤ3 ግድብ ግንባታ፣ ብድር እንዳይገኝ በየአቅጣጫው በተካሄደ ዘመቻ ሳቢያ፣ ቀደም ሲል ቃል ገብተው የነበሩት የአፍሪካ ልማት ባንክና የአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ ብድር ለመከልከል መወሰናቸውን ታስታውሱ ይሆናል። ጭራሽ፣ ኬንያንና ኢትዮጵያን የሚያገናኝ የኤሌክትሪክ መስመር ለመዘርጋት፣ የአለም ባንክ ብድር መስጠቱንም ተቃውሟል - የሂዩማን ራይትስ ዎች ሰነድ።
በዚህ መሃል...    
በቱርካና አካባቢ፣ ከፍተኛ የነዳጅ ዘይት ክምችት፣ እንዲሁም የኬንያን የውሃ ፍላጎት ለ70 ዓመታት ሊያሟላ የሚችል የከርሰ ምድር ባህር እንደተገኘ ሪፖርቱ ይጠቅሳል። በዚህ የነዳጅና የውሃ ክምችት ላይ፣ ማንም ኢትዮጵያዊ የይገባኛል ጥያቄ ያቀርባል ተብሎ አይጠበቅም። የቱንም ያህል በነዳጅና በውሃ እጥረት ብንቸገር፣ ኬንያ ውስጥ የሚመነጭ ውሃና ነዳጅ ላይ፣ ጥያቄ እናነሳለን? ኬንያዊያን ይህንን አይጠብቁም። ሙሉ ለሙሉ ራሳቸው ቢጠቀሙበት፣ ውንጀላ አይሰነዘርባቸውም።
ታዲያ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚመነጭ ውሃ ላይ፣ ቢያንስ ቢያንስ ግማሽ ያህሉን ለመጠቀም አስባችኋል የሚል ውንጀላ ኢትዮጵያ ላይ የሚሰነዘረው ለምንድነው?   
የሐይቁ መጠንና ጥልቀት አልቀነሰም!
የሐይቁ ጥልቀት፣ በ1970 ዓ.ም ከነበረበት ደረጃ፣  በ6 ሜትር ቀንሷል... የሚል መረጃ ልታዩ ትችላላችሁ። ጥልቀቱ፣ በየጊዜው ከፍና ዝቅ እንደሚል ግን፣ ሳይጠቅሱ ያልፉታል። ከ1930ዓ.ም እስከ 1965 ዓ.ም  ከነበረው ጥልቀት ጋር ሲነፃፀር፣ አሁን ያለው የሃይቁ ጥልቀት ይበልጣል(World Lakes Database)።
እንዲያውም፣ ጊቤ1 ግድብ ስራ ከመጀመሩ በፊት ከነበረው ጥልቀትም፣ አሁን ያለው ጥልቀት ይበልጣል። እነዚህ መረጃዎች፣ በሂዩማን ራይትስ ዎች ሪፖርት ውስጥ፣ ሳይጠቀሱ ተዘለዋል።
ይህም ብቻ አይደለም።
ወደ ሐይቁ የሚገባው ውሃ፣ በአብዛኛው (90%) ያህል፣ ከኢትዮጵያ... ማለትም ከኦሞ ወንዝ የሚመጣ ነው ይላል - የሂራዎ ሪፖርት። ይህን ልብ በሉ።
የዩኤንዲፒ ጥናት ደግሞ፣ ቀደም ሲል፣ የኦሞ ወንዝ ድርሻ 80% እንደነበር ይጠቅሳል። ድሮ ድሮ፣ ወደ ሐይቁ የሚገባው ውሃ፣ 80% ከኦሞ ወንዝ፣ 20% ደግሞ እዚያው ኬንያ ከሚገኙ ወንዞች (በተለይም ከቱርክዌል ወንዝ) የሚመጣ ነበር።
ታዲያ፣ ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ?
 የዛሬ 25 ዓመት፣ ኬንያ ውስጥ ግድብ ተገንብቷል - በቱርክዌል ወንዝ ላይ። ለምን? ኤሌክትሪክ ለማመንጨትና ለመስኖ። በዚህም ምክንያት፣ ከኬንያ ወንዞች ወደ ሐይቁ የሚገባው የውሃ መጠን ቀንሷል።
ይሄ እውነታ፣ በሂራዎ የ103 ገፅ ሪፖርት ውስጥ አንዴም አልተጠቀሰም። ኬንያ ውስጥ ግድብና መስኖ ሲገነባ፣ ምንም ጥያቄ አይነሳበትም። አይወገዝም። ኢትዮጵያ ውስጥ ግድብና መስኖ ከተገነባ ግን፣ ‘ትልቅ የሰብአዊ መብት ረገጣ’ የሚሆነው በምን ምክንያት ነው?
ኢትዮጵያዊያን ወራሪዎች ናቸው?
በኢትዮ ኬንያ ድንበር አካባቢ የሚኖሩ ከብት አርቢዎችን በሚመለከት ጥናት የሚያካሂዱ ሰዎች፣ በየጊዜው ግጭቶችና የከብት ዝርፊያዎች እንደሚፈፀሙ ይገልፃሉ። በጎሳ ተቧድኖ ግጭትና ዝርፊያ መፈፀም፣ የኋላቀርነት ምልክት መሆኑ አያጠራጥርም። መቅረትም አለበት።
የሂዩማን ራይትስ ዎች ሪፖርት ግን፣ ከሌሎች ሪፖርቶች ይለያል። የጅምላ ውንጀላ ላይ ያተኮረ ነው። በቃ... ኬንያ ውስጥ፣ በጎሳ ተቧድኖ ፣ግጭት የሚቆሰቁስና ዝርፊያ የሚፈፅም አንድም ሰው የለም። ሁሌም ተጠቂዎች ናቸው። ሁሌም በጎሳ ተቧድነው ወረራና ዝርፊያ የሚፈፅሙት፣ የኢትዮጵያ ነዋሪዎች ናቸው - በኬንያዊያን ላይ።አንድ የሰብአዊ መብት ተቋም፣ እንዲህ አይነት፣ የጅምላ ውንጀላዎችን በጭፍን ሲያሰራጭ በጣም ያሳዝናል። ለነገሩ፣ ሰብአዊ መብትን ትቶ፣ “የአካባቢ ጥበቃ”ን ማንገብ የጀመረ ተቋም፣ ውሎ አድሮ ወደ ጭፍንነት መግባቱ እንዴት ይቀርለታል? “የባህል ጥበቃ ተቆርቋሪ” በሚል ሽፋን፣ “በጎሳ የተቧደነ ጥንታዊ የድህነት አኗኗር” ለዘላለም እንዲቀጥል ዘመቻ ማካሄዱም አይገርምም።
እንዴት?
“ሁሉም አካባቢ፣ የሰው እጅ ሳያርፍበት፣ የቀድሞ ገፅታው ‘ተጠብቆ’፣ ለዘላለም መቀጠል አለበት”... የሚል የአካባቢ ጥበቃ ዘመቻ፣ ማንኛውንም ግንባታ፣ በመስኖ እርሻም ይሁን በኢንዱስትሪ መስክ፣ ማንኛውንም የኢኮኖሚ እድገት መቃወሙ የማይቀር ነው። የሂራዎ ሪፖርት፣ ከዳር እስከ ዳር፣ በዚህ የጥፋት ዘመቻ የተቃኘ ነው።
እስቲ አስቡት። ከድህነት መላቀቅና ወደ ብልፅግና መራመድ፣... የተቃውሞ ዘመቻ ሊካሄድበት ቀርቶ፣ ከነጭራሹ ጥያቄ ውስጥ መግባት የሌለበት ጉዳይ መሆን ነበረበት። ትልቁ ችግራችን፣ ከድህነት አለመላቀቃችን አይደለም እንዴ? የመስኖ እርሻ እና የፋብሪካ ስራ አለመስፋፋቱ አይደለም እንዴ? በዘመናዊ እርሻና በኢንዱስትሪ ዘርፍ፣ ኢንቨስትመንት በፍጥነት አለማደጉ አይደለም የቸገረን?
አዎ፤ በኦሞ ወንዝ የሚገነቡ የጊቤ ግድቦች፣ በተለይ ደግሞ፣ የስኳር ፋብሪካዎችና የመስኖ እርሻዎች... በመንግስት ስር ከሚሆኑ ይልቅ፣ በግል ኢንቨስትመንት ቢከናወኑ ኖሮ፣ የብክነትና የመጓተት ኪሳራዎችን ለመቀነስ፣ እንዲሁም ይበልጥ ውጤታማና ጠቃሚ ለመሆን በተቻለ ነበር። ነገር ግን፣ ሂራዎ፣ የግል ኢንቨስትመንትን ይበልጥ ይቃወማል - በጅምላ ‘የመሬት ወረራ’ በማለት ያወግዛል።
ሂራዎ፣ “የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪና የመስኖ እርሻ እድገት፣ ለቱርካና ሐይቅ አደጋ ነው” በማለት አለማቀፍ ዘመቻውን የጀመረው ሌላ ጊዜ ቢሆን ኖሮ፣ መራራነቱ ብዙም ላይሰማን ይችል ይሆናል።
 ዛሬ፣ በዝናብ እጥረት ምክንያት ከ8 ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያዊያን የምግብ ተመፅዋች በሆኑበት፣ ከወትሮው የከፋ አመት ላይ፣ ለዚያውም በሚቀጥሉት ወራት፣ እስከ መጪው ክረምት የተረጂዎቹ ቁጥር 15 ሚሊዮን እንዳይደርስ በተሰጋበት አስጨናቂ ዓመት ላይ፣ ግድብንና የመስኖ እርሻን፣ እንዲሁም ኤሌክትሪክንና ኢንዱስትሪን በጭፍን የሚያወግዝ ሪፖርት ማዘጋጀት፣ በጣም መራራ ነው።       

• 34ኛው የቤተ ክርስቲያኒቱ አጠቃላይ የሰበካ ጉባኤ ስብሰባ ሰኞ ይጀመራል

    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ማዕከል የሆነው የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፣ የሁለትዮሽ የሒሳብ አመዘጋገብ ሥርዐትን በመከተል አሠራሩን ዘመናዊ ማድረጉ ተገለጸ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ ዘመናዊውን የሁለትዮሽ የሒሳብ አሠራር /Double entry accounting system/ እንድትከተል፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጽ/ቤት በባለሞያዎች ያካሔደውን የፋይናንስ ፖሊሲና ማኑዋል ጥናት በቋሚ ሲኖዶስ በማስወሰን ባሳለፍነው የበጀት ዓመት ተግባራዊ ማድረግ መጀመሩ ታውቋል፡፡ በዚህም “ቤተ ክርስቲያኒቱ ዘወትር ስትወቀስበትና ስትተችበት የነበረውን፣ ለቁጥጥር የማያመቸውንና በሕግም ተቀባይነት የሌለውን የነጠላ ሒሳብ አሠራር” ጽ/ቤቱ ማስቀረቱ ተገልጧል፡፡በፖሊሲው ላይ የተመሠረቱና ከማኑዋሉ ጋር የሚስማሙ የሒሳብ ሰነዶችና ቅጻቅጾች ተዘጋጅተው ጥቅም ላይ የዋሉ ሲሆን የጽ/ቤቱ የሒሳብና በጀት መመሪያ ሠራተኞችም ለትግበራው የሚያስፈልጉ ልዩ ልዩ ሥልጠናዎችን እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡
የተቋሙን አጠቃላይ ሀብትና ዕዳ በማወቅ፣ የፋይናንስና የንብረት አጠቃላይ አስተዳደሩንና እንቅስቃሴውን ለቁጥጥር ግልጽ ለማድረግ፤ ተፈላጊውን መረጃ በሪፖርት በማውጣትና በመተንተን ተገቢ ውሳኔ ለመስጠት ምቹ የሆነውን የሁለትዮሽ አመዘጋገብ ተግባራዊነት ተከትሎ፣ ጽ/ቤቱ ማዕከላዊ የሒሳብ አሠራር በመከተሉ፣ ወጪ ቆጣቢና ውጤታማ ሥራ ለማከናወን መቻሉ ተገልጧል፡፡ ከ16 የጽ/ቤቱ መመሪያዎችና ድርጅቶች፣ በጀታቸውን በራሳቸው እያንቀሳቀሱ ሲሠሩ የነበሩት የሰባቱ የገቢና ወጪ ሒሳብ በአንድ ቋት ተጠቃልሎ በሁለትዮሽ አመዘጋገብ ዘዴ በመሠራቱ ከሐምሌ 1 ቀን 2006 ዓ.ም. እስከ ጥቅምት 30 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ የተሠራው ሒሳብ ተመርምሮ ተዘግቷል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ በየጊዜው በሚታየው የዋጋ ግሽበት ተጎጂ ሆና የቆየች ሲሆን በሕጋዊና አስተማማኝ የግዢ ሥርዐት ዓመታዊ ግዥ በመፈጸም ዕቃዎች በመጋዘን እንዲቀመጡ በማድረግ፣ ከጉዳቱ ለመዳን መቻሉ በመረጃው ተጠቅሷል፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሠራተኞች የደመወዝ ክፍያ፣ የቤቶችና ሕንፃዎች ኪራይ አሰባሰብ በባንክ በኩል በማስፈጸም ሒደቱን ቀልጣፋ በማድረግ ውጤታማ ሥራ መሠራቱ ተመልክቷል፡፡
በአሁኑ ወቅት በአገር ውስጥና በውጭ ለተቋቋሙት 50 አህጉረ ስብከት የበላይ ሓላፊና አመራር ሰጪ የሆነው የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ዋነኛ የፋይናንስ ምንጭ፣ ቤተ ክርስቲያኒቷ በየአጥቢያው ባቋቋመቻቸው ሰበካ ጉባኤያት የሚሰበሰበው የገንዘብ አስተዋፅኦ ነው፡፡ ከ34 ዓመታት በፊት በሳንቲም ደረጃ የተጀመረውና ለጽ/ቤቱ ፈሰስ የተደረገው የሰበካ ጉባኤያት ጠቅላላ ገቢ በበጀት ዓመቱ ከብር 125 ሚሊዮን በላይ መድረሱ የተገለጸ ሲሆን ይህም ካለፈው ዓመት ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ ብልጫ እንዳለው ተመዝግቧል፡፡
የገቢዋ ዕድገት ቤተ ክርስቲያኒቷ መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ልማታዊ አገልግሎቶቿን በራስዋ አቅም ለማከናወን እንደሚያስችላት የሚታመን ሲሆን ለዚህም ጠቅላይ ጽ/ቤቱ መከተል የጀመረው ዘመናዊው የሁለትዮሽ የሒሳብ አያያዝ በተዋረድ በሁሉም አህጉረስብከት እና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ተግባራዊ እንዲሆን ተጠይቋል፡፡ በቀጣዩ ሰኞ በጽ/ቤቱ አዳራሽ የሚጀመረውና ከ800 ያላነሱ የመላው አህጉረ ስብከት ልኡካን የሚሳተፉበት 34ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባ በጉዳዩ ላይ ጠንካራ የጋራ አቋምና ውሳኔ እንደሚያሳልፍ ይጠበቃል፡፡

በጎጃም በርካታ ሰዎች እንዲረሸኑና በጅምላ እንዲቀበሩ አድርገዋል ተብሏል


በደርግ የአገዛዝ ዘመን ዜጎችን በመግደል፣ በማሰርና በማሰቃየት ተከስሰው ሞት የተፈረደባቸው አንድ ስማቸው ያልተገለጸ የቀድሞ የደርግ ባለስልጣን፤ በሆላንዷ ከተማ አምስቴልቪን በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋላቸውን ኤንኤል ታይምስ የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ትናንት ዘገበ፡፡
በሆላንድ የሚገኘው የአለማቀፍ ወንጀሎች ምርመራ ቡድን አቃቤ ህግ፣ ግለሰቡ እ.ኤ.አ በ1978 ባስተላለፉት ትዕዛዝ፣ በጎጃም አካባቢ ታስረው የነበሩ በርካታ ሰዎች ተረሽነው አስከሬናቸው በጅምላ መቃብር እንዲቀበር ተደርጓል ማለታቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡ተጠርጣሪው ከሁለት ሳምንታት በፊት በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንደዋሉ የጠቆመው ዘገባው፣ አምስቴልቪን ከተማ ውስጥ በሚገኘው የግለሰቡ መኖሪያ ቤት ውስጥ በተደረገ ፍተሻ የተለያዩ ማስረጃዎች የተገኙ ሲሆን በሄግ የሚገኘው ፍርድ ቤትም ከትናንት በስቲያ በዋለው ችሎት፣ ግለሰቡ ለ90 ቀናት በእስር ላይ እንዲቆዩ ወስኖባቸዋል ብሏል፡፡የሆላንድ ፖሊስ ግለሰቡ የተጠረጠሩባቸውን የወንጀል ድርጊቶች ስለመፈጸማቸው ምርመራ ማድረግ መጀመሩን ዘገባው ገልጾ፣ ፖሊስም የምስክሮችን ቃል መቀበሉንና ተጠርጣሪው ድርጊቶቹን ስለመፈጸማቸው ምስክርነታቸውን ከሰጡ ግለሰቦች አብዛኞቹ በውጭ አገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን  እንደሆኑ አስታውቋል፡፡ምስክሮቹ በሰጡት ቃል ግለሰቡ በጎጃም አካባቢ የደርግ ባለስልጣን ሆነው ባገለገሉባቸው አመታት የተጠቀሱትን የወንጀል ድርጊቶች ስለመፈጸማቸው ተናግረዋል ያለው ዘገባው፣ የሆላንድ የወንጀል ምርመራ ባለስልጣናትም ግለሰቡን ለሞት ቅጣት ያበቃቸውን የወንጀል ክስ የተወሰነ መረጃ ከኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት መረከቡን ገልጧል፡፡የአለማቀፍ ወንጀሎች ምርመራ ቡድን፣ በደርግ የአገዛዝ ዘመን በደብረ ማርቆስና በመተከል እስር ቤቶች ውስጥ የግድያና የስቃይ ድርጊቶችን በፈጸሙ ግለሰቦች ላይ ትኩረት በማድረግ ምርመራ እያደረገ እንደሚገኝ ዘገባው አስታውቋል፡፡
61 አመታቸው እንደሆነ የተነገረላቸው እኒሁ ባለስልጣን፤ ከጥቂት አመታት ወዲህ ነዋሪነታቸውን በሆላንድ እንዳደረጉና የአገሪቱ ዜግነት እንደተሰጣቸው ያስታወሰው ዘገባው፣ ግለሰቡ በኢትዮጵያ ፍርድ ቤት በሌሉበት የእድሜ ልክ እስራትና የሞት ቅጣቶች እንደተጣሉባቸውም ገልጧል፡፡



 ታዋቂው የኮምፒውተርና የስማርት ፎን አምራች ኩባንያ አፕል በዊስኮንሲን ማዲሰን ዩኒቨርሲቲ ስም የተመዘገበን የፈጠራ ውጤት በሚያመርታቸው አይፎን 5 ኤስ፣ አይፎን 6 እና አይፎን  6 ፕላስ ሞባይሎቹ ውስጥ ተጠቅሞ በመገኘቱ እስከ 862 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ቅጣት ሊጣልበት እንደሚችል ተዘገበ፡፡ፕል ይህንን በዩኒቨርሲቲው ባለቤትነት ስር የሚገኝ የተለየ አይነት ፕሮሰሰር ከሞባይሎቹ በተጨማሪ በአንዳንድ የአይፖድ ምርቶቹ ውጥስ መጠቀሙን የጠቆመው የኢንዲፔንደንት ዘገባ፣ ኩባንያው ግን የዩኒቨርሲቲው የባለቤትነት መብት ውድቅ የተደረገ በመሆኑ ልወነጀል አይገባም ሲል ተከራክሯል፡፡
ጉዳዩን ሲመለከት የቆየው የማዲስን ፍርድ ቤት ግን ቴክኖሎጂውን የተጠቀምከው ባለቤቱን ሳታስፈቅድ ነው ሲል አፕልን ጥፋተኛ እንዳደረገውና ዊሊያም ኮንሊ የተባሉ ዳኛም አፕል በካሳ መልክ እስከ 862 ሚሊዮን ዶላር እንዲከፍል ሊፈረድበት እንደሚችል መናገራቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡

  - አማጺው የሰላም ስምምነቱን አፍርሼ ወደ ጦርነት እመለሳለሁ ብሏል
                 
    የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር የአገሪቱ ግዛቶች ቁጥር ከ10 ወደ 28 ማደግ አለበት ሲሉ ያስተላለፉት አወዛጋቢ ውሳኔ፣ ባለፈው ማክሰኞ ልዩ ስብስባውን ባከናወነው የአገሪቱ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ተቀባይነት ማግኘቱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር የግዛት ቁጥር ጭማሬ እርምጃ፣ ከአለማቀፉ ማህበረሰብ በስፋት ተቃውሞ ሲገጥመው እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ኢጋድም የፕሪዚዳንቱ ውሳኔ በምክር ቤቱ ተቀባይነት ማግኘቱ በአገሪቱ ተቀናቃኝ ሃይሎች መካከል የተፈረመውን የሰላም ስምምነት የሚጻረር ነው ሲል እንደተቸው ገልጧል፡፡
ውሳኔው ተግባራዊ የሚሆነው የደቡብ ሱዳን ፓርላማ ካጸደቀው በኋላ እንደሚሆን የጠቆመው ዘገባው፣ አንዳንድ የአማጺው ሃይል አባላትም ውሳኔው የማይሻር ከሆነ የሰላም ስምምነቱን አፍርሰው ዳግም ወደ ትጥቅ ትግል እንደሚገቡ ማስጠንቀቃቸውን ገልጧል፡፡
የአማጺው ሃይል አመራሮች የፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬርን ውሳኔ ህገ መንግስታዊ ያልሆነና ባለፈው ነሃሴ ወር በሁለቱ ሃይሎች መካከል ከተፈረመው የሰላም ስምምነት ያፈነገጠ ነው ሲሉ መተቸታቸውን የዘገበው ደግሞ ሱዳን ትሪቢዩን ነው፡፡ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር ከሁለት ሳምንታት በፊት በአገሪቱ የቴሌቪዥን ጣቢያ በኩል የአገሪቱን ግዛቶች ቁጥር ለማሳደግ መወሰናቸውን ይፋ ማድረጋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ በወቅቱም ይህን ያልተጠበቀ ውሳኔ ያስተላለፉት ለደቡብ ሱዳን ህዝቦች ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት እንደሆነ ማስታወቃቸውን ገልጧል፡፡
ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር ደቡብ ሱዳን 10 ግዛቶች ያሏት አገር ናት የሚለውን የህገ መንግስቱ አንቀጽ 162 እንዲያሻሽሉ ለአገሪቱ ህግ አርቃቂዎች ጥሪ ማስተላለፋቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

በቦብ ላይ የተቃጣውን የግድያ ሙከራ ይተርካል
   በሬጌ ሙዚቃ ንጉሱ በቦብ ማርሊ የህይወት ታሪክ ላይ ተመስርቶ፣ በጃማይካዊው ደራሲ ማርሎን ጄምስ የተጻፈው “ኤ ብሪፍ ሂስትሪ ኦፍ ሰቨን ኪሊንግስ” የተሰኘ የልቦለድ መጽሃፍ “ማን ቡከር ፕራይዝ” የተባለውን አለማቀፍ ሽልማት እንዳገኘ ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በ44 አመቱ ጃማይካዊ ደራሲ ማርሎን ጄምስ የተጻፈው መጽሃፉ፤ እ.ኤ.አ በ1970ዎቹ በቦብ ማርሊ ላይ የተቃጣ የግድያ ሙከራን መሰረት አድርጎ እንደተተረከ የጠቆመው ዘገባው፣ በወቅቱ በጃማይካ ስር ሰድዶ የነበረውን የፖለቲካ ሙስና እንደሚዳስስም ገልጧል፡፡
686 ገጾች ያሉት መጽሃፉ፣ ቦብ ማርሊ እ.ኤ.አ በ1976 በአገሪቱ መዲና ኪንግስተን በተዘጋጀ የሙዚቃ ኮንሰርት ላይ የአገሪቱን የፖለቲካ ውጥረት ለማርገብ ሲል፣ ሙዚቃውን ለመጫወት ባሰበበት ወቅት የተደራጁ ወንጀለኞች በመኖሪያ ቤቱ ላይ ተኩስ እንደከፈቱና ድምጻዊው ለጥቂት ከሞት እንደተረፈ ይተርካል፡፡
ይህን ሽልማት በማግኘት የመጀመሪያው ጃማይካዊ የሆነው ደራሲው፣ ለህትመት ያበቃው ሶስተኛ መጽሃፉ በሆነው በዚህ ስራው 50 ሺህ ፓውንድ እና ዋንጫ እንደተሸለመ የተገለጸ ሲሆን፣ ደራሲው በአሁኑ ወቅት በአሜሪካ ሚኒሶታ ግዛት የፈጠራ ጽሁፍ መምህር ሆኖ እየሰራ እንደሚገኝ ተነግሯል፡፡

    - ከግማሽ በላይ የሚሆነው የአለማችንን ሃብት የተያዘው፣ ከህዝቡ 1 በመቶ በሚሆኑ ባለጠጎች ነው
           - ግማሹ ድሃ የአለም ህዝብ፣ ከአለማችን ሃብት 1 በመቶ ብቻ ይደርሰዋል
  በያዝነው የፈረንጆች አመት 2015 ከግማሽ በላይ የሚሆነው የአለማችን ሃብት፣ ከአጠቃላዩ የአለም ህዝብ 1 በመቶ ያህል ብቻ በሚሆኑ የተለያዩ አገራት ባለጠጎች እጅ ውስጥ እንደሚገኝና በከፋ ድህነት ውስጥ የሚገኘው ግማሹ የአለማችን ህዝብ ከአጠቃላዩ የአለም ሃብት 1 በመቶውን ብቻ እንደያዘ በጥናት መረጋገጡን ዘ ኢንዲፔንደንት ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡ክሬዲት ሲዩሴ የተባለው ተቋም በ200 የተለያዩ የዓለማችን አገራት ዙሪያ የሰራውንና ባለፈው ማክሰኞ ይፋ ያደረገውን አለማቀፍ የሃብት ስርጭት አመታዊ ሪፖርት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ከአለማችን አገራት መካከለኛ ገቢ የሚያገኙ በርካታ ዜጎች ያሏት ቀዳሚዋ አገር ቻይና ሆናለች፡፡ከአለማችን ህዝብ 14 በመቶ የሚሆነው ወይም 664 ሚሊዮን ያህሉ፣ መካከለኛ ገቢ እንደሚያገኝ የጠቆመው ጥናቱ፣ 109 ሚሊዮን ያህል መካከለኛ ገቢ የሚያገኙ ዜጎች ያሏት ቻይና፣ አምና ቀዳሚ የነበረችውንና ዘንድሮ 92 ሚሊዮን መካከለኛ ገቢ የሚያገኙ ዜጎች እንዳሏት የተረጋገጠውን አሜሪካ ቀድማ የመጀመሪያውን ስፍራ መያዟን ገልጧል፡፡
እስካለፈው ግንቦት በነበሩት 12 ወራት በአለማችን የሃብት ክፍፍል ረገድ የሚታየው ክፍተት ክፉኛ መባባሱን የገለጸው የተቋሙ ሪፖርት፣ ከአለማችን ህዝብ 71 በመቶው ከ10 ሺህ ዶላር በታች፣ 21 በመቶው ከ10ሺህ እስከ 100 ሺህ ዶላር፣ 7.4 በመቶው ከ100 ሺህ እስከ  1 ሚሊዮን ዶላር፣ ቀሪው 0.7 በመቶ ህዝብ ደግሞ ከ1 ሚሊዮን ዶላር በላይ ሃብት አለው ብሏል፡፡
የአለማችን አጠቃላይ ሃብት አምና ከነበረበት የ12.4 ትሪሊዮን ዶላር ቅናሽ በማሳየት፣ ዘንድሮ 250 ትሪሊዮን ዶላር ደርሷል ያለው ሪፖርቱ፣ ከዚህ ሃብት 16 በመቶውን የያዘችው ቻይና ስትሆን፣ አሜሪካ በ12 በመቶ፣ እንግሊዝ ደግሞ 4 በመቶውን ይዘዋል ብሏል፡፡