Administrator

Administrator

  • ከ30ሺ በላይ ለሚሆኑ ጎብኚዎች ነጻ የህክምና ምርመራ ይሰጣል
            • ከህንድ፣ ዱባይ፣ ታይላንድ፣ ቱርክና ሌሎች አገራት የሚመጡ የጤና ተቋማትና ባለሙያዎች ይሳተፉበታል



       አፍሮ-ኤዥያ ዓለማቀፍ የጤና ኤክስፖ፣ እዚህ በመዲናዋ  ከግንቦት 9-11 ቀን 2016 ዓ.ም፣ በኤግዚቢሽን ማዕከል  እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ ገለጹ፡፡ በኤክስፖው ላይ ከ400 በላይ የአገር ውስጥና የውጭ ድርጅቶች፣ ከ30ሺ በላይ ጎብኚዎችና  ከ2ሺ በላይ የጤና አጠባበቅ ባለሙያዎች ይሳተፉበታል ተብሏል፡፡
የጤና ኤክስፖውን አስመልክቶ አዘጋጆቹና አጋር ተቋማት፣ ባለፈው ሰኞ ሚያዝያ 14 ቀን 2016 ዓ.ም በራማዳ  ሆቴል የሚዲያ ባለሙያዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት  ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ እንደተመለከተው፣ በጤና ኤክስፖው  ላይ የፓናል ውይይቶች፣ ዎርክሾፖችና ኤግዚቢሽኖችን ጨምሮ በርካታ ኹነቶች ይቀርባሉ፡፡ የጤና ባለሙያዎች የልምድ ልውውጥ የሚያደርጉበትና የቴክኖሎጂና የዕውቀት ሽግግር የሚካሄድበት እንዲሁም የትስስርና ትብብር ዕድሎች የሚፈጠርበት  መድረክም እንደሚሆን ተጠቁሟል፡፡
 “ድልድዮችን እንገንባ፣ ህይወትን እናድን” በሚል መሪ ቃል በሚካሄደው በዚህ ዓለማቀፍ ኤክስፖ፤ ከ30ሺ በላይ ለሚሆኑ ጎብኚዎች ነጻ የጤና ምርመራ እንደሚከናወን የተገለጸ ሲሆን፤ ለጤና  ባለሙያዎችም ነጻ ሥልጠና እንደሚሰጥ ለማወቅ ተችሏል፡፡  
ለሦስት ቀናት በሚቆየው የአፍሮ- ኤዥያ ዓለማቀፍ የጤና ኤክስፖ ላይ ከህንድ፣ ዱባይ፣ ታይላንድ፣ ቱርክ፣ ኢንዶኔዥያ፣ ማላይዥያና ሌሎችም አገራት የተውጣጡ በጤና ላይ የሚሰሩ ተቋማትና ባለሙያዎች እንደሚሳተፉበት ተጠቁሟል፡፡  ኤክስፖው ከወትሮው በተለየ በቢዝነስ ላይ ብቻ የሚያተኩር ሳይሆን፣ ተቋማት ማህበራዊ ሃላፊነታቸውን ለመወጣት ልዩ ዕድል የሚያገኙበት እንደሆነም ተነግሯል፡፡
ይህን ዓለማቀፍ የጤና ኤክስፖ ኤፍዚ ማርኬቲንግና ኮምዩኒኬሽን ኃ.የተ.የግ. ማህበር ከሰላም ኸልዝ ኮንሰልታንሲ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ሲሆን፤ ሳልማር ኮንሰልታንሲ፣ የኢትዮጵያ ጤና ሚኒስቴር፣ የኢፌዲሪ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን፣ የኢትዮጵያ ምግብና መድሃኒት ባለሥልጣን፣ የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የምግብና መድሃኒት ባለሥልጣን እንዲሁም የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት በአጋርነት እንደሚሳተፉበት ታውቋል፡፡

 መንግሥት ለእንዲህ ያሉ ተቋማት ድጋፍ እንዲያደርግ ተጠየቀ



          ከተከፈተ 17ኛ ዓመቱን ያስቆጠረውና እስካሁን ከ3ሺ800 በላይ የፋሽን ዲዛይነሮችን አሰልጥኖ ያስመረቀው ኔክስት ፋሽን ዲዛይን ኮሌጅ ፤ አዲሱን ከፍተኛ የማስተር ክላስ ሥልጠናውን ባለፈው ቅዳሜ ምሽት ሚያዝያ 12 ቀን 2016 ዓ.ም ቦሌ ዩጎ ሰርች አጠገብ በሚገኘው ሪያሊቲ ፕላዛ ህንጻ ላይ በይፋ መጀመሩን አስታወቀ፡፡
የፋሽን ማስተር ክላስ ለተማሪዎቹ ከሚሰጣቸው ሥልጠናዎች መካከል፡- ስፔሻል ፓተርን ዲዛይን፣ አርት ድሮዊንግ፣ ፋብሪክ ፔይንቲንግ፣ ፋሽን ስታይሊንግ፣ 3ዲ ዲዛይን፣ ፋሽን ማኔጅመንትና ሌሎችም ይገኙበታል ተብሏል፡፡
የኔክስት ፋሽን ዲዛይን ኮሌጅ መሥራችና ባለቤት ወ/ሮ ሣራ መሃመድ በምሽቱ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ “ማስተሪንግ ክላስ ሰዎች እንደ መክሊታቸው (ተሰጥኦዋቸው) ከፍተኛና ልዩ ሥልጠና የሚያገኙበት ፕሮግራም ነው” ብለዋል፡፡
በምሽቱ በኔክስት ፋሽን ዲዛይን ኮሌጅ ተመራቂዎች የተዘጋጀ አስደማሚ የፋሽን ትርኢት ለታዳሚዎች የቀረበ ሲሆን፤ ሞዴሎች የተለያዩ የፋሽን ዲዛይን ውጤቶችን ያሳዩት በመድረክ ላይ በቄንጥ እየተራመዱ ሳይሆን በየቦታው እንደ ሃውልት ወይም የቅርስ ጥበብ በየቦታው ተገትረው ነበር - በመጀመሪያ እይታ በልብስ መሸጫ መደብሮች የሚታዩትን አሻንጉሊቶች የመሰሏቸውም አልጠፉም፡፡
ኮሌጁ ባለፉት ዓመታት ከዓለማቀፍ ተመሳሳይ የማሰልጠኛ ተቋማት ጋር በፈጠረው መልካም የሥራ ግንኙነት 42 ዲዛይነሮች በህንድ አገር ሙሉ የነጻ ትምህርት እንዲያገኙ ያደረገ ሲሆን፤ሥልጠናቸውን ተከታትለው በመመለስም ለኢንዱስትሪውና ለአገራቸው ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ኮሌጁ ከሥልጠናው ጎን ለጎን፣ የተለያዩ የፋሽን ትርኢቶችን ከአገር ውስጥ ባሻገር በኒውዮርክ፣ ፈረንሳይ፣ ጣልያን፣ ጀርመን፣ ስዊዘርላንድ፣ ኡጋንዳና ሌሎችም አገራት በማቅረብ ስኬትና ዕውቅና ተቀዳጅቷል ተብሏል፡፡
ኔክስት ፋሽን ዲዛይን ኮሌጅ፤ በቅርቡ ከሳውዲ አረቢያ ተባረው ወደ አገራቸው የተመለሱ እንስት ኢትዮጵያውያንን በነጻ በማሰልጠን የሥራ ዕድል እንዲያገኙና ለሌሎች የሥራ ዕድል እንዲፈጥሩ ማስቻሉ ይነገርለታል፡፡ ሴቶችን ፋሽን ዲዛይንና ሞዴሊንግን ጨምሮ በሌሎች ዘርፎች በማሰልጠን ጉልህ አስተዋጽኦና ተጽዕኖ በመፍጠር ላይ የሚገኘው ኮሌጁ፤ እስካሁን የራሱን መሬት ባለማግኘቱ ለህንጻ ኪራይ ከፍተኛ ወጪ እንደሚያወጣ የተናገሩ አንድ የዕለቱ የክብር እንግዳ፤መንግሥት ለእንዲህ ዓይነቶቹ  ተቋማት ትኩረት ሰጥቶ መደገፍ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ “እኔ መንግሥት ብሆን መሬት የምሰጠው እንደ ኔክስት ፋሽን ኮሌጅ ላሉ የግል ተቋማት ነው፡፡” ሲሉም አክለዋል፡፡

 ዘመን ባንክ፤ የሠራተኞቹን ዕውቀትና ክህሎት ለማሳደግ፣ በዓለም  ትልቁ የኢንተርኔት የመማሪያ መድረክ ከሆነው ሊንክድኢን ለርኒንግ ጋር የአጋርነት ስምምነት ተፈራረመ፡፡
የዘመን ባንክ የሰው ሀብት ምክትል ዋና ኦፊሰር አቶ ታከለ ዲበኩሉ ስምምነቱን አስመልክቶ ባደረጉት ንግግር፤ “ዘመን ባንክ ለሰራተኞቹ ቀጣይነት ያለው የመማርና የሙያ እድገት ባህልን ለማሳደግ ቁርጠኛ ነው። ከሊንክድኢን ለርኒንግ ጋር ያደረግነው ስምምነት፣ ይህንን ቁርጠኝነት የሚያጎላ ከመሆኑም ባሻገር ሠራተኞቻችን የፋይናንስ ዘርፉ  የሚጠይቀውን ችሎታ፣ እውቀትና ክህሎት እንዲያዳብሩ  የሚረዳ ነው፡፡” ብለዋል፡፡
የሊንክድኢን ታለንት ሶሉዩሽን ዋና ኃላፊ ማቲው ግሬይ በበኩላቸው፤ ”ከዘመን ባንክ ጋር ያደረግነው ስምምነት የሰራተኞቹን የክህሎትና የእውቀት ክፍተቶች ለማሟላት እድሉን የሚሰጠን ከመሆኑም በላይ ሊንክድኢን ለርኒንግ በአፍሪካ ተመራጭ የክህሎት ልማት መድረክ ሆኖ  መቀጠሉን ስለሚያሳይ እጅግ ተደስተናል።“ ብለዋል፡፡
ኃላፊው አክለውም፤“ የዘመን ባንክ የሰው ሃብት ስትራቴጂ በቀጣይ አመታት ይበልጥ እንዲጎለብትና ውጤታማ እንዲሆን አብረን እንሰራለን።” ሲሉ ተናግረዋል፡፡



       ”--ካሙ የሳትረ የቅርብ ወዳጅ ነበር፡፡ ሆኖም ወዳጅነታቸዉ ከዘጠኝ አመት በኋላ በ1952 ዓ.ም ተቋጭቷል፡፡ በሁለቱ መካከል መቃቃር እንዲፈጠር ያደረገዉ ዐቢይ ምክንያት ካሙ በኮሚኒዝም ላይ ያንፀባርቀዉ የነበረዉ ትቸት ነዉ፡፡ አንድሬ ዢድ፣ ሊዮ ቶልስቶይ፣ ፊዮዶር ዶስቶቭስኪ፣ ሄርማን መልቬል እና ፍራንዝ ካፍካ ካሙ ላይ ታላቅ ተፅዕኖ የፈጠሩ ስመ ጥር ልብ ወለድ ደራሲያን ናቸዉ፡፡ --”
               መኮንን ደፍሮ


       (ክፍል አንድ)
ሕይወት እና ሥራዎች
አልበርት ካሙ ፈረንሳዊ ፈላስፋ፣ ልብ ወለድ ጸሐፊ፣ ጸሐፌ ተዉኔት፣ የቴአትር ተዋናይ፣ ጋዜጠኛ እና የፖለቲካ አክቲቪስት ነበር፡፡ ካሙ ጥቅምት 7 ቀን 1913 ዓ.ም ሞንዶቪ ዉስጥ ከገበሬ ወላጆቹ ተወለደ፡፡ ሞንዶቪ ቦን በተባለ የፈረንሳይ ቅኝ ግዛት ውስጥ የምትገኝ ትንሽ የምስራቅ አልጀሪያ ከተማ ናት፡፡
ካሙ ገና ጨቅላ ሳለ ነበር በአንደኛዉ የዓለም ጦርነት አባቱን ሉሲያ ኦጉስት ካሙን በሞት ያጣዉ፡፡ በእዚህም ምክንያት የአደገዉ የእስፔን የዘር ሐረግ ባላት እናቱ ካትሪን ሄለን ስንቴስ እጅ ነዉ፡፡ ስንቴስ ስሟን እንኳ መጻፍ የማትችል መሀይም ነበረች፡፡ ካሙ የልጅነት ጊዜዉን ያሳለፈዉ በአስከፊ ድህነት ዉስጥ ነበር፡፡ በ1932 ዓ.ም አልጀርስ ዩኒቨርሲቲ ገብቶ ፍልስፍና አጥንቷል፡፡ በ1942 ዓ.ም በገጠመዉ የሳንባ ደዌና አልጀሪያ ዉስጥ በነበረዉ የፖለቲካ ጭቆና ምክንያት አልጀሪያን ለቆ ወደ እናት አገሩ ፈረንሳይ አቀና፡፡ ፈረንሳይ ከገባ በኋላ በ1943 ዓ.ም ኮምባት ተብሎ የሚጠራዉንና ፈረንሳዮች የጀርመን ናዚን ወረራ በመቃወም ንቅናቄ ያደርጉበት የነበረዉ ምስጢራዊ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ሆኖ ሥራ ጀመረ፡፡ ከእዚህ ጋዜጣ ተሳታፊ ጸሐፍት አንዱ ዠን-ፖል ሳትረ ነበር፡፡
ጁሊያን ያንግ የተባለ የፍልስፍና ምሁር እንደ ገለፀዉ፣ ካሙ መልኩ አሜሪካዊዉን የፊልም ተዋናይ ሃምፕሬይ ቦጋርትን የሚመስል፣ ብዙ ጊዜ ከአፉ ጥግ ሲጋራ የማይጠፋ መልከ መልካም ነበር፡፡ ዘ አፍሪካን ኩዊን በተሰኘዉ የፊልም ሥራዉ ባሳየዉ ድንቅ ትወናዉ፣ በ1952 ዓ.ም ታላቁን የፊልም ሽልማት ኦስካር ያሸነፈዉ ሃምፕሬይ ቦጋርት፤በሲኒማ ታሪክ ስማቸዉ ጎልቶ ከሚጠቀስ ኮከቦች መካከል አንዱ ነዉ፡፡ ካሙ ሸበላነቱም ከሴቶች ጋር በቀላሉ እንዲቀራረብ አግዞታል፡፡ ይህ መልከ መልካም ሰው ለትዳር አጋሮቹ የማይታመን ሴት አውል ነበር፡፡ ካሙ ገና በወጣትነት ዕድሜዉ ጎጆ የቀለሰ ሰው ነበር፡፡ በ1934 ዓ.ም የአስራ ዘጠኝ አመት ወጣት ሳለ የመጀመሪያ የትዳር አጋሩን ሲሞን ሃይን አገባ፡፡ ሆኖም በሚስቱ አመንዝራነት ምክንያት ከአንድ አመት በኋላ ትዳራቸዉ በፍቺ ተቋጭቷል፡፡ ቆይቶ በ1940 ዓ.ም በሃያ ስድስ ዓመቱ ሁለተኛ ሚስቱን ፒያኒስትና የሒሳብ ሊቋን ፍራንሲን ፋዉርን አገባ፡፡ ከእሷ ሁለት መንታ ልጆችን አፍርቷል፡፡    
ካሙ ወደ ሥነጽሑፉ ዓለም እንዲቀላቀል በጎ ተፅእኖዉን ያሳረፈበት የፍልስፍና መምህሩ ዠን ግረነር ነዉ፡፡ ካሙ በሕግ የሚፈፀምን የሞት ቅጣ በፅኑ በማዉገዝ የሚታወቅ ፈላስፋ ነበር፡፡  ካሙ በመጀመሪያ ደረጃ ራሱን ጸሐፊ እንጂ ፈላስፋ አድርጎ አይቆጥርም ነበር፡፡ ይህ ሰው ሥራዎቻቸዉ በዓለም ዙሪያ በስፋት ከተነበቡላቸዉ ዘመናዊ ፈረንሳዊያን ደራሲያን መካከል አንዱ ነዉ፡፡   
ካሙ የሳትረ የቅርብ ወዳጅ ነበር፡፡ ሆኖም ወዳጅነታቸዉ ከዘጠኝ አመት በኋላ በ1952 ዓ.ም ተቋጭቷል፡፡ በሁለቱ መካከል መቃቃር እንዲፈጠር ያደረገዉ ዐቢይ ምክንያት ካሙ በኮሚኒዝም ላይ ያንፀባርቀዉ የነበረዉ ትቸት ነዉ፡፡ አንድሬ ዢድ፣ ሊዮ ቶልስቶይ፣ ፊዮዶር ዶስቶቭስኪ፣ ሄርማን መልቬል እና ፍራንዝ ካፍካ ካሙ ላይ ታላቅ ተፅዕኖ የፈጠሩ ስመ ጥር ልብ ወለድ ደራሲያን ናቸዉ፡፡
ካሙ፣ ገና በጎልማሳነት እድሜዉ በመኪና አደጋ ቢቀጭም፣ እጅግ ታላላቅ የሥነጽሑፍና የፍልስፍና ሥራዎችን ለዓለም አበርክቷል፡፡ ካሙ በ1937 ዓ.ም ያሳተመዉ የወግ ሥራዉ ቢቲዊክስ ኤንድ ቢቲዊን ይሰኛል፡፡ በቀጣዩ ዓመት በ1938 ዓ.ም ያሳተመዉ ሥራዉም ወግ ሲሆን፤ ነፕሾልስ ይሰኛል፡፡ በ1942 ዓ.ም ዘ ስትሬንጀር የተሰኘ የልብ ወለድ ሥራዉን አሳትሟል፡፡ ይህ ሥራ ለህትመት በበቃበት ወቅት ሳትረ ሳይቀር ታላቅ የፈጠራ ሥራ መሆኑን አወድሶ ኂሳዊ መጣጥፍ ጽፏል፡፡ ዘ ስትሬንጀር በብዛት የተሸጠና ከአርባ በላይ ወደ ሆኑ ቋንቋዎች የተተረጎመ የሃያኛዉ ክፍለ ዘመን የፈረንሳይ ልብ ወለድ ነዉ፡፡ የእዚህ ሥራ ዐቢይ ሴማ ወለፈንድ ነዉ፡፡ በእዚሁ አመት ያሳተመዉ ታላቅ የፍልስፍና ሥራዉ ዘ ሚዝ ኦፍ ሲስፈስ ኤንድ አዘር ኢሴይስ ይሰኛል፡፡ ይህ ሥራው ዘ ስትሬንጀር ዉስጥ የዳሰሰዉን ወለፈንድ በጥልቀት የፈከረበት ሥራዉ ነዉ፡፡ በ1944 ዓ.ም ለመድረክ የበቃ የተዉኔት ሥራዉ ክሮስ ፐርፐዝ ይሰኛል፡፡ ካሊጉላ በቀጣዩ ዓመት በ1945 ዓ.ም ለመድረክ የበቃ የተዉኔት ሥራዉ ነዉ፡፡ እነዚህን ሥራዎች ተከትሎ በ1948 ዓ.ም ስቴት ኦፍ ሲይጂ፣ በ1950 ዓ.ም ደግሞ ዘ ጄስት የተሰኙት ሥራዎቹ ለመድረክ በቅተዋል፡፡ በ1947 ዓ.ም ያሳተመዉ ዝነኛ የልብወለድ ሥራዉ ዘ ፕለይግ ይሰኛል፡፡ በ1951 ዓ.ም ዘ ሪቤል፣ አን ኢሴይ ኦን ማን ኢን ሪቮልት የተሰኘዉን ሥራዉን አሳተመ፡፡ በ1956 ዓ.ም ያሳተመዉ ሌላኛዉ የልብ ወለድ ሥራዉ ዘ ፎል ይሰኛል፡፡ ከአንድ አመት በኋላ በ1957 ዓ.ም ኤግዛይል ኤንድ ዘ ኪንግደም የተሰኘ ሥራዉን አሳትሟል፡፡ ካሙ ከሞተ በኋላ በ1994 ዓ.ም በሕይወት ሳለ ጽፎ ያላገባደደዉ የሕይወት ታሪኩ ላይ የተመሠረተዉ የልብ ወለድ ሥራዉ ዘ ፈርስት ማን ታተመ፡፡ ይህ ሥራ ካሙ ላይ የመኪና አደጋ በደረሰበት ወቅት ሳምሶናይቱ ዉስጥ የተገኘ ሥራ ነዉ፡፡ ከእዚህ ድርሰቱ ጋር አብሮ የተገኘው ሌላኛው መጽሐፍ የፍሪድሪክ ኒቼ ዘ ጌይ ሳይንስ ነው፡፡                
ካሙ ለዓለም ሥነጽሑፍ ማለፊያ ሥራዎችን በማበርከቱ  October 16 1957 ዓ.ም ታላቁን የኖቤል ሽልማት በሥነጽሑፍ ተሸልሟል፡፡ ነገር ግን የኖቤል ሽልማትን ከተቀበለ በኋላ በእዚህ ዓለም የኖረዉ ለሦስት ዓመታት ብቻ ነዉ፡፡ ካሙ በተወለደ በአርባ ስድስት አመቱ የጋሊማርድ አሳታሚ ባለቤት ጋስቶኦን ጋሊማርድ ዘመድ ከሆነዉ ጓደኛዉ ሚሼል ጋሊማርድ ጋር ከመኖሪያ መንደሩ ሎርምረን ወደ ፓሪስ በመኪና እየተመለሱ ሳለ፣ በመኪና አደጋ ጥር 4 ቀን 1960 ዓ.ም ከእዚህ ዓለም በሞት ተለየ፡፡ ካሙ እና ሚሼል ጋሊማርድ መኪና በፍጥነት የማሽከርከር ሱስ ነበረባቸዉ፡፡ የካሙ ሥርዓተ ቀብር የተፈፀመው ሎርምረን ውስጥ ነው፡፡  
፩. የሕይወት ትርጉም
የበርካታ ፈላስፎችን ትኩረት ከሳቡ ዐቢይ ፍልስፍናዊ ጉዳዮች መካከል አንዱ የሕይወት ትርጉም ነዉ፡፡ ለእዚህ ወሳኝ ፍልስፍናዊ ጉዳይ ልዩ ትኩረት ሰጥተዉ ከተፈላሰፉ ፈላስፎች መካከል አንዱ ካሙ ነዉ፡፡ ካሙ ዘ ሚዝ ኦፍ ሲስፈስ በተሰኘ የፍልስፍና ሥራው እንደሚነግረን፣ ሕይወት ፋይዳ አለዉ ወይስ የለዉም የሚለዉ ጥያቄ ፍልስፍና ሊመልሰዉ የሚገባ እጅግ አንገብጋቢ ጥያቄ ነዉ (ካሙ፣ 1955)፡፡ ለካሙ ከሕይወት ትርጉም ጥያቄ የሚቀድም ወሳኝ ጥያቄ የለም፡፡ ለእሱ የሕይወት ትርጉም ፍልስፍና ሊፈታው የሚገባ ብቸኛው ወሳኝ ተግዳሮት የሆነው ራስን ከማጥፋት ድርጊት ጋር በቀጥታ ስለሚሰናሰል ነው፡፡
ወለፈንድ         
ዘ ሚዝ ኦፍ ሲስፈስ ካሙ የሕይወት ወለፈንድነት ወይም ትርጉም አልባነት ምንጩ ምን እንደ ሆነ እንዲሁም ሕይወት ፋይዳ ቢስ በመሆኑ ምክንያት ራስን መግደል ተገቢ ነዉ አይደለም የሚለዉን ጥያቄ የመለሰበት ፍልስፍናዊ ሥራዉ ነዉ፡፡ ብዙ ጊዜ ግለሰቦች ራሳቸዉን ለመግደል ዉሳኔ ላይ የሚደርሱት የሕይወትን ወለፈንድነት ወይም ከንቱነት ሲረዱ ነዉ (ዊክ፣ 2003)፡፡ ለካሙ ሕይወት ወለፈንድ ነው (ቶዲ፣ 1959)፡፡ ይህ ሐቅ የሰዉ ልጅ ፈፅሞ ሊሸሸዉ የማይችለዉ ሐቅ ነዉ፡፡
እንደ ካሙ እሳቤ፣ የሕይወት ወለፈንድነት ምንጩ በፍፁማዊ ትርጉም ፈላጊዉ የሰዉ ልጅና በፍፁማዊ ትርጉም አልባዉ ሁለንታ መካከል ያለ ግጭት፣ ሞት አይቀሬ ታላላቅ ስኬቶቻችንን ሁሉ በቅፅበት መና አንደሚያደርጋቸዉ መታዘባችን፣ ሁለንታ ለእኛ ትልምና ፍላጎት መልስ አልባ መሆኑን መታዘባችን፣ የሰዉ ልጅ ኅሊና የሁለንታን ምስጢር ለመግለፅ ብቁ አለመሆኑ እና የዉሃ ቅዳ ዉሃ መልስ ጨዋታ የሆነዉን አታካቹን የሰርክ ሕይወታችንን መታዘብ ነዉ (ካሙ፣ 1955፤ ቶዲ 1959፤ ኮፕልስተን፣ 1994፤ ደ ሉፕ፣ 1966፤ ዌበር 2018፤ ቤኔት 2001፤ ፎለይ 2008፤ ኮፕልስተን፣ 1956)፡፡ ዮንግ (2003) እንደሚነግረን፣ ለካሙ የሰው ልጅ ሕልውና ትርጉም አልባ የሆነበት ሰበብ፣ የፈጣሪ በህልውና አለመኖር ነው  (ዮንግ፣ 2003)፡፡  
ራስን ማጥፋት      
ካሙ እንደሚነግረን፣ ሰዉ ከሕይወት ከንቱነት ሐቅ ጋር ሲላተም ራስን ማጥፋትን መፍትሄ አድርጎ ይወስዳል (ዮንግ፣ 2003)፡፡ ራስን የመግደል ስሜት ሬስቶራንትን ጨምሮ በማንኛውም ጊዜ ሊፈጠር ይችላል (ካሙ፣ 1955)፡፡ ለመሆኑ ራስን መግደል የሕይወት ፋይዳ ቢስነት ትክክለኛ መፍትሄ ይሆናል? በፍፁም ይለናል ካሙ፡፡ እንደ እሱ እሳቤ፣ ራስን መግደል የሕይወት ፋይዳ ቢስነት ስሜት ትክክለኛ መድኃኒት አይደለም፡፡ በመሆኑም ተግባሩ በፅኑ የሚወገዝ ነው፡፡    
ተስፋ
ለካሙ እንደ ራስን መግደል ሁሉ ተስፋ፣ ቂል ሰው ለወለፈንድ ስሜት ትክክለኛ መፍትሄ አድርጎ የሚወስደው፣ በእውነቱ ግን ትክክል ያልሆነ መፍትሄ ነው (ዊክ፣ 2003)፡፡ ተስፋ ካሙ አበክሮ የሚተቸው የዴንማርካዊዉን ኤግዚስቴንሻሊስት ፈላስፋ ሶረን ኪርክጋርድ ጽንሰ ዐሳብ ነው፡፡ ይህ ጽንሰ ዐሳብ ከሃይማኖታዊ እሳቤ ጋር የተሰናሰለ ሲሆን፤ወለፈንድን ከመጋፈጥ ይልቅ በሰማያዊ ሕይወት ተስፋ ማድረግንና ከፈጣሪ ጋር ህብረት መፍጠርን ይሰብካል፡፡ እንደ ካሙ እሳቤ፣ ተስፋ ለሕይወት ፋይዳ ቢስነት ተግዳሮት ትክክለኛ መፍትሄ ሆኖ መቅረብ አይችልም፡፡ ተስፋ ለካሙ ወለፈንድን የመሸሽ ተግባር በመሆኑ የተወገዘ ነዉ (ዊክ፣ 2003)፡፡ የካሙ ፍልስፍና የሚነግረን፣ በእዚህ ዓለም እየኖርነው ካለነው ሕይወት ውጪ ሌላ ተስፋ የምናደርገው ሕይወት አለመኖሩን ነው፡፡ ለካሙ፣ ተስፋ ፍልስፍናዊ ራስን ማጥፋት ነው፡፡ ለምን ቢባል ምክንያታዊነትን መግደል ስለሆነ (ዮንግ፣ 2003)፡፡
ከላይ እንዳየነው ለካሙ ራስን ማጥፋትም ሆነ ተስፋ ለወለፈንድነት ስሜት ትክክለኛ መፍትሄዎች አይደሉም፡፡ ታዲያ እውነተኛ መፍትሄው ምንድር ነው? ካሙ እንደሚነግረን፣ የወለፈንድነት ስሜት ትክክለኛው መፍትሄ አድማ ነው፡፡ ይህን ጽንሰ ዐሳብ በቀጣዩ ጽሑፍ እናያለን፡፡            
ከአዘጋጁ፡-
መኮንን ደፍሮ ልብወለድ ጸሐፊ፣ ገጣሚ እና የሥነ ጽሑፍ ኀያሲ ነው፡፡ የባችለር ድግሪውን በ2009 ዓ.ም፣ የማስተርስ ድግሪዉን ደግሞ በ2015 ዓ.ም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በፍልስፍና አግኝቷል፡፡ በተማረው የሙያ መስክ በጅማ፣ በመቐለ እና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት ሠርቷል፡፡ ጸሐፊው አዲስ አድማስ ጋዜጣን ጨምሮ በተለያዩ መጽሔቶች ግጥሞቹንና የልብ ወለድ ሥራዎቹን አሳትሟል፡፡      መኮንን በርካታ የኢትዮጵያ ታላላቅ ደራሲያን ሥራዎች ላይ ኂሳዊ መጣጥፎችን ጽፏል፡፡

  የግሪካዊው ደራሲ ኒኮስ ካዛንታኪስ ”The Last Temptation of Christ“ የተሰኘ ልብወለድ መጽሐፍ ”የመጨረሻው ፈተና” በሚል በማይንጌ ወደ አማርኛ ተመልሶ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡
ኒኮስ ካዛንታኪስ በ1883 ዓ.ም. (እ.ኤ.አ) በክሪት ከተማ ተወለደ፡፡ ከአቴንስ ዩኒቨርስቲ የሕግ ዲግሪውን ካገኘ በኋላ፣ በታዋቂው ፈላስፋ ሄንሪ በርግሰን ሥር የፍልስፍና ጥናቱን በፓሪስ አካሂዷል፡፡ ሥነ ጽሑፍና አርትን ደግሞ በጀርመንና ጣልያን ተዟዙሮ አጥንቷል፡፡ ስፔን፣ እንግሊዝ፣ ሩስያ፣ ግብፅ፣ እስራኤል፣ ቻይናና ጃፓን ከተጓዘባቸውና ለተወሰኑ ጊዜያት ከቆየባቸው አገራት ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡ በ1945 ዓ.ም. ለአጭር ጊዜ በግሪክ የትምህርት ሚ/ር ሚኒስትር ዲኤታ በመሆን ተሾሟል፡፡ ከ1947-48 ዓ.ም. ድረስ ደግሞ በዩኔስኮ የትርጉም ቢሮን በዳይሬክተርነት መርቷል፡፡ በአጠቃላይ 30 የሚሆኑ ልብ ወለዶችን፣ ቲአትሮችንና የፍልስፍና መጽሐፎችን ጽፏል፡፡ ልብወለድ መጻፍ የጀመረው በአመሻሽ ዕድሜው ቢሆንም፣ ከ65 ዓመቱ ጀምሮ ባሉት ዘጠኝ ተከታታይ ዓመታት ስምንት የልብወለድ መጻሕፍትን ማበርከት ችሏል፡፡ ታዋቂ ከሆኑት ልብወለዶቹ መካከል፣ Zorba the Greek, The Greek Passion እና The Last Temptation of Christ (የመጨረሻው ፈተና) ይገኙበታል፡፡
በተደጋጋሚ ለሥነጽሑፍ የኖቤል ሽልማት የታጨ ቢሆንም፣ በተለይ ደግሞ በ1952 ዓ.ም. በአንድ ድምፅ ብቻ ተበልጦ ሳይሸለም ቀርቷል፡፡ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየው በ1957 ዓ.ም. ነው፡፡ የመቃብር ሀውልቱ ላይ እንዲጻፍ አደራ ያለው ቃል፡-
“ምንም አልፈራም፣   I fear nothing
ምንም አልጠብቅም፣ I hope for nothing
ነፃ ነኝ!” የሚል ነበር፡፡ I am free.

 ሁለት ንሥሮች ስለወደፊት ዕጣ-ፈንታቸው ይጨዋወታሉ፡፡ አንደኛው - “እኛ ንሥሮች፤ ሰዎች እንዳያጠቁን በየጊዜው እየተገናኘን መወያየት፣ መነጋገር፣ ደካማ ጎናችንን እያነሳን መፍትሔውን ማግኘት ያስፈልገናል፡፡ ስለዚህ ሁሉንም ንሥሮች ሰብስበን እንነጋገርና አንድ ዓይነት አቋም እንያዝ”
ሁለተኛው ንሥር - “በዕውነቱ በጣም ቀና ሀሳብ ነው፡፡ ሁሉም እንዲሰበሰቡ ማስታወቂያ እንለጥፍ” አለ፡፡
በዚህ ተስማምተው በዓይነቱ ልዩ ነው የሚባል (Extraordinary) አጠቃላይ ስብሰባ ጠሩ፡፡ ንሥር- ሜዳ በሚባል ሰፊ ቦታ በተባለው ሰዓት ማንም ንሥር እንዲመጣ፤ የቀረ ከመላው ንሥሮች እንቅስቃሴ ያፈነገጠ፣ ከሀዲ (Saboteur) ነው የሚል ማስጠንቀቂያም ታከለበት፡፡
በተባለው ቦታና ሰዓት የአገሩ ንሥር ሁሉ ተሰበሰበ፡፡ ‘አጀንዳው “ከዛሬ ጀምሮ ሰው እንዳያጠቃን አንድ ዓይነት አቋም ይዘን በጥንቃቄ እንድንንቀሳቀስ ይሁን፣” የሚል ነው፡፡ በመሰረቱ ሰው እኛን መናቁ ያለ ነገር ነው፡፡ ነገር ግን ማንኛውም ነገር ከትንሽ ጀምሮ ወደ ትልቅ እንደሚያድግ፣ ከቀላሉ ወደ ውስብስቡ እንደሚሄድ ካለመረዳት የሚመጣ ግብዝነት ነው፡፡ ስለዚህ ምንም አቅማችን ትንሽ ቢሆን፣ ቀስ በቀስና ከቀን ቀን ስለምንጠነክር ትንሽነት አይሰማችሁ፡፡ ብርታት ከትንንሾች ህብረት የሚመጣ ነው” አለና ንግግር አደረገ፣ ሰብሳቢው ንሥር፡፡ ሁሉም በክንፎቻቸው አጨበጨቡ፡፡ በንሥራዊ ድምጽም እልልታቸውን አሰሙ፡፡ “የንሥሮች ኅብረት ለዘለዓለም ይኑር” የሚል መፈክር በአንድነት አሰገሩ፡፡
ይህ ስብሰባ በተካሄደ በጥቂት ጊዜ ውስጥ በአንድ ጫካ ውስጥ አንድ አዳኝ ቀስትና ደጋን ይዞ ታየ፡፡ ንሥሮቹ ሁሉ እየተመካከሩ ሸሹ፡፡ አዳኙም ተናዶ ወደ መንደሩ ተመለሰ፡፡ ሌላም ቀን ለአደን መጣ፡፡ ንሥሮቹ ተጠራርተው በረሩ፡፡
አንድ ቀን ግን አዳኙ ንስሮቹ በማያውቁት አቅጣጫ ዞሮ ወደ ጫካው ገባ፡፡ ከንሥሮቹ አንዳቸውም አልጠረጠሩም፡፡ ኮሽታ ታህልም ድምጽ አልሰሙም፡፡
አዳኙ ዓልሞ ወደ አንደኛው ንሥር አነጣጠረ፡፡ ቀስቱን ስቦ ሲለቅቀው አንደኛው ንሥር ልብ ላይ ተተከለ፡፡ ንሥሩ ልቡ ላይ የተተከለው ስል ቀስት በጣም ባሰቃየው ጊዜ፣ በጣሩ ቅጽበት ወደ ኋላ ዞሮ ተመለከተ፡፡ የቀስቱን ጫፍ አየው፡፡ የቀስቱ ጭራ የተሰራው ከንስር ላባ ነው፡፡ ህመሙ በርትቶበት ሊሞት ሲል እንዲህ አለ፡-
“እኛ እራሳችን በሰጠነው መሣሪያ ስንወጋ ነው ለካ፣ ቁስሉ የበለጠ ጥልቀት የሚኖረው”
ከዚያም ለምታስታምመው ንሥር እንዲህ አላት፡-
“ከእንግዲህ ለጠላታችን አለመመቸት ማለት የራሳችንን መሳሪያ አለመስጠት ማለት ብቻ አይደለም፡፡ ይልቁንም ወደ እኛ መምጫዎቹን በሮች በሙሉ ጠንቅቆ ማወቅና መዝጋት ነው፡፡ ይህንን ለወገኖቻችን ሁሉ ንገሪ” ብሎ ትንፋሹ አበቃ፡፡
***
መክረው ተመካክረው የሰሩት መንገድ ብዙ ዘመን ያስኬዳል፡፡ የሰው ቤት አያስፈርስም፡፡ የድሃ መተዳደርያ አይነፍግም፡፡ የሰው ድንበር አያስዘልልም፡፡ ማህበራዊ ምስቅልቅል አያስከትልም፡፡ ብዙ ኩርፊያ፣ ብዙ ቅያሜ አይፈጥርም፡፡ ቢሳሳቱ ስንመክር ተሳስተን ነበር፤ ያላየነው - ያላስተዋልነው ነገር ነበር ለማለት አይከብድም፡፡ ራሳችን የሰጠነው መሳሪያ ክፉኛ እንዳቆሰለን ገብቶናል ለማለት ያስችላል፡፡ መሰብሰብ፣ ሸንጎ መዋል የተለመደና የነበረ ነው፡፡ ከዚህ እሳቤ በመነሳት በሀገራችን ከጥንት እስከዛሬ በሽንጎ መምከር ክፉ-ደግ መመርመር የተዘወተረ ነው፡፡ በተለይ የኢትዮጵያ ተማሪዎችና መምህራን በዚህ ቀዳሚውን ቦታ የሚይዙ መሆናቸው አሌ አይባልም፡፡ ትምህርት ቤቶች ነጻ የውይይት መድረክ እንዲኖራቸው ብዙ ትግል ተካሂዷል፡፡ ትክክልም ይሁኑ ስህተት በጥቂቶች አነሳሽነት የሚጠሩ ምድር ሰማይ የሚደባልቁ፣ መንግስት የሚነቀንቁ፣ የአገር ዕውነት የሚናገሩ ስብሰባዎች ነበሩ፡፡ ቀስ በቀስም የጎሹት እየጠሩ፣ የጎለደፉት እየተሳሉ፣ የሻከሩት እየለሰለሱ ለሀገር ወደሚበጅ ሁነኛ ጥያቄና መፍትሔ እንዳደጉ አይተናል፡፡ አበው “መንገድና ትውልድ የማያውቅ የተጎዳ ነው” እንዲሉ መንገድ የሚያውቅ፣ በዕውቀት የታነጸ፣ ጠያቂና አስተዋይ ትውልድ ማፍራት ከየዘመኑ ይጠበቃል፡፡ ጊዜ ይጠይቃል እንጂ ፍሬ ያለው ትውልድ ይገኛል፡፡ ቀና ተመኝ ቀና እንድታገኝ ነው፡፡
ከፍተኛ የትውልድ አስተሳሰብ የምናፈልቀው የዕውቀት ምንጭ ከሆነው ት/ቤት ነው፡፡ ለት/ቤት የምንሰጠው ክብር፣ ለዕውቀት የምንጠሰው ክብር ነው፡፡ ለዕውቀት የምንሰጠው ክብር፣ ለትውልድ የምንሰጠው ክብር ነው፡፡  የትምህርት ፖሊሲዎች ጊዜ የተወሰደባቸው፣ ብዙ አዕምሮ የፈሰሰባቸው፣ ለሀገር የማደግ ተስፋን የሚጠምቁ መሆን ይገባቸዋል፡፡  ለመሻሻል እፈልጋለሁ የሚል ዕምነት ያለው ፖሊሲ - ቁራጭ፤ በሂደትና በተመክሮ ስህተት ቢያይ፣ ተከታትሎ ለማረም፤ ተሳስቼ ነበር ለማለት ድፍረት ሊኖረው ይገባል፡፡ ከእኔ እጅ በሰላም ከወጣ እንደፍጥርጥሩ በሚል ስሜት በተግባር የሚያውሉትን ወገኖች ሌላ አበሳ ውስጥ የሚከትት ከሆነ፣ ችግርን ለመፍታት ችግር ያለበት መፍትሄ እንደ መስጠት ይቆጠራል፡፡ ተመሳሳይ ሰዎች በተመሳሳይ አስተሳሰብ “ልክ ነው” ያሉት ውሳኔ ውሎ አድሮ በተግባር ሲታይ ሌላ ዕዳ ይዞ ይመጣል፡፡ በዳተኝነትም ይሁን በብልጠት እሰይ እሰይ ያሉት ሥራ፣ የማታ ማታ “ሰነፍና ገብሎ ራሳቸውን እንደነቀነቁ ይኖራሉ” የሚለውን ተረት ከማስታወስ በቀር የረባ ለውጥ አያመጣም፡፡
ትላንት የተማርንበት ት/ቤት፣ ዛሬ ተዳክሞ ላለማየት ብርቱ ጥረት ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡ ቢያንስ ለመልካም ትዝታችን ቦታ መስጠት፣ የጠንካራን ትውልድ ምንነት ለማጤን ይጠቅማል፡፡ የሠራንበት መስሪያ ቤት ከምናውቀው ተዳክሞ ስናይ፣ የሚሰማን የቁጭት ስሜት የሀገርን መዳከም እንደሚጠቁም ለማየት የአዕምሮ አቅም ማጣት የለብንም፡፡
በተደጋጋሚ የሚወጡ መመሪያዎች፣ ማሻሻያዎች ማጠናከሪያዎች የሚፈጥሩትን እሮሮ፣ እምቢታ፣ የተቃውሞ ምላሽ መመልከት በተለይ እንደኛ ላለ አገር መሰረታዊነትና ተገቢነት አለው፡፡ ብዙ ሰው ተቃውሞ ቀርቶ፣ አልገባንም የሚለውን ጉዳይ ቆም ብሎ አለመመርመር ጎጂ ነው፡፡ ብዙ ሰው የሚያወርደውን እርግማን መናቅ የበለጠ ጎጂነት አለው፡፡ አበው “እርግማን ንግግር እየመሰለ ይገድላል፡፡ ፀበል ውሃ እየመሰለ ይምራል” የሚሉት ለዚህ መሆኑን ልብ ማለት ዋና ነገር ነው፡፡

 የፖለቲካ ሹመኞች በሙያተኞች ላይ በሚያሳድሩት ጫና የመንግሥት ሥራ እየተደናቀፈ ነው ሲሉ በተለያዩ የመንግስት ተቋማት ውስጥ የሚሰሩ ባለሙያዎቹ ለአዲስ አድማስ ተናገሩ። በብዙዎቹ የመንግስት መ/ቤቶች ሃላፊዎች ሥልጣን ላይ የሚቀመጡት በፖለቲካ ታማኝነት እንጂ በዕውቀትና በብቃት ባለመሆኑ በሙያተኞች ላይ የሚያሳድሩት ጫና ሥራውንም ባለሙያውንም እየጎዳው መሆኑንም ያስረዳሉ። እየጎዳው ነው ተብሏል፡፡
በአንድ የመንግስት መ/ቤት ውስጥ በከፍተኛ ኤክስፐርትነት የሚሰሩት ግሩም ኤሊያስ (ዶ/ር) የተባሉ ግለሰብ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ በመ/ቤቱ ውስጥ  በከፍተኛ ኤክስፐርትነት ቢቀጠሩም፣ በሃላፊነት የተመደበው ዋና ሥራ አስፈጻሚ የፖለቲካ ሹመኛ በመሆኑ ሙያተኞች ሥራቸውን በቅጡ መስራት አልቻሉም ብለዋል።
እንደ ኤክስፐርቱ ገለፃ፣ ለሀገር ይጠቅማል ብለን የምናጠናው ጥናት፣ የምናቅደው ስትራቴጂክ ዕቅድ በሙሉ በዋና ስራ አስፈጻሚው ውድቅ ይደረጋል። የተሻለ ሀሳብ አይቀርብም፣ የተለፋበት ጥናትና እቅድ መና ይቀራል፡፡ እኛ ግን ከፍተኛ ደሞዝ እየተከፈለን ቀጥለናል። ይህ ደግሞ ህሊና ላለው ሰው ከባድ ነው ብለዋል፤ ግሩም ኤልያስ (ዶ/ር)።
ለደህንነታቸው ሲሉ የመስሪያ ቤታቸው ስም እንዳይጠቀስ የፈለጉት እኚህ ከፍተኛ ኤክስፐርት፤ በሥራ ባልደረቦቻቸው ዘንድ በማያምኑበት ጉዳይ ሁሉ ከአለቃቸው በመቃወም የሚታወቁ ሲሆን በዚህም ሳቢያ ከአንዴም ሶስት ጊዜ በዲሲፕሊን ጥሰት የደሞዝ ቅጣት፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ ከደረጃ ዝቅ የመደረግ ዕጣ ፈንታ እንደገጠማቸው ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል።
ግሩም ኤርምያስ ላለፉት ዓመታት ሲሰሩ በቆዩበት መስሪያ ቤት፣ ሥራቸውን በብቃትና በትጋት ከሚሰሩ ኤክስፐርቶች  ይልቅ ለበላይ አካል ወሬ የሚያቀብሉና የሚላላኩ፣  የመስሪያ ቤቱ “ቁንጮ ሰራተኞች” ተብለው ይሸለማሉ፣ ደሞዛቸው ያድጋል ይመነደጋል፤ የደረጃ እድገትም ያገኛሉ መንግስት ይህን፤ አገርንም ህዝብንም የሚጎዳና እድገትን የሚጎትት የፖለቲካ ሹመኞች ፈላጭ ቆራጭነት በጊዜ ማስተካከል ካልቻለ፣ አገር ወደፊት መራመድ አትችልም ብለዋል። እርሳቸው በሙያቸው አገር ማገልገል ስላለባቸው ወደ ግል ተቋማት እያማተሩ መሆኑንም ገልፀዋል፡፡
ሌላው በኢትዮ ቴሌኮም በከፍተኛ ባለሙያነት የሚሰራው ዘሪሁን አማን (ስሙ ተቀይሯል) የተባለ ወጣት ኤክስፐርት በበኩሉ፤ ከደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ዩኒቨርሲቲ ሁለተኛ ዲግሪውን ይዞ ወደ ሀገሩ መመለሱን ይናገራል። በለውጡ ሰሞን በኢትዮ ቴሌኮም የተቀጠረው ይሄው  ወጣት ባለሙያ፤ ለውጡ የመጣ ሰሞን የነበረውን ተስፋና የለውጡ መንግስት ሥልጣን በያዘ ሰሞን በአገሪቱ የተስተዋለውን መነቃቃት በመተማመን ሀገሩን ለማገልገል ወጣትነቱን፣ ትኩስ ጉልበቱንና እውቀቱን ይዞ ወደዚህ መስሪያ ቤት መግባቱን ገልጿል።
በተለይ የመሥሪያ ቤቱ ዋና ስራ አስፈጻሚ ወይዘሪት ፍሬህይወት ከተሾመች በኋላ ኢትዮ ቴሌኮም ብዙ ፈጣን ለውጦችን እንዲሁም አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን  ማስተዋወቁን የሚናገረው ወጣቱ፤ ከሃላፊዋ ስር ያሉ የፖለቲካ ሹመኞች ግን ተቋሙ የበለጠ እድገት እንዳያስመዘግብ ሙያተኞች ላይ የሚያሳድሩት ጫና ከፍተኛ ነው ይላል በምሬት። “ለሙያውና ለቴክኖሎጂው ያለኝን ቅርበትና የውጪ ተሞክሮዎችን በመጠቀም ተቋሙ የሌላው አገር ቴሌኮሙኒኬሽን የደረሰበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ ሌት ተቀን የማደርገው ጥረት ለአለቃዬ ምቾት አይሰጠውም፣ ያለው ወጣቱ፤ ከፍተኛ ኤክስፐርት፤ ይህም በሀገሬ በሙያዬና በአጠቃላይ ባለው በሁኔታ መሰላቸትና ተስፋ መቁረጥ ውስጥ እያስገባኝ ነው ብሏል።
ወጣቱ አክሎም፤ ቢያንስ የፖለቲካ ሹመኞች የፖለቲካ ታማኝነታቸው እንዳለ ሆኖ ለሚመሩት መስሪያ ቤትና የስራ ጠባይ ቢቻል ሙያውን የተማሩና በዘርፉ እውቀት ያላቸው፣ ካልተቻለ ተቀራራቢ ሙያ ውስጥ ያሉ ቢሆኑ አገርን ከዘርፈ ብዙ ችግር መታደግ ስለሚችል መንግስት ጉዳዩን ያስብበት ጥሪ አቅርቧል።

 • ገዳሙን ለመታደግ 100 ሚ.ብር ያስፈልጋል


        ለአቡነ ሐራ ድንግል አንድነት ገዳም፣ በዛሬው ዕለት ከቀኑ 10  ሰዓት ጀምሮ፣ በካፒታል ሆቴል ዓለማቀፍ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃግብር የሚካሄድ ሲሆን፤ገቢው በገዳሙ ይዞታ ላይ ለሰፈሩ ነዋሪዎች ካሣ በመክፈል ይዞታውን ለገዳሙ ለማስመለስ ነው ተብሏል፡፡ የገዳሙ ገቢ ማሰባሰቢያ ኮሚቴ እንደገለጸው፤ ገዳሙን ለመታደግና ለማስፋፋት በአጠቃላይ 100 ሚሊዮን ብር ያስፈልጋል፡፡
 ገዳመ ወንያት አቡነ ሐራ ድንግል የአንድነት ገዳም፣ በ1574 የተመሰረተና የጻዲቁ አባት አቡነ ሐራ ድንግል ገድልና ገቢረ ተዓምራት የሚካሄድበት ገዳም ነው - ይላሉ የገዳሙ መነኮሳት፡፡
ከ400 ዓመት በላይ ታሪክ ያለው ይህ ትልቅ ገዳም በሰሜን ጎጃም፣ ባህርዳር ዙሪያ የሚገኝ ሲሆን፣ ጻዲቁ አቡነ ሐራ ድንግል፣ ከፈጣሪያቸው በተገባላቸው ቃልኪዳን መሠረት፣ ደዌን ሲፈውሱና ተዓምራትን ሲሰሩ የቆዩበትና አሁንም የሚሰሩበት ጥንታዊ ገዳም መሆኑን፣ የገዳሙ ገቢ አሰባሳቢ ኮሚቴ ባወጣው  መግለጫ ጠቁሟል፡፡ ይሁን እንጂ ይህ ገቢረ ተዓምር የሚሰራበት ታሪካዊ ገዳም፣ ትልቅ ችግር እንደተጋረጠበት መነኮሳቱ ተናግረዋል፡፡
“ለፈውስና ለድህነት ከመላው አገሪቱ ወደ ገዳሙ የሚመጡ ምዕመናን ድህነትና ፈውስ ካገኙ በኋላ፣ ገዳሙን ተጠግተው ቤት በመሥራት እዚያው እየኖሩ፣ ገዳሙ ይዞታውን እየተነጠቀ ከመጣበቡም በላይ፣ የገዳሙን ቅድስና የሚያረክሱ ተግባራት እየተፈጸመበት ይገኛል፡፡”  ይላል፤ የኮሚቴው መግለጫ፡፡
የገዳሙ መነኮሳት የታሪክ ዶሴና ማስረጃ ላይ ተንተርሰው እንደሚናገሩት፤ ዓጼ ዮሐንስ በነቀርሳ ተይዘው በአቡነ ሐራ ድንግል ጸበል በመዳናቸው ነበር ለገዳሙ የአንድ ሰዓት የእግር መንገድ ያህል ስፋት ያለው ቦታ ለገዳሙ የሰጡት፡፡ ደርግ ሥልጣን ሲይዝ በገዳሙ 800 የሚደርሱ መናንያን እንደነበሩ የሚያስታውሱት መነኮሳቱ፤ በወቅቱ “መሬት ላራሹ” የሚል አዋጅ በመታወጁ የገዳሙን ይዞታ አርሶ አደሮች እየተቆጣጠሩት እንደመጡና መናንያኑ ገዳሙን ጥለው መኮብለላቸውን ያስረዳሉ፡፡
በአሁኑ ወቅት በገዳሙ ይዞታ ላይ ከ250 በላይ አባወራዎች ሰፍረው እንደሚገኙ የሚገልጹት መነኮሳቱ፤ ይህን ችግር ለመቅረፍ ለመንግሥት በተደጋጋሚ አቤቱታ ካቀረቡ በኋላ፣ መንግሥት ነዋሪዎቹን አንስቶ ሌላ ቦታ ለማስፈር ፈቃደኛ ቢሆንም፣ ለነዋሪዎች ካሣ ለመክፈል በጀት እንደሌለው በመግለጽ፣ ገዳሙ ካሣውን እንዲከፍል መወሰኑን ይናገራሉ፡፡
ሆኖም የሚከፈለው ካሣ ከገዳሙ አቅም በላይ በመሆኑ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃግብር ማዘጋጀት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል የሚለው  የገዳመ ወንያት አቡነ ሐራ ድንግል አንድነት ገዳም የገቢ ማሰባሰቢያ ኮሚቴ፤ ባለፈው ሐሙስ  በጠቅላይ ቤተክህነት አዳራሽ፣ ስለ ገዳሙ አሁናዊ ሁኔታና ስለ ገቢ ማሰባሰቢያ   መርሃ ግብሩ  ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል፡፡
በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ እንደተነገረው፣ የአማራ ክልል ካቢኔ ለገዳሙ ሁሉንም ይዞታውን ባይሆንም 60 ሄክታር የሚደርስ ቦታ እንዲመለስለት የወሰነ ሲሆን፤ ገዳሙ በበኩሉ ለአርሶ አደሮቹ የሚገባቸውን የመሬት ካሣ መክፈል ይጠበቅበታል፡፡  ይህን የመሬት ካሣ ለመክፈልና ለገዳሙ የማስፋፊያ ልማት ለማከናወን፣ ዛሬ  ቅዳሜ ሚያዝያ 19 ቀን 2016 ዓ.ም በካፒታል ሆቴል፣ በቀጥታ የቴሌቪዥን ሥርጭት፣ ከቀኑ 10 ሰዓት ጀምሮ እስከ ሌሊቱ 6 ሰዓት የሚቆይ  ዓለማቀፍ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃግብር እንደሚያካሂድ  ኮሚቴው  አስታውቋል፡፡ ለአርሶ አደሮቹ የመሬት ካሣውን ለመክፈልና የገዳሙ ይዞታ ከተለቀቀ በኋላ በሥፍራው ለሚከናወኑ ልማቶች በአጠቃላይ 100 ሚሊዮን ብር እንደሚያስፈልገው የገለጸው የገቢ አሰባሳቢ ኮሚቴው፤ በመላው ዓለም የሚገኙ የቤተክርስትያን ልጆችና የጻድቁ አቡነ ሐራ ወዳጆች በዚህ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር ላይ በንቃትና በትጋት እንዲሳተፉ ጥሪ አቅርቧል፡፡
በአሁኑ ወቅት በገዳሙ የሚገኙ መናንያን ቁጥር 5ሺ እንደሚደርሱና በጾም ወቅት የጸበልተኛው ቁጥር ከ50 ሺ በላይ መሆኑን የጠቆመው  የገቢ አሰባሳቢ ኮሚቴው፤ እኒህን ሁሉ በአግባቡ የሚያስተናግድ በቂ መጠለያና የልማት ሥራዎች ማከናወን አስፈላጊ እንደሆነ በአጽንኦት ተናግሯል፡፡


ስብሐቲዝም የሀሳብ ውይይት የፊታችን እሁድ ሚያዝያ  20 2016 ዓ.ም ከቀኑ 8:00 ጀምሮ በኢትዮጵያ ቤተመዛግብት እና ቤተመጻሕፍት አገልግሎት(ወመዘክር) አዳራሽ ውስጥ ይካሄዳል።

"የሕላዌ እንቆቅልሽ " የተሰኘ መጽሐፍ ነገ ይመረቃል

የደራሲ ማንደፍሮ ማሩ "የሕላዌ እንቆቅልሽ" የተሰኘ አዲስ መጽሐፍ ቅዳሜ ሚያዝያ 19 2016 ዓ.ም ከቀኑ 10:00 ጀምሮ በወመዘክር አዳራሽ ይመረቃል።

Page 1 of 704