የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህል ኪነጥበብና ቱሪዝም ቢሮ ዘንድሮ ባዘጋጀው የ"ዝክረ ኪነጥበብ" መርሃ ግብር፣ የበርካታ ቴአትሮች ደራሲ የሆነው ፀሐፌ ተውኔት ውድነህ ክፍሌ የክብር ዲፕሎማና እውቅና ዛሬ የካቲት 26 ቀን 2016 ዓ.ም በሀገር ፍቅር ቴአትር ቤት ተበርክቶለታል።
ጸሃፌ ተውኔት ውድነህ ክፍሌ፤ ግማሽ ጨረቃ፣ የደፈረሱ አይኖች፣ ባቢሎን በሳሎን ፣ ቅጥልጥል ኮከቦች፣ የሌሊት ሙሽሮች፣ ንጋት ፣ የሌሊት ጧፍ፣ ሦስቱ ሰዎች፣ የቼዝ አለም ፣ ቤርሙዳ እና ሌሎች የመድረክና የስክሪን ድራማዎች ደራሲ መሆኑ ይታወቃል፡፡
በእውቅናው ሥነሥርዓት ላይም በፀሐፌ ተውኔት ውድነህ ክፍሌ ላይ የሚያጠነጥን ዘጋቢ ፊልም፣ በተውኔቶቹ ላይ የባለሞያ ዳሰሳና ከ“የደፈረሱ ዓይኖች” ቴአትር ላይ ቅንጫቢ ተውኔት ቀርቧል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህል ኪነጥበብና ቱሪዝም ቢሮ በየዓመቱ በሚያዘጋጀው "ዝክረ ኪነጥበብ" ልዩ መርሃ ግብር፣ ለሀገራቸው ኪነጥበብ በሙያቸው የላቀ አስተዋጽኦ ካበረከቱ ጠቢባን አንዱን በመምረጥ የክብር ዲፕሎማና እውቅና ሲሰጥ ቆይቷል::
Published in
ኪነ-ጥበባዊ ዜና