Saturday, 10 February 2024 10:03

ወንበር ላይ ያለ ሰው ማመን ያቆምኩበት አጋጣሚ!

Written by  አሌክስ አብርሃም)
Rate this item
(3 votes)

ከዓመታት በፊት አንድ ወዳጃችን ታሞ አማኑኤል ይዘነው ሄድን፡፡ በስርዓት እንግዳ መቀበያው ውስጥ ተቀምጠን እሱም በስርዓት ህመሙ በፈቀደለት መጠን የማይያያዙ ነገሮች እያወራ ነበር።
ድንገት ግን  ወንበር እያነሳ መወርወር ጀመረ፤ በተለይ እኔን ካልገደልኩ አለ!
ዘልዬ ወንበር ላይ ቆምኩ (ደመነፍስ መሰለኝ)፤ ከውጭ ሰዎች ሲንጫጩ እሱም ከእኔ ፊት ለፊት ያለ ወንበር ላይ ወጥቶ ቆመ፤ ታማሚም ወንበር ላይ አስታማሚም ወንበር ላይ! ነርሶችና ሁለት ሰዎች

ተሯሩጠው ገቡ፤ አንዱ የተቀባበለ  ስሪንጅ ነገር ይዟል ....ወደ እኔ በቀስታ እየተጠጋ፤ “ማንም አይነካህም፤ አይዞህ ውረድ ወንድሜ” እያለ እንደ ህፃን ያባብለኛል፤ ሊወጋኝ!
“እንዴ እኔ አይደለሁም እሱ ነው...ይዘነው መጥተን ...ከዛ ድንገት እቃ ሲያነሳ ...ከዛ ወንበር ሲያነሳ ...ከዛ “ አልኩ በፍርሃት በተረበሸና በተኮላተፈ ድምፅ፡፡ ደግሞ ስናገር በጣም ነበር የምጮኸው፡፡

ወደሱ ሲዞሩ   ከእኔ በጣም በተረጋጋና ለስለስ ባለ  ድምፅ ወደ እኔ እየጠቆመ፤ “እሱ ነው ዶክተርዬ፤ እባካችሁ  እርዱት” አለ። ሁሉም አምነውት ነበር ....እኔም ተስፋ ቆርጬ፣ የት ላይ ቢወጉኝ

እንደሚሻል ሳስብ ሌላ ጓደኛችን መሃል ገብቶ አተረፈኝ!.... ከዛ ቀን በኋላ ነው በድምፅም በምስልም ከመድረክ የጠፋሁት፤ እና ወንበር ላይ ያሉ ሰዎችንም አላምንም!

Read 901 times