Thursday, 09 November 2023 20:10

ነጩ እና ጥቁሩ የዓይነ-ስውርነቶች

Written by 
Rate this item
(0 votes)

ነጩ እና ጥቁሩ የዓይነ-ስውርነቶች

በዓለም ላይ በከፍተኛ መጠን ዓይነ-ስውርነቶች ከሚያስከትሉ ምክንያቶች ሁለቱ ቀዳሚዎቹ ነጩ እና ጥቁሩ ዓይነ-ስውርነቶች በመባል ይታወቃሉ፡፡

ነጩ - ሞራ ግርዶሽ

ሌንስ፡- የዓይን ፊተኛዉ ክፍል ዉስጥ ያለ ንዑስ-ዓይን አካል ሲሆን - በተፈጥሮዉ ጥርት ያለ ነዉ፡፡ ስራዉ ብርሃንን ወደ ኃለኛዉ የዓይን ክፍል - የብርሃን ግድግዳ(ረቲና) - መርቶ ማሰተላለፍ አንዱ ነዉ፡፡

ሞራ ግርዶሽ፡- ሌንስ ጥራቱን በተለያዩ ምክንያት ሲያጣ - በተለያየ መጠን ወደ ነጭነት ሲቀየር እና ዋናዉ አገልግሎቱ ሲታወክ - ሞራ ግርዶሽ ተከሰተ ይባላል፡፡ ይህ ዓይነ-ስዎርነትን ከሚያመጡ ምክንያቶች በዓለም ላይ በአንደኛ ደረጃ ይቀመጣል ፡ ይህም ከግማሽ በላይ ይይዛል፡፡ ሞራ ግርዶሽ አብዛኛዉ ከእድሜ ጋር ተያይዞ የሚክሰት ሲሆን ሌላው ደግሞ ከእድሜ መግፋት ጋር ያልተያያዘ ነዉ፤ በብዙ ምክንያት ሊመጣ ይችላል ፡ ለምሳሌ .. ከግርዶሹ ጋር አብሮ በመወለድ(ብዙ ምክንያቶች አሉት)፣ በምት ፣ እስቴሮይድ መድሃኒት ከመጠቀም ጋር የተየያዘ፣ በዉስጣዊ የዓይን ቁጣ፣… ወዘተ

ሆኖም ይህ የሞራ ግርዶሽ በቀዶ-ጥገና የሚግላገሉት የዓይነ-ስዉርነት ምክንያት ነዉ፡፡ በዚህም ምክንያት ከጥቁሩ - ግላኮማ ይልቅ ነጩ-ሞራ ግርዶሽ ለታማሚዉም ለሀኪሙም ቀዶ-ጥገና ከተከናወነ በኃላ ትልቅ የእርካታ እና የደስታ ምንጭ ነዉ፡፡ የሀዘን እና የብስጭት ምንጭ የሚሆነዉ ሞራ-ግርዶሹ ተጉዳኝ የዓይነ-ስዉርንት የሚያመጣ ምክንያት ካለዉ/ካሉት ነዉ….አንዱም ያ..ጥቁር-ግላኮማ ሊሆን ይችላል፡፡

ጥቁሩ - ግላኮማ

የዓይን ነርቭ፡- የዓይን ህዋሳት ከብርሀን ግድግዳ (ረቲና) ተሰባስበዉ ህብረ-ህዋስ ፈጥረዉ በኃለኛዉ የዓይን ክፍል ወደ አንጎል የሚጉሀዙበት ገመድ ነዉ፡፡ ስራዉም ብርሃንን እና ያየነዉን ምስል/እንቅስቃሴ በነርቭኛ ተርጉሞ ወደ እይታ-አንጎል ክፍል መማስተላላፍ ነዉ፡፡

ግላኮማ፡- የአይን ነርቭ መጎዳት ሲሆን ፤ የዓይናችን ነርቭ ጉዳት ለመገንዝብ ያህል በግላኮማ ምክንያት እና በሌላ ምክንያት ብለን መክፈል እንችላልን፡፡ ግላኮማ - በጊዜ ሂደት ጉዳቱ የሚጨምር ፣ የማይድን ግን የሚታከም የራሱ አይነተኛ አጎዳድ ያለዉ፤ የራሱ አይነተኛ የዓይን -አድማስ እክል የሚያምጣ ነዉ፡፡ ለግላኮማ አጋላጭ ከሆኑት ዉስጥ ዋናው ከፍተኛ የዓይን ግፊት (ከ 21 ሚሜ.ሜር በላይ) ሲሆን ፤ ነገር ግን የግድ ከፍተኛ ግፊት ላይኖር ይችላል፡፡

ብዙ አይነት ግላኮማ አለ… በመንስኤዉ - የሚታወቅ እና የማይታወቅ፣ በእድሜ - የህጻናት ፡ የወጣቶች እና የአዋቂዎቸ፤ በማዕዘኑ(የዓይን ፈሳሽ የሚፈስበት ቦይ)- ማዕዘነ ክፍት እና ማዕዘነ-ዝግ… ተብሎ በዋናነት ይከፍላል፡፡

የህጻናት ገላኮማ፡- ከ4 ዓመት በታች ያለዉን እድሜ ክልል የሚያጠቃልል ሲሆን፣ ከሌላዉ ዕድሜ የሚለየው አልፎ አልፎ የሚከሰት መሆኑ፤ ሁሌም ክፍተኛ የዓይን ግፊት መኖሩ፣ ጉዳቱ የዓይን ነርቭ ላይ ብቻ ሳሆን ሁሉም እድገታቸዉን ያልጨረሱ የዓይን ክፍሎች ላይ መሆኑ፤ ጠቁሮ ያልጠቆረ…የሚታይ ምልክቶች ማለትም ሶስትዮሽ መገለጫ ያለዉ …ማንባት፡ ብርሃን መፍራት እና የዓይን ቆብን መጭመቅ፡፡ ህክማናዉም የዓይኑን ግፊት በቀዶ-ጥግና መቀነስ ነዉ፡፡ ጉዳቱ እንዳይቀጥል ማድረግ ነዉ ህክምናዉ….የደረሰዉ ተጎዳ አይምለስም፡፡

የወጣቶች እና አዋቂዎች ግላኮማ፡- እነዚህ በጥቁር የሚመሰሉት … ሲጀመሩ ምንም ምልክት የማያሳዩ፤ በጭለማ እንደሚዘርፍ ልባ … ከፍተኛ ጉዳት ካመጡ በኃላ ነዉ የሚታወቁት ምክንቱም የዓይን እይታን መጀመርያ ኣከባቢ ምንም አቀንሱም፡፡ የአይን አድማስ በከፍተኛ ሁኔታ ጠቦ ከነገሮች ጋር ስንጋጭ ወይም ዓይነ-ስዉርት ሲክስተ ነዉ የሚታወቀዉ… ይህ እንግዲህ በዓለም ከነጩ-ሞራ ግርዶሽ ቀጥሎ በሁለተኛ ደረጃ ዓይን-ስዉርነትን ከሚያመጣዉ የማዕዘነ-ክፍት ግላኮማ አይነት መገለጫ ነዉ፡፡

ይህም ዕድሜያቸዉ ከ40 ዓመት በላይ ተጋላጭ ሲሆኑ….ዕድሜ በጨመረ ቁጥር ተጋላጭነትም ይጭምራል፡፡ ለዚህም ሲባል በዚህ ዕድሜ ክልል ዉስጥ ያለ ሰዉ ቢያንስ አንዴ የዓይን ምርመራ ማድረግ ይመከራል፡፡ ተጨማሪ ተጋላጭነት ያላቸዉ ሰዎች ለምሳሌ የቅርብ ቤተሰብ አባል በግላኮማ የተጠቃ ካለ….የቅርብ ክትትል ያሰፈልጋቸዋል፡፡ ወደ ህክምናዉ ስንመጣ ብቸኛዉ ማከሚያዉ (የማይድን ነዉ ብለናል) መንገድ የዓይን ግፊቱን ካለበት መነሻ መቀነስ ነዉ፡፡ ይህም ጉዳቱን ባለበት ማቆም ወይም ዓይነ-ስውርነትን እንዳይከሰት ማቆየት ነው፡፡ ግፊቱን ካለበት ለማዉረድ ሶስት ዓይነት ህክመና አማራጮች አሉት….እናሱም የአይን ጠብታ፣ ጨረር እና ቀዶ-ህክምና ናቸዉ፡፡

ነጩም ይዳን፤ ጥቁሩም ይታከም!
ብርሃኖን ይጠብቁ፡፡
ሙሉቀን ጎ.ኃ፣ ሐኪም
የዓይን ህክምና ሪዝደንት- አአዪ


የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas

Read 501 times