Saturday, 04 November 2023 00:00

“የግርማ ጥበባዊ ፍልስፍናዎች”

Written by  አብዲ መሀመድ
Rate this item
(1 Vote)

ግርማ ተስፋው የሁለት ድንቅ ዘውጎች ባለተሰጥኦ ነው፡፡ አንድም የድርሰት፣ አንድም የገጣሚነት፡፡ ገጣሚነት ፍልስፍናዊ ሐሳቦችን በመጠቀ ቋንቋ መግለጥ እንደመሆኑ ግርማም በስነ - ግጥሞቹ በ”ሰልፍ ሜዳ” ውስጥ የፈለቀቃቸው እምቅ ፍልስፍናዎቹን እዚህ “የጠፋችውን ከተማ ዳሰሳ” ስነ - ግጥሙ ውስጥ ደግሟቸዋል ማለት ይቻላል፡፡ የቋጠራቸው ሁሉም የስነ - ግጥም ስንኞቹ ተጠየቃዊ እሳቤን ያዘሉ
ናቸው፡፡ እናም ያመራምራሉ ፣ አቋምን አስፈትሸውም ያስቀለብሳሉ ፡፡

በአንድ ሰው ፣ በጥቂት ሳምንት ብቻ ተቃኝተው የሚተው አይደሉምና ቀጣይነት ያለው፣የሌላን የጥበብ ባለሟል (ስነግጥም ላይ የተሻለ እይታ፣ ገፋ ያለንባብ ያላቸውን) ሙያዊና ሂሳዊ ምልከታን ይሻሉ፡፡ እኔም ከጥቂት ሳምንት በፊት በግጥሞቹ እያዋዛሁ አንድ ለናቱ የሆነው ድርሰቱ “ ሰልፍ ሜዳ” ላይ አጠር ያለ ዳሰሳ ማቅረቤ ይታወሳል፡፡ተከታዩን ክፍል በቀጣይ ሳምንት ለማቅረብ ባስብም እንዳቀድኩት ሳይሆን ቀረ፡፡ በራሴ ስንፍና ነውና ለተፈጠረው ክፍተት አንባቢያንን ይቅርታ እየጠየኩ ተከታዩን ክፍል እነሆ እላለሁ፡፡

እግዜርማ ነበረ፤የዘላለም ጥበቡን የውበት ንድፉን ባንቺ ቋጭቶወደ ዝምታው ተሰደደ-ዕዳ መርገምን ትቶ፡፡ ለምን እንደሆነ አላውቅም አንዳንድ የጥበብ ስራዎችን፣ ለአንዴ አንብቤአቸው ብቻ እንደዋዛ አልገላገላቸውም፡፡ ዘመን የማያደበዝዘው ትዝታቸው፣ ለጋ ጥፍጥናቸው… ዘወትር በምናቤ ሲመላለስ
ይኖራል፡፡የደራሲና ገጣሚ ግርማ ተስፋው “ሰልፍሜዳ” ከእነዚህ ተርታ አንዱ ሆኖ ለብዙ ጊዜ ይከተለኝ ነበር፡፡ ልክ እንደ ጥላ፣ ደግሞም እንደሸኚ…እንደ አድራሽም፡፡ አመርቂም አርኪም ሆኖ! ከነለዛው እና ከነውበቱ…ከነምናምኑ፡፡በርግጥ በያዙት ጥልቀ እውቀታቸውና በማይዘነጋ ትዝታቸው ስነጽሑፍ ተብለው በአንድ ጥቅል ወይም በአንድ ዘርፍ ይቅረቡ እንጂ የያዙት እውነት ግን ከአንድ በላይ ነው፡
፡ ፕሮፌሰር ባየ ይማም ቆየት ያለ ለአንድ ስነ ጽሑፍ ጥናት ውስጥ ባሰፈሩት ቀዳሚ ቃላቸው ፤…“ስነ ጽሑፍ ጅረቱ አንድ ቢሆንም፣ ምንጮቹ ብዙ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡

ጅረቱም ከነምንጮቹ፣ ምንጮቹም ከጅረቱ ጋር እያገናዘቡ ወደ ኋላ እና ወደፊት ማየቱ የተሻለ ግንዛቤ ያስጨብጣል” ይላሉ፡፡ ግርማ ተስፋው የቀድሞ አዲስ ነገር ጋዜጣ ከመስራቾቹና አዘጋጆች መካከል አንዱነበር፡፡ በፖለቲካ፣ ኢኮኖሚ፣ አርት ጉዳዮች እና የጉዞ ማስታወሻዎችን ይጽፍ እንደነበር ስለደራሲው ፍንጭ ይሰጥ ዘንድ፤ከግጥም መድብሉ ጀርባ ተዘግቧል፡፡ ከጋዜጣዋ መዘጋት በኋላ በስደት የመን እና ሌሎች አረብ ሀገራት ከርሟል፣ በትምህርት ደግሞ ካሊፎርኒያ፣ ፓሎ አጋቶ በማምራት…አጥንቷል፡፡

ግርማ ግጥሞቹን የሚያስባቸው የትምነው፡፡ እነዚህም - እዚያም፡፡ በሚወዳት እና በሚናፍቃት አዲስ አበባ ሲመላለስ የተጠነሱ ስንኞች፣ በቦሳሶ በኩል የመሰደድ ነገርን እያሰላሰለየ ባቱን፣ የቱሉዲምቱ ተራራዎች እየታሰቡት በምዕናቡ የጠነሳሰቸው፣ የባሌ ኦሮሞ ባህላዊ ዜማን እየሰማ ያሰባቸው በርካታ ናቸው፡፡ እኚህን ሀሉ አደራጅቶ በባእድ አገር ላይ መደምደሚያቸውን፣ ማሰሪያቸውን ያበጅላቸዋል፡፡ የሀገርፍቅሩ፣ ናፍቆቱ እና
ቁጭቱ ሁሉ በጣሙን ብርቱ ነው፡፡ ልጆችሽን እንደልደታ ንፍሮለአገር ለወንዙ በትነሽ የዕጣን ሽታ የናፈቀው የተዘጋ መቅደስ ነሽ፡፡

ባይነርግብ እንደ ጋረዷት እንደምታሳሳ ኮረዳ በገጽሽ ውበት ይፈሳል ከዐይኖችሽ እየተቀዳ፡፡ ደመና ከሌለው ሰማይ የወረድሽ የበረሐ ጠል አንቺነሽ የውበት ዐምባ፤ አንቺነሽ የጸደ ይጠለል፡፡ አገሬ…ቅኔ…ምድሬ፡፡
ፊታውራሪ ተክለ ሐዋርያት ተክለ ማርያም በአውቶ ባዮግራፊያቸው እንዳነበብነው፤ ጅቡቲ ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ መርከብ ሲያዩ ተራራ መስሏቸው ነበር፡፡ በኋላ መርከብ መሆኑን ሲያውቁ በቁጭት ስሜት “የእኛ አባቶች ምን ሲሰሩ ከረሙ? ብለው ድማሜና ቁጭት እንዳደረባቸው ሁሉ፣ ግርማም… የሰው አገር ካላዩ የራስን አገር አያውቁም፣ የሰው አገር እያየን ስለአገራችን እንናፍቃለን፣ እንቆጫለን”
ይላል በመግቢያው፡፡ ይኼን ቁጭት ያዘለ ናፍቆቱን ደግሞ እርሱም ልክ እንደ ተክለሐዋርያት እየጠየቀ በግጥሙ እንዲህ ይቀኛል፡፡
ሰው አልነበረውም? ይህ ባድማ መሬት፣እንክርዳድ የሞላው ቁጫጭ የናኘበት፣አሻራ እንዴት ዕጣ? ሕልሙስ የት ደረሰ?መንገዱ ፍኖቱ ኸረ እንዴት ፈረሰ?ግርማ በሀገር ጉዳይ አብዝቶ ይቆዝማል፡፡ከቁጭት ባሻገር በእጅጉ ተብሰልሳይ መሆኑ መነሻው ላይ ባሰፈረው ዘለግ ያለ ሀተታና በግጥሞቹም ውስጥ በስፋት ይንጸባረቃል፡፡

እንደ ሰው ከእነክብራችን ከኖርን እና ካሰብን የማንደርስበት የኢኮኖሚ እድገት እና የቁስ ብልጽግና ደረጃ የለም የሚል እምነት ያለው ይመስላል፡፡ ይኼንንም አቋሙን እንዲህ ሲል አትቷል ፡፡ …“የቁስእድገት እነርሱን ግዙፍ እኛን ደግሞ እጅግ ትንሽ አድርጎ ያሳየናል፡፡ እነርሱን የማይደረስባቸው አስመስሎ እያሳየ ያለንን ሁሉ አውጥተን እንድንጥል እና እራሳችንን እንድንጠራጠር አድርጎናል፡፡ የእነርሱ ብቻ መልካም የእኛ ደግሞ ኋላ ቀር እና እርባናቢስ እንዲመስለን ኾነናል፡፡ መልካሙ ዜና ግን የማይደረስበት የማቴሪያል ብልጽግና እንደሌለነው ፡፡ የኤሽያ እና የላቲን አሜሪካ አገሮች እያሳዩን ያሉትም ይህንኑ ነው” ይላል፡፡

ግርማ በዚህ መንፈስ ሆኖም “ቤሌማ” እንዲሁም” ሽፍትነት”፣ “ጥጋብ” እና “ብህትውና” በሚል ርዕስ ስር ይህንኑ ሀሳብ የሚያነሳ፣ ለዚሁ የተጠጋ ስንኞችን ቋጥሯል፡፡ሰው   አልነበረውም? ይህ ባድማ መሬትእንክርዳድ የሞላው ቁጫጭ የናኘበት፤አሻራ እንዴት ዐጣ ህልሙስ የት ደረሰ?መንገዱ ፍኖቱ ኸረ እንዴት ፈረሰ?ደንቁርና አገር ወርሮይሰዋለታል ጥበብ፤ ይገበርለታል ኑሮሽፍትነት እና ብሕትውና ዱር መቅረትም አይደል ደንቡሸንጎ ተገኝቶ ልክ ልኩን ማፍረጥ ነው ግቡሽፍትነትህ ከአንተ ተርፎ ለአዲስ ትውልድ ካላለፈንጋታችን መቼ መጣ? ጽልመታችን

Read 434 times