Monday, 03 July 2023 09:34

“እኔ በአምላኬ ፊት ምንም ነኝ“

Written by  ዋስይሁን ተስፋዬ
Rate this item
(1 Vote)

በህንድ በፓኪስታንና በአንዳንድ ሀገራት እኛ ስለምናውቀው የእግር ኳስ ብትነግራቸው፣ እስኪ አሁን እግር ኳስ ምን የሚወደድ ነገር ሆኖ ነው ይሏችኋል። ለነዚህ ሀገራት ሰዎች፤ ስፖርት ማለት፣ ጨዋታ ማለት ክሪኬት ነው። በነዚህ ሀገራት ያሉ የክሪኬት ኮከብ ተጫዋቾች የሚሰጣቸው ክብርና ዝና ይገርማል።
በዚህ ስፖርት ዝነኛ የሆነ አንድ የክሪኬት ኮከብ፣ በሚሊዮን ዶላሮች የዝውውር ጥያቄ የሚቀርብለት፤ ባለፈ ባገደመ ቁጥር በአድናቂዎች የሚከበብ ሰው ይሆናል። ከነዚህ በተለይ በህንድና በፓኪስታን እንደ ተአምር ከሚታዩ ኮከቦች መሀል ፓኪስታናዊው የክሪኬት ኮከብ ባባር አዛም አንዱ ነው። ባባር አዛም የነዚህ ሀገራት ሮናልዶ፣ ሜሲ ወይም የጊዜው ሀላንድ ማለት ነው።
ሰሞኑን ሀጅ ለማድረግ ወደ መካ የተጓዙ ህንዳውያን፣ ይህን ተጫዋች ከሀጅ ስነስርአት በኋላ አሸዋ ላይ አረፍ ብሎ ናፕ ሲያደርግ አዩት፤ “ይህ ዝነኛው የክሪኬት ኮከብ አዛም ባባር ነው አይደለም“ እያሉ ተጠግተው አዩት፤ እራሱ ነው።  “እኔኮ እንትና ነኝ ሳይል. ..“ ዝናም ሆነ ስም  ከሌላቸው ሰዎች መሀል ተኝቶ በማየታቸው ተደንቀው ይህን ፎቶ አንስተው በሶሻል ሚዲያ ለቀቁት። ፎቶው በሚሊዮኖች ዘንድ ተሰራጨ፡፡
ባባር አዛም ይህን ካየ በኋላ ግን አልገረመውም፤ “ እኔ በአምላኬ ፊት ምንም ነኝ፤ መልካም ስራዬ እንጂ የኔ ዝናም ሆነ ክብር በርሱ ዘንድ ቦታ የለውም። ስለዚህ መተናነሴ አይግረማችሁ“ ሲል ምላሽ ሰጥቷል።
(ዋስይሁን ተስፋዬ)

Read 711 times