ከ16 አገራት የተውጣጡ 130 ኩባንያዎች ይሳተፉበታል
5ኛው ʺአግሮፉድ ኢትዮጵያ እና ፕላስትፕሪንትፓክ ኢትዮጵያʺ ዓለማቀፍ የንግድ ትርኢት፣ ከሰኔ 1- 3 ቀን 2015 ዓ.ም ለሦስት ተከታታይ ቀናት በሚሊኒየም አዳራሽ እንደሚካሄድ ተገለጸ፡፡በንግድ ትርኢቱ ላይ የግብርና፣ ምግብ ማቀነባበሪያ፣ የምግብ ግብዓት ንጥረነገሮች፣ ፕላስቲክ፣ ህትመትና ማሸጊያ ቴክኖሎጂዎች እንዲሁም መፍትሄዎች ይቀርባሉ ተብሏል፡፡
የንግድ ትርኢቱ አዘጋጆች ባለፈው ሰኞ ግንቦት 14 ቀን 2015 ዓ.ም በስካይ ላይት ሆቴል ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
አዘጋጆቹ በመግለጫው ላይ እንደጠቆሙት፤ በንግድ ትርኢቱ ላይ ከ16 አገራት የተውጣጡ 130 ድርጅቶች የሚሳተፉ ሲሆን አገራቱም ኢትዮጵያን ጨምሮ ኦስትሪያ፣ ቡልጋሪያ፣ ቻይና፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ህንድ፣ ጣሊያን፣ ዮርዳኖስ፣ ኬንያ፣ ኮሪያ፣ ኩዌት፣ ኔዘርላንድስ፣ ታይዋን፣ ታይላንድና ቱርክ ናቸው፡፡ ትርኢቱን ከ3ሺ በላይ ሰዎች ይጎበኙታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በንግድ ትርኢቱ ላይ ከቻይና የመጡ ከ60 በላይ ኩባንያዎች የሚሳተፉ ሲሆን፤ ከኩዌት የመጡ 8 ድርጅቶችም ተሳታፊ እንደሚሆኑ ታውቋል፡፡
“በኩዌት አምርቱ” የንግድ ትርኢቱ የወርቅ ስፖንሰር ነው ተብሏል፡፡
5ኛው አግሮፉድ ፕላስትፕሪንትፓክ ኢትዮጵያ ዓለማቀፍ የንግድ ትርኢት የተዘጋጀው፣ በጀርመኑ የንግድ ትርዒት ስፔሽያሊስት ፌር ትሬድ መሴ እና በኢትየጵያው አጋሩ ፕራና ኢቨንትስ ትብብር ነው፡፡