የኒውዚላንዷ ከተማ ኦክላንድ በዘንድሮው የኢኮኖሚስት መጽሄት ለኑሮ ምቹ ምርጥ የአለማችን ከተሞች ዝርዝር ውስጥ በአንደኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠች ሲሆን፣ ከተማዋ ለዚህ ክብር ከበቃችባቸው ጉዳዮች መካከልም በኮሮና ወረርሽኝ ወቅት ትምህርት ቤቶች፣ ቲያትር ቤቶች፣ ሬስቶራንቶችና ሌሎች የባህል ማዕከላትና መስዕቦች እንዳይዘጉ ለማድረግ የተከተለችው ስኬታማ አካሄድ በጉልህ እንደሚጠቀስ ተነግሯል፡፡
በ2021 የአለማችን ለኑሮ ምቹ ከተሞች ዝርዝር ውስጥ በሁለተኛነት የተቀመጠችው የጃፓኗ ከተማ ኦሳካ ስትሆን፣ የአውስትራሊያዋ አዴላዴ፣ የኒውዚላንዷ ዌሊንግተን፣ የጃፓኗ ቶክዮ፣ የአውስትራሊያዋ ፐርዝ፣ የስዊዘርላንድ ከተሞች ዙሪክና ጄኔቫ፣ እንዲሁም የአውስትራሊያዎቹ ከተሞች ሜልቦርንና ብሪስባኔ እንደ ቅደም ተከተላቸው እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡
የኢኮኖሚስት መጽሄት የምርመራ ክፍል የአለማችንን ከተሞች ሰላምና መረጋጋት፣ የጤና አገልግሎት፣ ባህልና አካባቢ ጥበቃ፣ እንዲሁም ትምህርትና መሰረተ ልማት በተሰኙ ስድስት ዋና ዋና ምድቦች ከ30 በላይ በሚሆኑ የመለኪያ መስፈርቶች እየገመገመ በየአመቱ በሚያወጣው በዚህ ሪፖርት፣ ዘንድሮ ከኮሮና ቫይረስ ጋር በተያያዘ የከተሞች ደረጃ ሰፊ ልዩነት ማሳየቱ ተነግሯል፡፡ ከእነዚህም መካከል ላለፉት አመታት በአንደኛ ደረጃ ላይ የነበረችውና ዘንድሮ ወደ 12ኛ ደረጃ ዝቅ ያለችው የኦስትሪያዋ ከተማ ቪየና ትገኝበታለች፡፡
Published in
ከአለም ዙሪያ