Saturday, 11 June 2016 13:53

አንጋፋው ሐያሲ አብደላ እዝራ!! (አጭር የህይወት ታሪኩ)

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

አብደላ እዝራ ከአባቱ ከአቶ መሐመድ ሳልህ አልአረግስኢ እና ከእናቱ ወ/ሮ መሪሃም በ1950 ዓ.ም በአዲስ አበባ፣መርካቶ አንዋር መስጊድ አካባቢ ተወለደ፡፡ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን ከ1ኛ-6ኛ ክፍል በአፍሪካ አንድነት ትምህርት ቤት የተከታተለ ሲሆን 7ኛ እና 8ኛን በልዑል ወሰን ሰገድ ትምህርት ቤት፣የ2ኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ በተፈሪ መኮንን ተምሯል፡፡ ወደ የመን፣ ሰንዓ በመጓዝም  የመጀመሪያ ዲግሪ ትምህርቱን አጠናቋል፡፡ እዚያው የመን ውስጥ በየመኒ ኤርዌይስ ተቀጥሮም ጡረታ እስከወጣበት ጊዜ ድረስ ሠርቷል፡፡
አብደላ አብላጫውን የሕይወት ዘመኑን በሥነጽሑፍ ሥራዎች ላይ ጥናትና ምርምር በማድረግ ያሳለፈ ሲሆን ወደ ኢትዮጵያ ከመጣ በኋላም የበርካታ ገጣምያንና ደራስያን ሥራዎችን በሂሳዊ ብዕሩ ጎብኝቷል፡፡ ሃያሲው ቀደም ባሉት ዓመታት በ“አዲስ ዘመን” እና “የዛሬይቱ ኢትዮጵያ” ጋዜጦች እንዲሁም የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር (ኢደማ) በሚያዘጋጀው “ብሌን” መጽሔት ላይ ከዚህ ዓለም በሞት እስከተለየበት ጊዜ ድረስ ደግሞ በ“አዲስ አድማስ” ጋዜጣ ላይ ጥልቅ የሥነጽሁፍ ትንታኔዎቹን አቅርቧል፡፡ አንጋፋው ሃያሲ ሥራዎቻቸውን በጥበባዊ ሂስ ከተነተነላቸው ዕውቅና ድንቅ ደራሲያን መካከል በዓሉ ግርማ፣ ደበበ ሰይፉ፣ ሲሳይ ንጉሡ፣ አዳም ረታ፣ ስብሐት ገብረእግዚአብሔር፣ ነቢይ መኰንን፣ ዓለማየሁ ገላጋይ፣ አበራ ለማ፣ ኤፍሬም ሥዩም፣ ደምሰው መርሻና በድሉ ዋቅጅራ ይጠቀሳሉ፡፡  
 አብደላ እዝራ ድንገት ባደረበት ሕመም፣ለአጭር ጊዜ ሕክምና ሲከታተል ቆይቶ፣ባለፈው ቅዳሜ ግንቦት 27 ቀን 2008 ዓ.ም ከቀኑ10፡30፣ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡ በነጋታው እሁድ ሥርዓተ ቀብሩ ጥቂት ሰዎች በተገኙበት በቅዱስ ዮሴፍ ቤተክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡  

Read 1818 times