Saturday, 19 September 2015 09:42

“እኔ የማውቀው የስነ - ፅሁፍ ወዝአደር መሆኔን ነው”

Written by  ደረጀ በላይነህ
Rate this item
(7 votes)

 የዛሬ 2 ሳምንት ከገጣሚ ወንድዬ ዓሊ ጋር ቀልጠፍ ያለች ቃለ - ምልልስ ጀምረናል፡፡ ውይይታችን ድንበር ሳይሻገር በሀገራችን ጥበባት ዙሪያ ሲሽከረከር ነበር፡፡ ዛሬም እዚሁ ሀገራችን፣ ይልቁንም በጥበባት ትኩስ ምጣድና እንጀራ፣ በፉንጋውና ቆንጆው፣ በአይነ ልሙና አይነ ኮከቡ ለጥበባችን እልፍኝ ድምቀት፣ ለዘመናችን ውበት ይሆነን ዘንድ እመኛለሁ፡፡
                     

    ግራጫው፤ አማረም አረረም በየሣምንቱ አዳዲስ የግጥም መድበሎች ይወጣሉ፡፡ ገልጠህ ስታነባቸው ግን ራሳቸው ለራሳቸው የደፉትን ባርኔጣ ያህል የማይመዝን ሥራ ሆኖ ስታገኘው አንዳች ነገር ሰውነትህን ይወርረዋል፡፡ ልብህ ይሰበራል፡፡ እነዚህ በአቻ ግፊት ወይም ገጣሚ በመሆን ውስጣዊ ረሀብ ያሳተሙት ናቸው፡፡
በየመሀሉ ደግሞ ከፍላት እንዳመለጠች በቆሎ ጠጣር ነገር ይዘው ብቅ ያሉ ነገር ግን ቅድም ባነሳናቸው የሕትመት ጐርፍ ተውጠው፣ ትኩረት የተሳናቸውም አሉ፡፡ ለምሣሌ ዕድሜውን በወጣት ሣጥን ውስጥ የማላስቀምጠው ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ ፣ ወጣቶቹ ቴዎድሮስ ፀጋዬ፣ በዕውቀቱ ስዩም፣ ታገል ሰይፉ፣ ወንድወሰን ካሳ፣ አሌክስ አብረሃም፣ ወዘተ…
ዶክተር በድሉንና አሌክስ በሺህ የሚቆጠሩ የፌስ ቡክ ደቀመዛሙርት አሏቸው፣ ግን አድናቆቱ ባብዛኛው ጥልቀት የለውም፡፡ ምርቱን ከገለባው ከሚለዩ ደፋር ሃያሲዎች ጋር አልተፋጠጡም፤ በዚያው እንዳይቀጥሉ ነው ስጋቴ፡፡ ጅምላ ፍካሬና የጀሌ ጩኸትን ያህል የጥበብን ሰው የሚያደነዝዝ ነገር የለም፡፡
ቴዎድሮስ ፀጋዬ መካከል ላይ ያለ ብርቱ ልጅ ነው፡፡ ወንድወሰን ካሳ ዓይናፋር ሳይሆን አይቀርም፤ እርሱ አይጮህም፣ የጮኸለትም የለም፡፡ ይህ የእኔ ግንዛቤ ነው፡፡
ቅርፁና ይዘቱ ምንም ይሁን ምንም፣ ሙገሣው ካፖርት የደረበላቸውና ሙቀት ያደነዘዛቸው ገጣሚያን፤ ከፈዘዘ ማለዳቸው ሲባንኑና ምድርን ሲረግጡ፣ ሌላ መካሻ ይዘው እንደሚመጡ ተስፋ አደርጋለሁ፤ ለስነ ግጥም ተወልደው ከሆነ ቢፈዙም አይጠፉም፡፡
አየህ ሙገሳ የመሸታ ያህል ስካር አለው፤ የሚያድርና የሚሰነብት “ሀንጐቨር” አለው፡፡ ከዚያ መላቀቅ ቀላል አይምሰልህ!
ሰው ለጥበብ ይወለዳል?...ወይስ ራሱ በፍቅር ጥበብን ይወልዳል?...ምናልባትስ ከትምህርት ቤት ይሸምት ይሆን?
በኔ አተያይ ከነብዙ አባዜው ጥበብ መወለድን ይጠይቃል፤ መታደልም ነው፤ ግና በትምህርት፣ በንባብና በሕይወት ተሞክሮ መበልፀግ ግድ ይለዋል፡፡ ለጥበብ ተወልደን ራሳችንን የምንኮተኩትባቸው በርካታ ነገሮች ያስፈልጉናል፡፡ እነዚያ ነገሮች ሲያንሱን ነገር ዓለሙ ይሳከርብናል፡፡ ዕውቀት መሬት ያስረግጠናል፣ በተለይ ንባብ፣ ከሚያነብበው በላይ የሚናገር ሰው ግልብነቱ ያፈጥጥበታል፡፡
ጥበብን ወዳፈቀረው እንምጣ፡፡
ማኅበራዊ ሕይወታችን እስቲ እንየው፡፡ ያፈቀረ ሁሉ ጥሩ ባል ወይም ሚስት ሊሆን/ልትሆን ይችላል/ትችላለች? አይሆንም፡፡ ኪነጥበብን የተማረ ሁሉ ገጣሚ አሊያም ሰዓሊ ሊሆን አይችልም፡፡ ነገር ግን የጥበብ ፍቅርና ትምህርትን የተጐናፀፉ ሰዎች ግሩም ሃያሲያንና መምህራን በአጠቃላይ ቱንቢ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ መጣመማችንን ወይም ቀጥተኛነታችንን እየመዘኑ የሚነግሩን እነሱ ናቸው፡፡ ጥቂቶች ናቸው እንጂ በእኛም ሀገር ብርቱ ሰዎች አሉን እኮ፡፡ ስም ልጥራ እንዴ? እነ ብርሃኑ ገበየሁን የመሰሉ፡፡
የኃይለ ቃልና ምናብ ምንጭህን ንገረኝ እስቲ?
በአእምሮዬና በልቡና የተጐሰጐሱ፣ በጥበብ ጥማት ለቃተተች ነፍሴ ዋርካ የሆኑኝን ሰዎችም ሆኑ የሕይወት መንገዴን መቸቶች መዘርዘር አይቻለኝም፡፡ ፊውዳል ነክ፣ ነገር ግን የባላገር ሥልጡን የሆነው ቆምጫጫ አባቴ፣ ባህሪዬን በጥበብ የሳለው ይመስለኛል፡፡ ለአባቱ የተፃፈውን ከ“ወፌ ቆመች” ውስጥ “ዱባና ንፍሮ”ን በከፊል እንመልከት፡-
ቶፋ ሙሉ ዱባ - ታሽቆ             እቀምሰው ብል   - ከምክኑ            የዱባ ቁርጥ - ተንፈቅፍቆ             እበላ ብል - ከክሽኑ!
እንቅብ ስፍር -  ንፍሮ
ዛሬስ አልጥምህ አለኝ…ሌማቱ
ኩስኩስቱን ሙሉ - ተነፍሮ            ዱባ ከንፍሮ - ብልቱ
እሳቱ ላይ - በእንክርት፣             እንዳልበላው - መታከቴ
ዛሬም አለ -  ከመደቤ ፊት ለፊት፡፡         ድንገቱ ዛሬ - ኩራቴ
ሁሌም - በየቀኑ                 እየታየኝ የራብ ሞቴ
ባየው ባየው - እሱኑ                 አዬ - ሆድ!
ቶፋውም                    ኩስኩስቱም
እንክርቱም፡፡     
ያደግሁበት ማኅበረሰብ የጥበብ ብልጽግና ከግዕዙ፣ ዐረቡ፣ ኦሮሚፋው፣ አፋሩ ተዳቅለው የጐመሩበት፣ በአጭሩ “ወሎኛ” በመሆኑ እጅግ ገላጭ የሆኑትን ሥነ - ቃላት እየሰማሁ ማደጌ፣ መጽሐፍ ቅዱስን ደግሜ፣ ደግሜ፣ ደጋግሜ ማንበቤ፤ ጠቅሞኛል፡፡ በብሉይ መጽሐፍት ሲሶዎን ከያዙት ግጥሞች ለነፍስ የሚሆን አንዳች ስንቅና ክርክር የማይታጣባቸው መዝሙረ ዳዊትንና ኢዮብን፣ መኃልይ መኃል..ንማንበቤ ጠቅሞኛል፡፡
በዓለማችን ላይ ያሉ ታላላቅ ባለቅኔዎች ያደግንበት ዋርካ፣ አለ… የነፍሳችንን ክሮች ተርትሮ የገባ፣ የልብ ማህተም አለ ይላሉ፣ አንተስ ፈር ቀዳጅህ ማነው?
በእኔ ዕድሜ የሚገኝ ሰው በከበደ ሚካኤል ታሪክና ምሳሌ ያልተማረ የለም፡፡ እሳቸው አፊዎት፣ (በእንግሊዝኛው የኔ ትውልድ Inspiration ናቸው፡፡ በውስጥህ አፈር ለብሶ የፈዘዘውን ዘር እንድታበቅል የሚረዱ የጥበብ ጠብታዎች አባት ናቸው፡፡ የሥነ ግጥም አተያዬን (እንደ አብዮት) የገለባበጠው ግን ፀጋዬ ገብረመድህን ነው፡፡ “እሳት ወይስ አበባ” መድበሉን ገና እስከዛሬ አውቄ አልጨረስኳትም፡፡ ሁሌ ተማሪዋ ነኝ፡፡ በእውነት እልሃለሁ ውስጤ የተቀበረውን የገጣሚነት መንፈስ ያኳሹት ግን ኦቴሎ፣ ሐምሌት፣ ማክቤዝ የሚባሉት የዊልያም ቬክስፒር ትርጉሞች ናቸው፡፡ የቴዎድሮስን ድራማ ሣይማ ልቤ ቀለጠች፣ እንግዲህ ጋሽ ፀጋዬ ነው፤ ኃይለቃልን፣ ፍንገጣን፣ በራስ ላይ ማመፅን፣ የስነ ግጥም ፍልስፍናን ያስተማረኝ፡፡ ከእሱ ሲቀጥል የደበበ ሰይፉን የግጥም መጽሐፍት እወዳቸዋለሁ፣ በመጠኑ አቃንተውኛልና፡፡ (በጽጌረዳ ብዕር ከታተመው በቀር)
አስቸርህ ባጣ (ለፀጋዬ ማስታወሻ የተፃፈ)
በአየር - ደንገላሳ፣
በጨረር - የሳንሳ፣
በነፋስ ትከሻ - በገሞራው እስትንፋስ
ለመንጠቅ - አንደዜ! - ስውር ጥበብ ላስስ፣
ትንሽ ልፋሰሰው! - ዛቴን እዚህ ትቸው
በሰማያት ጀርባ - በማይጐረብጠው፡፡
በል - ንሳ - በልልኝ
በል- ንሳ - በልልኝ
ማዕበልን አቅፌ - መብረቅን፣ ጨብጬ
እቶንን - ደርቤ - አውሎ ተጫምቼ
በደመናት - ዋሻ
ውበት - መናገሻ፣
በነጐድጓድ ወንበር፣ - ሁሉንም ንገረኝ- ጉባኤ እንቀመጥ፣
አክናፍ ወቅኔያት፣ - ይንጠቁኝ ልብነነው- ባቴ እዚሁ ይቅለጥ፡፡
ልቀቀው! - አይተንፍግ - ታምቆ እስከመቼ?- ገሞራው ይፈንዳ
ሽቅቡን ወደ ላይ - ሽቅብ የሽቅቡን - እኔነቴን ይንዳ፡፡
(ከ“ወፌ ቆመች” በከፊል የተወሰደ)
የሀገራችን የስነ ጽሑፍ ምሁራን ለማስተማሪያ ባዘጋጁቸው መጽሐፍት አንተን “ገጣሚ” ብለው ነው ያስተዋወቁን፡፡ ምናልባት በዝርው የፃፍካቸውን መፃህፍት የማያውቁም ስላሉ … ይሆናል፡፡ አንተ ምን እንድትባል ነው የምትፈልገው?
እኔ እንጃ! በርግጥ ከ“ወፌ ቆመች” በኋላ፣ የታሪክ መጻሕፍትን፣ ግለ ታሪኮችንና (እንደፈለገ - ብርሃኑ ያሉ) ጽፌያለሁ፡፡ በርካታ የአርትዖት ስራዎችን ሠርቻለሁ፣ ጥናትና ምርምሮችም እንደዚሁ፡፡
ያሻችሁን በሉኝ፡፡ እኔ ግን የሥነጽሑፍ ወዝአደር መሆኔን አውቃለሁ፡፡
አሁን የአዲስ ዘመን ጐህ ላይ ነን፣ ስለቀጣዩ ዘመን መጠየቅ ያሠኛልና፣ ወደፊት ምን ታስባለህ?
ሁለት ነገሮች ቢሳኩልኝ ደስ ይለኛል፡፡ “ወፌ ቆመችን” ለብቻዋ፣ አሊያም ከ“ውበት እና ሕይወት” ጋር አዳምሬ ማሳተም እፈልጋለሁ፡፡
ሌላው ተዝረክርከው ከተቀመጡትና ቁጥራቸውን በቅጡ ከማላውቀው ግጥሞቼ መካከል መርጬ፣  በዚህ ዘመን ከተለመዱት ጥራዞች በተለየ ጠብደል ያለ ጥራዝ ባሳትም ምኞቴ ነው፡፡ ሌላውን ስንደርስ እናየዋለን፡፡ ሁሉንም ለማየት ያብቃን! 

Read 2750 times