የሩሲያ የሳይንስና የባህል ማዕከል ከጀርመን የባህል ተቋም ጋር በመተባበር፣ ከመቶ አመት በፊት የተነሱ የአዲስ አበባ ፎቶግራፎችን ለአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም በስጦታ አበረከተ፡፡ ፎቶግራፎቹ ከመቶ አመት በፊት ለህክምና አገልግሎት ወደ ኢትዮጵያ በመጡ ሩሲያዊ ሀኪም እንደተነሱ የተገለፀ ሲሆን የዚያን ጊዜውን የአዲስ አበባና ነዋሪዎቿን የህይወት ገፅታ አጉልተው እንደሚያሳዩም ተጠቁሟል፡፡
ፎቶግራፎቹ በሩሲያ ሴንት ፒተርቡርግ በሚገኘውና በታላቁ ንጉስ ጴጥሮስ ስም በተሰየመው እውቁ የኩንስትካሜራ ሙዚየም ባለቤትነት ተመዝግበው የሚገኙ ሲሆን ይህን ታሪካዊ የፎቶግራፍ ስብስብ አዲስ አበባ የሚገኘው የጀርመን የባህል ተቋም ከሙዚየሙ ባገኘው ፈቃድ፣ በከፍተኛ ጥራትና በልዩ የህትመት ዘዴ በማሳተም፣ ለአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ባለፈው ማክሰኞ በስጦታነት አበርክቷል፡፡ በእለቱ የሩሲያ ፌደሬሽን አምባሳደር፣ የጀርመን ሪፐብሊክ አምባሳደር፣ በኢትዮጵያ የሩሲያ ኩንስትካሜራ ሙዚየም ዳይሬክተር፣ የመንግስት ባለስልጣናት፣ የታሪክ ተመራማሪዎችና የዩኒቨርሲቲ ምሁራን የተገኙ ሲሆን የፎቶግራፍ ኤግዚቢሽንም ተጎብኝቷል፡፡
Saturday, 14 June 2014 12:23
የአዲስ አበባን የድሮ ገፅታ የሚያሳዩ ፎቶግራፎች ለአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተበረከተ
Written by ናፍቆት ዮሴፍ
Published in
ኪነ-ጥበባዊ ዜና